11/18/2025
''ትምህርት ሚኒስተር ልክ እንደ አፄ ስርአት እየሆነብን ነው''ሸይኽ ሀጂ ኢብራሂም ቱፋ
ከኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የተሰጠ መግለጫ
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት በጠቅላይ ም/ቤቱ ማቋቋሚ አዋጅ ቁጥር 1207/2012 እና በህገ መጅሊስ 2015 በተሰጠው ስልጣን መሰረት ማንኛውም የመንግስት አካል የሚወስናቸው ውሳኔዎች እና የሚፈጽማቸው ተግባራት የህዝበ ሙስሊሙን ሀይማኖታዊ መብት የሚጋፉ/የሚጣረሱ መሆናቸው ሲያረጋግጥ እርምት/ማስተካከያ እንዲደረግ የማድረግ ሙሉ ሀላፊነት ተሰጥቶታል፡፡
በዚሁ መሰረት የብዝሀ ሃይማኖት ባለቤት የሆነችው አገራችን ኢትዮጵያ በልዩነት ውስጥ ያለ መከባበርና መደጋገፍ ተምሳሌት እንደሆነችና ይህም ልዩ ውበቷ መሆኑ ይታወቃል፡፡ እንደ መንግስትም ይህንን እሴት በመጠበቅና የህዝበ ሙስሊሙ ለረዥም ግዜ ሲጠይቃቸውና ሲታገልላቸው የነበሩ ጥያቄዎች እየተመለሱ መሆኑ እናምናለን፡፡
ቀሪ ያልተመለሱ ጥያቄዎች እንዳሉና እነዚህም በአላህ ፈቃድ ወደ ፊት እንደሚመለሱ ተስፋም እናደርጋለን፡፡ በተጨማሪም በመንግስት በኩል ከመቼውም ግዜ በላቀ ሁኔታ ከህዝበ ሙስሊሙ መሪ ተቋም ጋር ተግባብቶና ተናቦ አመርቂ ስራዎች እየሰራን እንገኛለን ለዚህም ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስተራችን ዶ/ር አብይ አህመድ እና ለመንግስታቸው እንደተለመደው ሁሉ ከልብ የመነጨ ምስጋናችንን እናቀርባለን፡፡
ነገር ግን በተለያዩ ግዜያት በትምህርት ሚኒስቴር በኩል የሚወሰኑ ውሳኔዎች፣ የሚወሰዱ እርምጃዎች እና እየተወሰዱ ያሉ አቋሞች የህዝበ ሙስሊሙ መብት በእጅጉ የሚጋፉ ሆኖ አግንተናቸዋል፡፡ እነዚህ ድርጊቶች ከግዜ ግዜ ይሻሻላሉ፣ ከመሪ ተቋሙም ጋር በውይይት ይፈታሉ በሚል በትዕግስት ብንጠባበቅም በተለያዩ ግዜያት በክቡር የትምህርት ሚኒስተሩ በኩል እየተወሰዱ ያሉ የተናጥል እርምጃዎችና የተያዙ አቋሞች የህዝበ ሙስሊሙን መብት በእጅጉ የሚጥሱ እና በተጨባጭ ከኢ.ፌ.ድ.ሪ መንግስት አቋም የተለየ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡ እነዚህም፦
1. የሙስሊም ሴት ተማሪዎች የእምነት አለባበስ (ሂጃብ) ለብሶ የመማር መብት በተመለከተ፦
ከኢ.ፌ.ድ.ሪ ህገ መንግስት ጀምሮ በሀገሪቱ ውስጥ ያሉ የተለያዩ ህጎች ብንመለከት ሙስሊም ሴት ተማሪዎች ሀይማኖታቸው ግዴታ ያደረገባቸው ልብስ ለብሰው ትምህርት እንዳይማሩ የሚከለክል ህግ የለም፡፡ ቢኖር እንኳን በህግ መንግስቱ አንቀጽ 27 የተደነገገው የሀይማኖት፣ የእምነትና የአመለካከት ነጻነት መብት ጋር የሚጋጭ በመሆኑ እና የህገ መንግስቱ አንቀጽ 9(1) መሰረት የማንኛውም የመንግስት አካል/ባለስልጣን ውሳኔ ከህገ መንግስቱ ጋር የሚጋጭ ከሆነ ተፈጻሚነት አይኖረውም ይላል በመሆኑም ሙስሊም ሴት ተማሪዎች ሀይማኖታቸው ግዴታ ያደረገባቸው ልብስ ለብሰው መማር አይችሉም የሚል የባለስልጣን የግል ውሳኔ ከህገ መንግስቱ ጋር በቀጥታ የሚጣረስ በመሆኑ ተፈጻሚነት ሊኖረው አይገባም፡፡
ነገር ግን ህገ መንግስቱ በዚህ ልክ ግልጽ ሆኖ እያለ የትምህርት ሚኒስቴር እንደ ተቋም እና ሚኒስተሩ በተለያየ ግዜ በሚያደርጓቸው ንግግሮች እና በሚሰጧቸው ማብራሪያዎች ሙስሊም ሴት ተማሪዎች ሀይማኖታቸው ግዴታ ያደረገባቸው ሂጃብ የተሳሳተ ትርጉም ሲሰጡ እና ለብሰው መማር አይችሉም የሚል አንድምታ ያለው ንግግር ሲያደርጉ ይስተዋላል፡፡ ይህ ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው ህዝበ ሙስሊሙ እና የህዝበ ሙስሊሙ መሪ ተቋም እያሳዘነ ያለ ጉዳይ ነው፡፡ ትምህርት ሚኒስተር ወቅቱ በሚመጥኑ በተለያዩ የትምህርት ጥራት ሊያመጡ በሚችሉ ጉዳዮች ላይ ማተኮር በሚጠበቅበት በዚህ ወሳኝ ወቅት በየግዜው የሙስሊም ሴት ተማሪዎች ሂጃብ ጉዳይ ለምን አጀንዳ እንዲሆን እንደፈለገ እና የተፈለገው ውጤት ምን እንደሆነ መገመት አይሳነንም፡፡
ሙስሊም ሴት ተማሪዎች የሌላውን መብት ሳይነኩ እና በትምህርት ቤት ውስጥ ሊከሰቱ የሚችሉ የቅድመ ጥንቃቄ የደህንነት ጉዳዮች በሌሎች አማራጮች መከላከል እየተቻለ ሀይማኖታቸው ግዴታ ያደረገባቸው ልብስ ለብሰው እንዳይማሩ መከልከሉ ህጋዊ ያልሆነ እና በምንም አመክንዮ ተቀባይነት ያለው አይደለም፡፡ በዚህ ረገድ ሚኒስተሩ ጨምሮ አንዳንድ አካላት የኢ.ፌ.ድ.ሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 11 እና አንቀጽ 90(2) የሚረዱበት መንገድ ከድንጋጌዎቹ አውድ ውጪ እና ከህገ መንግስቱ አጽዳቂ ጉባኤ አባላት ሃሳብና ፍላጎት ውጪ በመሆኑ ተቀባይነት ያለው አይደለም፡፡
በመሆኑም የትምህርት ሚኒስቴር የሙስሊም ሴት ተማሪዎች አለባበስ በተመለከተ እየወሰደው ያለው እርምጃ እና የያዘው አቋም ከህዝበ ሙስሊሙ መሪ ተቋም ውይይት ያልተደረገበትና መግባባት ላይ ያልተደረሰበት በመሆኑ በኛ በኩል አጥብቀን እንቃወመዋለን፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ የትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትሩ በ02/03/2018 በአዳማ ከተማ በተካሄደው አገራዊ የትምህርት ጉባኤ ላይ በሂጃብም ሆነ በሰላት ጉዳይ ከመጅሊስ ሀላፊዎች ጋር መግባባት ላይ ተደርሷል በሚል ያስተላለፉት ንግግር ከእውነት የራቀ እና እንደ መጅሊስ ከሚኒስተሩ ጋር የተግባባንበት ምንም አይነት ነገር እንደሌለ እየገለጽን በሚኒስተሩ በኩል ተቋማችን በሚመለከት ለተሰራጨው ሀሰተኛ መረጃ በግልጽ ማስተካከያ እንዲደረግ በጥብቅ እናሳስባለን፡፡
2. በአማራ ክልል ሙስሊም ተማሪዎች ግዕዝ በግዳጅ እንዲማሩ በትምህርት ቢሮው በኩል የተወሰነው ውሳኔ በተመለከተ፦
የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ በክልሉ ውስጥ በሚገኙ ሁሉም የ1ኛ ደረጃ ት/ቤቶች ከወላጆች እና ከህዝበ ሙስሊሙ መሪ ተቋም መጅሊስ ጋር ውይይት ሳይደረግበት ሙስሊም ተማሪዎች ያለፍላጎታቸው በግዳጅ ግዕዝ እንዲማሩ የወሰነው ውሳኔ መላው የክልሉ ህዝበ ሙስሊም እና በተለያየ እርከን ያሉ የክልሉ መጅሊስ ተቃውመውታል፡፡
ስለሆነም እንደ ኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤትም የክልሉ ህዝበ ሙስሊም እና መሪ ተቋሙ ያልተቀበለው፣ ምክክር ያልተደረገበት እና ህጻናትን በግዳጅ ለማስተማር ሊያደርግ የሚችል የህግ መሰረት በሌለበት ግዕዝን በግዳጅ ለማስተማር ያሳለፈው ውሳኔ ክልሉ ያለበትን ውስብስብ ችግር በበለጠ የሚያባብስ እና ውጤቱም እጅግ በጣም አደገኛ ሊሆን የሚችል በመሆኑ እንደ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤትም ውሳኔው የምንቃወመው ሲሆን የክልሉ ት/ቢሮም ውሳኔው በድጋሚ እንዲያጤነው እና የእርምት እርምጃ እንዲወስድ እንጠይቃለን፡፡
የክልሉ ት/ቢሮ ውሳኔ ከአገራዊ የትምህርት ፖሊሲው እና ከአጠቃላይ የትምህርት አዋጅ ቁጥር 1368/2016 አንቀጽ 28 እና አንቀጽ 29 ጋር የሚጋጭ በመሆኑ እና ይህንን የማስቆም ሙሉ ሀላፊነትና ጉዳዩም በቀጥታ የሚመለከተው የትምህርት ሚኒስተር በመሆኑና ትምህርት ሚኒስተር በጉዳዩ ላይ ጣልቃ በመግባት ጉዳዩ እንዲያስቆመውና በህግ የተጣለበትን ሀላፊነት እንዲወጣ እናሳስባለን፡፡
3. የትግራይ ክልል ሙስሊም ሴት ተማሪዎች የእምነት አለባበስ ጉዳይ በተመለከተ፦
በትግራይ ክልል ያሉ ሴት ተማሪዎች በፌደራሉም ሆነ በክልሉ ህገ መንግስት እንዲሁም በሌሎች የአገሪቱ ህጎች የተፈቀደላቸውን የእምነት አለባበስ ለብሰው የመማር መብታቸው ተጥሶ ላለፉት 2 ዓመታት ከትምህርት ገበታ ውጪ ሆነዋል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከተው የትምህርት ሚኒስተር ተማሪዎቹ ወደ ትምህርታቸው እንዲመለሱ ምንም አይነት ጥረት አላደረገም፡፡
ይልቁንም የክልሉ መጅሊስ የተማሪዎቹ ህገ መንግስታዊ መብታቸው ለማስከበር በፍ/ቤት ክስ አቅርበው ጉዳዩ እስከ ክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ድረስ ደርሶ ፍርድ ቤቶቹ የተማሪዎቹ ሂጃብ ለብሰው የመማር መብት እንዳላቸው ውሳኔ ቢሰጡም የክልሉ መንግስት የፍ/ቤት ውሳኔ ለመፈጸም አሻፈረኝ ብሎ ተማሪዎቹ እስካሁን ወደ ትምህርታቸው አልተመለሱም፡፡
በመሆኑም የክልሉ መንግስት በፍ/ቤቶቹ ውሳኔ መሰረት ሙስሊም ተማሪዎች ሀይማኖታቸው ግዴታ ያደረገባቸው ሂጃብ ለብሰው እንዲማሩ እንዲያደርግና የፍርድ ቤቶቹ ውሳኔ እንዲፈጽም እየጠየቅን የትምህርት ሚኒስተርም ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከተው በመሆኑ በጉዳዩ ላይ ጣልቃ በመግባት ተማሪዎቹ ወደ ትምህርታቸው እንዲመለሱ እንዲያደርግና በህግ የተጣለበትን ሀላፊነት እንዲወጣ እናሳስባለን፡፡
በአጠቃላይ ከላይ የጠቀስናቸው የሙስሊም ተማሪዎች አሳሳቢ ጉዳይ እንደ መንግስት በዋናነት የትምህርት ሚኒስቴር በራሱ ከችግሩ እንዲላቀቅ እና ችግሩን ከስሩ እንዲፈታው እየጠየቅን የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴርም ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከተው በመሆኑ በህግ የተጣለበትን ሀላፊነት እንዲወጣ እናሳስባለን፡፡ ሌሎች የሚመለከታችሁ መንግስታዊም ሆነ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችም ጉዳዩ የሚመለከታችሁ በመሆኑ በዚሁ አጋጣሚ ጉዳዩ በልዩ ትኩረት እንድታዩት እና የሰላም መደፍረስ እንዳያስከትል እናሳውቃለን፡፡
በመጨረሻም እንደ ኢትዮጲያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ም/ቤቱ ጉዳዮቹን በቅርበት እየተከታተልናቸው የምንገኝ ሲሆን ከላይ የተጠቀሱት ችግሮችን ጨምሮ ሌሎች ህዝበ ሙስሊሙ የሚመለከቱ ችግሮች ከስር መሰረታቸው ለመፍታት እና ዘላቂ መፍትሄ ለማምጣት ይረዳ ዘንድ በዛሬው ዕለት ከተለያዩ ባለድርሻ ማለትም ከኡለማ፣ ከህግ ሙሁራን፣ ከማህበረስብ፣ ከሴቶችና ከወጣቶች እና ከሚዲያ ባለሙያዎች የተውጣጣ ከሚቴ በማዋቀር ወደ ስራ እንዲገባ ያደረግን መሆኑን እናሳውቃለን ሲል ጠቅላይ ምክር ቤቱ በመግለጫው አስታውቋል፡፡