25/12/2025
ከግንዛቤ ጉድለት የመነጭ የስም ማጥፋት ዘመቻ - ስለ "አሻራ የጋራ መኖሪያ መንደር" እውነታው ምንድን ነው?
ሰሞኑን በማህበራዊ ሚዲያ "አዳነች አበቤ ንግድ ባንክን ሿሿ ሰራችው" በሚል ርዕስ የሚዘዋወረው ጽሁፍ የቤቶች ግንባታን እና የሪል ስቴት አሰራርን ካለመረዳት የመነጨ ፍጹም የተሳሳተ መረጃ ነው። ትችቱ እውቀት ላይ ያልተመሰረተና የሰዎችን ስም ለማጥፋት ታስቦ የተዘጋጀ በመሆኑ፣ እውነታውን ለህዝብ ግልጽ ማድረግ አስፈላጊ ሆኗል።
1. የ "Gross Area" እና "Net Area" ልዩነት (ያልተረዳችሁት ትልቁ ነጥብ): በማንኛውም የጋራ መኖሪያ ህንፃ (Apartment) ግንባታ ላይ Gross Area (ጠቅላላ ስፋት) እና Net Area (የውስጥ ስፋት) የሚባሉ መለኪያዎች አሉ።
👉 Net Area: በአራቱ ግድግዳዎች ውስጥ ያለውን የመኖሪያ ክፍል ስፋት ብቻ የሚለካ ነው።
👉 Gross Area: የግል ክፍሉን ስፋት ጨምሮ፣ የጋራ መጠቀሚያዎችን (ኮሪደር፣ ደረጃ፣ ሊፍት፣ እና የግድግዳ ውፍረት) በየቤቱ ድርሻ ተከፋፍሎ የሚታከልበት ነው።
2. ካርታ የሚሰራው በ Gross Area ነው! የከተማ አስተዳደሩም ሆነ የትኛውም ሪል ስቴት ካርታ የሚያዘጋጀው በ Gross Area ነው። የንግድ ባንክ ሰራተኞችም ሆኑ ባንኩ ክፍያ የፈጸሙት የጋራ መጠቀሚያዎችን (Common areas) ጨምሮ ለያዙት ጠቅላላ ይዞታ ነው። መሬት ላይ ያለው ሴራሚክ ብቻ ተቆጥሮ "ካሬው ጎደለ" ማለት፣ ስለ ህንፃ ግንባታ እና የባለቤትነት ህግ ምንም አለማወቅ ነው። "52 ካሬው በ76 ካሬ ተጻፈ" የሚለው ቅሬታ፣ ያ 24 ካሬ ልዩነት የቤቱ ድርሻ የሆነው የጋራ መተላለፊያ እና የህንፃው አካል መሆኑን ካለመረዳት የመነጨ ነው።
3. "ሿሿ" ወይስ ህጋዊ አሰራር? የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ግዙፍ እና በባለሙያዎች የተሞላ ተቋም ነው። እንዲህ ያለውን ትልቅ ግዥ ሲፈጽም በኢንጂነሮች እና በህግ ባለሙያዎች ጥናት አድርጎ እንጂ በግርግር አይደለም። ከተማ አስተዳደሩም የህንፃ ስታንዳርድን ጠብቆ ያስረከበ እንጂ ማጭበርበር አልፈጸመም።
4. የስም ማጥፋት ወንጀልና ኃላፊነት፡ እውነታውን ሳያጣሩ፣ ተቋማትን እና ግለሰቦችን በሌሉበት "አጭበረበሩ" ብሎ መክሰስ ህጋዊ ተጠያቂነት የሚያስከትል የስም ማጥፋት ወንጀል ነው። የፖለቲካ ትችት ማቅረብ መብት ቢሆንም፣ የቴክኒክ እውቀትን መሰረት ያላደረገ የሀሰት ወሬ ማሰራጨት ግን ህዝብን ማሳሳት እና ተቋማትን ማዳከም ነው።
ማጠቃለያ፡ መሬት ላይ ያረፈ የግል ቪላ ቤት እና የጋራ መኖሪያ ህንፃ (Apartment) የካሬ አሰላልፋቸው የተለያየ መሆኑን ይገንዘቡ። ካላወቁ መጠየቅ እንጂ በለየለት ስህተት ተቋማትን መወንጀል አይገባም።