10/11/2025
ዕውቁ የታሪክ ምሑር ፕሮፌሰር ላጲሶ ጌታሁን ድሌቦ ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ
ዕውቁ የታሪክ ምሑር ፕሮፌሰር ላጲሶ ጌታሁን ድሌቦ በ87 ዓመት ዕድሜ ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ዛሬ እሑድ ጥቅምት 30/2018 ነው።
በኢትዮጵያ ታሪክ ጥናት ጉልሕ አሻራ ማሳረፍ የቻሉት ፕሮፌሰሩ በርካታ መጻሕፍትን ለአንባቢያን አቅርበዋል። ከሥራዎቻቸው መካከል የኢትዮጵያ ረጅም የሕዝብና የመንግሥት ታሪክ እና የኢትዮጵያዊነት ታሪካዊ መሠረቶችና መሣሪያዎች ተጠቃሽ ናቸው።
ላጲሶ ጌታሁን ድሌቦ የተወለዱት በቀድሞው ከንባታና ሐዲያ አውራጃ በኩፋላ ቀበሌ ግንቦት 12/1930 ነው። የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን በቢቾ ሆሣዕና ሚሽን፣ በመንግሥት ትምህርት ቤት እንዲሁም ኋላ ላይ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን አዳማ በሚገኘው በዐፄ ገላውዴዎስ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተምረዋል።
ከዚያም መዳረሻቸውን አሜሪካ በማድረግ በኮሙኒቲ ኮሌጅ የከፍተኛ ትምህርታቸውን ተከታትለው በኀብረተሰብ ታሪክ የመጀመሪያ ዲግሪ አጠናቀዋል። ከሐዋርድ ዩኒቨርሲቲ በአፍሪካ ታሪክ ጥናት ሁለተኛ ዲግሪ፣ በኢትዮጵያ፣ በአፍሪካና በአውሮፖ ታሪክና በፍልስፍና ደግሞ የዶክትሬት ዲግሪ ወስደዋል።
ዶክትሬታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ የፕሮፌሰርነት ማዕረግ ተሰጥቷቸው ለሁለት ዓመታት በቨርጂኒያ ዩንየን ዩኒቨርሲቲ ውስጥ አስተምረዋል። ፕሮፌሰር ላጲሶ ድሌቦ የኢትዮጵያ ታሪክ የእስልምናው፣ የክርስትናው እና የሌሎች ሃይማኖቶች እንዲሁም የበርካታ ቋንቋዎች እና ሕዝቦች መስተጋብር ነው በሚለው ሙግታቸው ይታወሳሉ። (ሚንበር ቲቪ)
★ ★ ★
Ethio Sat | 11545 | H | 45000
!