05/04/2026
በልባችን ይገባና የኃጢአትን መሠረት ያጠፋ ዘንድ የሚቻለው፤ የሰው ልጆች ወዳጅ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደጅ ቆሞአል። በቤተ ፋጌ ዓለም በተራራው ዲያብሎስ አጠገብ የምንገኝ እኛን ከማዕሠረ ኃጢአት ይፈታ ዘንድ ወዳጆቹን ልኳል። ልዑል የሆነው ዘንባባ ብቻ የሚቀርብለት አይደለም በእሳት የማይቃጠል ሌቦች ቆፍረው የማይሰርቁት ሰማያዊ ሀብት በደጁ ያለ ነው።
የሆሣዕናው ንጉሥ እንደ ኢዩ የሚያልፍ ጨርቅ የምናነጥፍለት አይደለም የልባችንን በር የምንከፍትለት ነው፤ እንደ እስራኤል ንጉሥ በሰዎች አንደበት ብቻ የሚመሰገን አይደለም ሕጻናትና መላእክት የሚያመሰግነት ነው።
በክብር የመጣው ንጉችን አህያይቱንና ውርንጫዋን አልናቃቸውም፣ ታዲያ እንዴት እኛን ይጠየፈናል? በሰው ዘንድ ብንናቅም በክብር ጌታ ዘንድ ክቡራን ነን፤ በኃጢአት ብንወድቅም የሚያነሳን አባት አለን፤ በሆሣዕና አክብሮ በአርብ በሚሰቅል ዓለም መጽናኛችንና መተማመኛችን በልባችን ቤተ መቅደስ የምናከብረው፤ አንጽሖት እንዲያደርግልን በእልልታና በምስጋና ወደ ሰውነታችን ቤተ መቅደስ የምንጠራው የሆሣዕናው ጌታ የእኛ የተናቅነው መነሻችን፣ ከምንፈራው መደበቂያችን፣ ከጨለማ መውጫ ብርሃናችን ክርስቶስ ኢየሱስ ነው ደግሞ ካለፈው ዓመት ላይ ወደ ልባቸው ቢመለሱ ብሎ አንድ ዓመት የንስሐ እድሜ ጨምሮ ለዚህ አደረሰን ክብር ለስሙ ይሁን !
+ ብፁዕ አቡነ ሄኖክ ሊቀ ጳጳስ እንደጻፉት እንኳን ለበዓለ ሆሣዕና በሰላምና በጤና አደረሰን አደረሳችሁ !