
07/29/2025
ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ የአቋም መግለጫ፤
*****
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የማዕከላዊ ኮሚቴ ከሐምሌ 19 እስከ 20 ቀን 2017 ዓ.ም ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ፣ በአማራ ክልል፣ በሀገራዊ እና ቀጠናዊ ጉዳዮች ዙሪያ ሰፊ ወይይትና ግምገማ ያደረገ ሲሆን፣ ይሄን ተከትሎ በልዩ ሁኔታ አቋም የተያዘባቸውን ጉዳዮች በመለየት የሚከተለውን የአቋም መግለጫ አውጥቷል።
1. የአማራ ክልል ወቅታዊ የሰላምና ፀጥታ ሁኔታን በተመለከተ፤
በአማራ ክልል ውስጥ ያለው ከፍተኛ የፀጥታ፣ የሰብአዊ እና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ተባብሶ እንደቀጠለ ይገኛል። በዚህ ምክንያት በዜጎች ህይወት እና ንብረት ላይ እየደረሰ ያለው ጉዳት አሳሳቢ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ይታወቃል። በርካታ ንጹሃን ወገኖቻችን ህይወታቸውን እያጡ ሲሆን፣ ብዙወች አካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፣ ከመኖሪያ ቀያቸው ተፈናቅለዋል። የተፈጠረውን ግጭት፣ አለመረጋጋት እና አጠቃላይ የደህንነት ስጋት ተከተሎ የዝርፊያ ወንጀል በስፋት እየተፈፀመ ይገኛል። ስለሆነም እነዚህ የህዝባችንን ሰቆቃ ያራዘሙ የጥፋት ድርጊቶች በፍጥነት እንዲቆሙ አብን በጥብቅ ይጠይቃል።
በአሁኑ ወቅት የአማራ ህዝብ በክልሉ ውስጥ ለዘመናት ያላያቸው ከፍተኛ ሰቆቃዎች እና ጥፋቶች እየደረሱበት ነው። በዚህም የአማራ ልጆች ከትምህርት ገበታቸው ተስተጓጉለዋል፣ እናቶችና ህጻናት ከክትባት፣ ገበሬዎች ከእርሻ ስራ እና ከእንስሳት እርባታ ተግባራት፤ ነጋዴዎች ከንግድ እንቅስቃሴ ተሰተጓጉለው እየባከኑ ያለበት አሳዛኝ ሁኔታ ተፈጥሯል። ሴቶች ተደፍረዋል፣ ሰላማዊ ሰወች ታግተዋል፣ ተዘርፈዋል፣ በተኩስ ልውውጥ ሙሉ ቤተሰብ በከባድ መሳሪያ ተቀጥፏል፣ ንጹሀኖች በወጡበት ቀርተዋል። ባጠቃላይ ግጭቱ ክልላዊ ብሎም ሃገራዊ ፈተና የደቀነ በመሆኑ ተሳታፊ አካላቱ፣ የአማራ ህዝብ እና የህዝባችን ወዳጆች በሙሉ በቃ ሊሉት ይገባል።
በዋናነት ለአማራ ህዝብ መሰረታዊ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት እና ዘላቂ ጥቅሙን ለማስከበር ከሰላማዊ ትግል ባሻገር ያለ አዋጪ መንገድ እንደሌለ በግልፅ ሊሰመርበት ይገባል። እስካሁን ባለው የትግል ሂደት ገና እልባት ያላገኙ ጥያቄዎች መኖራቸው ግልጽ ነው። ሆኖም ከችግሮቹ ስፋት እና ውስብስብነት እንዲሁም ከጠላቶቹ ክፋትና ሴራ አኳያ በአንፃሩ አጭር በሚባል ጊዜ ቀላል የማይባሉ ድሎችን ማሳካት ተችሎ ነበር። እነዚህ ድሎች እውን የሆኑት የአማራ ህዝብ ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ወገኖቹ ጋር በተግባቦትና በትብብር ባደርገው ትግል ነው። ስለሆነም በአሁኑ ወቅት የአማራን ህዝብ እና ኢትዮጵያን በቀውስ አዙሪት ውስጥ የማስገባት ዘላቂ ግብ ያላቸው ታሪካዊ ጠላቶች ክልሉን የሴራ ፖለቲካቸው መተወኛ መድረክ አድርገው ለመጠቀም የሚያካሂዱትን የጥፋት ስምሪት የአማራ ህዝብ በግንባር ቀደምነት ሊቃወመው ይገባል።
ከዚህ አንፃር በክልሉ ዉስጥ የሚንቀሳቀሱት የታጠቁ ኃይሎች የአማራን ህዝብ የሰላም ፍላጎት አክብረው የመፍትሄ አካል እንዲሆኑ አብን ጥሪውን ያቀርባል። እንደሚታወቀዉ ባለፉት ዓመታት የአማራ ህዝብ ብሎም መላው የኢትዮጵያ ህዝብ በከባድ ፈተናዎች ውስጥ አልፈዋል። አብዛኞቻችሁ የህዝባችሁን እና የሀገራችሁን ጥሪ በቅን ልቦና ተቀብላችሁ እና በጀግነንት ተሰልፋቸሁ መታገላችሁ ይታወቃል። ነገር ግን በአሁኑ ወቅት የወሰዳችሁት አቋምና የተከተላችሁት የትግል መስመር እንደምታዩት የህዝባችንን ሁኔታ ከድጡ ወደ ማጡ ከማሸጋገርና ይባስ ብሎም ለፀረ-አማራና ፀረ-ኢትዮጵያ ኃይሎች መጠቀሚያ ከመሆን ያለፈ ዉጤት የለውም።
ይሄን እውነታ ለመረዳት እና ውሳኔያችሁ በአማራ ህዝብ ላይ ያስከተለውን ቀውስ ለመገምገም ከበቂ በላይ ግዜ አልፏል። ስለሆነም ከምር ግባችሁ የአማራ ህዝብ ደህንነት ከሆነ በህዝባችን ላይ ከእስካሁን በደረሰው ሁለንተናዊ ጉዳት እና በቀጣይ ባለው ክልላዊና ሀገራዊ ስጋት ዙሪያ የተሻለ ግንዛቤ ይዛችኋል ብለን እናምናለን። ከሁሉም በላይ የህዝባችን አሁናዊና የነገ ሁኔታ ሊታያችሁና ሊያሳስባችሁ ይገባል። የሰላም መንገድ ረጅም ቢሆን እንኳ የህዝባችንን ዘላቂ ግብና ፍላጎትን ለማሳካት ብቸኛው አማራጭ መሆኑን በድጋሚ ማስታወስ እንሻለን።
በዚህ ረገድ፤
ለመላው የአማራ ህዝብ፦
እንደሚታወቀው ላለፉት በርካታ አሰርት-አመታት በኢትዮጵያ ጠል ሃይሎች የጥፋት ተልዕኮ አማካኝነት የኢትዮጵያ የፖለቲካ ታሪክ የተለየ ባለእዳ ተደርገህ በመፈረጅህ ከፍተኛና ያልተገባ ዋጋ ስትከፍል መቆየትህ ፀሐይ የሞቀው ሀቅ ነው። ይህን እኩይ የባለእዳነት ትርክትና ጥቃት ለመቀልበስ የተጀመሩ ጥረቶች ሁሉ በጠላት ሴራ እየተጠለፉ ሲዳከሙ ብሎም ሲከሽፉ ማስተዋላችን የትናንት ብቻ ሳይሆን የዛሬም ገጠመኛችን ሆኖ ባጅቷል።
በመሰረቱ ህዝባችን ትልቅ ህዝብ ሆኖ ሳለ ጠንካራ አደረጃጀቶችን ፈጥሮ በመታገል ልክ እንደ ጥንቱ ለራሱ ህልውና ብቻ ሳይሆን ሃገርን የሚያፀና ሚና መጫወት እንዳይችል እየተደረገ ያለበት አሻጥር በቃ ሊባል ይገባል። ህዝባችን በተደራጀ ሰላማዊ ትግል ከግብና አላማው መድረስ ይችላል በሚለው ሃቅ ላይ ቅንጣት ጥርጣሬ የለንም።
ለመላው ኢትዮጵያውያን፦
ሃገራችን የሰላም አየር አግኝታ በዘላቂ የህዝቧ ጥቅም መረጋገጥ ላይ እንዳታተኩር ፋታ የማይሰጥ የቀውስ አዙሪት ውስጥ እንድትቆይ ማድረግ የሩቅና የቅርብ ታሪካዊ ጠላቶቿ ስትራቴጂካዊ ግብ ሆኖ ቀጥሏል። ከዚህ የጠላት ወጥመድ መውጫ ብቸኛው መንገድ ጠንካራ የሆነ የአንድነት እና የህብረት መንፈስ ብቻ ነው። ትናንት አያት ቅድመ አያቶቻችን የጥቁር ዘር የኩራትና ክብር ምንጭ የሆነውን ድል የማስመዝገባቸው ምስጢር ኢትዮጵያዊ ህብረትና አንድነታቸው ነበር። የወቅቱን የባርነትና የቅኝ ግዛት ጥላ የገፈፉትና ያስወገዱት በህብረታቸው ነበር። የአሁኑ ትውልድም መልካቸውን ቀይረው የገጠሙትን ከትናንት ተንከባላይ ፈተናዎች መሻገሪያ ድልድይ ህብረት ብቻ መሆኑን ላፍታም መዘንጋት የለብንም።
ለመንግስት ሚዲያወች እንዲሁም ለግል ሚዲያዎች፦
እንደሚታወቀው ሃገራችን በዙሪያ መለስ ፈተናዎች ውስጥ እያለፈች ነው። በዚህ አውድ ውስጥ የሚደረጉ የህዝብ ግንኙነትና የመረጃ ስርጭት ተግባራት እንድነትንና ሰላምና አንባሪ መሆን ይጠበቅባቸዋል። ከዚህ አንፃር በአማራ ክልልም ሆነ በሌሎች አካባቢዎች መሳሪያ ያነሱ ኃይሎች የሰላም መንገድን መርጠውና ሰላምን ተቀብለው በሚመጡበት ወቅት የመንግስት ሚዲያወች ይህንን የሰላም እርምጃ ከማበረታታትና ከመደገፍ ይልቅ አሉታዊና ገፊ የሆኑ አገላለፆችን ከመጠቀም እንዲቆጠቡ በጥብቅ እናሳሰባለን።
ለአብነትም በአማራ ክልል ውስጥ ታጣቂወች ይዘውት የነበረው መንገድ ለህዝባቸው እና ለሃገራቸው የማይበጅ መሆኑን ተረድተው የሰላም መንገድን የመረጡ ወንድሞችና እህቶች ትተውት በመጡት የቀደመ ተግባር "ፅንፈኞች" ተብለው መገለፅ የለባቸውም። በኦነግ ሸኔ ታጣቂዎችም እንዲሁ የሰላምን መንገድ መርጠው ሳለ ከሽብር ድርጅቱ ጋር መፈረጅ የለባቸውም። የሰላምን ጥሪ አዳምጦ አክብሮና ተቀብሎ ወደ ሰላም የሚመጣ ሀይልን አሁንም "ፅንፈኛ" እያሉ መፈረጅ በህዝባችን ላይ እየደረሰ ያለውን ሰቆቃ እውቅና አለመስጠትና ሰላምንም አለማበረታታት ተደርጎ የሚወሰድ ሀላፊነት የጎደለው ብያኔ ካልሆነ በቀር ሌላ ሊባል አይችልም። በመሆኑም የሚዲያ አካላት በዚህ መሰል ጉዳዮች ላይ የሚኖራቸው የህዝብ ግንኙነት ስራ በጥንቃቄና ከፍተኛ ሃላፊነት በተሞላበት መንገድ እንዲሆን እናሳስባለን።
2. ሀገራዊ ሁኔታ፣ የፀጥታ አለመረጋጋት እና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች፤
ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት የበርካታ ፈተናዎች ማዕከል ሆናለች። የፀጥታ አለመረጋጋት፣ የኑሮ ውድነት እና የማህበራዊ ትስስር መላላት የሀገሪቱን አንድነትና ሰላም አደጋ ላይ ጥለዋል። የዜጎች የኑሮ ሁኔታ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየከፋ የመጣ ሲሆን፣ የዋጋ ግሽበት የበርካታ ቤተሰቦችን አቅም አሟጧል። በመሆኑም ከሁሉም ወገን በተለይም ከመንግሶቶ ለሃገራዊ መፍትሄዎች ሁሉ ያላሰለሰ ቁርጠኝነት እንዲኖረው ስንል እንጠይቃለን።
ብሄራዊ ምክክር እንደ ስሙ በብሄራዊ ደረጃ ተካሂዶ የሁሉም የህብረተሰብ ክፍል ተሳትፎ እንዲረጋገጥ አብን ያሳስባል። እውነተኛ እና ሁሉን አቀፍ ውይይት ከሌለ፣ የሀገሪቱን ዘላቂ ሰላም እና ብልፅግና ማረጋገጥ አይቻልም። ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች እና ባለድርሻ አካላት በሰከነ መንፈስ ተነጋግረው ሀገራዊ መግባባትን እና ዘላቂ መፍትሄዎችን እንዲሹ ጥሪያችንን እናቀርባለን። የዜጎች ሰብአዊ መብት በሀገር ደረጃ እንዲከበር እና ሁሉም ዜጋ የህግ የበላይነት እንዲጠበቅለት አብን አጥብቆ ያሳስባል። የመድብለ ፓርቲ ስርዓት እንዲጠናከር እና ዴሞክራሲያዊ ተቋማት ገለልተኛ ሆነው እንዲሰሩ መንግስት በቁርጠኝነት እና በላቀ ነሳሽነት እንዲሰራ እንጠይቃለን። ዴሞክራሲያዊ ተቋማትን በማጠናከር ሂደቱ ከፓርቲያችን የሚጠበቅን ሚናም ያለማመንታት እንወጣለን።
3. ቀጠናዊ ጉዳዮች፣ የአፍሪካ ቀንድ፣ የባህር በር ጥያቄ እና የሻዕቢያ ሰሞነኛ አቋም፣
የአፍሪካ ቀንድ አካባቢ የፖለቲካ አለመረጋጋት እና ግጭቶች የተሞላበት ቀጠና ሲሆን፣ ይህ ሁኔታ በኢትዮጵያ ላይ ቀጥተኛ ተፅዕኖ እያሳደረ ይገኛል። የኤርትራና የሱማሊያ ጉዳይ፣ የሱዳን ቀውስ እንዲሁም በሌሎች አጎራባች ሀገራት ያሉ ችግሮች በኢትዮጵያ ውስጣዊ ጉዳዮች ላይ አሉታዊ ተፅእኖ አላቸው። የጎረቤት ሀገራት መረጋጋት ለኢትዮጵያ ሰላም ወሳኝ እንደሆነ አብን በጥብቅ ይገነዘባል። ውስጣዊ አንድነትና መረጋጋት የልማት ፍላጎታችን ማሳኪያ ብቻ ሳይሆን በዚህ አደገኛ ቀጠና ህልውናችንን የማረጋገጫ ፍኖትም ነው።
ከዚህም ባሻገር የባህር በር ጥያቄ የሀገሪቱን ህልውና እና ብልፅግና የሚመለከት ወሳኝ ጉዳይ ነው። ይህ ጥያቄ ብሄራዊ መግባባትን ሊፈጥር ይገባል ብለን እናምናለን። ስለሆነም የፖለቲካና ርዕዮት ዓለም ልዩነቶች በዘላቂ ብሄራዊ ጥቅሞቻችን ላይ ጥላ ማጥላት የለባቸውም። በመሆኑም የባህር በር ጥያቄን መላው ኢትዮጵያዊያን እና አደረጃጀቶች ሁሉ ልንታገልለት የሚገባ ብሔራዊ ጥቅማችን ነው ብሎ አብን በፅኑ ያምናል።
የባህር በር ጉዳይ የኢትዮጵያ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን የመላው ቀጠና ሰላም እና መረጋጋት ጋር የተቆራኘ መሆኑ ግንዛቤ ሊያዝበት ይገባል። ስለሆነም በዚህ ረገድ የሻቢያ መንግስት ባልተገራ ሁኔታ በሀገራችን የውስጥ ጉዳዮች የሚያድርገውን ጣለቃገብነት፣ በተለይም የሃገራችንን ሰላም ለማናጋት የሚፈጽማቸውን የፕሮፖጋንዳ፣ የሴራ እና ህቡዕ የጥፋት ስምሪቶች ባስችኳይ እንዲያቆም እናሳስባልን።
ምናልባት ሻዕቢያ በሂደት ተገንዝቦ ከጥፋት ድርጊቱ ሊታቅብ ይችል ይሆናል በሚል፣ ካልሆንም ሻዕቢያን በታሪክ ማህደር ለማስቀመጥ፤ ታሪኩን፣ ምግባሩን እና ፍላጎቱን በተመለከተ ቀደም ባሉ መግለጫዎቻችን ላይ በግልጽና በዝርዝር ለኢትዮጵያ ህዝብ ስናስገነዝብ ቆይተናል። ሆኖም አሁንም አፍራሽ ተግባራቱን አጠናክሮ የቀጠለ በመሆኑ በመጨረሻ ለሚከሰተው ጥፋት ሃላፊነት እንደሚወስድ ለማሳሰብ እንወዳለን። አንባገነኑ ሻዕቢያ የያዘው መንገድ ለጭቁን የኤርትራ ህዝቦች የማይጠቅም መሆኑንም አበክረን መግለፅ እንፈልጋለን።
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)
ሐምሌ 21 ቀን፣ 2017 ዓ.ም