02/12/2025
ኢትዮጵያ በየትኛውም መመዘኛ የባህር በር የባለቤትነት መብት ልትነፈግ አትችልም
ሰመራ፤ ህዳር 22/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በየትኛውም መመዘኛ የባህር በር የባለቤትነት መብት ልትነፈግ እንደማትችል ተመላከተ።
ኢትዮጵያ በህጋዊ፣ በመልክአ ምድራም ይሁን በታሪክ ከቀይ ባህር ልትነጠል የማትችል በመሆኑ የባህር በር ባለቤት መሆኗ የህልውና ጉዳይ ነው።
በመሆኑም የባህር በር ባለቤትነት ጉዳይ የትውልድ ጥያቄ በመሆኑ ምላሽ ማግኘት አለበት።
የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄን በማስመልከት በአፋር ክልላዊ ፓርቲ ሆኖ የሚንቀሳቀሰው የአፋር ነፃ አውጭ ግንባር(አነግፓ) ፓርቲ ሊቀ መንበር ሃንፈሬ አሊሚራህን ኢዜአ አነጋግሯል።
የኢትዮጵያ ህዝብ ቀይ ባህርን በአቅራቢያው እያየ መውጫ መግቢያ እንዳይኖረው መታጠሩ ፍፁም ተገቢነት የሌለውና ፍትሃዊነት የጎደለው መሆኑን ሊቀመንበሩ ገልጸዋል።
በመሆኑም ኢትዮጵያ በየትኛውም መመዘኛ የቀይ ባህር የባለቤትነት መብትን ልትነፈግ የማትችል መሆኑን አንስተው የባህር በር ባለቤት ልትሆን ግድ ይላል ብለዋል።
ኢትዮጵያ የባህር በር ያጣችበት መንገድ የተዳፈነ እና ግልጸኝነት የሌለው ሆኖ ከ30 ዓመታት በላይ መዝለቁን አስታውሰውአሁን ታሪክንና ሃቅን በመያዝ የትውልድ ጥያቄ ሆኖ መነሳቱ ተገቢና ምላሽ ሊሰጠው የሚገባ ጥያቄ መሆኑን ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ ብሄራዊ ጥቅምና በሉአላዊነቷ ማንም ኢትዮጵያዊ ሊደራደር እንደማይገባ አንስተዋው ጥያቄው ተገቢው ምላሽ እንዲያገኝ በጋራ እንደሚሰሩም አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ታሪካዊ እና ህጋዊ መሰረት ያለው፤ የኢኮኖሚ ህልውና እና የብሔራዊ ደህንነት ጉዳይ ጭምር በመሆኑ በሰላማዊ፣ በጋራ ተጠቃሚነትና በህጋዊ መንገድ ለማሳካት እየተሰራ መሆኑ ይታወቃል።
#ኢዜአ