09/08/2026
ኅሊና እና ሀገር
-------------------
(አርክቴክ ዮሐንስ መኮንን - የግል አስተያየት)
ማንኛውም ሰው እንደ አንድ ግለሰብ የራሱ እምነትና ፍላጎት አለው። እንደ ጉዳዩ ክብደትና ቅለት ደግሞ ይህንን የግል ፍላጎቱን «የእኔ» ለሚለው ቡድን ሲል አሳልፎ ሊሰጥ ይችላል። የአንድ ቡድን እምነትና ፍላጎት በአባላቱ ፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የመሰባሰቢያ አጀንዳ ነው። ነገር ግን የሀገር ጉዳይ ከግልም ይሁን ከቡድን እምነታችንና ፍላጎታችን ጋር ተቃራኒ እና ተገዳዳሪ ሆኖ ሲመጣ «የቱ ይቅደም?» ለሚለው ጥያቄ የምንሰጠው መልስ በታሪክ ፊት የምንታወስበት ዋንኛ ጉዳይ የሚሆን ይመስለኛል። የህሊናዬን ፍርድ እና የሀገሬን ጥቅም በማስቀደም የቡድን ፍላጎቴን እተዋለሁ ወይስ ሀገሬን ለቡድኔ ፍላጎት እሰዋታለሁ?
በአሁኑ ወቅት በጠረጴዛ ዙሪያ ባሰባሰቡን አገራዊ የምክክር መድረኮች ላይ የሚንጸባረቁ ሃሳቦች ከዚህ ውጪ አይደሉም። የግል፣ የቡድን እና የሀገርን ጥቅም ማስታረቅ ዋነኛ ፈተናችን ሆኖ ወጥቷል። በእርግጥ ነገሩ ግን እንደ መናገር ቀላል አይደለም፤ እጅግ ውስብስብና ከባድ ነው! በጉባኤው ላይ ተመካካሪዎች ይህንን ሚዛን ለመጠበቅ ሲጨነቁ፣ ሲጥሉና ሲያነሱ ታዝቤአለሁ።
ለዚህ ጥሩ ማስታወሻ የሚሆነኝ ስለ ከተሞች እጣ ፈንታና የወደፊት አኗኗራችን ስንመክር ያጋጠመኝ ኩነት ነው። ከምስራቅ የሀገራችን ክፍል የመጣ አንድ ወንድማችን በአስተርጓሚ በቡድን ስብሰባችን ላይ ያቀረበው ሃሳብ እጅግ ልብ ይነካል፤
«እኛ እኮ እንደ ማህበረሰብ የታሪክና የባለቤትነት ጥያቄ ነበረን። የኔ ቡድን ከዚህ አቋም ፍንክች እንዳንል አስጠንቅቆኝ ነበር የላከኝ። አሁን እዚህ መጥቼ የሌሎች ኢትዮጵያውያን ወገኖቼን እምነት፣ ስጋትና ፍላጎት ሳዳምጥ... ይዤ የመጣሁትን "የእኔ ብቻ" የሚለውን ሃሳብ ለማቅረብ ኢትዮጵያውያንን አፈርኩ!» አለን።
ይህ ወንድሜ ከግልም ሆነ ከቡድን አጥር አንጻር ሲመዝነው የጋራ የሆነው የሀገር ጉዳይ ከብዶት ከህሊናው ጋር ያደረገውን ታላቅ የሞራል ሙግት እገነዘባለሁ። እንደሀገር የጋራ እጣ ፈንታችን እና የሁላችንም የህልውና ጉዳይ መሆኑ ሲገባው "የእኔ ብቻ" የሚለው ነባር ትረካ ሚዛን ሊደፋለት አልቻለም።
ሁሉም ሰው ግን እንዲህ አይነት የላቀ የሞራል ልዕልና ያለው አቋም ያራምዳል ማለት አይደለም። ከብሔር፣ ከሃይማኖትና ከፓርቲ አጥር ተሻግሮ ሀገርንና የጋራ መኖሪያችንን ማየት የሚቸገረው አሁንም ሞልቷል።
በተለይ እንደሀገር የጋራችን በሆኑ ፍላጎቶች ላይ የተወጠሩ አጀንዳዎችን ከመጠን በላይ በሁለት ጫፍ እየተጓተቱ ያለመጠን መለጠጥ መዘዙ ቀላል አይመስለኝም። ሀገርንና የጋራ ጥቅማችንን አስቀድመን መሃል ላይ መቆም ካልቻልን፤ "የኔ ካልሆነ ሞቼ እገኛለሁ" ብለን ይዘነው በመጣነው አቋም ላይ ተቸንክረን የምንቀር ከሆነ ወደ አማካይ መንገድ የሚያቀራርብ አይሆንም።
የሌሎች ሀገሮች ልምድ ምን ያሳየናል?
በሰሜን አየርላንዱ የጉድ ፍራይደይ ስምምነት (Good Friday Agreement - 1998) በቤልፋስት (Belfast) ከተማና አካባቢዋ የካቶሊክና የፕሮቴስታንት ማህበረሰቦች "የከተማዋ/የቀጠናው ባለቤት እኔ ነኝ" በሚል ለሦስት አሥርታት ያህል በደም አፍሳሽ ጦርነት ውስጥ ነበሩ። በምክክሩ ወቅት የቤልፋስትና የሰሜን አየርላንድ የባለቤትነት እጣ ፈንታ በቀጥታ ከሚወሰን ይልቅ፣ “Principle of Consent” (የጋራ ስምምነት መርህ) በመጠቀም ጉዳዩ በጊዜ ሂደት እንዲቆይ አደረጉ። አጀንዳውን Park አደረጉት፤ ይህም ሀገሪቱን ከእርስ በእርስ ጦርነት አዳናት።
በደቡብ አፍሪካው ምክክር (1991–1993) ወቅት፣ የነጮቹ አፓርታይድ መንግሥት እና የኤን.ኤን.ሲ (ANC) ዋና ከተማዋን፣ የመሬት ባለቤትነትን እና የስልጣን ክፍፍልን በተመለከተ እጅግ የተወጠረና "የኔ ካልሆነ ሞቼ እገኛለሁ" የሚል አቋም ነበራቸው። በወቅቱ ድርድሩ እንዳይፈርስ ያደረገው "Sunset Clauses" (ጊዜያዊ ማቆያ ድንጋጌዎች) የሚል ስልት ነበር።
አጨቃጫቂ የነበሩ የመሬትና የከተሞች ባለቤትነት/አስተዳደር ጉዳዮችን ለጊዜው አቆይተው (Park አድርገው)፣ አስቀድመው ሀገራዊ ሕገ-መንግሥቱንና የሽግግር መንግሥቱን መሠረት ጣሉ። ከጊዜ በኋላ ሕዝቡ እርስ በእርስ የመተማመን ደረጃው ሲያድግና ስጋቱ ሲቀንስ፣ የቆዩት አጀንዳዎች በሰላማዊ መንገድና በፓርላማ ውይይት መፍትሔ አገኙ።
እኛስ ምን እናድርግ?
የምዕራባውያኑን "Parking the issue" የድርድር ጥበብ ብንጠቀምስ? እጅግ ባላመቹና ባላቀቃረቡን፣ ከዚህ በላይ ብንገፋቸው ምናልባትም ማኅበራዊ መሠረታችንን የሚንዱ አጀንዳዎችን ለጊዜው ብናቆያቸውስ? ነገሮችን አቆይተን ሀገር የምትቀጥልበትን እና የሁላችንም የሆነውን የጋራ ወርቃማውን አማካይ እስክናገኝ የተካረሩ አጀንዳዎችን በይደር መተው አይበጅ ይሆን?
_____________
በጨዋነት እንወያይበት!