የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/

  • Home
  • Ethiopia
  • Addis Ababa
  • የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/

የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/ is a Facebook social networking site based on the Doctrine and Canon of the EOTC.
(1)

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የመገናኛ ብዙኃን ሥርጭት አገልግሎት ድርጅት
/ Ethiopian Orthodox Tewahedo Church Broadcasting Service Agency/

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብዙኃን መገናኛ አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት የ2017 ጉዞውን ገመገመ(  ሐምሌ 22 ቀን 2017 ዓ.ም)ላዕከ ዜና አስቻለው ሽፈራው++++++++++...
29/07/2025

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብዙኃን መገናኛ አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት የ2017 ጉዞውን ገመገመ

( ሐምሌ 22 ቀን 2017 ዓ.ም)

ላዕከ ዜና አስቻለው ሽፈራው

+++++++++++++++++++++++++++++++++++++

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብዙኃን መገናኛ አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት ዓመታዊ የግምገማና ሥልጠና መርሐ ግብር አካሄደ ።

በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ዩኒቨርስቲ ለሁለት ቀናት በተካሄደው መርሐ ግብር የኢኦተቤ ቴቪ (EOTC TV) እና የአፋን ኦሮሞ ሚዲያ ኔትዎርክ (AON) የ2017 ሪፖርት እና የ2018 ዕቅድ ቀርቦ ውይይት ተደርጓል ።

መርሐ ግብሩ በብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብዙኃን መገናኛ አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት የበላይ ኃላፊ ፣ የሰሜንና ምሥራቅ አፍሪካ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ጸሎት የተከፈተ ሲሆን፣ ብፁዕነታቸው ጉባኤውን እየመሩ በሪፖርትና ዕቅዱ ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጓል ።

በመርሐ ግብሩ ላይ በመገናኛ ብዙኃን ድርጅቱ በበጀት ዓመቱ የነበሩ ክንውኖች፣ ስኬቶችና ክፍተቶች በየሥራ ክፍሎች በዝርዝር ቀርበው ሰፊ ውይይት ተካሂዶባቸዋል።

ውይይቱን ተከትሎም ብፁዕነታቸው በሰጡት አባታዊ የሥራ መመሪያ ፣ የመገናኛ ብዙኃን ድርጅቱ ያላሻሻላቸው የሙያና የአስተዳደር ክፍተቶች አሁንም መኖራቸውን ጠቅሰው፣ በቀጣዩ የሥራ ዓመት እነዚህ ክፍተቶች እርምት ሊወሰድባቸው እንደሚገባ አሳስበዋል። ውይይትና ግምገማው ቀጣይነት እንዳለውም ለተሰብሳቢዎች አሳውቀዋል።

በመርሐ ግብሩ ላይ መምህር ዶክተር አካለወልድ ተሰማ የመገናኛ ብዙኃን ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ ኦርቶዶክሳዊነት በዓለም ላይ እየገጠመው ስላለው ፈተናና ፣ ቤተ ክርስቲያን ትልቅ ኃላፊነት የሰጠቻቸው የቤተ ክርስቲያን ሚዲያዎች ስለሚጠበቅባቸው ድርሻ አብራርተዋል ።

በተጨማሪም መጋቤ ሐዲስ ለማ በየነ የአፋን ኦሮሞ ኔትዎርክ ዋና ሥራ አስኪያጅ ቴሌቭዥን ጣቢያው ከአፋን ኦሮሞ ጋር በስምንት የአገር ውስጥ ቋንቋዎች ሥርጭቱን በውጭ ላሉ ተመልካቾች ጭምር ተደራሽ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰው፣ በቀጣይ ቴሌቭዥን ጣቢያውን በሙያና ቴክኖሎጂ ለማሳደግ በአስተዳደሩ በኩል ያለውን ፍላጎትና ዝግጁነት ገልጸዋል ።

በጉባኤው ሁለተኛ ቀን በዘመናዊ የሚዲያ አሠራርና በተቋማዊ ለውጥ ላይ ያተኮረ ሥልጠና፡ የአስተዳደርና ሥራ አመራር መምህር በሆኑት ዶክተር ግርማ መኮንን በስፋት ተሰጥቷል።

እንዲሁም በአገር ውስጥና በዓለም አቀፍ ታላላቅ የቴሌሽዥን ጣቢያዎች ሰፊ ልምድ ያላቸው ባለሙያዎች ተገኝተው ለሁለቱም የቴሌቭዥን ጣቢያዎች ዕውቀትና ልምዳቸውን በስልጠና አካፍለዋል።

የጉባኤው ተካፋዮች በስልጠናው ላይ የቀረቡት ሙያዊና አስተዳደራዊ ትምህርቶች ሰፊ ልምድ የቀሰሙበት እንደነበር በሰጡት አስተያየት ገልጸዋል ።

የሃይማኖት ተቋማት በአየር ንብረት ለውጥ  ጉዳይ ተሰባሰቡ(  ሐምሌ 22 ቀን 2017 ዓ.ም)ሪፖርተር  ሙሉቀን ሐሰን+++++++++++++++++++++++++++++++++++++በኢትዮጵያ ኦርቶ...
29/07/2025

የሃይማኖት ተቋማት በአየር ንብረት ለውጥ ጉዳይ ተሰባሰቡ

( ሐምሌ 22 ቀን 2017 ዓ.ም)

ሪፖርተር ሙሉቀን ሐሰን

+++++++++++++++++++++++++++++++++++++

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ከ ACT Alliance እና consortium of climate change Ethiopia(CCCE) ከተባሉ ትቋማት ጋር በመሆን የሃይማኖት ተቋማትን ያሰባሰበ መድረክ አዘጋጁ። መድረኩ በመጪው ጳጉሜን 2017 ዓ/ም በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ላይ ይመክራል ተብሎ ለሚጠበቀው አህጉር አቀፍ ገባኤ የሃይማኖት ተቋማትን ሃሳብና አስትያየት በግብአትነት ለማካተት ያለመ እንደሆነ ታውቋል ።

አዲስ አበባ ላይ በተካሄደው ስብሰባ የልዩ ልዩ ሐይማኖት ተቋማት የተወከሉ መሪዎች ተሳትፈዋል። በተጨማሪም አቶ ገብረ ሥላሴ አብርሃ የኮሚሽኑ የልማት መምሪያ ምክትል ኃላፊ፣ አቶ ተዋነይ ሠይፈ ሥላሴ የልማት ኮሚሽኑ የሰላምና አድቮኬሲ መምሪያ ኃላፊ እንዲሁም ከአፍሪካ የተውጣጡ ባለድርሻዎችን ጨምሮ የተለያዩ አካላት ተገኝተዋል

‎መድረኩ የሃይማኖት ተቋማት የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ ለመቋቋም ያላቸውን ሰፊ ልምድና ሚና በማሳይት የተሻለ ተጽኖ ፍጣሪ መሆናቸውን ለማስገነዘብ የሚረዳ እንድሆነም ተገልጿል።

ስምከ ሕያው ዘኢይመውት(ከ፲፱፻፴፪ - ፲፱፻፹፪ ዓ.ም)መ/ር ጌታቸው በቀለ( )+++++++++++++++++++++++++++++++++++++“ሰው የተመኘውን ከሠራ የሚጠብቀው ሞቱን ነው” የሚሉት...
29/07/2025

ስምከ ሕያው ዘኢይመውት
(ከ፲፱፻፴፪ - ፲፱፻፹፪ ዓ.ም)

መ/ር ጌታቸው በቀለ

( )

+++++++++++++++++++++++++++++++++++++

“ሰው የተመኘውን ከሠራ የሚጠብቀው ሞቱን ነው” የሚሉት ታላቁን የቤተክርስቲያን አባት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሐምሌ ፳፪ ቀን ፲፱፻፹፪ ዓ.ም ዐረፉ፡፡ ዘንድሮ ፳፻፲፯ ዓ.ም ፴፭ኛ ዓመታቸው ነው፡፡ ጥቂት ስለ ብፁዕነታቸው፡-
መልካሙ ሥራቸው እንደ አጥቢያ ኮከብ ዘወትር ሲያበራ ከሚኖሩት አበው መካከል አንዱ የሆኑት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ በ፲፱፻፴፪ ዓ.ም በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት በደሴ ከተማ ከአባታቸው ከአቶ ገበየሁ እሰየና ከእናታቸው ከወ/ሮ አሰለፈች ካሣ ተወለዱ፡፡ ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ በደሴ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ሲማሩ ቆይተው፤ ወደላቀ የትምህርት ደረጃ ለመሸጋገርና ፍላጎታቸውን ከዳር ለማድረስ ወደ ላስታ በመሄድ አባ ብሩክ ገዳም ገቡ፡፡ ከዚያም በተለያዩ ቦታዎች እየተዘዋወሩ ትምህርታቸውን በመቀጠል ዕውቀታቸውን አስፋፍተዋል፡፡
በ፲፱፻፶፪ ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ መጥተው በዳግማዊ ምኒልክ መታሰቢያ ቤት ታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም ከመጋቤ ምሥጢር ጌራወርቅ የዳዊትን ትርጓሜ፣ በደብረ ሊባኖስ ገዳም የሐዲስ ኪዳን ትርጓሜን፣ መጽሐፈ ሊቃውንትን ከመ/ር ቢረሳው ተምረዋል፡፡ ትርጓሜ መጻሕፍት ያስተማሯቸው አባ ክፍሌ ቀለም በፍጥነት የመያዝ ችሎታቸውን ለመግለጽ “መዝገበ ሥላሴ” የሚል ስም አውጥተውላቸዋል። ማዕረገ ዲቁናን ከወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ ወደ አዲስ አበባ መጥተው በታዕካ ነገሥት በኣታ ለማርያም ገዳም ሐዲሳትን ተማሩ። በደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንድነት ገዳም መዓርገ ምንኩስና ተቀብለዋል፡፡ ወደ አዲስ ዓለም በመሄድም ከመምህር አፈ ወርቅ መንገሻ ቅኔን ከእነ አገባቡ ወደ ደብረ ሊባኖስ ተመልሰው መምህር ፍሥሓ ከተባሉ ሊቅ የሐዲሳትን ትርጓሜና ትምህርተ ሃይማኖትን፣ መምህር ቢረሳው ከተባሉ ሊቅ ደግሞ መጽሐፈ ሊቃውንትን ወደ ደብር ቅዱስ ደብረ ጽጌ ማርያም ተጉዘው ከመምህር ገብረ ሕይወት የሐዲሳትን ትርጓሜና ቅዳሴን አደላድለው ተመርቀዋል።

ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ መዓርገ ቅስናን ተቀብለዋል። ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት ወደ ሐረር ተልከው ሕዝቡን እያስተማሩ ጎን በጎን የ፩ኛ የ፪ኛ ደረጃ ዘመናዊ ትምህርታቸውን በጥሩ ውጤት አጠናቀቁ።የቁልቤ ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አስተዳዳሪ በማድረግ የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳዳር ሾማቸው ለ፪ ዓመታት አገልግለዋል፡፡

ወደ ውጭ ሀገር በመሔድ ያለውን ባሕልና የትምህርት አሰጣጥ ሁናቴ ተመልክተው ቢመጡ የነገዋን ቤተ ክርስቲያን በመረከብ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንዲሚያበረክቱ ስለታመነበት በ1963 ዓ/ም ለከፍተኛ ትምህርት ወደ ግሪክ ተላኩ። ደሴተ ፍጥሞ በተባለችው ቦታ በሚገኘው ከፍተኛ የነገረ ሃይማኖት ትምህርት ቤት ለ፪ ዓመታት ተምረው ዲፕሎማ ተቀብለዋል። በዚያው ወደ አቴና ዩኒቨርስቲ በመግባት ለአራት ዓመታት የነገረ መለኮት ትምህርታቸውን በመከታተል በማስተርስ ዲግሪ ተመረቁ። ለከፍተኛ ትምህርትም ወደ ስዊዘርላንድ በማቅናት ፍሪቦንግ ዩኒቨርስቲ የፈረንሳይኛ ቋንቋ አጥንተው ዲፕሎማ አገኙ። በግሪክ የነገረ መለኮት ኮሌጅ የዐረብኛ ቋንቋን አጥንተው ሰርቲፊኬት ተቀብለዋል። ወርኀ ጥር 1971 በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንብሮተ ዕድ ከተሾሙት መካከል አንዱ ሁነው መዓርገ ጵጵስና ተቀበሉ። የቅዱስ ፓትርያርኩ እንደራሴና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ሁነው አገልግለዋል።

ዝዋይ በጎርጎርዮስ
በዝዋይ የካህናት ማሰልጠኛ በርካታ ሥራዎችን ሠርተዋል። ዕብራይስጥ፣ እንግሊዝኛ ዐረብኛ ቋንቋዎችን የሚያውቁት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ በዝዋይ ሐመረ ብርሃን የቅዱስ ገብርኤል ገዳም የዕውቀት ዓምባ አቋቁመው ኢትዮጵያዊውን ታሪክ ከዓለሙ ጋር እያነጻጸሩ ለደቀ መዛሙርቶቻቸው ሲያሰተምሩ ቆይተዋል። ብዙዎች ዝዋይ ለኮርስ መጥተው ሕይወት ጣፍጧቸው መለየት ቢያቅታቸው ሁሉን ትተው ቀርተውባታል፣ አያሌ ካህናት ዐይናቸውን ገልጠውባታል፣ በነበራቸው ወጣቱን ትውልድ የመያዝ ፍላጎትና ችሎታ በወቅቱ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ይማሩ የነበሩ ተማሪዎችን በክረምት ወደ ገዳሙ እንዲገቡ በማድረግ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትምህርት በመማር ዘመኑን እንዲዋጁ አድርገዋል። እርሳቸው ሰብስበው ያስተማሯቸውና የመከሯቸው ተማሪዎች ዛሬ ቊጥራቸውን አበራክተው በማኅበረ ቅዱሳን በመሰባሰብ በዕውቀታቸውና በገንዘባቸው ቤተ ክርስቲያንን እያገለገሉ ይገኛሉ።

የብፁዕነታቸው መጻሕፍቶች

ታላቁ ሊቅ የብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ ታሪካቸው በደማቅ ቀለም የተጻፈላቸው፣ ምኞታቸው የተተገበረላቸው፣ ርዕያቸውን ማሳካት የቻሉ አባት ናቸው፡፡ ብፁዕነታቸው በጽሑፋቸው፣ በትምህርታቸው እና ለኢትዮጵያና ለአፍሪካ ባላቸው ጽኑዕ ፍቅር ከእምነት ድንበር ባሻገር የሁሉንም ኢትዮጵያዊ ልቡና ሊገዛ የሚችል ስብዕና የነበራቸው አባት ነበሩ። ብፁዕነታቸው የታተሙም ያልታተሙም መጻሕፍቶች አሏቸው፡፡ ታዲያ ከሊቀ ጳጳሱ የታተሙ ሥራዎች መካከል የታሪክ መጻሕፍቶቻቸው ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ዘመን የማይሽራቸው የቤተ ክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክና የቤተ ክርስቲያን ታሪክ በኢትዮጵያ መጻሕፍቶቻቸው ናቸው። ታዲያ የእኒህን አርቆ አሳቢ ሊቀ ጳጳስ የታሪክ መጻሕፍት የማርታት ሥራ በአማን ነጸረ እና ተመስገን ዋና አዘጋጅተውት የሊቀ ጳጳሱንም ታሪክ ጨምረውበት፣ ታትሞ በገበያ ላይ ወጥቷል፡፡ ይኸ ድንቅ አበርክቶት ነው፡፡

ብፁነታቸው ሐምሌ ፳፪ ቀን ፲፱፻፹፪ ዓ.ም በመቂ ደብረ አሚን ቅዱስ ጊዮርጊስና በቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ለሚገኙ ምእመናን ትምህርተ ወንጌል ለመስጠት ሲፋጠኑ በድንገተኛ የመኪና አደጋ በተወለዱ በሃምሳ ዓመታቸው ዐረፉ። ሥርዐተ ቀብራቸው ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳስት ዘኢትዮጵያ፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳስት በተገኙበት ዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ቤተ መቅደስ ውስጥ ተፈጽሟል።

የብፁዕነታቸው በረከት ይደርብን

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዋቤ መጻሕፍት፡-
✍️ የቤተክርስቲያን ታሪክ በኢትዮጵያ
✍️ ሐመር መጽሔት
✍️ ዜና ጳጳሳት ኢትዮጵያውያን

ቅዱስ ዑራኤልእንኳን ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል (ሐምሌ ፳፪) ቀንበሰላም አደረሰን፤ አደረሳችሁ !!!  መ/ር ጌታቸው በቀለ ( )                ++++++++...
29/07/2025

ቅዱስ ዑራኤል

እንኳን ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል (ሐምሌ ፳፪) ቀን
በሰላም አደረሰን፤ አደረሳችሁ !!!

መ/ር ጌታቸው በቀለ

( )
++++++++++++++++++++++++++++++++

ቅዱስ ዑራኤል ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ነው፡፡ የቅዱስ ዑራኤል ቅዳሴ ቤቱ የሚከበርበትና ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል የዕውቀትን ጽዋ ያጠጣበት ሐምሌ ፳፪ ቀን በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል፡፡

ዑራኤል ማለት ትርጉሙ “የብርሃን ጌታ፣ የአምላክ ብርሃን” ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዑራኤል ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ “በእግዚአብሔር ፊት የሚቆሙ ሰባት መላእክትን አየሁ” /ራዕ 8፡2/ እንዳለ ሰባቱ ሊቃነ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል፣ ቅዱስ ገብርኤል፣ ቅዱስ ሩፋኤል፣ ቅዱስ ራጉኤል፣ ቅዱስ ዑራኤል፣ ቅዱስ ፋኑኤል እና ቅዱስ አፍኒን ናቸው፡፡ ቅዱስ ዑራኤል በመብረቅና በነጎድጓድ ላይ የተሾመ መልአክ ነው፡፡ የፀሐይን፣ የጨረቃን፣ የከዋክብትንና የሰማይ ሠራዊትን ብርሃንን የሚመራው ይኸው ገናና መልአክ ነው /ሄኖክ ፳፰፥፲፫/፡፡

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለዓለም ቤዛ ሆኖ በተሰቀለ ጊዜ ክቡር ደሙን በብርሃን ጽዋ ተቀብሎ በብርሃነ መነሳንስ በዓለም ላይ የረጨው ይኸው ገናና መልአክ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል ጽዋ ጥበብን አጠጥቶ ሰማያዊውን ምሥጢር የገለጠለት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው /ዕዝራ ፪፥፩/፡፡
ዕውቀት ተሠውሮበት ለነበረው ለኢትዮጵያዊው ሊቅ ለአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም በእመቤታችን ትእዛዝ ጽዋ ጥበብን አጠጥቶ ሰማያዊውን ምሥጢር የገለጠለት ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ስትሰደድ መንገድ እየመራ ወደ ግብጽ እና ወደ አገራችንን ኢትዮጵያ ያመጣቸው ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡

የቅዱስ ዑራኤል ተራዳኢነት

የመላእክት አለቃ ቅዱስ ዑራኤል በዘመናት ለነገሡ የሀገራችን ነገሥታት ያደረገውም ውለታ እጅግ ብዙ ነው፡፡ ዳግማዊ ቆስጠንጢኖስ የተባለ ንዋየ ማርያም በነገሠበት ዘመነ መንግሥት ቅዱስ ዑራኤል በጸሎቱ በመራዳትና እስከ ግዛቱ ፍጻሜ ባለመለየት ሀገሩን እንዲመራ አድርጓል፡፡ ንጉሡም ሃይማኖቱ የቀና እና የአምላክን እናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን የሚወድ ስለነበር ኢትዮጵያን በቀናች ሃይማኖት ሊመራት ችሏል፡፡ ንጉሥ ዘርዐ ያዕቆብ በዘመነ መንግሥቱ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስና ቅድስት ድንግል ማርያም ስም ከሠራቸው አብያተ ክርስቲያናት በተጨማሪ በቅዱስ ዑራኤል ስም ቤተ ክርስቲያን በደብረ ብርሃን በማሠራት የመልአኩ ስም እንዲጠራና በዓላቶቹ እንዲከበሩ አድርጓል፡፡

የንጉሥ ዘርዐ ያዕቆብ ልጅ በእደ ማርያም በነገሠ ጊዜ በቅዱስ ዑራኤል ስም ቤተ ክርስቲያንን አሠርቷል፡፡ ለበዓሉ መታሰቢያም ይሆን ዘንድ ለደብሩ ዐርባ ዐራት ርስተ ጉልትን ሰጥቷል፡፡ የደብሯንም ስም “ምስዓለ ማርያም” ብሎ ሰይሟታል፡፡ ይህም ንጉሥ የአባቱን ፈለግ ተከትሎ ሌሎችን አብያተ ክርስቲያናትን ሠርቷል፡፡ ከንጉሥ ይኩኖ አምላክ ጀምሮ እስከ ንጉሥ ናዖድ ድረስ ያሉትን ዘጠኙ ቅዱሳን አባቶችና ነገሥታት የሥራቸውን ዜናና የቀናች ሃይማኖታቸውን ጽንዓት በድርሳነ ዑራኤል ተጽፏል፡፡

እንደማጠቃለያ

መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል በዓመት ሦስት ዐበይት በዓላት አሉት፡፡ ጥር ፳፪ በዓለ ሲመቱ፤ መጋቢት ፳፯ የጌታችንን ክቡር የሆነ ወርቀ ደሙን ለዓለም የረጨበት፤ ሐምሌ ፳፪ ቀን ቅዳሴ ቤቱ የሚከበርበትና ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል የዕውቀትን ጽዋ ያጠጣበት ዕለት ነው፡፡

የሊቀ መላእክት የቅዱስ ዑራኤል ረድኤት በረከት ይደርብን፡፡ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዋቤ መጻሕፍት
✍️ መጽሐፍ ቅዱስ
✍️ ድርሳነ ዑራኤል
✍️ መጽሐፈ ስንክሳር

ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ
29/07/2025

ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ

ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሰማእተ ጽድቅ ዘ ኢትዮጵያ
29/07/2025

ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሰማእተ ጽድቅ ዘ ኢትዮጵያ

በሀድያና ስልጤ ከበጎ አድራጊ ምዕመን በተሰጠ 5500 ካሬ ሜትር  መሬት ለቤተ ክርስቲያን መስሪያ የመሠረት ድንጋይ ተጣለ ።(  ሐምሌ 21 ቀን 201ብ7 ዓ.ም)+++++++++++++++++++...
29/07/2025

በሀድያና ስልጤ ከበጎ አድራጊ ምዕመን በተሰጠ 5500 ካሬ ሜትር መሬት ለቤተ ክርስቲያን መስሪያ የመሠረት ድንጋይ ተጣለ ።

( ሐምሌ 21 ቀን 201ብ7 ዓ.ም)

+++++++++++++++++++++++++++++++++++++

በሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት በሶሮ ወረዳ ቤተ ክህነት በጃጁራ ከተማ አዲላ አንጃንቾ ኤርዶሎ የተባሉ ምዕመን ቤተሰብ አባላት ካላቸው ይዞታ ላይ በሰጡት 5500 ካሬ ሜትር መሬት አዲስ ለሚሠራ ቤተክርስቲያን የመሠረት ድንጋይ ማስቀመጥ ሥነ ሥርዓት ተካሄደ።
የመሠረተ ድንጋዩ በሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሕይወት ቀሲስ ንጉሤ ባወቀ በተገኙበት፣ ቆሞስ አባ ገብረ ማርያም ስዩም ባርከው አስቀምጠዋል ።

አዲል አንጃንቾ ኤርዶሎ ከቤተሰቦቻቸው ጋር በመነጋገር ለቤተክርስቲያን መሥሪያ መሬት ለመስጠት የወሰኑት የአከባቢው ምዕመናን በቅርብ ርቀት ቤተክርስቲያን ባለመኖሩ ከ2 ሰዓት በላይ አቋርጠዉ ለመሄድ መገዱዳቸውን ተመልክተው እንደሆን ተናግረዋል ። አካባቢው በዚህ ሁኔታ የተቸገሩ ከ50 በላይ ክርስቲያን አባወራዎች እምዳሉበትም ታውቋል ።

በጎ አድራጊው "ይህቺን ቅድስት ቤተክርስቲያን እንድረዳት የረዱኝና በብዙ ትጋት ያሰተማሩኝን የጀጁራ ደብረ መንክራት አባቶቻችንና ምዕመናን አመስግናለሁ ፣የእኔ አምላኬ ሰማይና ምድርን የፈጠረ እግዚአብሔር ነው ብለዋል።

በመጨረሻም የሀገረስከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ቦታውን በልግስና የሰጡትን አባቶች አመስግነው ከሁሉም በላይ የእግዚአብሔር ክብሩ የተገለጠበት ቦታ መሆኑን ተናግረዋል ። መርሐግብሩም በሀገር ሽማግሌዎች ምርቃትና በክብር መልአከ ሕይወት ቀሲስ ንጉሤ ባወቀ ጸሎት ፍጻሜው ሆኗል ።

© ብሕንሳ ሚዲያ

ነገረ ማርያምን የሚያስረዱ ስንት መጻሕፍት ታውቃላችሁ?(  ሐምሌ 21 ቀን 2017 ዓ.ም)                                                                ...
28/07/2025

ነገረ ማርያምን የሚያስረዱ ስንት መጻሕፍት ታውቃላችሁ?

( ሐምሌ 21 ቀን 2017 ዓ.ም)
መ/ር ጌታቸው በቀለ

+++++++++++++++++++++++++++++++++++++
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በርካታ የግእዝ የእጅ ጽሑፎች/መጻሕፍት (Manuscripts) አሏት። እነዚህ መጻሕፍት/ ጽሑፎች፡- የአጋእዝት ዓለም ሥላሴን ክብር (Glorification of the Trinity)፣ ምሥጢረ ሥጋዌ (Incarnation)፣ ነገረ ማርያም (Mariology)፣ ስለ ቃል ኪዳኑ ታቦት (the Ark of covenant)፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትርጓሜያት ማብራሪያዎች፣ መልእክታት፣ የሥነ ምግባር ትምህርቶችን (Christian ethical teachings) ወዘተ… የያዙ ናቸው፡፡
በዚህ ልጥፍ ከግእዝ ጽሑፎቹ ወይም መጻሕፍት መካከል ስለ ነገረ ማርያም (Prominent Mariological Texts) የሚያስረዱትን እንመለከታለን፡፡ ስለ ነገረ ማርያም ከሚያስረዱን ጽሑፎች (መጻሕፍት) ስንቶቹን እናውቃቸዋለን? ስንቶቹንስ አንብበናቸዋል? የሚከተሉት ጽሑፎች (መጻሕፍት) ነገረ ማርያምን በስፋትና በጥልቀት የሚያስረዱን ናቸው፡፡

1. መጽሐፈ ልደታ ለማርያም (The story of Mary’s Nativity)
2. ነገረ ማርያም (The story of Mary)
3. መጽሐፈ ዕረፍታ ለማርያም (Book of Dormition of Mary)
4. መጽሐፈ ዕርገታ ለማርያም (Book of Assumption of Mary also called)
ዜና ዕርገታ (News of her Assumption)
5. ድርሳነ ማርያም (Homily [in honor] of Mary)
7. ውዳሴ ማርያም (Praise of Mary)
8. አንቀጸ ማርያም (Gate of the light also called)
አንቀጸ ወግናይ (Gate of the praise)
9. ተአምረ ማርያም (Miracles of Mary)
10. መልክአ ማርያም (Image of Mary)
11. አርጋኖን (Arganon also called)
አርጋኖነ ውዳሴ (Harp of Praise or)
አርጋኖነ ድንግል (Harp of the Virgin)
12. ቅዳሴ ማርያም (Anaphora of Mary)
13. ራእየ ማርያም (Vision of Mary)
14.ማሕሌተ ጽጌ (Canticle of the Flower)
15. እንዚራ ስብሐት (Harp of Praise)
16. መልክአ ኤዶም (Images of Edom)
17. መልክአ ሥዕል (Images of the Icon)
18. ድርሳነ ጽዮን (Homily [in honor] of Zion)
19.መልክአ ጽዮን (Effigies of Zion)
20.መዝሙረ ድንግል (Paslter of the Virgin)
21.ሰዓታተ ዘሌሊት ወዘነግህ (The Hours of the Night and the Day also called Horologim)
22. ሰቆቃወ ድንግል (Lamentation of the Virgin)
23. ስብሐተ ፍቁር (Praise of the Beloved also called)
ብፅዕት አንቲ (Blessed you are)
24. ኆኅተ ብርሃን (The Gate of Light)
25. ውዳሴ አንቀጸ ነቢያት (Praise of the Gate of the Prophets)
26. የሰኔ ጎልጎታ (Golgotha of Sane)
27. አኮኑ ብእሲ (It is not a man)
28. ምስጢረ ጽጌያት (Mysteries of Flowers.)
እንደ መውጫ

ከዚህ በላይ የተጠቀሱት መጻሕፍት ስለ ነገረ ማርያም (Mariology) በስፋትና በጥልቀት የሚያስረዱን ናቸው፡፡እነዚህን መጻሕፍት ቤተክርስቲያን ለአገልግሎት የምትጠቀምባቸው፣ ምእመናንም የሚያነቧቸው ናቸው፡፡ “የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ኹሉ ለትምህርትና ለተግሣጽ፣ የልብንም ለማጽናት፣ በጽድቅ ላለው ምክር ይጠቅማል” እንዲል፤ መንፈሳውያን መጻሕፍት ሕይወታችን የምንመራባቸው፣ ከእግዚአብሔር ጋር የሚያገናኙን በመኾነቸው ጠቀሜታቸው ከፍተኛ ነው፡፡ /፪ኛ ጢሞ.፫፥፲፮/፡፡ እንደዚሁ ሁሉ ስለ ነገረ ማርያም የሚያስረዱን እነዚህን መጻሕፍት ስናነብ የእመቤታችንን ታሪክ በሰፊው እንረዳለን፤ ከተሰጣት ቃል ኪዳንም በረከት እናገኛለን፡፡ ከላይ የተገለጹት ቅዱሳት መጻሕፍት ሰፊ ዕውቀት የምንገበይባቸው፣ ቅድስት ድንግል ማርያምን የምንማጸንባቸው በመኾናቸው አዘውትረን ልናነባቸው ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

እንኳን አደረሳችሁ!
28/07/2025

እንኳን አደረሳችሁ!

EOTC TV | ፍኖተ ሕይወት || ኦቲዝም     Spectrum Disorders
28/07/2025

EOTC TV | ፍኖተ ሕይወት || ኦቲዝም Spectrum Disorders

+++++++++++++++++++++++++++++++++++++ https://youtu.be/Wqgq1KebrOo 🇪🇹 "የቤተክርስቲያን የሆነውን ብቻ" 🇪🇹ተቋሙን በገንዘብ ለማገዝ፡- የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 👉1000...

Address

Addis Ababa

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/ posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት/ EOTC Broadcasting Service Agency/:

Share

EOTC BROADCASTING SERVICE AGENCY

የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኃን አገልግሎት ስርጭት ድርጅት