10/11/2025
«ኢትዮጵያ የታሪክ ጸሐፊ የላትም። የጎሳ ተወካይ ጸሐፊ ነው ያላት።» ፕሮፌሰር ላጲሶ ጌታሁን ዴሌቦ
በታላቁ የኢትዮጵያ የታሪክ ምሁር ፕሮፌሰር ላጲሶ ጌታሁን ዴሌቦ ሞት የተሰማኝን ጥልቅ ሀዘን ለመግለጽ እወዳለሁ። ፕሮፌሰር ላጲሶ በኢትዮጵያ የታሪክ ጥናት መስክ በተለይም አውራ (ሜይንስትሪም) ተደርጎ በተወሰደው የኢትዮጵያ የታሪክ ክፍል፣ ኾን ተብለው የተዘነጉና የተተዉ የሀገራችንን ሕዝቦች ታሪክ ደጋግሞ በማጥናትና በመመራመር ታሪካቸውን ለእውቀት ብርሃን ያበቁ ታላቅ ምሁር ነበሩ። በዚህ መስክ የሰፊውን ደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦችና በኢትዮጵያ የእስልምና እና ሙስሊሞችን ታሪክ መጥቀስ ይቻላል።
የሀዋርድ ዩኒቨርሲቲ ምሩቁ ፕሮፌሰር ላጲሶ ሚዛን ለጎደለው የሀገራችን የታሪክ ጽሕፈት ሞያ ትልቅ ክፍተት የሞሉና ለዚህም በብዙ መስኩ የተሳካላቸው ነበር ማለት ይቻላል። ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ታሪካቸውን በከፊል እንኳ ሊሰንድላቸው የሚችል የታሪክ ባለሞያ ባልነበረበት ዓመታት ፕሮፌሰሩ ያደረጉት ጥረት እጅግ ከፍተኛ አክብሮትና ምስጋና የሚቸረው ነው። እናመሰግናለን ፕሮፌሰር። ለቤተሰቦችዎና ወዳጆችዎ ሁሉ መጽናናትን እመኛለሁ።