31/12/2025
የህዳሴ ግድብ የቅኝ ግዛት አስተሳሰብ እንዲያበቃ በማድረግ አዲስ የትብብር ምዕራፍ ከፍቷል - ስዊድናዊው ተመራማሪ እና ፕሮፌሰር አሾክ ስዌን
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የአባይ ወንዝ ላይ የቅኝ ግዛት አስተሳሰብ እንዲያበቃ እና አዲስ ምዕራፍ እንዲከፈት ያደረገ ፕሮጀክት መሆኑን በስዊድን ኡፕሳላ ዩኒቨርሲቲ የሰላም እና ግጭት ምርምር ክፍል ፕሮፌሰር አሾክ ስዌን ገለጹ።
ፕሮፌሰር አሾክ ስዌን ከምርምር ስራቸው ባሻገር የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ተቋም(ዩኔስኮ) የዓለም አቀፍ የውሃ ትብብር ሊቀ መንበርም ናቸው።
ፕሮፌሰሩ የህዳሴ ግድብ ተመርቆ ስራ የጀመረበት ጊዜ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዲፕሎማሲ ውስጥ እያደገ የመጣውን ተጽእኖ ፈጣሪነቷ ይበልጥ እያደገ መምጣቱን ሚያሳይ መሆኑን ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ በህዳሴው ግድብ ምርቃት አማካኝነት ለአፍሪካ ጠንካራ መልዕክት ማስተላለፏን ተናግረዋል።
ህዳሴ ግድብ ትልቅ የምህንድስ ስኬት እና የዲፕሎማሲ ድል መሆኑን ጠቅሰው ግንባታው ውጫዊ ጫናን በመቋቋም እና በእቅድ በመመራት ለውጤት መብቃት መቻሉን አመልክተዋል።
ኢትዮጵያ ከግብጽ እና ከአጋሮቿ የደረሰባትን ጫና በመቋቋም ግዙፉን ፕሮጀክት አጠናቃለች ሲሉ ገልጸዋል።
ህዳሴ ግድብ ኢትዮጵያውያን ከመንግስት ጋር በጋራ በመቆም እውን ያደረጉት ብሄራዊ ስኬት መሆኑንም የዩኔስኮው የዓለም አቀፍ የውሃ ትብብር ሊቀ መንበር ተናግረዋል።
ግድቡ አፍሪካ በራሷ ማድረግ ትችላለች የሚለውን እሳቤ በተግባር ገልጦ ማሳየቱን ነው ያነሱት።
የአፍሪካ ሀገራት ከውጭ ፋይናንስን ከመጠበቅ ይልቅ በራሳቸው አቅም ግዙፍ ፕሮጀክቶችን መገንባት እንደሚችሉ የሚያስተምር እንደሆነም ተናግረዋል።
ግድቡ የአባይ ወንዝ የአንድ ሀገር ብቻ ነው በሚል ለረጅም ጊዜ የቆየ የቅኝ ግዛት እሳቤ እንዲያከትም አድርጓል ነው ያሉት።
አባይ ወንዝ ለበርካታ ሀገራት ጥቅም የሚሰጥ መሆኑን የገለጹት ፕሮፌሰሩ አባይን በፍትሃዊነት እና እኩልነት መጠቀም እንደሚቻል አሳይቷልም ብለዋል።
የላይኛው ተፋሰስ ሀገራት የራሳቸውን ወንዞች ለልማት የመጠቀም መብት እንዳላቸውም አስገንዝበዋል።
ህዳሴ ግድብ ለኢትዮጵያ እድገት ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት እና የኤሌክትሪክ ኃይል ለህዝቧ፣ ለኢንዱስትሪዋ እና ለከተሟቿ ያስፈልጋታል ሲሉ ተናግረዋል።
ግድቡ ከሀገር አልፎ ለቀጣናው ሀገራት ጠቀሜታዎች እንዳሉት ነው ያስረዱት።
ግብጽ በቀጣናው የኃይል ትብብር ተጠቃሚ መሆን ትችላለች ያሉት ፕሮፌሰሩ የውሃ ጉዳዮች የተጠናጥል እርምጃዎችን ከማድረግ ይልቅ ከተፋሰሱ ሀገራት ጋር በትብብር መስራት እንዳለባት አመልክተዋል።
ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የተፋሰሱ ሀገራት በድንበር ተሻጋሪ የውሃ ሀብቶች በጋራ የማልማት መብት እውቅና እንደሰጠ አንስተው ግብጽ ይህን ልታከብር እንደሚገባ ተናግረዋል።
በሌላ በኩል ኢትዮጵያ የባህር በር የማግኘት ጥያቄዋ ትክክለኛ እንደሆነ አንስተው የባህር በር የማግኘት መብቷን የሚያደናቅፉ እንቅስቃሴዎች ተገቢ እንዳልሆኑ ነው ያነሱት።
የተፋሰሱ ሀገራት በውሃ ሃብቶች አጠቃቀም ላይ ያሉ ጉዳዮችን በውይይት መፍታት እንዳለባቸውም አሳስበዋል።
#ኢዜአ