የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ አገልግሎት/Addis Ababa Diocese Media Service

  • Home
  • Ethiopia
  • Addis Ababa
  • የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ አገልግሎት/Addis Ababa Diocese Media Service

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ አገልግሎት/Addis Ababa Diocese Media Service ይህ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ የፌስቡክ ገጽ ነው።
መንፈሳዊ አገልግሎትና ሰሞነኛ ጉዳዮች ይቀርቡበታል።

የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ቃለ በረከት  ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣  #የ2018 ዓ,ም   መግባት አስመልክተው የእን...
10/09/2025

የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ቃለ በረከት

ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ #የ2018 ዓ,ም መግባት አስመልክተው የእንኳን አደረሳችሁ ቃለ ምእዳንና ቡራኬ ሰጥተዋል ፣ የቅዱስነታቸው ሙሉ መልእክት የሚከተለው ነው።

ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ርእሰ ዐውደ ዓመት ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰንመቱ ዓመተ ምሕረት፤

በስመ ኣብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ኣሐዱ ኣምላክ ኣሜን!

• በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣
• ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፣
• የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣
• በሕመም ምክንያት በየፀበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣
• እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያት በሙሉ፣
ኣምላክነቱን ኣውቀን እንድናመልከው ዕድሜንና ዘመናትን የሚሰጠን እግዚብሔር ኣምላካችን እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ ስምንት ዓመተ ምህረት የርእሰ ዐውደ ዓመት በዓል ኣደረሰን ኣደረሳችሁ!

‹‹ወገብረ ኵሎ ኅቡረ ወኵሎ ኣሕዛበ እምአሐዱ ዕጓለ እመሕያው ከመ ይንበሩ ዲበ ኵሉ ገጸ ምድር፤ ወሠርዐ ዕድሜሁ ወዓመታቲሁ መጠነ ይነብሩ በዘየኃሥዎ ለእግዚአብሔር፤ እመ ይረክብዎ፤ ወያደምዕዎ፤ ወኢኮነ ርሑቀ እምኵልነ፡- ምናልባትም እየመረመሩ ያገኙት እንደሆነ እግዚአብሔርን ይፈልጉ ዘንድ በምድር ሁሉ ላይ እንዲኖሩ የሰውን ወገኖች ሁሉ ከኣንድ ፈጠረ፤ የተወሰኑትንም ዘመኖችና ለሚኖሩበት ስፍራ ደረጃ መደባላቸው፤ ቢሆንም ከእያንዳንዳችን የራቀ ኣይደለም›› (የሐ. ሥራ. ፲፯÷፳፮)።

ፈጣሬ ፍጥረታት እግዚአብሔር ትዕይንተ ዓለምንና በውስጡ የሚገኙ ፍጥረታትን የፈጠረ ኣምላክ ነው፤ እግዚአብሔር የፈጠራቸው ፍጥረታት የሚታዩና የማይታዩ ተብለው በጥቅል በቅዱስ መጽሓፍ ተገልጸዋል፤ የሰው ልጅ ከፍጥረታት መካከል ሆኖ ከኣንድ ወገን የተገኘ እንደሆነ በዚህ ጥቅስ ተጽፎኣል፤

የሰው ልጅ ከፍጥረታት ሁሉ የተለየ ክብርና ደረጃ እንዳለው በቅዱስ መጽሓፍ በተደጋጋሚ ተገልጾኣል፤ ልዩ የሚያደርገውም ከኣፈጣጠሩ ጀምሮ ነው።

ሰው ልዩ ፍጡር መሆኑን ከሚገለጽባቸው መካከል እግዚአብሔር በሦስትነቱ “ሰውን በኣርኣያችንና በኣምሳላችን እንፍጠር” በሚል ልዩ ኣገላለጽ መፈጠሩ፣ ኣፈጣጠሩም በእግዚአሔር መልክና ኣምሳል መሆኑ፣ በእግዚአብሔር እፍታ ሕያው ነፍስ እንዲኖረው መደረጉ፣ በሥልጣንም የፍጥረታት ሁሉ የበላይ ሆኖ መሾሙ ከሌሎች ፍጥረታት ልዩ ያደርገዋል፡፡

ከዚህ ኣንጻር ሰው በዚህ ዓለምም ሆነ በወዲያኛው ዓለም ከፍጥረታት ሁሉ በላይ ነው፤ የሁሉም ገዥ ነው፤ በተለይም በዚህ ዓለም ከሰው በላይ ሆኖ የፍጡራን ገዥ የሆነ ፍጡር እንደሌለ ሁላችንም የምናየውና የምናውቀው ነው።
በላይኛው ዓለምም ቢሆን መላእክትን ጨምሮ ሰማይና ምድርን ከነግሣንግሡ እየገዛ ያለው ሰው የሆነ ጌታ ነው፤ ምክንያቱም ኢየሱስ ክርስቶስ የፍጥረት ገዥ ነው፤ እሱ ሰብእናችንን በፍጹም ተዋሕዶ የተዋሓደ በመሆኑ ሰብእናችን በተዋሕዶተ ቃል ኣምላክ ሆኖ የፍጥረታት ሁሉ ገዥ ሆኖኣልና ነው።
ቅዱስ መጽሓፍም “ወተኰነኑ ሎቱ መላእክት ወሥልጣናት ወኵሉ ኃይል፡- መላእክት፣ ሥልጠናትና ኃይል ሁሉ ተገዙለት” በማለት ይህንን ያረጋግጣል፤ ይህ እግዚአብሔር ለኛ ለሰዎች ያጐናጸፈን ግሩምና ኣስደናቂ ጸጋ ነው፤ ለዚህም ነው “ወሰብእ ይከብር እምኵሉ ፍጥረት፡- ሰው ከፍጥረት ሁሉ ይከብራል” ተብሎ የሚዘመረው።

• የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውንና ኢትዮጵያውያት!
እኛ ሰዎች የእግዚአብሔር ክብር መገለጫ ሆነን እንድንኖር በእግዚአብሔር ስንፈጠር በሕይወት እንድንኖር ነው፤ እግዚአብሔር በምድር ላይ በሕይወት ይኖሩ ዘንድ ሰውን ከኣንድ ፈጠረ የሚለው መጽሓፍ ቅዱሳዊ ኣስተምህሮም ይህንን ያመለክታል።

ሰዎች በምድር ላይ በሕይወት እንዲኖሩ የተፈጠሩ ሆነው እያለ በሕይወት እንዳይኖሩ ማድረግ ከፈቃደ እግዚአብሔር ጋር መጋጨትን ያስከትላል፤በዘመናችን ዓለማችንን እየፈተነ ያለው ተቀዳሚ ፈተና ሰዎች በሕይወት እንዳይኖሩ የማድረግ ዝንባሌ ነው።

እንደዚህ ዓይነቱ ዝንባሌ በዓለም ባይኖር ኖሮ በመቶ ሚሊዮኖች የሚቈጠሩ ድሆች ባሉበት ዓለም ለሰው ልጅ ሕይወት ማጥፊያ የሚሆን መሳሪያ ለማምረት ኁልቈ መሣፍርት የሌለው ገንዘብ ኣይወጣም ነበር።

ይህ ክፉ የዓለም ዝንባሌ እንደ ክፋት ብቻ ሳይሆን እንደ ሞኝነትም የሚያሳይብን ነው፤ማንኛችንም ሰዎች ‹‹ሰው ማጥፋት ይሻላል ወይስ ማዳን›› ተብለን ብንጠየቅ መልሳችን ምን እንደሚሆን ይታወቃል።

ነገር ግን ኣንፈጽመውም፣ ሞኝነት የሚያሰኘውም እዚህ ላይ ነው፤ የሚጠቅመንንና የመሰከርንለትን ትተን የሚጐዳንንና፣ ያልመሰከርንለትን እንፈጽማለንና ነው።

ስለሆነም በሕይወት እንዲኖር የተፈጠረውን ሰው በሕይወት የመኖር መብቱን ከመንፈግ መቆጠብ የኣዲሱ ዓመት ትልቁ ኣጀንዳ ኣድርገን ብንወስድ ለሁላችንም ይበጀናልና እንቀበለው እንላለን፤

• የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን! ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት!

ሰው በሕይወት እንዲኖር በእግዚአብሔር ሲፈጠር እግዚአብሔርን የሚፈልግበትና የሚያገኝበትን ዕድሜና ዘመንም እንደተሰጠው ከተጠቀሰው ክፍለ ንባብ እንገነዘባለን፤ መቼም እግዚአብሔር ሁሉን የፈጠረ በስራ ለስራ እንደሆነ የምንስተው ኣይሆንም፤ እግዚአብሔር ዕድሜና ዘመን ለሰዎች ሲሰጥ ሊሰራበት ነው፤ ስራውም መንፈሳዊና ዓለማዊ ነው፤ ተደምሮ ሲታይ ደግሞ ለሰው ጥቅም የሚውል ነው፤

እኛ ሰዎች በተሰጠን ዕድሜና ዘመን በመንፈሳዊው ስራችን እግዚአብሔርን ፈልገን እንድናገኝ ተፈጥረናል፤ እሱን ማግኘት የማይቻል የሚመስለን ካለንም እሱ ከእያንዳንዳችን የራቀ ኣይደለም ተብለናልና በመንፈስ ከፈለግነው በመንፈስ እንደምናገኘው መጽሓፉ ያስረዳናል፤ስለሆነም በተሰጠን ዘመን ይህንን ስራ መስራት ይኖርብናል፤

በሌላ በኩል ለኑሮኣችን የሚያስፈልገንን ፍጆታ በበቂ ሁኔታ እንድናገኝ ላባችንን ኣንጠፍጥፈን መስራት ይገባናል፤ ይህም ከሰራን ያለጥርጥር የምናገኘው ነው፤ ሁለቱም የጐደሉብን በኛ ኣስተሳሰብ፣ ኣሰራርና ኣጠቃቀም እንጂ እግዚአብሔር ሳይፈቅድልን ቀርቶ ወይም ነፍጎን ኣይደለም፤ እግዚአብሔር የሰጠን ምድር በልዩ ልዩ ሀብተ ጸጋ የተሞላች እንደሆነች፣ የምንረግጠው መሬትም ወደ ሀብት መቀየር እንደሚቻል የተረጋገጠ ነው።

ነገር ግን እኛ በምንራመድበት በእግራችን ሥር ያለውን ሀብት ትተን በሩቅ ያለውን ስንመለከት ሁሉን ያጣን ሆነን በችግር ወድቀን እንገኛለን፤ በተለይም እኛ ኢትዮጵያውያን በኣሁኑ ጊዜ እየተፈታተነን ያለው ይኸው የተሳሳተ እሳቤ ነው።
ኢትዮጵያ የሁላችንም ኢትዮጵያውያን ኣድርገን በማመን በእኩልነት፣ በኣንድነትና በስምምነት ከመጠቀም ይልቅ ያ የኔ ነው ያም የኔ ነው በሚል ኣባባል ምን ያህል ዋጋ እየተከፈለ እንደሆነ እያየን ነው፤ ይህ ግለኝነት ያየለበት ኣስተሳሰብ ገታ ኣድርገን በእኩልነትና በኣብሮነት የሚያሳድገንን ኣስተሳሰብ በእጅጉ ይጠቅመናል። ይህንንም የኣዲሱን ዓመት ምርጥ እሳቤ ኣድርገን ብንወስድ የተሻለ መግባቢያ ሊሆን ይችላል፤ ኣዲሱ ዓመት በኣዲስ እሳቤ ካላጀብነው ኣዲስ ሊሆን ኣይችልምና ነው።

ስለሆነም ኣዲሱን ዓመት መልካም በሆነ ኣዲስ ኣሳብ ፣እግዚአብሔርንና ሰውን በሚያገናኝ ቅዱስ ተግባር፣ በልማት፣ በሰላም፣ በፍቅር፣ በዕርቅና በስምምነት እንድንቀበለው ወቅታዊ ጥሪያችን ነው።

በመጨረሻም፣
ኣዲሱ ዓመት ለሀገር ሰላምና ልማት፣ ለሕዝቦች ኣንድነትና ስምምነት እንደዚሁም ኣለመግባባትን በፍትሕና በዕርቅ ለመፍታት ከልብ የምንተጋበት መልካም የስኬት ዘመን እንዲሆንልን እንጸልይ፣ በዚህም መላ ሕዝባችን ጠንክሮ እንዲሰራ ለመላ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት ሁሉ ኣባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን።

እግዚአብሔር ኣምላካችን ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ
ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣

 #ገጹን ይወዳጁ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደር ልማት ድርጅት በየጊዜየው የሚያከናውናቸውን ዘርፈ ብዙ ሥራዎች መሰረት በማድረግ ደንበኛ ተኮርና በቴ...
10/09/2025

#ገጹን ይወዳጁ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደር ልማት ድርጅት በየጊዜየው የሚያከናውናቸውን ዘርፈ ብዙ ሥራዎች መሰረት በማድረግ ደንበኛ ተኮርና በቴክኖሎጂ የተደገፈ አልግሎትን ተግባራዊ በማድረግ የሚያደርገውን ጥረት ይደግፉ ይከታተሉ ።

1. በፌስቡክ ገጹ
https://www.facebook.com/share/1CUnRWepR9/
2. በቴሌግራም ገጹ
Telegram channel: https://t.me/eotchbada
3. በኢሜል : [email protected]
ላይ መረጃዎችን ያሳውቃል።
በመሆኑም የሚመከታቸው የተዋሕዶ ልጆች ከላይ የምትመለከቱትን ማስፈንጠሪ እየነካችሁ ቤተሰብ እንድትሆኑ እና ለሚመለከታቸው ሁሉ እንድታጋሩ በቅድስት ቤተክርስቲያን ስም እንጠይቃለን ።

የኢ/ኦ/ተ/ቤተክርስቲያን የቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደርና ልማት ድርጅት

የኢትዮጵያ ኦርቶዶስክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መገናኛ ብዙኃን ሥርጭት አገልግሎት ድርጅት የበላይ  ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የተመራ የሥራ አመራር ቦርድና አስተዳደር ልኡክ ለብፁዕ አቡነ...
10/09/2025

የኢትዮጵያ ኦርቶዶስክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መገናኛ ብዙኃን ሥርጭት አገልግሎት ድርጅት የበላይ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የተመራ የሥራ አመራር ቦርድና አስተዳደር ልኡክ ለብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ ሊቀ ጳጳስ የአዲስ ዓመት መልካም ምኞቱን ገለጸ።

ጳጒሜን ፭/፳፻፲፯ ዓ/ም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶስክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መገናኛ ብዙኃን ሥርጭት አገልግሎት ድርጅት የበላይ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የተመራ የሥራ አመራር ቦርድና አስተዳደር ልኡክ ለብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባና ሀዲያ ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የአዲስ ዓመት መልካም ምኞቱን ገለጸ።

ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የምሥራቅ ና የሰሜን አፍሪካ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የመገናኛ ብዙኃኑ የበላይ ሐላፊ የተመራ ልኡኩ በዛሬው ዕለት በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ብፁዕ ሊቀ ጳጳስ ጽ/ቤት በመገኘት ለብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ እና የሀዲያና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንኳን ለ፳፻፲ወ፰ቱ ዓ/ም ዘመነ ቅዱስ ማርቆስ በሰላም በጤና አደረሰዎ በማለት መልካም ምኞቱን ገልጿል።

ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ ሊቀ ጳጳስ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትን በበላይነት የሚመሩት ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ ለመገናኛ ብዙኃኑ ብሎም ለሚዲያ ባላቸው መልካም መረዳት ምክንያት EOTC TV የሚጠናከርብትን በተለይም በጾመ ፍልሰታ ለማርያም ድጋፍና ትብብር እንዲደረግለት በማድረግ ትልቅ ሥራ እንደሠሩ ገልጸው አመስግነዋል።

በቀጣይም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የቤተ ክርስቲያናችን ልሳን የሆነውን EOTC TV ቴሌቪዥን በአስፈላጊ በሚባለው ሁሉ ትብብርና ድጋፍ እንደሚቀጥል ተስፋቸውን ገልጸዋል።
💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠
ሙሉ መልእክታቸው እንደሚከተለው ይነበባል።

እንኳን ለ፳፻፲ወ፰ ዓ/ም ዘመነ ቅዱስ ማርቆስ በሰላም አደረሰዎ።

የዘመናት ባለቤት አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር እንኳን በሰላምና በጤና በመንበረ ጵጵስናዎ ጠብቆ ለ፳፻፲ወ፰ቱ ዓ/ም ዘመነ ቅዱስ ማርቆስ በሰላም አደረሰዎ እያልን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብዙኃን መገናኛ ስርጭት ድርጅት የሥራ አመራር ቦርድ፣አስተዳደር እና በሠራተኞች ስም የመልካም ምኞት መልእክታችንን ስናስተላልፍ ታላቅ ደስታ ይሰማናል።

ብፁዕነትዎ ባሳለፍነው ፳፻፲ወ፯ቱ ዓ/ም በአባትነት የሚመሯቸውን አህጉረ ስብከት፣ ካህናት እና ምእመናን በማስተባበር ለተቋማችን ያደረጉት የአባትነት አስተዋጽኦ ከፍተኛ ዕውቅና የምንሰጠው የአባትነት ተግባር ነው።

የዚህ ዓይነቱ የቤተ ክርስቲያንን ተቋም የመደገፍ ተግባር ተጠናክሮ መቀጠልም የቤተ ክርስቲያናችንን ሐዋርያዊ ተልእኮ ከዳር ለማድረስ ቁልፍ ሚና እንደሚኖረው እምነታችን ጽኑዕ ነው።

ስለሆነም ብፁዕነትዎ እስከ አሁን አባታዊ አመራር በመስጠት ሲያደርጉልን እንደቆዩት ሁሉ በመጪው ፳፻፲ወ፰ቱ ዓ/ም ዘመነ ቅዱስ ማርቆስም ተቋማችን በገንዘብ፣ በቴክኖሎጂ ቁሳቁስ እና ተባብሮ በመሥራት የበለጠ የሚታገዝበትን መንገድ እንደሚያመቻቹልን በመተማመን በድጋሚ እንኳን ለ፳፻፲ወ፰ቱ ዓ/ም ዘመነ ቅዱስ ማርቆስ በሰላም አደረሰዎ በማለት የመልካም ምኞት መልእክታችንን እናስተላልፋለን።

ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ
የኢኦተቤ የመገናኛ ብዙኃን ድርጅት የበላይ ሐላፊና የምሥራቅና የሰሜን አፍሪካ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
ጳጉሜን ፭/፳፻፲፯ ዓ/ም

"የምሥራቹን ወንጌል እስከ ምድሪቱ ጠረፍ ተደራሽ ለማድረግ የጋራ ግብ ማስቀመጡ አስፈላጊ ነው"... መልአከ ሰላም ዳዊት ያሬድጳጒሜን ፭/፳፻፲፯ ዓ/ም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያየኢትዮ...
10/09/2025

"የምሥራቹን ወንጌል እስከ ምድሪቱ ጠረፍ ተደራሽ ለማድረግ የጋራ ግብ ማስቀመጡ አስፈላጊ ነው"... መልአከ ሰላም ዳዊት ያሬድ

ጳጒሜን ፭/፳፻፲፯ ዓ/ም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽ/ቤት ስብከተ ወንጌል
እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ዋና ኃላፊ መ/ሰላም ዳዊት ያሬድ በዛሬው ዕለት በመንበረ ፓትርያርክ ጠ/ጽ/ቤት በሰጡት መግለጫ "የምሥራቹን ወንጌል እስከ ምድሪቱ ጠረፍ ተደራሽ ለማድረግ የጋራ ግብ ማስቀመጡ አስፈላጊ ነው ሲሉ ተናገሩ።

የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ የስብከተ ወንጌል ተደራሽነቱን ለማስፋት የሚቻልበትን ምክክርና ውይይት ከሁሉም አህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆችና ከባለድርሻ አካላት ጋር መስከረም 6 ቀን 2018 ዓ.ም በኢሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ለማድረግ ዝግጅት መጠናቀቁን አስመልክቶ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስና የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በተገኙበት በዛሬው ዕለት መግለጫ ተስጥቷል።

የመምሪያው ዋና ኃላፊ በምክክር መድረኩ ለውይይት እና ለምክክሩ መነሻ የሚሆኑ ጥናታዊ ጽሑፎች በምሁራን የሚቀርብ መሆኑን እና በመድረኩ የሚነሱ ሐሳብና አስተያየቶችን በግብዓትነት በመያዝ መምሪያው በቀጣይ ከያዛቸው ታላላቅ ዕቅዶቹ ጋር በማዋሀድ ተግባር ላይ የሚውሉበትን መንገድ የሚያመቻች ይሆናል ብለዋል።

ዋና ኃላፊው አክለውም ጥሪው ቀደም ብሎ በልዩ ልዩ መንገድ የተላለፈላችሁ ባለድርሻ አካላት ሁሉ በተጠቀሰው ቀንና ሰዓት ካዛንቺስ አካባቢ በሚገኘው በኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል እንድትገኙልን ሲሉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀጳጳስ ቅዱስ ወንጌል የቅድስት ቤተክርስቲያናችን ተቀዳሚ ተግባር በመሆኑ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥተን መሥራት ይገባናል ብለዋል።

ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ አክለውም መድረኩ በመምሪያው የተዘጋጀበትም ዋና ዓላማ በአገልግሎቱ ተደራሽነት ዙሪያ ተነጋግረን እና የጋራ አቅጣጫ አስቀምጠን የአገልግሎት አድማሳችንን ለማስፋት ስለሆነ ጥሪ የተደረገላችሁ ባለድርሻ አካላት ሁሉ ጥሪውን አክብራችሁ በቦታውና በስዓቱ እንድትገኙ በማለት አባታዊ መመሪያ አስተላልፈዋል።

🔵የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ
ስለ አንዲት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን

🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚 https://www.facebook.com/AddisAbabaDiocese?mibextid=2JQ9oc

ከዚህ በተጨማሪ በሌሎች የበይነ መረብ አማራጮች ለመከታታል
በቴሌግራም: https://t.me/AddisAbabaDiocese

በዩቱዩብ: http://www.youtube.com/

በቲውተር: https://twitter.com/AADioceseMedia/media
በቲክቶክ:http://tiktok.com/
መጠቀም ይችላሉ።

"እግዚአብሔር ይዌልጥ ዓመታተ እግዚአብሔር  ዘመናትን ይለውጣል " ት.ዳን 2:21--------------------------------------------------------------‎      ...
10/09/2025

"እግዚአብሔር ይዌልጥ ዓመታተ
እግዚአብሔር ዘመናትን ይለውጣል " ት.ዳን 2:21
--------------------------------------------------------------
‎ በመልአከ ምሕረት አባ ገብረመድኅን ንጉሤ (ቆሞስ)
‎ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ
‎---------------------------------------------------------------

በዘፍ 1:14 "እግዚአብሔርም አለ። ቀንና ሌሊትን ይለዩ ዘንድ ብርሃናት በሰማይ ጠፈር ይሁኑ፤ ለምልክቶች፣ ለዘመኖች፣ ለዕለታት፣ ለዓመታትም ይሁኑ" እንዲል ብርሃናት ምልክቶች ለተባሉ ለበዓላትና ለአጽዋማት ዘመኖች ለተባሉ ለአራቱ ወቅቶች ዕለታት ለሆኑ ለሰባቱ ቀናት እና ዓመታት ለተባሉ ከአንድ ዓመት በላይ ለሆኑ ዘመናት እንደሚያስፈልጉ ያጠይቃል።

በኢትዮጵያ ቀመር መሠረት አራቱ ወቅቾች የሚባሉትም
1. ዘመነ ክረምት ከሰኔ 26 እስከ መስከረም 25 ፤
2. ዘመነ መፀው ከመስከረም 26 እስከ ታኅሳስ 25፤
3. ዘመነ ሐጋይ (በጋ) ከታኅሳስ 26 እስከ መጋቢት 25
4. ዘመነ ፀደይ (በልግ) ከመጋቢት 26 እስከ ሰኔ 25 ድረስ ናቸው።

መቼም ቸሩ አምላካችን ዘመን ለንስሐ እየሰጠን አሮጌውን እያሳለፈ አዲስ ዘመን እየተካ እኛም በብልየት፣ በኃጢአት ያደፈው ማንነታችን በንስሐ በምግባር ይታደስ ዘንድ እያኖረን ይገኛል፡፡

የዘመን መለወጡ አላማ እኛ እንድንለወጥ ነው ፡፡ ቅ/ጳውሎስ " የእግዚአብሔር ፈቃድ እርሱም በጎና ደስ የሚያሰኝ ፍጹምም የሆነው ነገር ምን እንደ ሆነ ፈትናችሁ ታውቁ ዘንድ በልባችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ።" ሮሜ 12:2 እንዲል ፦

መስከረም 1 ቀን ጻድቁ ኢዮብ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ ከደዌው የተፈወሰበትና በእጥፍ የተባረከበት፣ አትክልተኛው ሐዋርያ በርተሎሜዎስ በርበር በሚባል ሀገር በሰማዕትነት ያረፈበት፣ ገባሬ ተአምራት ወመንክራት የሆነ በስሙ ብቻ አጋንንት የሚወጡለት አባ ሚልኪ ቁልዝማዊ በዓለ ረፍቱ ሲሆን የቅዱስ ራጉኤል መልአክ መታሰቢያም ነው።

✍ ነገር ግን ዘመን መለወጫችን ብዙ ስያሜ አለው፡፡ ይኸውም "እንቁጣጣሽ" ሌላው "ቅ/ዮሐንስ" ይባላል፡፡

1. ዕንቍጣጣሽ

በእኛ በኢትዮጵያውያን ዘንድ ለየት ያለ በዓል ነው ፡፡ የብሩህ ፣የደስታ ፣ የተስፋ እና የአዲስነት በዓላችን ነው ፡፡ ዐውዳዊ ፍቺውን ስንመለከት ግን ዕንቍ የከበረ መዓድን ስለሆነ በጣም ነጭና ላሸበረቀ ነገር የሚቀጸል ነው። ምድር በወርኃ መስከረም ቡቃያና አበባ አብቅላ የምታጊጥ ስለሆነ በጣም በነጭ ጌጣጌጥ ያሸበረቀ ሰውን ዕንቁጣጣሽ መስሏል እንደሚባል ሁሉ አዲሱ ዘመን በመልካም ነገር እንደ ዕንቍ ያሸበርቅ ዘንድ ስንመኝ " ዕንቍጣጣሽ" በማለት እንጠራዋለን።

አንድም፦ ገጸ በረከት ማለት ሲሆን በአገራችን ለመዠመሪያ የዕንቍጣጣሽ ግብር የተሰጠው ለንግሥተ ሳባ (ማክዳ) ነው ፡፡ በሀገረ ኢየሩሳሌም ከሰሎሞን የተጸነሰው ሚኒሊክ ሲወለድ ንጉሥ ተወለደ ብለው የሀገራችን ሴቶች የአበባ ዕንቍጣጣሽ አበረከቱላት፡፡ ንጉሥ ሰሎሞንም ልጅ በመውለዱ ደስ ተሰኝቶ ዕንቍ ለጣትሽ ብሎ መታሰቢያ እንዲሆናት የዕንቍ ቀለበት የሰጣት በመሆኑ ከዚ ተያይዞ ዕንቍጣጣሽ እያልን እናከብራለን፡፡

አንድም፦ ዕንቍ "ዕጣ ወጣሽልኝ" ማለት ሲሆን የኖኅ ልጅ ካም ከወንድሞቹ ጋር ርስት በተከፋፈሉ ጊዜ አፍሪካ ደርሳው በመስከረም ወር ሲመጣና ሲያርፍባት የአበቦቹን ማማር የምድርን ማጌጥ ተመልክቶ " ዕንቍ ዕጣ ወጣሽልኝ" ብሎ በመናገሩ ዕንቍጣጣሽ እንላለን።

ዕንቁጣጣሽ ታሪካዊ አመጣጡን ስንመለከት በግዕዙ ለአንድ ሲሆን ✍ዕንቁ ✍ ብሎ ለብዙ ሲሆን ደግሞ "አዕናቁ" ይላል ፡፡ ጣጣሽ የሚለው ደግሞ "ጻዕጻዕ" ሲሆን ጣጣ ፣ ግብር ፣ መባዕ መፍቀድ፣ ገጸ በረከት ማለት ሆኖ ሙሉውን "እንቁጣጣሽ" ማለት የእንቁጣጣሽ ግብር ገጸ በረከት ማለታችን ነው ፡፡ የብሉይ መጽሐፍት ለእግዚአብሔር የሚቀርበውን የከበረ መባዕ "ጻዕጻዕ" ይሉታል፡፡ /ግዕዙን ተመልከት/

=> ለወንድ/ንጉስ/ አበርክተው ቢሆን "እንቁጣጣሁ" ይባል ነበር ለሴት ስለተበረከተ "እንቁጣጣሽ" እንላለን፡፡

ዛሬ ድረስ በአንዳንድ አከባቢ ግብር ልክፈል ሲሉ "ጣጣ" ልክፈል ይላሉ ፡፡

=> ከዚህ ባሻገር በታሪክ ደረጃ አስቀድሞ ሰሎሞን ሲገናኛት የገበረችለት "ተንካራ" የተባለ ቀለበት ነበር ፡፡ እርሱን ዕንቍጣጣሽ ይሁንሽ ብሏት ነበር ይባላል ፡፡

=> 2. ቅዱስ ዮሐንስ ይባላል ፡፡

በመጥምቁ ዮሐንስ ስም ተሰይሟል ፡፡ ለምን ሲባል ንጉስ ሔሮድስን "የወንድምህ ሚስት ላንተ ልትሆን አልተፈቀደም"ብሎ ስለገሰጸው ጳጉሜ አንድ ቀን ታስሮ መስከረም 2 ቀን አንገቱ ተቆርጧል ፡፡ ይህ ነቢይና ሰማዕት መታሰቢያው የአዲስ ዘመን መታሰቢያ ቀን ተደርጎ ይከበራል ፡፡ "ርእሰ አውደ አመት ዮሐንስ ወላዴ መጥቅዕ ወአበቅቴ" እየተባለ ይዘመርለታል ፡፡

ለምን ከተባለ ለብሉይ ዘመን አሳላፊ ለአዲስ ዘመን ተኪ ዘመን ላይ ንስሐ ግቡ ብሎ ሰብኳል ፡፡ ስለዚህ አሮጌው ዘመን ማለፊያ አዲሱ ዘመን መዠመሪያ ላይ በዓሉ በስሙ ተሰይሟል ፡፡

ይህን አስተውል " ዘመነ ዮሐንስ" ከተባለ ወንጌላዊውን ይገልጣል አራተኛውን ወንጌል የጻፈው ሲሆን መስከረም 1 ቀን በመጥምቁ ዮሐንስ ስም የተሰየመው በዓሉ እንጂ ዘመኑ አይደለም፡፡

=> ካድያ ዘመናት ሲተኩ በሐጢአት ያጎደልንውን የጽድቅ በረከታችን በጽድቅ ልንሞላ የበደልን ልንክስ የቀማን ልንመልስ ንስሐ ያልገባን ልንገባ ስጋ ወደሙን ያልተቀበልን ልንቀበል ያስፈልጋልና ዘመናችን የመልካምና የደስታ የማግኘትና በጽድቅ የመበልጸግ እንዲያደርግልን የዘመናት ጌታ አምላከ ቅዱሳን አምላካችን እግዚአብሔር ፈቃዱ ይሁንልን ፡፡

የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደደነፆር ዳንኤልና አናንያን አዛርያንና ሚሳኤልን ጨምሮ እጅግ ብዙ ነውር አልባ ሕጻናትን የከለዳውያንን ቋንቋና ጥበብ አስተምረዎ በፊቱ ያቆሙ ዘንድ አዝዞ ነበር። "ንጉሡም ነውር የሌለባቸውንና መልከ መልካሞቹን፥ በጥበብ ሁሉ የሚያስተውሉትን እውቀትም የሞላባቸውን ብልሃተኞችና አስተዋዮች የሆኑትን፥ በንጉሡም ቤት መቆም የሚችሉትን ብላቴኖች ከእስራኤል ልጆች ከነገሥታቱና ከመሳፍንቱ ዘር ያመጣ ዘንድ የከለዳውያንንም ትምህርትና ቋንቋ ያስተምሩአቸው ዘንድ ለጃንደረቦች አለቃ ለአስፋኔዝ ነገረ። " ዳን 1:34 እንዲል።

በዚያ ወራት ሕልም ዓይቶ መንፈሱ ስለታወከ ሕልሙ ጠፍቶበታልና እነዚህን ጥበበኞች አስጠርቶ ሕልሙንም ፍቺውንም አስታውቁኝ አላቸው።
ሕልሙንና ፍቺውን የሚነግረው ባጣ ጊዜ እየተንከባከበ ያኖራቸውን ጥበበኞች የሚባሉትን ይገድሉ ዘንድ አዘዘ። ዳንኤል በጥበብ ቃል ገዳዩ አርዮክን አናግሮ የሦስት ቀን ቀጠሮ እንዲሰጠው ከጠየቀ ኋላ ከሠለስቱ ደቂቅ ጋር ሱባኤ ገቡ።

"ወእምዝ ተከሥተ ሎቱ ለዳንኤል በራዕየ ሌሊት" ዳን 2:19

ከዚህ በኋላ ለዳንኤል ዕለቱን ተገለጠለት፤ ስለምን ቢሉ ጥሬ እንብላ በማለት ጨክኖ ነበርና ስለ ተገለጠለት ግን ዕለቱን አልወጣም ሱባዔ ለማስከበር ነው:: ለሠለስቱ ደቂቅ በሦስተኛው ቀን ተገልጦላቸዋል::

"ወአእኰቶ ዳንኤል ለአምላከ ሰማይ" እንዲል ሰማይን የፈጠረ እግዚአብሔርን እያመሰገነው "እግዚአብሔር ይዌልጥ ዓመታተ፣ ወመዋዕለ" በማለት በጋውን፡ በክረምት፣ ክረምቱን፡ በበጋ፣ ፄዋዌን፡ በሚጠት፡ የሚለውጥ፡ እሱ፡ ነው፧

አንድም፡ ማቴዎስን በማርቆስ፣ ማርቆስን በሉቃስ፣ ሉቃስን በዮሐንስ የሚለውጥ እሱ ነው።

አንድም፡ ዓመተ ደዌን በዓመተ ጥኢና፣ ዓመተ ጥኢናን በዓመተ ደዌ የሚለውጥ እሱ ነው።

አንድም:- ሌሊቱን በመዓልት መዓልቱን በሌሊት የሚለውጥ እሱ ነው።

አንድም፡ ሰኞን በማክሰኞ ማክሰኞን በረቡዕ የሚለውጥ እሱ ነው።

አንድም፡ መዋዕለ ሐዘንን በመዋዕለ ፍሥሐ መዋዕለ ፍሥሐን በመዋዕለ ሐዘን የሚለውጥ እሱ ነው።

እግዚአብሔር ጊዜያትንና ዘመናትን የሚለውጠው ለምንድነው ?

#የዘመናት ጌታቸው ዘመናትን የሚያፈራርቀው ለእኛ ጥቅም ነው እንጂ እርሱ አይለወጥም። ት.ሚል 3:6 እኔ እግዚአብሔር አልለወጥም። እንዲል የማይለወጥ እግዚአብሔር ዘመንን የሚሰጠን እኛ እንድንለወጥበት ነው።

በመዝ 101:27 "አንተሰ አንተ ክመ ወዓመትከኒ ዘኢየሃልቅ" አንተ ግን አንተ ነህ ዓመቶችህም አያልቁም ሲል የመልክዓ እግዚአብሔር አብ ደራሲም "እምቅድመ ዘመን ዘመናዊ ወድኅረ ዘመናት ሐዲስ፣ እንዘ ለዘመናት አንተ ሕገ ዛኅን ወመርስ" ከዘመናት በፊት ዘመናዊ ከዘመናት ኋላ አዲስ የዘመናት ጸጥታ፣ ረፍትና ወደብ እንዲሁም ሞገስ የሆነ እግዚአብሔር መሆኑን ያስረዳ ሲሆን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም "ልዩ ልዩ በሆነ እንግዳ ትምህርት አትወሰዱ ኢየሱስ ክርስቶስ ትላንትና፣ ዛሬ፣ እስከ ዘለዓለሙ ያው ነው" በማለት ለግዛቱ ወሰን ድንበር፣ ለምሥጋናው ሥፍር ቁጥር ፤ ለመንግሥቱ ፍጻሜ እንደሌለው አስረድቷል። ሰው ግን ጧት አስቀምጠውት ለማታ የማይገኝ ፣ ጠዋት የተናገረውን ለከሰዓት የማይደግም በመሆኑ ዘመን የማይቆጠርለት እግዚአብሔር አዲስ ዘመንን የሰጠን ለእኛ ጥቅም መሆኑን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ " ዘመን ላንተ ፣ስላንተ ነው። ዘመን አንተ ነህ በዘመኑ መልካም ብታደርግ ዘመኑ መልካም ይሆንልሃል ክፉም ብታደርግ ክፉ ይሆንብሃል። እንዲል

ዘመን ሲለወጥ እኛ ምን እናድርግ ?

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ " ያለፈው ዘመን እንደይበቃል" በማለት በርኵሰትና እግዚአብሔር የማይወድደውን ተግባር በመፈጸም ተቀያየምን ልንቀጥል፣ እንደ ተገፋፋን፣ እንደ ተጠላላን አዲሱን ዘመን ልንቀበለው አይገባንም።

"ምንተ ንግበር"

® አዲስ ሰው እንሁን ፣ ኤፌ 4:22 "ፊተኛ ኑሮአችሁን እያሰባችሁ እንደሚያታልል ምኞት የሚጠፋ አሮጌውን ሰው አስወግዱ" እንዲል

® ንስሐ እንግባ
ሚል 3:7 " ወደ እኔ ተመለሱ እኔም ወደ እናንተ እመለሳለሁ ይላል እግዚአብሔር " እንዲል

"እምድኅረ ሞቱ ለሰብእ አልቦቱ ንስሐ~> ሰው ከሞተ በኋላ ንስሐ የለውም" እንዲል ትርጓሜ ወንጌል መች እንደምንሞት አናውቀውምና ተዘጋጅተን ልንኖር ይገባናል።

"አልቦቱ ካልዕ ሕሊና ለአዳም ዘእንበለ ብካይ ላዕለ ኃጢአቱ= ለአዳም ስለኃጢአቱ ከማልቀስ በቀር ሌላ ሐሳብ አልነበረውም" {ትርጓሜ ወንጌል፣ ትርጓሜ ውዳሴ ማርያም } እንዲል

ንስሐ ሳይገባ የሞተን ሰው ነፍስ አጋንንት የገሐነም እጅ መንሻ ያደርጉታል። እንዲል ርቱዓ ሃይማኖት

=> ስንማር አልሰማ ለምንል ሰዎች "የምድርን አፈር በውኀ ብታጥባት በአፈር ላይ አፈር ትጨምራለህ እንጂ ልታነጻት አትችልም። እንዲሁ ሠነፍን በጥበብ ቃል ብትመክረው ልትለውጠው አትችልም" አባ ጊዮርጊስ

ልበ አምላክ ዳዊትም "ከመ መቃብር ክሡት ጎራዒቶሙ" መዝ 5:9 ፣13:4

✍️ የተጣላን እንታረቅ የበደልን እንካስ

ሳንታረቅ መጸለይ ጥቅም አልባ ያደርገናልና "ጸሎቱ ለመስተቀይም ኢ ውክፍት በቅድመ እግዚአብሔር ~> የቂመኛ ሰው ጸሎት በእግዚአብሔር ፊት ተቀባይነት የለውም" እንዲል ሳል ይዞ ስርቆት ቂም ይዞ ጸሎት እንዲሉ "የበደሉንን ይቅር እንደምንል ይቅር በለን" የምንል እኛ ማቴ 6:9 መታረቅ ይገባናል። ማቴ 5:2
ወንድሙን ጠልቶ እግዚአብሔርን ወድደዋለሁ የሚል ሐሰተኛ ነውና 1ዮሐ 4:20 ልንታረቅ ይገባል

® ሥጋ ወደሙን እንቀበል። ዮሐ 6:53-56

✔ #በመጨረሻም በ2017 ዓ.ም እንደኖርነው ሳይሆን በተሻለ መልኩ በመንፈሳዊነት ማማ ልንቆም ይገባናል። የኃጢአት ቀጠሮ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ጋር በፍቅስ ለመኖር ቀጠሮ መያዝ፣ ንስሐ ለመግባት፣ በልባችን መታደስ ለመለወጥ ስንቶቻችን ቀጠሮ ይዘን ይሆን? በአዲሱ ዘመን አዲስ ሰው እንድንሆን ቅዱስ ጳውሎስ "በክርስቶስ ኢየሱስ አዲስ ሰው መሆን ይጠቅማል" ገላ 6:15 በማለት ይናገራልና አዲስ ሰው የመሆን ጥቅሙ አዲሲቱን ሰማይና አዲሲቱን ምድር ለመውረስ ነው። ራዕ 21:1

። አሜን!!!

#ቅድስት ሀገሬ ኢትዮጵያ!!!

#የወለድሻቸው ልጆችሽ ይውለዱሽ!!!

#ልጆችሽ ይሟገቱልሽ እንጂ አይሞግቱሽ!!!

#በስደት ያሉ ልጆችሽ በበረከት ይመለሱልሽ!!!

#ድንበርሽን እሳት መሀልሽን ገነት አድርጐ የዓለም ማረፍያ ያድርግሽ #አሜን
‎ መልአከ ምሕረት አባ ገብረመድኅን ንጉሤ (ቆሞስ)
‎ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራአስኪያጅ
‎--------------------------------------------------
ጳጕሜ 5-2017 ዓ.ም አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ብፁዕ ወቅዱስ  አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ምርቃትን አስመልክቶ የደስታ መግለጫ መልዕክት አስተላለፉ።የቅዱስነታቸው መልእክት የሚከተለው ነው።በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱ...
09/09/2025

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ምርቃትን አስመልክቶ የደስታ መግለጫ መልዕክት አስተላለፉ።
የቅዱስነታቸው መልእክት የሚከተለው ነው።

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

‹‹ወስሙ ለካልእ ፈለገ ግዮን ወውእቱ ዘየዐውድ ኵሎ ምድረ ኢትዮጵያ፦
"የሁለተኛውም ወንዝ ስም ግዮን ነው፤ እርሱም የኢትዮጵያን ምድር ሁሉ ይከብባል " (ዘፍ 2+13)

ኢትዮጵያ የሚለው ስም ጽርዓዊ፣ ደኃራዊ ስም ሲሆን ቀደም ሲል የኖኅ የልጅ ልጅ በሆነው በኵሽ ምክንያት የኵሽ ምድር እንዲሁም ምድረ አዜብ፣ ምድረ ሳባ፣ ምድር ኣግዐዚት በመባል ተጠርታለች፡፡ ለዘመናት ኢትዮጵያን ቋሚ አድርገው ካቆዩ ዐምዶች መካከልም ፈለገ ግዮን የተባለው የዓባይ ወንዝ እና ‹‹ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኀበ እግዚአብሔር- ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች›› (መዝ. 67÷31) የሚለው የተስፋ ቃል እንደሆነ የታመነ ነው፡፡ በመሆኑም በመግቢያችን ላይ ባነሳነው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የኢትዮጵያ ትእምርት ተደርጎ የተጠቀሰው ፈለገ ግዮን በእኛ ዘመን ለሕዝቡ ብርሃን እያበራ አገልግሎት መስጠት የሚችልበት ሁኔታ ተፈጥሮ በማስከተልም የዛሬዋን ቀን በመናፈቅ የግድቡ ግንባታ ከተጀመረበት ዕለት አንስቶ አቅማችሁ የፈቀደውን ሁሉ ለዚህ ሥራ በማዋጣት ታሪክ በመልካም የሚያስታውሰውን ዋጋ የከፈላችሁ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት ልጆቻችንን እንኳን ደስ አላችሁ! ለማለት እንወዳለን፡፡

በመጨረሻም የታላቁ ሕዳሴ ግድብ መጠናቀቅ ወደቀጣይ የልማት ሥራ የሚያሸጋግር እንዲሆን፤ ከምንም በላይ _ ሰላም በምድራችን ላይ እንዲስፍን ሕዝባችንም እግዚአብሔር የሰጠው በነፃነት የመኖር መብት ተከብሮለት የልማቱን በረከት መሳተፍ እንዲችል ሁሉም ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በትኩረት ሊሠሩ ይገባል ስንል አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!! አሜን።

አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
ጳጉሜን 4 ቀን 2017 ዓ.ም.

 #ርእሰ ዐውደ ዓመት  #የአዲስ ዘመን መጀመሪያ📜ዘመን የመስጠትና የመንሳት የማዳንና የማሳመም ሥልጣን የለውም፡፡𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪በላእከ ወንጌል በእደ ማር...
09/09/2025

#ርእሰ ዐውደ ዓመት #የአዲስ ዘመን መጀመሪያ
📜ዘመን የመስጠትና የመንሳት
የማዳንና የማሳመም ሥልጣን የለውም፡፡
𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪𓆩♱𓆪
በላእከ ወንጌል በእደ ማርያም ይትባረክ
የሀገረ ስብከቱ የትምህርት ሥርጭት ሐላፊ

በኢትዮጵያ ያለፈው ዓመት አልቆ የሚተካው የሚጀመርበት መስከረም አንድ ቀን ስለሆነ በቤተክርስቲያናችን ሥርዓት መሠረት ርእሰ ዐውደ ዓመት ይባላል፡፡ ዘመን ሲያልፍ ዘመን ይተካል፡፡ ትውልድም ሲያልፍ ትውልድ ይተካል፡፡ ለኅልፈትና ለውላጤ የተፈጠረ ፍጡር ሁሉ ወቅትና ጊዜ አለው፡፡ በዚያው በተሰጠው ዘመን ሁሉም ሥራውን ያከናውናል አከናውኖም ያልፋል ያለሥራ የተፈጠረ ፍጡር የለምና፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ፍጥረታትን ፈጥሮ ሲፈጽም “ወርእየ እግዚአብሔር ኵሎ ዘገብረ ከመ ጥቀ ሠናይ” (እግዚአብሔር አምላክ የፈጠረው ፍጥረት ሁሉ መልካም እንደሆነ አየ) ይላል /ዘፍ. 1፥31/ ይህም የሚያስረዳው የተፈጠረው ፍጥረት ሁሉ ያለ አገልግሎት የተፈጠረ አለመሆኑን ነው፡፡
በሰው ዘንድ እግዚአብሔር ከፈጠራቸው ፍጡራን መካከል የሚወደዱና የሚጠሉ ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ በአምላክ ዘንድ ግን ሁሉም ፍጥረታት የተወደዱ ናቸው፡፡ ይህንንም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲያስረዳ “እግዚአብሔር የፈጠረው ሥነ-ፍጥረት ሁሉ ያማረና የተወደደ ነው ምንም የሚጣል የለውም ብሏል” /1ኛ ጢሞ. 4፥4/
እግዚአብሔር ፈጥሮ አይጥልም፣ አይረሳም፣ አይዘነጋምም ፍጥረቱን ሁሉ በመግቦቱ ተንከባክቦ ጠብቆ እስከ ወሰነለት ጊዜ ያኖረዋል፡፡ በይበልጥ ለሰው የሚያደርገው ልግስና የሚሰጠው ጸጋ፣ ጥበብ ከሌላው ፍጥረት በእጅጉ የላቀ ነው፡፡

በምግብ በልብስ እንዳይቸገር ከማድረጉም ሌላ ዘመኑን የሚሰፍርበትና የሚቆጥርበትም አዘጋጅቶ እንዲጠቀም ማስተዋልን ሰጥቶታል፡፡ ስለዚህ ሰከንዱን በደቂቃ፣ ደቂቃውን በሰዓት፣ ሰዓቱን በቀን፣ ቀኑን በሳምንት፣ ሳምንቱንም በወር፣ ወሩን በዓመት እያጠቃለለ ምድራዊ ሕይወቱን ከማገባደድ ይደርሳል፡፡ ከዚህም የተነሳ ከላይ እንደተገለጸው አንዱ ዓመት አልፎ ሌላው ሲተካ ርእሰ ዐውደ ዓመት የዓመት መጀመሪያ ይባላል፡፡

በኢትዮጵያ የዘመን አመዳደብ ዘመናቱ አራቱን ክፍላተ ወንጌል በጻፉት በአራቱ ወንጌላውያን ስም እንዲጠሩ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ወስነዋል፡፡ ወንጌላውያኑም ማቴዎስ ማርቆስ ሉቃስና ዮሐንስ ናቸው፡፡ ከእነርሱም ማቴዎስና ዮሐንስ ከአስራ ሁለቱ ሐዋርያት መካከል ሲሆኑ ማርቆስና ሉቃስ ከሰባ ሁለቱ አርድእት ናቸው፡፡
በኢትዮጵያችን የዓመቱ መጀመሪያ የሚጠራው ቅዱስ ዮሐንስ እየተባለ ነው፡፡ ወንጌላውያን ግን በየዓመቱ ይፈራረቃሉ ድርሻቸውም ማቴዎስ ማርቆስ ዮሐንስ 365 ቀን ሲሆን የሉቃስ 366 ቀኖች ይሆናሉ፡፡ በዓመቱ መጀመሪያ ቀን በቤተክርስቲያን በእውቀት ከፍተኛ ደረጃ ያላቸው ሊቃውንት የበዓላትና የአጽዋማትን ቀኖች ለምእመናን የሚያሰሙበት ዕለት በመሆኑ “ርእሰ ዐውደ ዐመት ወላዴ መጥቅዕ ወአበቅቴ” ዮሐንስ የዓመቱ መጀመሪያ የመጥቅዕና የአበቅቴ አስገኝ ነው ተብሎ ተጽፏል፡፡

መጥቅዕ የበዓላትና የአጽዋማት ማውጫ ሲሆን አበቅቴ ደግሞ ከሠርቀ መዓልትና ከሕፀፅ ጋር ተደምሮ የሌሊት ማውጫ ነው፡፡ በዚህ ርእሰ ዐውደ ዓመት ዕለት ልብ አድርገን ልንመለከተው የሚገባ ዐቢይ ነገር አለ፡፡ ይኸውም ከዓመት እስከ ዓመት የሠራነውን ሥራ ነው፡፡
ዘመን ፍጡራንን ሁሉ የሚያታግል የትግል መስክ ነው፡፡ እርስ በእርሳቸው የሚታገሉ ሰዎች ሁለቱም የድል ባለቤቶች ሊሆኑ አይችሉም፡፡ አንድ ጊዜ የማሸነፍ ሌላ ጊዜ ደግሞ የመሸነፍ ዕድል ሊገጥማቸው ይችላል፡፡ ግን አንድ ጊዜ ተሸነፍኩኝ ብሎ ተስፋ መቁረጥ ተገቢ አይደለም፡፡ ምን ጊዜም ቢሆን እግዚአብሔርን ረዳትና አጋዥ አድርጎ ለመልካም ነገር መጣርና መታገል ያስፈልጋል፡፡
በዚህ ዓለም ጠንክሮ ካልታገሉ ሥጋዊ ኑሮን አሸንፎ በሰላምና በደስታ ለመኖር አይቻልም፡፡ ሰው በሕይወተ ሥጋ እስከአለ ድረስ ጠንክሮ የመሥራት ግዴታ አለበት፡፡ ዘመን አልፎ ዘመን ሲተካ እጅን አጣምሮ እግርን ኮርትሞ ቢመለከቱት ለውጥ አይገኝም፡፡

ዘመን የሥራን፣ የንቃትና የትጋትን፣ የፍቅርንና የሰላምን ተሳትፎ በብርቱ ይጠይቃል፡፡ ዘመን አልፎ ከሄደ በኋላ አይመለስም አስቀድሞ የተዘጋጀ ብቻ አብሮት ለመራመድ ይችላል፡፡
በዘመን የማይለወጥ ነገር የለም ዛሬ ያገኘው ነገ ያጣል ዛሬ ያጣው ነገ ያገኛል፡፡ ዛሬ በጽኑዕ የታመመው በሽተኛ ጥቂት ቀን ሰንብቶ ሊፈወስ ይችላል፡፡ ዛሬ ጤነኛ ነኝ የሚለው ከጊዜ በኋላ ደግሞ በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ ተይዞ ሊጨነቅ ይችላል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ችግር በደረሰ ጊዜ ዘመን አመጣብን ብሎ በዘመኑ ማመካኘት አይገባም፡፡ ዘመን የመስጠትና የመንሳት የማዳንና የማሳመም ሥልጣን የለውምና፡፡

ሁሉም ያለፈጣሪ ሊፈጸም አይችልም፡፡ ዘመናትም ሆኑ ሌሎች ፍጥረታት ያለ እግዚአብሔር ፈቃድ የደስታም ሆነ የችግር ምክንያቶች ለመሆን አይችሉም፡፡ ያለፈው ዓመት በጅቷቸው በዐውደ ዓመቱ የሚደሰቱ ሲኖሩ ዘመኑ ከፍቶባቸው እያዘኑ ያለፈውን ዘመን መልሰህ አታምጣብን የሚመጣውን ዘመን የደስታ አድርግልን በማለት እግዚአብሔር አምላክን የሚማጸኑ አሉ፡፡

አሳቡ መልካም ነው፡፡ ሁሉም ያለ እርሱ ፈቃድ አይሆንምና ለደስታም ሆነ ለኀዘን ለብልጽግናም ሆነ ለድህነት ምንጩ ዘመን እንደሆነ አድርገው የሚናገሩ አንዳንድ ሰዎች አይታጡም፡፡
ዘመን ግን ታዛዥ እንጂ አዛዥ አይደለም፡፡ ዘመን ለሰው ልጆች የሥራ መሥሪያ እንዲሆን ከእግዚአብሔር የተሰጠ በመሆኑ በሰው ላይ መጥፎ ነገርን እንዲያመጣ የተፈጠረ አይደለምና፡፡
“ያለፈው ዘመን አልሆነኝም ይህ ዘመን ግን ይሆነኛል በይበልጥ ደግሞ ከርሞ የሚመጣው ክፍሌ ነው” እያሉ ራሳቸውን በራሳቸው የሚደልሉ አንዳንድ ሰዎች መኖራቸው አያጠራጥርም፡፡
ይህ ሁሉ ከንቱ አስተሳሰብ ስለሆነ እግዚአብሔርን ረዳት አድርጎ ሳይጠራጠሩ ጠንክሮ መሥራት ከማንኛውም ችግር ሊያድን ይችላል፡፡

አሮጌው ዘመን አልፎ አዲሱ ሲተካ ባለፈው ዘመን የሠሩትን ሥራ ማስተዋል ያስፈልጋል፡፡ የሰነፈ ቢኖር ባለመሥራቱ ተጸጽቶ ለወደፊቱ ጠንክሮ ለመሥራት ታጥቆ መነሣት አለበት፡፡ ክፉ ሥራ ሠርቶ ከእግዚአብሔር አንድነት የተለየ ቢኖርም ንስሓ ገብቶ ወደ ፈጣሪው ለመቅረብ መዘጋጀት ይኖርበታል፡፡ ይህንንም በሚመለከት ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “ኃጢአት የሠራችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃል” /1ኛ ጴጥ. 4፥3/ በማለት ተናግሯል፡፡

በዚህ መሠረት ዘመን ሲለወጥ እኛም መለወጥ አለብን፡፡ ርእሰ ዐውደ ዓመት ተብሎ የተሰየመውን የዓመት መጀመሪያ ስናከብር አዲሱን ዘመን የሰላም፣ የፍቅር፣ የበረከትና የደስታ ዘመን እንዲያደርግልን እግዚአብሔርን በመለመን ነው፡፡
በአዲሱ ዘመን ከእስካሁኑ የተሻለ ሥራ ሠርተን በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት እንዲሁም በቅዱሳን አማላጅነት መንግሥተ ሰማያትን እንድንወርስ ልዑል እግዚአብሔር ወሰን በሌለው ቸርነቱ ይርዳን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር!!! አሜን።

🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚

#ስለአንዲት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን"

በፌስቡክ https://www.facebook.com/AddisAbabaDiocese?mibextid=2JQ9oc

ከዚህ በተጨማሪ በሌሎች የበይነ መረብ አማራጮች ለመከታታል
በቴሌግራም: https://t.me/AddisAbabaDiocese
በዋትስ አፕ: https://whatsapp.com/channel/0029VaJznc90rGiNUScgwn3U
በዩቱዩብ: http://www.youtube.com/
በቲውተር: https://twitter.com/AADioceseMedia/media
በቲክቶክ:http://tiktok.com/
መጠቀም ይችላሉ።

 #የጳጒሜን ቅዱስ ሩፋኤል በዓል በአየር ጤና መካነ ስብሐት ቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ፎቶ:- ሪፖርታዥዲ/ን ቅዱስ ጥበቡበረከት ኃይለ ሚካኤል  የመልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል ጥበቃው አይለየን!
08/09/2025

#የጳጒሜን ቅዱስ ሩፋኤል በዓል በአየር ጤና መካነ ስብሐት ቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን

ፎቶ:- ሪፖርታዥ

ዲ/ን ቅዱስ ጥበቡ
በረከት ኃይለ ሚካኤል

የመልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል ጥበቃው አይለየን!

የመልአኩ የቅዱስ ሩፋኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል በቢሾፍቱ ደብረ ዘይት ቅዱስ ሩፋኤል ካቴድራል ብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ አቡነ ዲዮስቆሮስና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በድምቀ...
08/09/2025

የመልአኩ የቅዱስ ሩፋኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል በቢሾፍቱ ደብረ ዘይት ቅዱስ ሩፋኤል ካቴድራል ብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ አቡነ ዲዮስቆሮስና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በድምቀት ተከብሮ ዋለ፡፡

ጳጒሜን ፫/፳፻፲፯ ዓ/ም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ

በወርኀ ጳጉሜን ከሚታሰቡ እና ከሚከበሩ በዓላት መካከል በየዓመቱ ጳጕሜን 3(፫) ቀን የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሩፋኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል በቢሾፍቱ ደብረ ዘይት ቅዱስ ሩፋኤል ካቴድራል ፣ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊ የራያ ሀገረስብከት ሊቀጳጳስ የቅርስ ጥበቃናየማህበራት ማደራጃ የበላይ ኃላፊ: ብፁዕ አባታችን አቡነ ጎርጎርዮስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳምና ሥራ አመራር መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ የቅዱስ ሲኖዶስ ቋሚ አባል እንዲሁም የኢትዮጵያ ሃይማኖቶች ተቋማት የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ ሰብሳቢ ፣ ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ መሥራችና የበላይ ኃላፊ፣ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ሰብሳቢ፤ በተገኙበት በታላቅ ድምቀት ተከብሯል።

በዓሉን አስመልክተው ስብሐተ እግዚአብሕር በካቴድራሉ ሊቃውንትና የሰንበት ዘማሪያን ያሬዳዊ ወረብ አቅርበዋል። ቀጥሎም የካቴድራሉ ዋና መልአከ ሰላም ቆሞስ አባ ወልደ ሩፋኤል ባለፉት ወራት የተሠሩ የልማት ሥራዎች እንዲሁም ሐምሌ 28 ቀን በከፍተኛ ዝናም ምክንያት ስለደረሰው ጉዳት የመልሶ ማቋቋሙን ሂደት በቀጣይ በዕቅድ ስለሚሠራው ግልፅና አጭር ሪፖርት አቅርበዋል ።

በመቀጠል በብፁዕ አባታችን አቡነ ጎርጎርዮስ መልካም ፈቃድ :- ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ "የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙርያ ይሠፍራል፤ ያድናቸውማል›› (መዝ. ፴፬፥፯) ላይ ያለውን መነሻ ቃል በማድረግ በዓሉን የዳሰሰ ትምህርተ ወንጌል አስተምረዋል።

በመጨረሻም በአረጋዊው አባት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል።

በክብረ በዓሉም ላይም:- የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት የየመምሪያ ክፍል ኃላፊዎች ፡ ክቡር መልአከ ሣህል ቀሲስ ነጋሽ ሀብተ ወልድ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የሀገረ ስብከቱ የየመምሪያ ክፍል ኃላፊዎች ፡ የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች ፡ ሊቃውንት ፡ የሰ/ት/ቤት ዘማርን በርካታ ኦርቶዶክሳውያን ምዕመናን ተገኝተዋል ።
©ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ

🔵የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ
ስለ አንዲት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን

🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚 https://www.facebook.com/AddisAbabaDiocese?mibextid=2JQ9oc

ከዚህ በተጨማሪ በሌሎች የበይነ መረብ አማራጮች ለመከታታል
በቴሌግራም: https://t.me/AddisAbabaDiocese

በዩቱዩብ: http://www.youtube.com/

በቲውተር: https://twitter.com/AADioceseMedia/media
በቲክቶክ:http://tiktok.com/
መጠቀም ይችላሉ።

  በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በጉለሌ ጽርሐ አርያም ቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ የምሥራቅ ጉራጌ ሀገረ ስብከት ጳጳስ በተገኙበት በድምቀት ተከብሯል።ከብፁዕነታቸው ጋ...
08/09/2025


በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በጉለሌ ጽርሐ አርያም ቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ የምሥራቅ ጉራጌ ሀገረ ስብከት ጳጳስ በተገኙበት በድምቀት ተከብሯል።

ከብፁዕነታቸው ጋር መልአከ ምሕረት አባ ገብረ መድኅን ንጉሤ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ መጋቤ ስብሐት ዐቢይ ዘለቀ የብፁዕ ሊቀ ጳጳስ ልዩ ጸሐፊ፣የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ በርካታ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ምእመናን ተገኝተዋል።

ፎቶ፦ ©ቅዱስ እግዚአብሔር ፔጅ
የመልአከ ቅዱስ ሩፋኤል ጠበቃው አይለየን።

🔵የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ
ስለ አንዲት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን

🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚 https://www.facebook.com/AddisAbabaDiocese?mibextid=2JQ9oc

ከዚህ በተጨማሪ በሌሎች የበይነ መረብ አማራጮች ለመከታታል
በቴሌግራም: https://t.me/AddisAbabaDiocese

በዩቱዩብ: http://www.youtube.com/

በቲውተር: https://twitter.com/AADioceseMedia/media
በቲክቶክ:http://tiktok.com/
መጠቀም ይችላሉ።

የመርካቶ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን አንቀጸ ብርሃን ሰ/ት ለተከታታይ ዓመታት ያስተማራቸውን ደቀ መዛሙርት ብፁዕ አቡነ በርናባስ ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት አስመረቀ።ጳጒሜን ፫/፳፻...
08/09/2025

የመርካቶ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን አንቀጸ ብርሃን ሰ/ት ለተከታታይ ዓመታት ያስተማራቸውን ደቀ መዛሙርት ብፁዕ አቡነ በርናባስ ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት አስመረቀ።

ጳጒሜን ፫/፳፻፲፯ ዓ/ም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ

በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የመርካቶ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ቤተክርስቲያን አንቀጸ ብርሃን ሰንበት ት/ቤት ለአራት ተከታታይ አመታት ያስተማራቸውን ደቀ መዛሙርት ብጹዕ አቡነ በርናባስ የዋግኽምራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት ጳጉሜን 02/2017 ዓ.ም አስመርቋል።

አንቀጸ ብርሃን ሰንበት ት/ቤት ላለፉት ሦስት አስርት አመታት ገደማ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ወጣቶችን መሠረታዊ የቤተክርስቲያን ትምህርቶችን በማስተማር ለአገልግሎት እያበቃ እንደሚገኝ ይታወቃል።

በዚህ ተልዕኮ ለባለፉት አራት አመታት ሲማሩ የቆዩ 74 ደቀመዛሙርትን ብፁዕ አቡነ በርናባስ የዋግኽምራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ኃይል ቆሞስ አባ ገ/ሥላሴ በላይ፣ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን የተመራቂ ተማሪዎች ቤተሰቦችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት አስመርቋል።

በተጨማሪም በዕለቱ በአምስተኛ ዓመት የትምህርት መርሐግብር ኦርቶዶክሳዊ ትምህርተ መለኮት መግቢያን፣ ንጽጽራዊ ትምህርተ መለኮትን እንዲሁም ዕብራውያን ትርጓሜን የተከታተሉ ደቀ መዛሙርት ተመርቀዋል።

ደቀመዛሙርቱን ለዚህ ላበቁ መምህራንም በብጹዕ ሊቀጳጳሱ በኩል የምስጋና ስጦታ ተበርክቷል።

የዕለቱ የክብር እንግዳ ብፁዕ አቡነ በርናባስ የዋግኽምራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተመራቂ ተማሪዎች የተማሩትን በማሳደግ ዕቅብተ ዕምነት ላይ በትኩረት እንዲሠሩ አሳስበዋል።

የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ኃይል ቆሞስ አባ ገ/ሥላሴ በላይ በበኩላቸው ተመራቂ ደቀመዛሙርት ትምህርቱን በመቀጠል በሰንበት ትምህርት ቤትና በተለያዩ መስኮች ማገልገል እንደሚገባቸው አመልክተዋል።

በምርቃት መርሐግብሩ ማጠቃለያ በደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ኃይል ቆሞስ አባ ገ/ሥላሴ በላይ አስተባባሪነት ለዋግኽምራ ሀገረ ስብከት 10 አብያተ ክርስቲያናት የሚውል የመቀደሻ ልብስ ልብሰ ተክህኖ ድጋፍ ተደርጓል።
©አንቀጸ ብርሃን ሚዲያ

🔵የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ
ስለ አንዲት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን

🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚 https://www.facebook.com/AddisAbabaDiocese?mibextid=2JQ9oc

ከዚህ በተጨማሪ በሌሎች የበይነ መረብ አማራጮች ለመከታታል
በቴሌግራም: https://t.me/AddisAbabaDiocese

በዩቱዩብ: http://www.youtube.com/

በቲውተር: https://twitter.com/AADioceseMedia/media
በቲክቶክ:http://tiktok.com/
መጠቀም ይችላሉ።

 #የጳጒሜን ቅዱስ ሩፋኤል በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት የቃሊቲ ሠፈረ ሰላም ቅድስት አርሴማ እና ቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ዓመታዊ የቅዱስ ሩፋኤል ...
08/09/2025

#የጳጒሜን ቅዱስ ሩፋኤል
በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት የቃሊቲ ሠፈረ ሰላም ቅድስት አርሴማ እና ቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ዓመታዊ የቅዱስ ሩፋኤል ክብረ በዓል

🔵የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ
ስለ አንዲት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን

🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚🎚 https://www.facebook.com/AddisAbabaDiocese?mibextid=2JQ9oc

ከዚህ በተጨማሪ በሌሎች የበይነ መረብ አማራጮች ለመከታታል
በቴሌግራም: https://t.me/AddisAbabaDiocese

በዩቱዩብ: http://www.youtube.com/

በቲውተር: https://twitter.com/AADioceseMedia/media
በቲክቶክ:http://tiktok.com/
መጠቀም ይችላሉ።

Address

4Kilo
Addis Ababa

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ አገልግሎት/Addis Ababa Diocese Media Service posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ አገልግሎት/Addis Ababa Diocese Media Service:

Share

Category