11/06/2026
"ጦርነትን ሳይጀመር ማስቆም የሁሉም ኢትዮጵያውያን የጋራ የቤት ሥራ ሊሆን ይገባል!!" - ኢዜማ
ሀገራችን በታሪኳ እስከአሁን ድረስ በተለያዩ የኃይል አማራጮች ችግሮችን ለመፍታት እንዲሁም የመንግሥት ሥልጣንን ለመቀየር ስትባዝን አለች፤ ሆኖም የረጅም ዓመት ሀገረ መንግሥት ታሪኳን በማይመጥን መልኩ እስከአሁን ኋላቀር ከሚባሉት ሀገራት ግንባር ቀደም ከመሆን የዘለለ አንዳች ነገር አላገኘችም።
ላለፉት ከ 30 ዓመታት በላይ በሀገሪቱ ውስጥ ላሉ ችግሮች፣ ግጭቶች፣ ጥቃቶች እንዲሁም ሌሎች በርካታ ችግሮች በዋነኛነት ምክንያቱ ደግሞ ሕወሓት ሥልጣነ መንበሩን በኃይል ካረጋገጠ በኋላ ያሠፈነው የብሔር ፖለቲካ ነው። ይኽ የፖለቲካ ሥርዓት ከፍተኛ ችግር ያስከተለ ቢሆንም በሕወሓት ተንኳሽነት የተጀመረው እና ከሁለት ዓመታት በላይ የፈጀው የሰሜኑ ጦርነት ያስከተለውን የሰው ህይወትና የንብረት ውድመት በከፍተኛነቱ የሚስተካከለው የለም።
ከዚህ ጥፋት መልስ በፕሪቶሪያ ስምምነት ከጦርነት መውጣት የተቻለ ቢሆንም ይህ በዘላቂነት እንዳይቀጥል በተለይ ሕጋዊ ማንነቱን ባጣው ሕወሓት በኩል እንደሥምምነቱ እንዳይፈፀም የታዩ ዳተኝነቶች እና እንደ አጠቃላይ የፖለቲካ ሥሪቱ ላይ ውጤት ሊያመጣ የሚችለውን ሀገራዊ ምክክር፣ የ2018 ዓ.ም ምርጫ በትግራይ ክልል እንዳይከናውን በማድረግ፣ በክልሉ የሚገኙ ተፈናቃዮች ወደ ቀዬአቸው እንዳይመለሱ በታጋችነት በመያዝ በአጠቃላይ በክልሉ ያለው ችግር እንዳይፈታ በማድረግ ይኸው ችግር መልሶ ይፈጠር ይሆን የሚል ስጋትን እንደያዘ አለ።
ለትግራይ ማኅበረሰብ እቆረቆራለሁ የሚለው ይህ ቡድን ከእሰጠዓገባ ውጪ መኖር የማይችል በሚመስል መልኩ የተለያዩ ችግሮችን ለመፍጠር እየሞከረ የከረመ ሲሆን ሰኔ 02/2018 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ እና በክልሉ አፀደቀ በተባለው አዋጅ ግልጽ የጦርነት አዋጅን ለፍፏል። በተለይም በአዋጁ ያካተተው አስገዳጅ የወታደር ምልመላ፤ የተለዩ ድምፆች በትግራይ እንዳይሰሙ ያስቀመጠው ልጓም፤ ሁሉም ነገር ወደ ጦር ግንባር የሚመስለው የፕሮፖጋንዳ ልፈፋ ይኽንን ተፈጥሯዊ ጠበኛ ባሕርዩን እና ፍላጎቱ አሁንም የትግራይን እና አጠቃላይ የኢትዮጵያን ህዝብ በስንት ልፋት ወዳስቆመው ጦርነት እና እልቂት መክተት መሆኑን ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ነው።
በመሰረቱ አዋጁን ማውጣቱ እና በተለይም ከወታደር ምልመላ እና ጦርነቱን ካለመደገፍ ጋር በተገናኘ የተካተቱት ቅጣቶች ማኅበረሰቡ በጦርነቱ ለመሣተፍ ፍላጎት እንደሌለው እና በዚህም ቡድኑ ስጋት ያደረበት መሆኑን በግልፅ የሚያሣይ ነው፤ ይህ ተስፋ የቆረጠ እድሜያቸው የገፋ የሥልጣን ጥመኞች ስብስብ አሁንም በግጭት ውስጥ አፍላ ወጣቶችን የመማገድ ዓላማ አድርጎ ከዚህ ቀደም ልጆቻቸውን ያጡትን እናቶች፤ በስለት ከጦርነቱ የተረፈ የቀረ ልጅ ያላቸውን ጧሪ ቀባሪያቸውን ሊነጥቃቸው አሰፍስፎ መምጣቱ ለትግራይ ህዝብም ሆነ ለሰው ልጆች ሁሉ እንጥፍጣፊ ርህራሄ እንደሌለው ያሳያል። ይህንን ኃይል በቃህ ማለት እና በትግራይ ያሉ ወገኖቻችንን ከማያባራ መከራ መታደግ የሁላችንም ኢትዮጵያውያን የጋራ የቤት ሥራ ሊሆን ይገባል፤ ጦርነትን ሳይጀመር በፊት ማስቆም ይገባናል።
ኢዜማ የትኛውም ፖለቲካዊ ችግር በውይይት መፈታት አለበት ብሎ በጽኑ የሚያምን ሲሆን ይህንን ለማድረግ ፈቃደኛ ያልሆነን እንደ ሕወሓት ዓይነት ደም የማይጠረቃ አካል እና እሱን የሚዘውሩ ጥቂት ግለሰቦች በቃችሁ ብሎ ለማስቆም እና የትግራይ ህዝብን ካላስፈላጊ መከራ ለመታደግ በህዝብ ላይ ምንም አይነት መስዋዕትነት በማያስከትል መልኩ በሕገወጥ ቡድኑ ላይ ብቻ ያነጣጠረ አስፈላጊ ሕጋዊ እርምጃ በመንግሥት እና ከመንግሥት ጋር በጋራ በሚቆሙ ማንኛውም ለትግራይ ማኅበረሰብ በሚቆረቆር አካል ሊወሰድ እንደሚገባ ያምናል፤ ማኅበረሰቡም አሁን ለጦርነት ዕያሣየ ያለውን እምቢተኝነት በተጠናከረ መልኩ እንዲገፋበት ጥሪ እናቀርባለን።
በመጨረሻም በዚህ ሒደት ውስጥ ፓርቲያችን ማኅበረሰቡ እያለፈበት ያለውን ጭንቀት እየኖረበት ያለውን አሰቃቂ ሁኔታ ለመቅረፍ ባለው አቅም ሁሉ በቀጥታ ለማገዝ ከማንኛውም ሀገራዊ ኃይል ጋር በጋራ ለመሥራትና የበኩሉን ለማበርከት ዝግጁ መሆኑን ያረጋግጣል።
የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ)
ግንቦት 04/ 2018 ዓ.ም.