19/06/2026
ሊቨርፑል ለምን ዲዮማንዴን አጥብቆ ፈለገ?
በዘመናዊው እግር ኳስ እጅግ ተፈላጊ ከሆኑ የወቅቱ ተጨዋቾች መካከል አይቮሪኮስታዊው የ19 አመቱ የአርቢ ሌይብዚሽ ኮከብ ያን ዲዮማንዴ አንዱ ነው፡፡
ይህ ተጨዋች በተለይም በተጠናቀቀው የውድድር አመት ያሳየው ብቃት ይበልጥ የአውሮፓ ክለቦች ትኩረት እንዲያደርጉበት ምክንያት ሆኗል፡፡
ድዮማንዴ በሁሉም ውድድሮች ባደረጋቸው 36 ጨዋታዎች 13 ጎሎችን አስቆጥሮ 9 ግብ የሆኑ ኳሶችን ደግሞ አመቻችቶ ማቀበል ችሏል፡፡
የፈረንሳዩ ሀያል ክለብ ፓሪሴንት ዤርሜይን ለዚህ ተጨዋች ያለው ፍላጎት በየጊዜው ከፍ እያለ የሚገኝ ሲሆን ነገር ግን ሊቨርፑል ይበልጥ የፊት መስመር ክፍሉን ለማጠናከር ዲዮማንዴ ትክክለኛው ተጨዋች ስለመሆኑ ያምናል፡፡
የብዙ ክህሎቶች ባለቤት የሆነው ወጣቱን አመቱ ኮከብ ለማስፈረም የመርሲሳይዱ ክለብ በያዝነው ሳምንት 100 ሚልዮን ዩሮ ለጀርመኑ ክለብ አርቢ ሌይብዚሽ ቢያቀርብም 120 ሚልዮን ዩሮ ካለሆነ በፍጹም አልሸጥም ሲል አሳውቋል፡፡
ሊቨርፑል ባሳለፍነው የውድድር አመት በልዩነት ልዊስ ዲያዝን መሸጡ እንዲሁም የዲያጎ ጆታ ድንገተኛ ህልፈት እንዲሁም የግብጻዊው ኮከብ ሞሐመድ ሳላህ በጥሩ ብቃት ላይ አለመገኘት የፊት መስመሩ የበለጠ እንዲጋለጥ አድርጎታል፡፡
በበርካታ ሚልዮን ፓውንዶች ፈሶባቸው እንደ አሌክሳንደር ኢሳክ እና ሁጎ ኢኪቲኬ የመሳሰሉ ከዋክብቶች አንፊልድ ቢደርሱም ለአሰልጣኝ አርነ ስሎት እንዳይሰናበቱ ዋስትና መሆን አልቻሉም፡፡
በሊቨርፑል የነገሰው ሞሐመድ ሳላህ ሊቨርፑልን መልቀቅ እንዲሁም የኮዲ ጋክፖ በሚጠበቀው ልጅ አለመሆን ቀያዮቹ የፊት መስመር ክፍላቸውን የግዴታ ማጠናከር እንዳለባቸው የወሰኑበት ጉዳይ ሆኗል፡፡
ፍጥነት፣ የአንድ ለአንድ ግንኙነቶች ላይ ያለው አስደናቂ ብቃት፣ በግቦች ላይ የሚሳተፍበት አስደናቂ ንጻሬው በልዩነት መለያው የሆነው ዲዮማንዴ ደግሞ ለሊቨርፑላውያን ህልም ከሆነ ሰነባብቷል፡፡
100 ሚልዮን ዩሮ በአርቢ ሌይብዚሽ ውድቅ የሆነበት ሊቨርፑል የሂሳብ ማሻሻያ አድርጎ በድጋሚ ጥያቄ እንደሚያቀርብ ይጠበቃል፡፡
120 ሚልዮን ዩሮ እንደሚሸጠው የተማመነው አርቢ ሌይብዚሽ በተለይም ኮከቡ በዓለም ዋንጫ የምድብ ጨዋታ ሀገሩ አይቮሪኮስት ኢኳዶርን ባሸነፈበት ምሽት ያሳየው አስደናቂ ብቃት ጠረጴዛውን ወልውሎ ሚልዮን ዩሮዎችን እንዲጠበቅ ትልቅ የልብ ልብ ሰጥቶታል፡፡
እንደ አንቷን ሴሜንዮ ከመሳሰሉ ጋር የሰሩት እና ፈጣን የፊት መስመር ተጨዋቾችን ይበልጥ የሚያደንቁት የአንፊልዱ ተሿሚ አንዶኒ ኢራዮላ ዲዮማንዴ ለስብስባቸው ቁልፍ ተጨዋች እንደሚሆን ያምናሉ፡፡
ሊቨርፑል በክረምቱ ተጨማሪ ዝውውሮች በመፈጸም ይበልጥ ራሱን እንደሚያጠናከር ይጠበቃል፡፡