03/09/2025
ባህላዊ የኢንጅነሪንግ ጥበብ የጉራጌ ጎጆ ቤት አሰራር
የጉራጌ ብሄረሰብ እጅግ የሚደነቅ የበርካታ ባህላዊ እሴቶች ባለቤት ነዉ፡፡ ከዚህ ዉስጥ ባህላዊ የሳር ቤት(ጎጆ ቤት) አሰራር አንዱ ነዉ፡፡
በጉራጌ ብሄረሰብ የጎጆ ቤት ሥራ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቶ የሚከናወን ተግባር ሲሆን አባቶች ዘመናዊ የምህንድስና ትምህርት ምን እንደሆነ ሳያዉቁ የሳር ቤት አወቃቀርና የመንደር አመሰራረት እንዲሁም የቤት አያያዝና አጋጌጥ እጅግ የሚገርም ነዉ።
የጉራጌ ባህላዊ ቤት አንዲት ሚስማር ወይም የፋብሪካ ዉጤት ሳይገባበት ተሰርቶ እስከ 100 ዓመት ምንም ሳይሆን አገልግሎት መስጠት እንደሚችል መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
የጉራጌ ባህላዊ ቤቶች በአራት ደረጃ የሚከፈሉ ሲሆን እነሱም ጎየ(ትልቅ ቤት)፣ ኸራር(እልፍኝ ቤት)፣ ዘገር(የሙሹሮች ቤት) እና አራተኛው ደረጃ ቀለል ባለ መልኩ የሚሰራ እና ለከብቶች ገለባ ማስቀመጫነት የሚያገለግል "ሰንቃላ" በመባል የሚታወቀው ነው።
የጎጆ ቤት የዉስጡን ገጽታ ስንመለከት የጉራጌ ባለሙያዎች ተጠበዉና ተጨንቀዉ በሚሰሯቸዉ የእደ-ጥበብ ዉጤቶች የሚያሽቆጠቁጡት ሲሆን በተለይም ከስንደዶ፣ ከሸክላ፣ ከእንጨት፣ እንሰት ዉጤቶች(ቃጫና ገመድ) በመጠቀም እንዲሁም ከእንስሳት ተረፈ ምርቶች ማለትም ከቆዳ፣ከቀንድ ፣ከጭራና ከመሳሰሉት የተዘጋጁ ቁሳቁሶች በአግባቡና በሚያምር መልኩ ተደርድረዉ አስፈላጊ በሆነ ሰዓት ጥቅም ላይ ይዉላሉ፡፡
ጎጆ ቤት ሲገነባ በአንድ ጀንበር ታስቦ የሚከናወን ተግባር ሳይሆን ቤት የሚሰራዉ አባወራ ለቤቱ መስሪያ የሚሆኑ ቁሳቁስ ለማሰባሰብ ጊዜ ወስዶ የሚንቀሳቀስ ሲሆን የአከባቢው ህብረተሰብ ደግሞ አንድ አባወራ ቤት ሲሰራ ሌላው ዳር ሆኖ መመልከት የማይታሰብና እንደ ነዉር የሚታይ ስለሆነ ሁሉም ተረባርበዉ ቤቱን በጋራ መስራት የተለመደ ባህላዊ እሴት ነው።
በጉራጌ ባህል አንድ አባወራ ጎየ (ትልቅ) ቤት ለመስራት ሲያስብ የመጀመሪያ እርምጃዎቹ ለግንባታው አስፈላጊ የሆኑ ግብዓቶችን ከአካባቢው መሰብሰብ ነው። በዚህም መሰረት የበሰለ ቀይ በሀርዛፍ ወይም ጥድ መርጦ ለግድግዳ የሚሆኑ ቋሚ ፍልጦች(ጐርደራ) ማስፈለጥ፣ ለበር የሚቆሙ ዋና ቋሚዎች(ወፈንቻ) በሙያተኛ በወፍራሙ ማስጠረብ፣ ለቤቱ ጣራ መወጠሪያ የሚሆኑ ቀጥ ያሉ ረጃጅም ወራጆች ቆርጦ መሰብሰብ፣ ከወራጅ ጋር ከላይ ወደታች የሚደረደሩ ባሀርዛፎች በረዥሙ ጠርቦና ልጎ በብዛት ማዘጋጀት፣ ለቤቱ የውጭ ጣራና የውስጥ ጣራ መማገሪያ ቀርከሃ ሸንሽኖና ብዙ ቁጥር ያለው የዘንባባ ዛፍ ቅርንጫፍ በመመልመል ማዘጋጀት፣ ለጣራ ማሰሪያ የሚሆን የተመረጠ ገመድ (ወደረ) ለ2 ዓመት ያህል ጊዜ በመሰብሰብ በጥንቃቄ ማከማቸት፣ የውስጥና የውጪ ግድግዳ መማገሪያ ጌጠኛ ቀርከሃ እና የተጠረበ ማገር ገዝቶ ማከማቸት፣ የግድግዳ ማገር ማሰሪያ ጠንካራ ሀረግ(አብታ) ከጫካ በደቦ ማሰባሰብ፣ ቀጥና ዘለግ ብሎ የአንድ ጎልማሳ እቅፍ የሚሞላ የበሰለ ቀይ በሀርዛፍ ወይም የጥድ ዛፍ ለምሰሶ ማዘጋጀት፣ በላይኛው ጫፍና በመሀል የቤቱን ጣራ በመወጠር ለዓመታት የቤቱ ሚዛን እንዳይዛነፍ በምሰሶ ላይ ተተክለው ዙሪያውን የሚደግፉ ቀጥ ያሉና በሙያተኛ ተጠርበው ጌጥ የወጣላቸው ወጋግራዎች(ወካ) የማዘጋጀት ስራ ይሰራል፡፡
ከላይ ያየናቸው ቁሶችን የማሰባሰብ ስራ እንደተጠናቀቀ ቤቱ የሚያርፍበት የተመረጠው ቦታ (ሸመነ) የአካባቢው ህዝብ በጋራ ወጥቶ ውሀ ልኩን ያስተካክላል፡፡ የቦታው ውሀ ልክ መስተካከሉን ሙያተኛው እንዳረጋገጠ በራሱ መሪነት ግድግዳ ለማቆም ምሰሶ የሚቆምበት ቦታ የቤቱን መሐል በማድረግ ዙሪያውን በክብ ቅርፅ ይቆፈራል፡፡
የቤቱ የጣራ ግንባታ ተጠናቅቆ በወጋግራ (ወካ) እስከሚቀየር ድረስ ጣራው ከቤቱ በውስጠኛው በኩል ከመሬት ወደ ጣራው በሚወጠሩ ረጃጅም ወራጆች(ጡቃ) በጊዜያዊነት ይደገፋል። የጣራው ስራ እንደተጠናቀቀ በሙያተኛ አማካይነት መጠነኛ ውፍረት ያላቸው ቀጥ ያሉ የጥድ/ቀይ ባህር ዛፎች ተልገውና ተጊጠው በወጋግራነት (ወካ) በምሰሶው ወገብ ላይ ተተክለው የቤቱን ጣራ እንዳይዛነፍ ደግፈው እንዲይዙ የሚደረግ ሲሆን የውስጥ ስራ እንደተጠናቀቀ የቤቱ ጣሪያ በሳር ክፍክፍ ይከደናል፡፡