
22/12/2024
የአዲስ አበባን አዲሱ መልክን በተመለከተ ለወንድማችን ጃዋር ግንዛቤ አንዳንድ ነገሮችን ለማስታወስ ያህል፦
(ክብረህይወት አየለ ጥሩሰው ከአዲስቷ አዱገነት፣ አዲስ አበባ)
ወንድማችን ጃዋር ስራጅ መሀመድ ትናንት የአዲስ አበባን ለውጥ የሺሻ ቤት ብልጭልጭ ነው በማለት አጣጥሏል። እውነት ለመናገር ይህ አገላለጽ አንድ ከተማረ ሰው የሚጠበቅ ባለመሆኑ ለወንድማችን አዝኜለታለሁ። ልብ በሉ። አዝኜበታለሁ አላልኩም። አዝኜለታለሁ ነው ያልኩት። ምክንያቱም ይህ ትልቅ የሆነ የአቅል እጦት በመሆኑ ነው። ይታያችሁ እንግዲህ አንድ የፖለቲካ ሳይንቲስት ነኝ የሚል ሰው ስለ ሺሻ ስያወራ።
የሺሻ ሳይንሱን ቀምሰው ለሚያውቁት ለነጃዌ በመተው እኔ ግን እንዲህ እላለሁ።
1. የአዲስ አበባ ኮሪደር ልማት በወዳደቁ የሸራና ቆርቆሮ ቤት ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ብዙ ሺህ ቤተሰቦች የተሟላ መሠረተ ልማት ያለው የመኖሪያ ቤት እና የመኖሪያ አከባቢ ባለቤት እንዲሆኑ ያስቻላቸው ትልቅ የሆነ የለውጥ እሳቤ ነው።
2. የአዲስ አበባ ኮሪደር ልማት ኢትዮጵያ ከነበረችበት የድህነት አዙሪት ወጥታ ዘመኑን የዋጀ የስራ ባህል ባለቤት እንድትሆነ እያስቻላት የሚገኝ ታላቅ የለውጥ ንቅናቄ ነው። እኔ ለወንድማችን ጃዋር ያለኝ አንዲት ምጢጢዬ ምክር ሰሞኑን በቢቢሲ እንደተናገረው ወደ ኢትዮጵያ (አዲስ አበባ) የሚመላለስ ከሆነ ከኮሪደር ልማት የተነሳ ኢትዮጵያዊያን ወጣቶች፣ ሴቶች እና ከማዕከል እስከታችኛው እርከን ያሉ አመራሮች 24 ሰዓት በስራ ተጠምደው ለከተማቸውና ሀገራቸው ለውጥ እየተጉ መሆናቸውን ተዘዋውረው መጎብኘት አለበት። ያው የጀዋር ጉብኝት ለውጥ ያመጣል ብዬ ሳይሆን ቢያንስ የሚተችና የማይተች ነገር መለየት ቢችል የሚል ወንድማዊ ምክር ለመለገስ ካለኝ ፅኑ ፍላጎት በመነሳት ነው።
3. የኮሪደር ልማት ሀሳብ፣ በጀት እና ሞያተኞችም ከኢትዮጵያ ናቸው። ጃዋር የመጀመሪያ ድግሪውን የተማረበት ሲንጋፖር የምትባል ትንሿ የኤዢያ ሀገርን ጨምሮ ሁሉም የበለፀጉ ሀገራት ከድህነት እና ኋላ ቀርነት የወጡት በሀገር በቀል አስተሳሰብ ነው። በመሆኑም ኮሪደር በአይን ከሚታየው መሰረተ ልማት የተሻገረ፣ ኢትዮጵያን ወደማይቀለበስ የለውጥ ምህዋር ያስገባ ስርዓት መሆኑን ለማስገንዘብ ነው።
4. የመጀመሪያው ዙር የአዲስ አበባ ኮሪደር ልማት ብቻውን 50 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች የስራ ዕድል ፈጥሯል። ይህ ማለት ኮሪደር ለዜጎች ፍትሃዊ የኢኮኖሚ ክፍፍል እንድረጋገጥ አይነተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል ማለት ነው። በዚያው ልክ የሚሰሩ እጆች እንዲበራከቱ የበኩሉን ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ሁለተኛው ዙር የአዲስ አበባ ኮሪደር ልማት በብዛትም ሆነ በጥራት ካለፈው ዙር እጅጉን በሚልቅ መልክ እየተከናወነ ይገኛል።
በተቀሩ የኢትዮጵያ ከተሞች የተጀመረው የኮሪደር ልማት ይዞ የመጣውን ትሩፋት ከዚህ ተነስተው መተንተን የሚከብድ አይሆንም። አንዳንዴም ቢሆን ጥፋቱን ብቻ ሳይሆን የሚታይና የሚጨበጥ ልማቱንም መተንተኑ አይከፋም ብዬ ነው። ለዛሬው አበቃሁ።
ክብረህይወት አየለ ጥሩሰው
ከአዲስቷ አዱገነት፣ አዲስ አበባ