18/09/2025
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለኤርትራ ምላሽ ሰጠ
ኢትዮጵያ አሁን ላይ የባህር በር ያስፈልጋታል ወይስ አያስፈልጋትም የሚለውን መመለስ የምንችለው እኛና እኛ ኢትዮጵያዊያን ብቻ ነን ሲል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡ ሚኒስትር መስሪያ ቤቱ ይህንን የገለጸው በባህር ጥያቄ ላይ በኤርትራ በኩል የሚሰነዘሩ ሀሳቦችን በተመለከተ ማብራሪያ በሰጠበት ወቅት ነው።
የኢፌዴሪ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በዛሬው ዕለት በሰጠው ሳምንታዊ መግለጫ፤ 4 ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ትኩረት አድርጓል። እነርሱም የሕዳሴ ግድብ መመረቅ እና ዲፕሎማሲያዊ አድምታዎቹን፣ ባሳለፍነው ሳምንት የተከናወኑ የአፍሪካ ካሬቢያን ሀገራት እና የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤን በተለመለከተ እንዲሁም፤ በቀጣይ ሳምንት በሚከናወነው 80ኛው የተባበሩት መንግሥታት ጉባኤን የተመለከቱ ናቸው።
ቀጣይ ሳምንት በሚካሄደው 80ኛው የተባበሩትን መንግሥታት ድርጅት ጉባኤ መስራች የሆነችው ኢትዮጵያ በዚህ ጉባኤ ተሳታፊ ከሆኑ ሀገራት መካከል ስትሆን፤ ብሔራዊ ጥቅሟቿን ለማስጠበቅ ትሳተፋለች ሲሉም የሚኒስቴሩ ቃል አቀባይ አምባሳደር ነቢያት ጌታቸው ተናግረዋል።
አምባሳደሩ "ከሰሞኑ በተለያዩ መድረኮች የኢትዮጵያ ባለስልጣናት የባህር በርን በተመለከተ እየሰጡት ያለውን አስተያየት አስመልክቶ የኤርትራ መንግሥትን ምላሽ እንዴት ይመለከቱታል?" ተብለው ተጠይቀዋል።
ይህንን ሲመልሱም፤ የባህር በር አስፈላጊነትን በሚመለከት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ እንዲሁም ከፍተኛ አመራሮች በተደጋጋሚ የተገለጸ ነው ብለዋል።
በተጨማሪም "የባህር በር ለምን እንደሚያስፈልግ የምናውቀው እኛ ኢትዮጵያዊን ብቻ ነን!" ያሉ ሲሆን ለምን እንደሚያስፈልገን በግልፅ አስቀምጠናል" ሲሉም ገልጸዋል። ይህንን ማግኘት የምንችልበት ሰላማዊ፣ ዲፕሎማሲያዊ፣ ፍትሀዊ እና ሕጋዊ መንገድ በተመለከተ ይሆናል ሲሉም አስረድተዋል።
ይህ የባህር በር አስፈላጊነት በተመለከተ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በጎረቤት ሀገራት መሪዎች ጭምር መገለጹን አስረደተዋል። ከሰሞኑ የሶማሊያው ፕሬዝዳት ሀሰን ሼክ መሐመድ በሰጡት ቃል መልልስ ላይ የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ተገቢነት ያለው ነው ማለታቸው መዘገቡ ይታወሳል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ "ዛሬ የኛ የሆነውን ቀይ ባሕርን መልሶ ለመጠየቅ የሚሰጋ፣ የሚጠራጠር ትውልድ መፈጠሩ የሥነ-ልቦና ስብራት አካል ነው" ማለታቸው ይታወሳል፡፡