19/02/2023
የዘመናችን የእሾኽ አክሊል
ከዛሬ 40 ዓመታት በፊት የሸዋ ክፍለ ሀገር ሊቀጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ (2ኛ) በዝዋይ ገዳም ለዲያቆናት እና ካህናት ሃይማኖት ከምግባር እየመረመሩ ክህነት ይሰጡ ነበር።
ለሹመት ከቀረቡት መካከል አንደኛው በወጉ ያለተማረ በምግባርም ያልሰመረ አንድ እጩ አግኝተው "ዘንድሮ አልሾምህም። ለሚቀጥለው ዓመት በደምብ ተምረህ፣ በምግባርም ሰክነህ ስትመጣ ትሾማለህ" ብለው መለሱት።
አብረውት የመጡት ወዳጅ ዘመዶቹ ተሰብስበው ብፁዕነታቸውን "እባክዎ ከነ ችግሩም ቢሆን ይሹሙልን። ወገኖቹም ይጣሉናል። እርሱ ካልተሾመ
ቤተክርስቲያናችንም ትዘጋለች" ሲሉ በማስተዛዘን ልመና አቀረቡ።
አቡነ ጎርጎርዮስ ግን "የወገኖቹን ቁጣ ፈርቼ በሃይማኖቱ ያለጸና በምግባሩ ያልቀናን ሰው ካህን እንዲሆን ሾሜ ቤተክርስቲያኒቱ ላይ የማይነቀል እሾኽ ከምተክልባት ለጊዜው ብትዘጋ ይሻላል። ወደፊት የተሻለ እና ለክህነት የተገባ ሰው አግኝተን ስንሾም ያኔ ይከፍታታል።" ብለው መለሷቸው።
ዛሬ ላይ ቅድስት ቤተክርስቲያንን ለሁለት ካልሰነጠቅናት ብለው ቁም ስቅሏን የሚያሳዩዋት ግለሰቦች በሃይማኖት ጽናታቸው፤ በምግባርም መቅናታቸው የተመሠከረላቸው መሆኑ ሳይረጋገጥ የሆነ ወገንን ለማስደሰት በይድረስ ይድረስ የተሾሙ እንደነበሩ አሁን እሾኹ ደርሶ ሲወጋን ተረድተነዋል። ለቤተክርስቲያኒቱ የእሾኽ አክሊል ሆነው እየወጓትና እያደሟት ነውና!
ያለፈ አልፏል! አሁንም ቢሆን ባለሥልጣናትን ለማስደሰት ወይንም የአጃቢዎቻቸውን ጩኸት በመፍራት እንኳንስ ጵጵስና ዲቁና ለማይገባቸው፤ ከእግዚአብ ልጅነታቸው ይልቅ የብሔረሰብ ልጅነታቸው ደርሶ ለሚንጣቸው ዘውገኞች የክህነት ሹመት መስጠት በክርስቶስ መቅደስ ጉልላት ላይ ሌላ ተጨማሪ መርዛማ እሾኽ አክሊል እንደመድፋት ይቆጠራል።
(የኔታ ቡሩክ)