07/11/2022
ነፍስ ይማር አርቲስት አሊ ቢራ!
Ali Mohammed Birra – አሊ ቢራ
በ1939 ዓ .ም በድሬዳዋ ገንደ ቆሬ በተባለ ቦታ የተወለደው አሊ ቢራ በኢትዮጵያ የሙዚቃ ታሪክ ውስጥ ስማቸው ጎልተው ከሚነሱ አንጋፋ ድምፃውያን አንዱ ሲሆን የተለያዩ አይነት ሙዚቃዎቹን በኦሮምኛ አረብኛ ሀደርኛ ሶማልኛ ሃረርኛ እና አማርኛ ቋንቋዎች ተጫውቷል ።
አሊ ቢራ ሙዚቃ መጫወት የጀመረው በ14 አመቱ ገና በልጅነቱ ነው ። የኦሮሞን ባህልና ሙዚቃ ለማስተዋወቅ የተመሰረተውን "አፍረን ቀሎ" የሙዚቃ ቡድን በመቀላቀል መዚቃን አሀዱ ብሎ ጀመረ ። ታዲያ አፍረን ቀሎ የሙዚቃ ቡድን ውስጥ ይጫወት በጀመረበት ጊዜ ለመጀመሪያ ጊዜ የተጫወተው ሙዚቃ " ቢራ ዳ ባሬ" የተባለው ነበር ። አሊ የተባለ ሌላ ድምፃዊ ስለነበርና ሁለቱን አሊዎች ለመለየትም ጭምር ከሚጫወተው "ቢራ ዳ ባሬ" የተባለው ሙዚቃ ላይ "ቢራ" የሚለውን በመውሰድ ነበር "አሊ ቢራ" የሚለው ስም የወጣለት እና እስከ ዛሬ የአርቲስቱ መጠሪያ ስም ሆኖ የቀረው ።
አፍረን ቀሎ የሙዚቃ ቡድን በሚሰራቸው ስራዎች በ1958 ዓ, ም በመንግስት እገዳ ይጣልበትና የባንዱ አባላትም እየተፈለጉ ለእስር ይዳረጉ ስለነበር አሊ ቢራም በጊዜው ይህንን ሽሽት ወደ አዲስ አበባ ከተማ መጣ ።
ታዲያ አሊ ቢራም በተለያዩ ቋንቋዎች መዝፈን ይችል ስለነበር አዲስ አበባ እንደመጣ በሙዚቃው ለመቀጠል ብዙ አልተቸገረም ነበር ። አዲስ አበባ ውስጥ በተለያዩ ዝግጅቶች ላይ በሚሳተፍበት ወቅት ያገኘው የኦሮሞው ሙዚቀኛ አህመድ ታቂ" ጊታር ገዝቶ ስለሰጠው አሊ ቢራም ጊታሩን እየተጫወተና እየዘፈነ በተለያዩ ዝግጅቶች ላይ ሙዚቃውን በማቅረብ መሳተፉን ቀጠለ። በዚህ ወቅት ነበር በጊዜው የክቡር ዘበኛ ባንድ መሪ የነበሩትን አቶ እዩኤል ዩሃንስን በመተዋወቅ እና ሁዋላም ላይ ክቡር ዘበኛን ለመቀላቀል የበቃው ።
በኦሮሞ ታሪክ ውስጥ የመጀመሪያ የሚባለውን ኦሮምኛ የሙዚቃ አልበም ያሳተመውም አሊ ቢራ ሲሆን በ1963 ዓ, ም ነበረ ። ከዚያ ደግሞ በመቀጠል በጣም ተወዳጅ የሆኑለትን" Hin Yaadin" "Asabalee" "Ammalelee" እና "Gamachu" የተሰኙትን ሙዚቃዎችም ሰርቶዋል::
አሊ ቢራ ከክቡር ዘበኛ የሙዚቃ ባንድ ከአለም ግርማ ባንድ ራሱ በመሰረተው አዱ ቢራ ባንድ እና ሌሎችም በርካታ ባንዶች ጋር በቁጥር የበዙ ተወዳጅ አልበሞችን ለህዝብ ያደረሰ ጉምቱ ሙዚቀኛ ነው ።
አሊ ቢራ ከሰሞኑን በአዳማ ሪፈራል ሆስፒታል በህክምና ስረዳ የቆየ ሲሆን ትላንት ወደ መኖሪያ ቤቱ እንደሄደ ለማወቅ ተችሎል ።
ስለ አሊ ቢራ ተጨማሪ መረጃዎች እና ማስተካከያ ካለ ኮሜንት ላይ ማስፈር ይቻላል ።
ለመላዉ ቤተሰቡና ወዳጅ ዘመዶችና አድናቂዎቹ መጽናናትን እንመኛለን።