15/10/2025
በጉራጌ ዞን የመስህብ ሥፍራዎችን በማልማትና በማስተዋወቅ የተጀመሩ ተግባራት ውጤት እያመጡ ነው
ጥቅምት 5/2018 (ወልቂጤ ) በጉራጌ ዞን የቱሪዝም መስህብ ሥፍራዎችን በማልማትና በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግ የተጀመሩ ተግባራት ውጤት እያመጡ መሆኑን የዞኑ ባሕልና የቱሪዝም መምሪያ አስታወቀ ።
የጉራጌ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ሃላፊ መሠረት አመርጋ፤ ዞኑ ካላው እምቅ የቱሪዝም አቅምና መዳረሻዎች አንፃር ይገኝ የነበረው ጥቅም አነስተኛ ሆኖ መቆየቱን አስታውሰዋል።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ይህን መቀየር የሚያስችል ሥራ በተቀናጀና ባለድርሻ አካላትን ባሳተፈ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል።
በዚህም በዞኑ ያሉ የተፈጥሮ፣ ሰው ሰራሽና እና ታሪካዊ የመሥህብ ሥፍራዎችን በማልማትና በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል ።
በተለይም በዞኑ ያሉ የቱሪዝም መሥህቦችን ለማስተዋወቅ እና ለማስጎብኘት ከግሉ ዘርፍ፣ ከመገናኛ ብዙኃንና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት መሰራቱ ውጤት እያመጣ መሆኑን ተናግረዋል።
በዘንድሮው የመስቀል በዓል ከሃገር ውስጥ እና ከተለያዩ ዓለም ሃገራት በርካታ ጎብኚዎች ወደ ዞኑ መምጣታቸውን ጠቅሰው፤ በዚህም 230 ሚሊዮን ብር ገቢ መገኘቱን አንስተዋል ።
ከውጭ የሚመጡ ጎብኚዎች የ"ጀፎረ" የገጠር ኮሪደር ልማት ላይ የብስክሌት ሽርሽር ማድረግ እየተለመደ መምጣቱ እና በየአካባቢውም የሕዝቡ እንግዳ ተቀባይነት የቱሪስቱን የቆይታ ጊዜ ለማራዘም እያስቻለ እንደሆነም ጠቅሰዋል።
በዚህም የእደ ጥበብ ወጤቶች ተፈላጊነት መጨመር እና ለአገልግሎት ሰጪ ተቋማት መነቃቃት መፍጠሩን አውስተው፤ ለቱሪስቶች ማረፊያ የሚሆኑ የሆቴሎችና ሌሎች አመቺ ሥፍራዎችን የማስፋፋት ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን ገልጸዋል።
ዞኑ በዘርፉ ካለው አቅም አንጻር ብዙ ሊሰራ እንደሚገባ ያነሱት ሃላፊዋ፤ ለዚህም ይረዳ ዘንድ አዳዲስ የመሥህብ ሥፍራዎችን የማልማትና የማስተዋወቅ እንዲሁም መሰረት ልማት የማሟላት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አስረድተዋል
መረጃው የኢዜአ ነው