31/10/2019
በኢትዮጵያ የህጻናት የልብ ህክምና ማዕከልን ስራዎች ለመደገፍ የሚያስችል የገቢ ማሰባሰቢያና የግንዛቤ ማስጨበጫ ዝግጅት በዋሽንግተን ተካሂዷል። የኢትዮጵያ የህጻናት የልብ ህክምና ማዕከል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ሄለን በፍቃዱ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት ማዕከሉ በሙሉ አቅሙ እንዳይሰራ የአላቂ እቃዎች እጥረት ፈተና እንደሆነበት ገልፀዋል።
ማዕከሉ በሳምንት ሶስት የህጻናት ልብ ህክምና እንደሚያደርግ በመግለጽ፤ ቁሳቁሶች ቢሟሉለት ግን አምስት ህክምናዎችን ማድረግ እንደሚችል ዶክተር ሄለን ተናግረዋል። በአገር ውስጥም በውጭም ያሉ አጋር አካላት ድጋፋቸውን እንዲያጠናክሩ ጥሪ አቅርበዋል። በማዕከሉ የህጻናት ልብ ሃኪም ዶክተር ያዩ መኮንን በበኩላቸው ÷ በማዕከሉ ያላቸውን ተሞክሮና አጠቃላይ እንቅስቃሴዎች ገለጻ አድርገዋል።
አምባሳደር ፍጹም አረጋ የተካሄደው ዝግጅት አስቸኳይ የልብ ህክምና ለሚያስፈልጋቸው ህጻናት ለመድረስ ነው ያሉ ሲሆን የህጻናትን ልብ ለመታደግ ልባችሁ የሚነግራችሁን ስጡ ሲሉ ገልጸዋል። ኤምባሲው አጋር አካላትን በማስተባበር ለማዕከሉ ድጋፍ የሚያስገኙ ተግባራዊ ጥረቶችን እንደሚያደርግም አስታውቀዋል።