18/11/2025
"ተርጓሚዎቹ ሆነ ብለው እንጂ ባለማወቅ አላደረጉትም!"
ዕለተ ዕሁድ፣ ህዳር 7 ቀን 2018 ዓ.ም በሕንጸት የመጽሐፍ ክበብ የተገመገመው መጽሐፍ በዓይነቱ ለየት ያለ ነበር። ርዕሱ፣ "ተፋልሶ" ይሰኛል። ጸሐፊው፣ ከጥቂት ዓመት በፊት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የግሪክ ቋንቋ መምህር የነበሩ፣ መምህር ጌታቸው ተረፈ ሲሆኑ፣ መጽሐፉን የገመገሙት ደግሞ የሥነ መለኮትና የግሪክ ቋንቋ መምህሩ፣ አክሊሉ ኩማ ነው። ገምጋሚው የመጽሐፉ አዘጋጅ ለደከሙት ድካም እውቅናን የቸረ፣ ሥራቸው ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ስላለው ፋይዳ በስፋት የተነተነ ሲሆን ጥቂት ቢታከሉ ያላቸውን ሃሳቦችም አክሏል።
መጽሐፉ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ ከኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ጋር በመተባበር፣ በ2000 ዓ.ም ባሳተመችውና፣ "የሚሊኒየም መጽሐፍ ቅዱስ" የሚል ስያሜ በተቸረው አዲስ ትርጉም ላይ ያጠነጥናል። ይህ ትርጉም ከታተመበት ጊዜ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያኒቱ አንዳንድ ሊቃውንት ዘንድ ከፍተኛ ሙግት ሲነሳበት ቢቆይም እንደ መምህር ጌታቸው ድምጹን ከፍ አድርጎ የጮኸ ለመኖሩ ግን እርግጠኛ ዓይደለሁም። ከእሁድ ዕለቱ ስሜታቸው እንደታዘብኩት ደግሞ ዛሬም ድረስ እንኳ ድንጋጤው እና የልብ ሀዘኑ አለቀቃቸውም።
በመጽሐፍ ቅዱስ የትርጉም ሥራ ውስጥ የሚነሱ ሙግቶች በአብዛኛው በቃላት ምርጫና በአተረጓጎም ዘዴ ላይ የሚያተኩሩ መሆናቸው የተለመደ ቢሆንም መምህር ጌታቸው ተረፈ፣ በሚሊኒየሙ ትርጉም ላይ ያነሱት ምሁራዊ ሙግት ግና ጉዳዩን ከቀላል የትርጉም ሙግት ወደ ሌላ፣ እጅግ ከባድ ደረጃ ከፍ ያደርገዋል። በተለይም የቤተ ክርስቲያኒቱ የታወቀ የመጽሐፍ ቅዱስ ኮሌጅ አካል የሆነ ሰው፣ አንድን ይፋዊ የቤተ ክርስቲያን እትም፣ "ተፋልሶ" ብሎ የተቃውሞ መጽሐፍ እስከመጻፍ መድረሱ የርዕሰ ጉዳዩን ክብደትና ጥልቀት ያሳያል።
ለመምህር ጌታቸው የዚህ እትም በስህተት መሞላት የአጋጣሚ ስህተት ሳይሆን ሆነ ተብሎ የተደረገ፣ እውነትን የመበረዝ ተግባር እንደሆነ ተቆጥሯል። ተርጓሚዎቹ "ባለማወቅ ተሳስተዋል" ሳይሆን "ሆን ብለው መሠረታዊ የሆኑ አስተምህሮዎችን ለመለወጥ ሞክረዋል" የሚል ሙግትም አላቸው። ለዚህ ሥራ ግብረ መልስ የሰጡበት፣ "ተፋልሶ" የተበረዙትን ሃሳቦች ከቀደምት ምንጩ፣ የግሪክ ቋንቋ ጋር "በንጽጽር የሚያሳይ" መሆኑ፣ ጬኸታቸው በስሜት ወይም በወሬ ላይ የተመሠረተ ሳይሆን፣ ማስረጃዎችን በማቅረብ ስልታዊ በሆነ መንገድ የቀረበ መሆኑን ሥራቸውን ተዓማኒ ያደርገዋል።
መምህሩ ሙግታቸው በመጽሐፍ መልክ ታትሞ ወደ ሕዝብ እጅ እንዲገባ ከማድረጋቸው አስቀድሞ ለቅዱስ ሲኖዶስ እና ለሊቃውንት ጉባኤ፣ ከዚያም ተሻግረው ለመጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ሙግታቸውም ቢያቀርቡም ጥያቄያቸው ከየትኞቹም አካላት መልስ ሳያገኝ በመቅረቱ እጅግ ማዘናቸውን ገልጸዋል። ይህ ማለት ደግሞ ችግሩ የትርጉም ስህተት ብቻ ሳይሆን፣ የተቋማዊ ምላሽ አልባነትና የአመራር ቀውስ ጭምር መኖሩን በግልጽ ያሳያል።
እንዲያም ሆኖ መምህሩ ሃሳባቸውን ለመግለጽ የሄዱበት መንገድ ሥርዓትን የጠበቀና ለአንድ የቤተ ክርስቲያን ሊቅ የሚገባውን ኃላፊነት የተሞላበት ተግባር ነው። ጉዳዩን በቀጥታ ወደ ሕዝብ ከማድረሳቸው በፊት፣ ለሚመለከታቸው የበላይ አካላት፣ ማለትም ለቅዱስ ሲኖዶስ እና የሊቃውንት ጉባኤ አቅርበዋል። ይህም ለቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓትና መዋቅር ያላቸውን አክብሮትና የሙግት አቀራረባቸውን ጨዋነት ያሳያል። የመጽሐፉ ገምጋሚ፣ ወንድም አክሊሉ ለማም ይህንኑ አክብሮት በመጽሐፉ ውስጥ መመልከቱን በአድናቆት ገልጾታል።
መምህሩ፣ በኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስን የማስተርጎምና የማሳተም ሥልጣን ላለው የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበርም ጭምር ማብራሪያ ጠይቀው ምላሽ ማጣታቸው "ተፋልሶ" የተሰኘውን መጽሐፍ የማሳተማቸው የመጨረሻ አማራጭ ሆኗል። ባጭሩ፣ መምህሩ ወደ ሕዝብ የወጡት በሮች ሁሉ ከተዘጉባቸው በኋላ ነው። የዚህ ውሳኔያቸው ዓላማ አንዳንድ የዋሃት እንደሚያስቡት ቤተ ክርስቲያንን የማጥቃት ሳይሆን፣ ምላሽ ያጣው እውነት ድምጽ እንዲያገኝ የማድረግን፣ የሕሊናን ግዴታ መወጣት ነው። ለዚህም ነበር የዕለቱ መርሀ ግብር አሳላጭ፣ መጋቢ መርዓዊ ንጉሤ፣ "ኢትዮጵያዊው ሉተር" ያላቸው።
መምህር ጌታቸው፤ የቅዱስ ሲኖዶስ እና የሌሎች አካላት ዝምታ እና ቸልተኝነት የእግር እሳት ሆኖ ቢያንገበግባቸውም በእኔ ዕይታ ግን ጉዳዩ ከተራ ቸልተኝነት የከበደ ትርጉም አለው። ዝምታው በዋናነት ለቀረበው ሙግት መልስ መስጠት አለመቻልን ያሳያል። በመምህሩ የቀረበው ማስረጃ በጣም ጠንካራ ከመሆኑ የተነሳ፣ ሊቃውንቱ ሊከላከሉት እንዳልቻሉም ነው የምቆጥረው። ሌላው ግምቴ ደግሞ ቤተ ክርስቲያኒቱ በይፋ ያሳተመችውን መጽሐፍ፣ "ተሳስተናል" ብሎ መቀበል፣ ለብዙዎች ከባድ ውርደት ስለሚመስላቸው ዝምታን እንደ መከላከያ ተጠቅመውበትም ሊሆን ይችላል የሚል ነው።
እናም የቤተ ክርስቲያኒቱ መሪዎች ኃላፊነታቸውን ባለመወጣታቸው ምክንያት አሁን ላይ ሸክሙ በምዕመኑ ጫንቃ ላይ ወድቋል፣ ያሳዝናል! ውሎ አድሮም ቢሆን፣ "የትኛው መጽሐፍ ቅዱስ ነው ትክክለኛው?"፤ "ማንን ነው ማመን ያለብን?" የሚሉ የብዥታ ጥያቄዎች በምዕመናን ዘንድ መፈጠራቸውም አይቀሬ ነው። ዝምታው በከፍተኛ ደረጃ መተማመንን ይሸረሸራል። ምዕመኑ በመሪዎቹ ላይ ያለው እምነት በእጅጉ ይጎዳል። "ይህን ያህል ትልቅ ጉዳይ ደብቀው ዝም ካሉ፣ በሌላ ምን ጉዳይ ላይ ልናምናቸው እንችላለን?" የሚል ጥያቄም ይፈጥራል።
መምህር ጌታቸው ተረፈ፣ በዕለቱ፣ "ይህቺ መጽሐፍ ቅዱስን እና ክርስትናን ለሺ ዘመናት ጠብቃ ያቆየች ታላቅ ቤተ ክርስቲያን መጽሐፍ ቅዱስን በዚህ ደረጃ መበረዝ አይመጥናትም!" ማለታቸውም ከዚህ ቁጭታቸው ይነሳል። ይኼ አባባላቸው በጣም ልብ የሚነካና የጉዳዩን ክብደት በአንድ ዐረፍተ ነገር ያጠቃለለ ንግግር ሆኖ አግኝቼዋለሁ። አባባሉ ከተራ የአካዳሚክ ሙግት የዘለለ፣ ጥልቅ የሆነን የልብ ስብራት ያስተዋልኩበት ነው። መምህሩ፣ የሚሊኒዬሙ ትርጉም ዓለም አቀፋዊውን የመጽሐፍ ቅዱሰ ትርጉም ደረጃ ያልጠበቀ፣ በይዘቱ "ሴክቴሪያን" ወይም የአንድ ቡድን አስተምህሮ ብቻ ለማንጸባረቅ የተዘጋጀ መጽሐፍ ለመሆኑ አጽንኦት መስጠታቸውም በቤተ ክርስቲያናቸው እንዲህ ያለ ከባድ መሳት ያደረባቸውን ቁጭት ያሳያል።
መምህር ጌታቸው፣ ከዓለም አቀፋዊው ትርጉም በተለየ መልኩ የራስ እምነት ማንጸባረቂያ እንዲሆን ተደርጎ፣ እውነትን በሚያፋልሱ 596 ቃላት የተቀሽበውን፣ የሚሊኒዬሙን ትርጉም ያነጻጸሩት፣ ከይሖዋ ምስክሮች፣ "የአዲስ ዓለም ትርጉም" ከተሰኘ እትም እና ራሱን፣ "የኋለኛው ቀን ቅዱሳን" ብሎ ከሚጠራው "ዘ ቡክ ኦፍ ሞርሞንስ" ከተባለ የሃይማኖት መጽሐፍ ጋር ነው። መምህሩ፣ የሚሊኒየሙን ትርጉም ከእነዚህ ሁለት መጻሕፍት ጋር ሲያነጻጽሩ፣ በይዘት ፍጹም አንድ ናቸው እያሉ ሳይሆን ይልቁንም፣ የተጠቀሙበት ዘዴ እና ያስከተሉት ውጤት ተመሳሳይ በንጽጽር ለማሳየት የተጠቀሙበት ምሳሌ ነው።
እንግዲህ በሚያሳዝን ሁኔታ ይኼ ሸክም ቀኝና ግራውን በማያውቀው ሕዝበ ክርስቲያን ጫንቃ ላይ ወድቋል። ትናንት ያየሁት የመምህር ጌታቸው ተረፈ ውስጥን የሚያናውጥና አንጀትን የሚያላውስ ቁጭትም ይኼ ሕዝብ ከአምላኩ ጋር የሚገናኝበት፣ ኀጢአቱን ተገንዝቦ፣ በእርሱ አምኖ የሚድንበት ግልጽ የወንጌል መልዕክት ተበርዞ በመቅረቡ ነው። በመጨረሻም የእሳቸው ጩኸት የእኛም ጩኸታችን እንዲሆን አደራ ብለዋልና ይኸው እኔም ጩኸቴን አስተጋብቻለሁ። በእሳቸው በኩል ቁጭቴን ለአራተኛ ጊዜ ተንፍሻለሁ። እናንተም በምትችሉት መንገድ ይህንኑ ታደርጉ ዘንድ ጥሪዬን አቀርባለሁ። የዕለቱ መርኃ ግብር እና የመምህሩ ምላሾች ከጥቂት ሳምንታት በኋላ በሕንጸት ድረ ገጽ ላይ ስለሚጫንም ትመለከቱት ዘንድ ግብዣዬ ነው።
© ሽመልስ ይፍሩ
negerechristina