20/09/2023
የኢትዮጵያ ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን መሪ አገልጋይ የነበሩት አቶ ዮናስ ዱባለ ወደ ጌታ ሄዱ፡፡
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል፣ ሶዶ ወረዳ በአናቲ ቀበሌ በደረሰ የትራፊክ አደጋ የኢትዮጵያ ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን መሪ አገልጋይ የነበሩት አቶ ዮናስ ዱባለ ወደ ጌታ ሄዱ፡፡
በተያያዘ መረጃ በዚህ እጅግ አሳዛኝ የትራፊክ አደጋ የሆሳዕና ከተማ እናት ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን መሪና አገልጋይ ዮናስ ዱባለን ጨምሮ አብረዋቸው የነበሩ ሁለት ጓደኞቻቸው ሕይወታቸው ማለፉ የተነገረ ሲሆን ይህንን ተከትሎም የሆሳዕና ከተማ ምዕመናን መሪር ሀዘን ውስጥ ይገኛሉ ተብሏል።
አቶ ዮናስ ዱባለ ከአባታቸው ከአቶ አየለ ዱባለና ከጣሊያናዊዋ እናታቸው ከወይዘሮ ፕሪዮና አንቶኒዮ መስከረም 16 ቀን 1964 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ ተወለዱ፡፡ አቶ ዮናስ አያታቸው ዘንድ በማደረጋቸው እስከ ዕለተ ህልፈታቸው ድረስ ዮናስ አየለ ከመባል ይልቅ ዮናስ ዱባለ ተብለው በእርሳቸው ሥም ሲጠሩ ኖረዋል፡፡ አቶ ዮናስ ዕድሜያቸው ለትምህርት በደረሰ ጊዜ አዲስ አበባ በሚገኘው በጦር ኃይሎች መሰረተ ዕድገት 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት፣ እንዲሁም በአዲስ ከተማ ደግሞ የ10ኛ እና 11ኛ ከፍል ትምህርትቸውን ከተከታተሉ በኋላ ወደ ሆሳዕና በማምራት በየካቲት 25/67 የ11ኛ እና 12ኛ ክፍሎችን አጠናቀዋል፡፡
ትምህርት ወዳድ የነበሩት አቶ ዮናስ የከፍተኛ ተቋማት ትምህርታቸውን በመቀጠል
• ከኢትዮ ኢንተርናሽናል ኮሌጅ የህግ ዲፕሎማቸውን፣
• ለቤተ ክርስቲያን መጋቢያንና አገልጋዮች የበሚሰጠው የመጽሐፍ ቅዱስ ሥልጠና ወይም ቢቲሲፒ እንደገና ዲፕሎማቸውን፣
• ከሮያል ኮሌጅ በሥራ አመራር ወይም ማኔጅመንት የመጀመርያ ድግሪያቸውን የተቀበሉ ሲሆን፣
• ሕይወታቸው እስካለፈበት ዕለት ድረስ ደግሞ በቢዝነስ ማኔጅመንት የሁለተኛ ድግሪ ወይም ማስተርስ ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ እንደነበሩ ታውቋል፡፡
ከአገልግሎት አንጻር አቶ ዮናስ ዱባለ በኢትዮጵያ ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን በተለያን በተለያ መዋቅሮች ላይ በሃላፊነት መንፈስና በትጋት በመሰማራት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡ በዚሁ መሰረት፡-
• የኢትዮጵያ ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን ብሔራዊ ቦርድ አባል፣
• በደቡብ ሸዋ ቀጣና በዋና ሰብሳቢነት፣
• በሆሳዕና አብያተ ክርስቲያናት ህብረት በምክትል ሰብሳነት፣
• በሆሳዕና እናት ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን ለ2 ዙር ማለትም ለ12 ዓመታት በሰብሳቢነት፣
• እንዲሁም እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በሆሳዕና አናሌሞ አጥቢያዎች ህብረት በምክትል ሰብሳቢነት እያገለገሉ ቆይተዋል፡፡
ከቤተ ክርስቲያን ውጭ በነበራቸው ሃላፊነትም በቀድሞው ደቡብ ክልል የትራንስፖርት ማህበራት ሊቀመንበርና በደቡብ ክልል የደቡብ ውበት ትራንስፖርት አክሲዮን ማህበር ፕሬዚዳንት በመሆን እያገለገሉ ነበር፡፡
የሶዶ ወረዳ የትራፊክ አደጋ መከላከልና ፍሰት ቁጥጥር ማስተባበሪያ ትናንት መስከረም 8 ቀን 2015 ዓ.ም ከጠዋቱ 12 ሰአት ላይ አደጋው መድረሱን አስታውቋል። አደጋው የተፈጠረው የሕዝብ ማመላለሻ FSR የሰሌዳ ቁጥር "ደቡብ 13955 " የሆነ 49 ሰዎችን ጭኖ ከአዲስ አበባ እየወጣ ሳለ ከሆሳዕና ወደ አዲስ አበባ በመጓዝ ላይ ከነበረ የሰሌዳ ቁጥሩ " B-20669 " ላንድ ክሩዘር መኪና ጋር በሶዶ ወረዳ አናቲ ቀበሌ በመጋጨቱ መሆኑም ተያይዞ ተነግሯል፡፡ በዚህ አደጋ ሳቢያ የ4 ሰዎች ሕይወት ወዲያው ሲያልፍ ሌሎች 4 ሰዎች ደግሞ ለከባድ ጉዳት መዳረጋቸው ታቋል፡፡
ፖሊስ አደጋው የተከሰተበት ሰአት የአየር ንብረቱ ጭጋጋማ እንደነበረና አደጋው የደረሰበት አካባቢም መንገዱ ብልሽት ያለበት መሆኑን ገልጿል። ይህ ቦታ በየጊዜው አደጋ እንደሚደርስበትና በተደጋጋሚ በትራፊክ አደጋ የሰዎች ሕይወት የሚቀጥፍበት፣ ንብረትም የሚወድመት መሆኑንም ፖሊስ አያይዞ ተጠቁሟል። የአቶ ዮናስ ዱባለን ድንገተኛ ህልፈት ተከትሎ የኢትዮጵያ ቃለ ሕይወት ፕሬዚዳንት ዶክተር ጣሰው ገብሬና ዋና ጸሐፊው ዶክተር ስምዖን ሙላትን ጨምሮ፣ በአዲስ አበባ የሚኖሩ የሆሳዕናና አካባቢው ተወላጆች፣ የቀጣናና ልዩ ህብረቶች አመራሮችና በርካታ የቃለ ሕይወት ምዕመናን የተሰማቸውን ጥልቅ ሐዘን ገልጸዋል፡፡
በተያያዘ መረጃ በዚህ እጅግ አሳዛኝ የትራፊክ አደጋ የሆሳዕና ከተማ እናት ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን መሪና አገልጋይ ዮናስ ዱባለን ጨምሮ አብረዋቸው የነበሩ ሁለት ጓደኞቻቸው ሕይወታቸው ማለፉ የተነገረ ሲሆን ይህንን ተከትሎም የሆሳዕና ከተማ ምዕመናን መሪር ሀዘን ውስጥ ይገኛሉ ተብሏል። የአቶ ዮናስ ዱባለ የአስክሬን ሽኝት በሆሳዕና ከተማ ከሆሳዕና እናት ቤተ ክርስቲያን ወደ ኢየሩሳሌም አደባባይ በሚወስደው መንገድ ላይ በሚገኘው መኖርያ ቤታቸው ልክ ከጠዋቱ በ3 ሰዓት የሚጀምር ሲሆን፣ በመቀጠልም ወደ እናት ቤተ ክርስቲያን ከተወሰደ በኋላ ባገለገሏት ቤተ ክርስቲያን መካነ መቃብር መስከረም 10 ቀን 2016 ዓ.ም እንደሚፈጸም ታውቋል፡፡ አቶ ዮናስ ዱባለ ባለ ትዳርና የ2 ወንድ ልጆች አባት ነበሩ፡፡ ለቤተሰቦቻቸው፣ ለቀጣናውና መላው የኢትዮጵያ ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን ቤተሰቦች ሁሉ መጽናናትን እንመኛለን፡፡