18/12/2025
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለአርሶ አደሮች የግብርና ብድር አገልግሎት አስጀመረ
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለባለአነስተኛ ይዞታና ለተደራጁ አርሶ አደሮች የሚሰጥ የግብርና ብድር አገልግሎት በዛሬው ዕለት አስጀምሯል።
በማስጀመሪያ መርሐ ግብሩ የግብርና ሚኒስትር ዴዔታ መለስ መኮንን (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ አቤ ሳኖ ተወካይ እና የኮርፖሬት አገልግሎቶች ኤክስኪውቲቭ ም/ፕሬዚዳንት አቶ አፍሬም መኩሪያ እና የሌሎች ተቋማት ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።
አቶ ኤፍሬም በወቅቱ እንዳሉት፥ ንግድ ባንክ አዳዲስ አገልግሎቶችን በመተግበር ቀልጣፋና አስተማማኝ አገልግሎት እየሰጠ ነው።
የፋይናንስ አገልግሎት ተደራሽነትና አካታችነትን ይበልጥ ለማሳደግም በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸው፤ በተለይም ለግብርና ዘርፍ የሚሰጠውን የብድር አገልግሎት ለማስፋትና ለማጠናከር ትኩረት ተደርጓል ብለዋል።
ባንኩ ለአርሶ አደሮች የግብርና ስራዎችን ለማሳደግ ልዩ የብድር አገልግሎት ማስጀመሩ የገጠር ኢኮኖሚ ዕድገትን ለማሳደግ ያስችላል ነው ያሉት።
በአገልግሎቱ የእርሻ መሬት ያላቸው፣ በኩታገጠም በቡድን የተደራጁ፣ በባንኩ 6 ወርና ከዚያ በላይ የቆጠቡ፣ በሰብል ልማት፣ በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በወተትና ወተት ተዋጽኦ እንዲሁም በእንስሳት ሀብት ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ ይሆናሉ።
የብድር አገልግሎቶቹ የሰብል ምርት፣ የግብርና ማሽነሪና መሳሪያዎች፣ የእንስሳት እርባታ፣ የመጋዘን ደረሰኝ እና የፕሮጀክት ፋይናንስ አቅርቦት የተሰኙ ናቸው።
መለስ መኮንን (ዶ/ር) በበኩላቸው፥ የብድር አገልግሎቱ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ የዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግ እንደሚያስችል ተናግረዋል።
(መላኩ ገድፍ - ኤፍ ኤም ሲ)