18/09/2025
ልሳነ ግእዝ
የአራተኛ ዓመት የኮምፒውተር ሳይንስ ተማሪ ሳለሁ በወቅቱ Android የተባለው የሲስተም መምሪያ የገነነበት ጊዜ ነበር። ታዲያ የመጨረሻ ዓመት ፕሮጀክት ምን ልስራ እያልኩ ሳስብ ለምን የግእዝ መዝገበ ቃላት አልሰራም? በማለት ጽሁፌን አስገባው።
ከዚያም ጽሁፌን በማቀርብበት ጊዜ አንዱ Examiner የሰጠኝ ሃሳብ እስካሁን ድረስ ይከነክነኛል። "ግእዝ እኮ የሞተ ቋንቋ ነው። እዚህ ላይ ጊዜ ከሚጠፋ ለሌላ ቋንቋ ለምን አይሰራም?" ሲለኝ ዝምታን መረጥኩ። በዚያ ጊዜ ከExaminer ጋር መመላለስ ያስመታል።
መልሱን ግን አማካሪዬ በጥሩ ሁኔታ አብራርቶ መለሰለት። Even If it is dead, we have to work on it for it's revival ሲል ልቤ በደስታ ሲሞቅ ይሰማኝ ነበር። አሁን ድረስ አማካሪዬን በጣም ከልቤ አከብረዋለሁ። Thanks Dear Mohammed Yusuf!
ያ ፕሮጀክት በድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ከ15 ዩኒቨርስቲዎች ጋር በተደረገው የጥናት ውድድር ላይ የዋንጫ አሸናፊ ነበር። እኛም በA+ ደመደምነው።
አሁን ላይ ይህ ሃሳብ ሲነሳ ለግእዝ የሚወግኑ ሰዎች አስተሳሰብ በጣም ይገርመኛል። እነዚህ ሰዎች በደፈናው "ግእዝ ለምን ተነካብን?" በሚል ምናባዊ አስተሳሰብ ይመልሳሉ እንጂ ግእዝን ለማወቅ እንኳን ፍላጎት የላቸውም።
በግእዝ ቋንቋ ማዜም ፣ ማንበብ ፣ መገልገል የግእዝ ቋንቋ አዋቂነትን አይገልጽም። በተለምዶ የቅኔ ትምህርት የምንለው በመደበኛነት የሰዋስወ ግእዝ ትምህርት ነው። የተዘዋወረ ቀለም ነው። ቅኔ በግእዝ ቋንቋ ውስጥ ያለ አንድ ክፍል ነው እንጂ የግእዝ ቋንቋን በሙሉ የሚገልጽ አይደለም። የግእዝ ቋንቋን በአግባቡ ለመማር ቅኔ ቤት መግባት ያስፈልጋል።
ችግሩ ግን ያለው የአብዛኛው ተማሪ ፍላጎት እና እቅድ ቅኔ መቀኘት ነው። የትምህርቱ ዋነኛ ዓላማ ግን የግእዝን ቋንቋ ጠንቅቆ ማወቅ እና መረዳት ነው። ከእያንዳንዱ ቅኔ ዘረፋ በፊት የግስ እርባታ (Verb Generation with Tags) ከዘረፋው በኋላ ደግሞ የአገባብ ሙያ (Grammatical Feature) የሚሰጠው የግእዝን ቋንቋ ጠንቅቆ ለማወቅ ነው። መምህሩም መርቆ ሲሸኘው ቅኔ ተቀኝቷል በማለት ብቻ አይደለም። ቅኔ ከነአገባቡ ከነእርባ ቅምሩ ፣ ነገረ ጸያፍ ከነአዋጁ ጠንቅቆ ተምሯል ብሎ ነው እንጂ።
አሁን አሁን ግን የመጨረሻ ግቡ ተዘንግቷል። አባቶቻችን ትምህርቱ እንዳያሰለች በቅኔ በኩል ወደ ግእዝ ቤት እንድንገባ መንገዱን ሰርተውልናል። እኛ ግን ወደ ቤቱ ሳንገባ መንገዱ ላይ ቀርተናል።
መፍትሄ
ሞቷል ስንባል አልሞተም እያልን በተራ አጀንዳ ከምንሟገት አለመሞቱን ለምን አናሳይም? ግእዝን እንማረው ፣ እንቅረበው ፣ እንወቀው። Smart ከሆንን ደግሞ ልጆቻችን ላይ እንስራ። የኔታ ጋር ሄደው "ሀ ግእዝ ፣ ሁ ካዕብ" ይበሉ። መልእክተ ዮሐንስ ያንብቡ። ዳዊት ይድገሙ። ወንጌል ይስሙ። ቅኔ ይቁጠሩ ፣ ዜማውን ያዚሙት ፤ ይህ ከሆነ ግእዝ አደገ ተመነደገ ማለት እኮ ነው።
ግእዝ እንማርና ብሉይና ሐዲስን በጣዕመ ልሳን እናንብብ ፣ የጥበብ መጻሕፍትን እንጥገብ ፣ የአለቃ ተክለ ጽዮንን ፣ የአለቃ አድማሱን ፣ የነ ቄሰ ገበዝ ውብሸትን ቅኔ ሰምተን ይበል እንበል።
በመጨረሻም
አለቃ ተክለ ጽዮን ሊቅ ነበሩ። ቅኔውን በጽቡረ ሕሊና ይፈጥሩታል። የአራቱ ጉባኤያት መጻሕፍትን ወስነዋል። እውቀት በቃኝ አይሉም ነበር። ታዲያ አብዛኛው የግእዝ መጻሕፍት የተተርጎሙት ከአረብኛው ነበርና ያንን ቋንቋ ለመማር ከሼሆች ዘንድ እየሄዱ አረብኛውን ጠንቅቀውት ነበር። ትልቁ ሊቅ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም አረብኛውን ፣ ዕብራይስጡን ፣ ጽርዑን አጥንተዋል። ቋንቋ ያራቅቃል እንጂ አያጣላም።