11/08/2026
የአፍሪካ ድምፆች የሚገናኙባት ደማቋ ከተማ
*************
አዲስ አበባ የሀገራችን ዋና ከተማ ከመሆን ባለፈ በአፍሪካ የዲፕሎማሲ መድረክ ላይ ልዩ ስፍራ የያዘች ከተማ ናት።
አዲስ አበባ የአፍሪካ ሕብረት ዋና መሥሪያ ቤትን ጨምሮ የበርካታ ዓለም አቀፍና አህጉራዊ ተቋማት መቀመጫ በመሆኗ፣ ከአህጉሪቱ የሚመጡ መሪዎች፣ ዲፕሎማቶችና ባለሙያዎች የሚሰበሰቡባትና በጋራ ጉዳዮች ላይ የሚመክሩበት ዋነኛ መድረክ ለመሆን በቅታለች።
ይህ የመዲናዋ የዲፕሎማሲ ማዕከልነት በአንድ ጀምበር የተገነባ ሳይሆን፤ የኢትዮጵያ ረጅም የዲፕሎማሲ ታሪክ፣ በፓን-አፍሪካኒዝም እንቅስቃሴና በአህጉሪቱ ነፃነት ላይ የነበራት የጎላ ሚና እንዲሁም የአፍሪካ ሕብረት መቀመጫ መሆኗ ተደምሮ የተገኘ ታሪካዊ ውጤት ነው።
አፍሪካ በቋንቋ፣ በባህልና በፖለቲካዊ አወቃቀር የተለያየች ብትሆንም፤ አዲስ አበባ የተለያዩ ድምፆች የሚገናኙባት፣ የጋራ አቋም የሚያዙበት እንዲሁም የሰላምና የልማት ውይይቶች የሚደረጉበት አህጉራዊ መድረክ ሆና በማገልገል ላይ ትገኛለች።
በተጨማሪም የአፍሪካ ጉዳዮች ከዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር የሚነሱበትና የትብብር አቅጣጫዎች የሚቀየሱበት ዋነኛ የምክክር ማዕከል ሆናለች።
የዲፕሎማሲ ማዕከልነት ከፖለቲካዊ ጠቀሜታ ባሻገር ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ዕድሎችንም የሚፈጥር ሲሆን በየጊዜው የሚካሄዱ አህጉራዊና ዓለም አቀፍ ጉባኤዎች የሆቴል፣ የቱሪዝም፣ የመጓጓዣ፣ የኮንፈረንስና የአገልግሎት ዘርፎችን ያነቃቃሉ።
ከዚህ ባሻገር ለወጣቶች በዓለም አቀፍ ተቋማት፣ በምርምር፣ በሚዲያ፣ በትርጉምና በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ተጨማሪ የተሳትፎና የሥራ ዕድሎችን ይፈጥራል፡፡
አዲስ አበባም ይህን ተፈላጊነቷንና ቦታዋን በሚመጥን መልኩ ተቋማዊ አቅሟን በማጠናከር፣ ዘመናዊ መሠረተ-ልማቶችን በማስፋፋትና ዓለም አቀፍ ጉባኤዎችን የማስተናገድ ብቃቷን በማሳደግ የአፍሪካና የዓለም የዲፕሎማሲ መገናኛ ድልድይነቷን ይበልጥ እያጠናከረች ትገኛለች።
በኢንትሀድ አብራር