12/08/2026
ኢትዮጵያ የክፍያ ሥርዓቷን ከጥሬ ገንዘብ ወደ ዲጂታል ኢኮኖሚ እያሸጋገረች ነው ተባለ።
የብሔራዊ ባንክ የባንኮችና የክፍያ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሰለሞን ዳምጠው፣ ኢትዮጵያ ከጥሬ ገንዘብ ተኮር አሠራር ወደ ተገናኝቶ ወደሚሰራ ዲጂታል የፋይናንስ ሥርዓት እየተሸጋገረች መሆኑን ገለፀዋል።
አቶ ሰለሞን በ29ኛው የConnected Banking Summit ላይ ባደረጉት ንግግር፣ በሀገሪቱ የሞባይል ገንዘብ አካውንቶች ቁጥር በአጭር ጊዜ ከፍተኛ እድገት አምጥቷል ያሉ ሲሆን የተጠቃሚው ቁጥር ከ157 ሚሊዮን በላይ መድረሱን ጠቁመዋል።
ነገር ግን ከተመዘገቡት አካውንቶች ውስጥ በንቃት የሚጠቀሙ ሰዎች መጠን ከ15 በመቶ በታች መሆኑን ጠቁመው፣ የዲጂታል ክፍያ አጠቃቀምን ማሳደግ ቀጣዩ ትኩረት መሆኑን አስረድተዋል።
የክፍያ ሥርዓት ጉዳይ ከቴክኖሎጂ ባሻገር ከኢኮኖሚ ዕድገት፣ ከሥራ ዕድል ፈጠራና ከፋይናንስ አካታችነት ጋር ተያይዞ መታየት እንዳለበትም ሰለሞን ዳምጠው ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ የዲጂታል ክፍያ ሥርዓት ቀጣዩ ትኩረት የፋይናንስ አካታችነትን ማሳደግ፣ የግል ዘርፉን ተሳትፎ ማጠናከር፣ የክፍያ ሥርዓቶችን ማገናኘትና ዲጂታል ክፍያን ለኢኮኖሚ ዕድገት የበለጠ አስተዋፅኦ እንዲያደርግ ማድረግ እንደሆነ ተጠቁሟል።