
01/08/2025
ታግተናል በማለት ወላጆቻቸውን 500ሺህ ብር የጠየቁ ታዳጊዎቸ በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ እየተጣራባቸው መሆኑን የአዲስ ከተማ ክ/ከተማ ፖሊስ መምሪያ ገለፀ፡፡
***
የወንጀል ድርጊቱ የተፈፀመው በአዲስ ከተማ ክ/ከተማ ወረዳ 9 ልዩ ቦታው ኳስ ሜዳ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ነው።
አጋችና ታጋች በመምሰል የማታለል ወንጀሉን የፈፀሙት አራቱ ተጠርጣሪዎች ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ ሁለት ወንዶችና ሁለት ሴቶች ሲሆኑ ለሁለት ቀናት ከቤተሰቦቻቸው ወጥተው ሲዝናኑ ቆይተው ገንዘብ ሲያጥራቸው በመመካከር ለቤተሰብ ስልክ ደውለዋል፡፡
ወንዶቹ አጋች ሴቶቹ ደግሞ ታጋቾች በመሆን ለሴቶቹ ቤተሰቦች በደወሉት ስልክ 5 መቶ ሺ ብር የጠየቁ ሲሆን የሴት ወላጆች አቅራቢያቸው ወደሚገኝ ፖሊስ ጣቢያ ቀርበው ጥቆማ ሠጥተዋል።
ፖሊስም ለቀረበው ጥቆማ ተገቢውን ትኩረት በመስጠት መረጃዎችን በማሰባሰብ አራቱንም ተጠርጣሪዎች ካሉበት ቦታ በቁጥጥር ስር ሊያውላቸው ችሏል፡፡
የታዳጊዎቹ ቤተሰቦች በወቅቱ ሴት ልጆቻቸው መታገታቸውን ሲሰሙ ከፍተኛ ድንጋጤ ውስጥ ገብተው እንደነበር ተናግረው ፖሊስ ላከናወነው ተግባርም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
በልጆች አስተዳደግ ዙርያ የቤተሰብ ኃላፊነት ከፍተኛ ሲሆን በአንዳንድ ታዳጊ ወጣቶች ላይ የሚስተዋለው ባህሪ የነገ ተስፋቸውን ሊያጨልም የሚችል በመሆኑ ሊታረምና በወላጆች ዘንድም ከፍተኛ ጥንቃቄና ትኩረት ሊደረግበት እንደሚገባም የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ ጥሪውን ያቀርባል።