11/12/2025
ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል ለመሆን የምታደርገው ጥረት ወሳኝ ምዕራፍ ላይ መድረሱ ተገለጸ
ገበያ ሚዲያ ታህሳስ 02/2018 ዓ/ም
ኢትዮጵያ የአለም አቀፍ የንግድ ድርጅት አባል የመሆን ህልሟን እውን ለማድረግ ባደረገችው ፅናት የተሞላበት ጉዞና የድርድር ሂደት ወሳኝ ምዕራፍ ላይ ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ተናገሩ፡፡
ይህ የተገለጸው ንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር " ኢትዮጵያን በንግድ በማስተሳሰር ወደ ላቀ ደረጃ ማሸጋገር" በሚል መሪ ቃል የአለም የንግድ ድርጅት አባልነት የድርድር ሂደት እና እስካሁን በተከናወኑ ስራዎች ላይ ለባለድርሻ አካላት የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ ባተካሄደበት ወቅት ነው፡፡
በዚህም በ6ኛው የስራ ቡድን ስብሰባ ላይ የኢትዮጵያ የእስካሁኑ የስራ ቡድን ስብሰባ ሪፖርት ወደ ረቂቅ የስራ ቡድን ሪፖርትነት እንዲያድግ በመደረጉ የድርድር ሂደቱን አንድ እርምጃ ከፍ አድርጎታል ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህም የባለ ብዙ ወገን የድርድር ሂደት መቋጫ ላይ እየደረስን መሆኑን ያሳያል ብለዋል።
ኢትዮጵያን የአለም የንግድ ድርጅት አባል ለማድረግ የተጀመረው የድርድር ሂደት ከሁለት አስርተ ዓመታት በላይ የፈጀ ቢሆንም ባሰለፍናቸው 7 ወራት ውስጥ በተካሄዱ 5ኛ እና 6ኛ የስራ በድን ስብሰባዎችም የድርድር ሂደቱ ወሳኝ ምዕራፍ ላይ መድረሱን እንደሚያመላክት ከንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያሳያል፡፡