01/09/2025
♦️የዳይመንድ ሊግ አሸናፊዋ አትሌት ፋንታዬ በላይነህ ብ/ቡድኑን ተቀላቅላ ሆቴል ገባች
✍️በጋዜጠኛ ይስሀቅ በላይ(ሀትሪክ ስፖርት ኦፊሺያል)
ባለፈው ሐሙስ ምሽት ዙሪክ ላይ በተካሄደው የ2025 የዳይመንድ ሊግ ፍፃሜ ክስተት ሆና ያሸነፈችው የ24 ዓመትዋ አትሌት ፋንታዬ በላይነህ የቶኪዮ አለም ሻምፒዮና ተሳታፊ የሆነው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ብ/ቡድን ተቀላቅላ ሆቴል መግባቷ ተረጋግጧል
አመለሸጋው፣ልታይ ልታይ የማይለውና ተደብቆ ድምፁን አጥፍቶ በመስራት ውጤታማ በመሆን ተለይቶ በሚታወቀው ወጣቱ አሠልጣኝ ቴዎድሮስ ኃይሉ የምትሠለጥነው አትሌት ፋንታዬ በላይነህ የብዙዎቹን ቀልብ የሳበውን የ3000 ሜትር ውድድር በማሸነፍዋ ወደ ቶኪዮ አለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተሳታፊ የሚያደርጋትን ትኬት መቁረጧን መዘገባችን ይታወሳል።
አትሌት ፋንታዬ በላይነህ በዙሪኩ የ2025 የዳይመንድ ሊግ ፍፃሜ በ3000 ሜትር 8:40.56 በሆነ ሠዓት በመግባት በማሸነፏ በዓለም አትሌቲክስ አዲሱ ህግ መሰረት በWild Card በቀጥታ በማለፍ በቶኪዮ ጃፓን ከሴፕቴምበር 13-21/2025 የሚካሄደው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሀገርዋን ወክላ የምትሳተፍበትን ወርቃማ ዕድል አግኝታለች።
የአለም አትሌቲክስ ያወጣውን አዲስ ህግ ተከትሎ በWild Card በቀጥታ ተሳታፊ መሆኗን ያረጋገጠችው አትሌት ፋንታዬ በላይነህ ባለፈው ቅዳሜ ከዙሪክ አዲስ አበባ ገብታ ዛሬ(እሁድ) ቤልቪው ሆቴል በመግባት ለቶኪዮው የአለም ሻምፒዮና በዝግጅት ላይ የሚገኘውን የአትሌቲክስ ብ/ቡድን ተቀላቅላለች።
በአፍሪካ የአትሌቲክስ ሻምፒዮና በ5000ሜትር በ2022 የብርና በ2024 የወርቅ ሜዳልያ ባለቤት የሆነችው ወጣቷ አትሌት በቶኪዮው የአለም ሻምፒዮና በርቀቱ የመሳተፍ ዕድል ማግኘቷ ለኢትዮጵያ እንደመልካም አጋጣሚ የተወሠደ ሲሆን ሜዳልያ የማግኘት ዕድላችንን ከፍ እንደሚያደርገውም ባለሙያዎች አስተያየት እየሠጡበት ይገኛሉ።
ከአትሌቷ ስኬት ጀርባ የሚገኘውና ድምፁን አጥፍቶ ተደብቆ ስራውን ብቻ የሚሰራውና የነገ የአትሌቲክሱ አልጋወራሽ ይሆናል ተብሎ የሚጠበቀው ወጣቱ አስልጣኝ ቴዎድሮስ ሀይሉ በቶኪዮ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና አትሌት መዲና ዒሳ፣አትሌት ሳሙኤል ፍሬው፣ አትሌት አለሽኝ ባወቀንና አሁን ደግሞ ፋንታዬ በላይነህን በማስመረጥ ከፍተኛ አትሌቶችን ካስመረጡ አሰልጣኞች ተርታ እንዲሠለፍም አድርጎታል ።
አሠልጣኝ ቴዎድሮስ ኃይሉ የጀግናዋና የአመለሸጋዋ አትሌት መሠረት ደፋር ባለቤትም ነው።