13/11/2025
መድሎተ ጽድቅ ፫
ደራሲ: መምህር ያረጋል አበጋዝ
ዘውግ : ሥነ መለኮት
የመ/ር ያረጋል አበጋዝን (ከዚህ በኋላ መዓርጉን ሳልጠቅስ ስሙን ብጠራ የውዴታ እንጂ ክብሩን የመቀነስ ተደርጐ አይወሰድብኝ!) ሦስቱንም ቅጾች አንብቤያቸዋለሁ፡፡ ቅጽ ፩ዱን በተለያየ ጊዜ በልዩ ልዩ አጋጣሚ ተጠቅሜበታለሁ፡፡ ቅጽ ፪ን አንድ ጠበቃና የሕግ አማካሪ የሆነ የደሴ የፌስቡክ ጓዴ ቀድሞ አንብቦ አንዳንድ ነጥቦችን እያነሳሳ ቢተገትገኝ በመቀደሜ አፍሬ አነበብኩት፡፡ በቁጭት ዘለቅሁት፡፡ ቅጽ ፫ቱ ከእኔው ‹‹ጽንዐ ተዋሕዶ›› ጋር በተቀራራቢ ጊዜ ወጥቶ ስለነበረ ከሰነበተብኝ ‹የኅትመቱ እንዴት ይከናወን ይሆን› የሩቅ ሐሳብ መውጫ እንዲሆነኝ ጀመርኩት፡፡ ሳበኝ! ወደዘመኔ ሳበኝ! በተለይ እስከ ገጽ 206 የሚነሡት ጭብጦች አሁናዊ (ዘመናውያኑ contemporary የሚሏቸው) የክርስትና ፈተናዎች በመሆናቸው መሰጠኝ፡፡ ማስታወሻዬን ይዤ ወጣሁት፡፡ ስጨርስ ስለ ለሦስት ነገር መናገር ሻተኝ፡፡ እነዚህም፡- ቢሆን ቢጨመር ኖሮ መልካሙን መጽሐፍ እጅግ በጣም ሸጋ፣ እንደው ‹‹በሰንበት ላይ ደብረ ዘይት›› የሚባለው ዓይነት ዓመት በዓል ያደርገው ነበር ያልኳቸውን ሐሳቦች (ማሳዛኔ! ‹‹ኂስ›› ላለማለት መሽከርከሬ!)፣ የመጽሐፉ ጥቅል በረከት፣ ያረጋል አበጋዝ ምላሽ የሰጠባቸው የተመረጡ ጭብጦች የሚሉ ናቸው፡፡ እንሂድባቸው፡፡
---
ሀ . የመጽሐፉ በረከት
---
ይህ መጽሐፍ የሚሞግተውን ሐሳብ የፍልስፍና መነሻ በመቆፈር ስለሚነሳ በቅርንጫፍ ከመንጠላጠል ያድነናል፡፡ ለተጨማሪና ዘርፈ ብዙ ንባብ ይጋብዛል፡፡ በአቀራረብ ጥልቀቱ ከሃይማኖት ክበብ ውጪ ያለ ልበ ሰፊ ሰውም ሊያነበው የሚችል ጭብጥና አቀራረብ አለው፡፡ ‹‹የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤ/ክ አስተምህሮ /እምነትና ሥርዓት/ እንዲህ ነው!›› ብሎ ደንግጎ ለመነሣት የሚፈልግ የሌላ እምነት ወይም ዓለማዊ ጸሐፊ ሊያጣቅሳቸው ከሚገቡ መጻሕፍት ውስጥ የያረጋል አበጋዝ መድሎተ ጽድቅ ተከታታይ መጻሕፍት አስፈላጊ እንደሆኑ ይሰማኛል፡፡ እንደ ተለመደው ያረጋል የያዘውን ርእስ ያደማል፣ አቀራረቡ ኦሪጅናል ነው፣ ለወደፊት ጸሐፍት መነሻና ማጣቀሻ መሆን ይችላል፣ ክርክራዊ አቀራረቡ ፍሰት አለው፡፡ ቃል ይተረጕማል፣ ያራቅቃል፡፡ ዐውድ ይጠብቃል፤ ከጭብጥ አይወጣም፡፡ ለማስረጃዎች ተገቢነት ትኩረት ይሰጣል፤ ማለትም ጥቅስና የታሪክ ማስረጃ ሲያቀርብ ከጉዳዩ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነና አስፈላገነት ያለውን ነው፡፡ ያረጋል አበጋዝ አያመቻምችም! በዓለም ላይ የሚዋልሉ አሁናዊ ሐሳቦችን ለአንባቢ ውሳኔ ክፍት አድርጎ በምንታዌ አይተዋቸውም፡፡ አዙሮ አሽከርክሮ ኦርቶዶክሳዊውን እይታ ግን እንዲህ ነው ይለናል እንጂ፡፡ የያረጋል ቸርነት ለግል ውሳኔ መንገድ በመክፈት ሳይሆን በመጽሐፉ ዋጋ ነው የሚገኝ፡፡ ከይዘቱ፣ ከማጣቀሻው ብዛት፣ ከወሰደው ጊዜ፣ ከኅትመቱ ጥራት፣ ከመጻሕፍቱ ተፈላጊነት፣ ከጸሐፊው ልፋትና ማንነት (ፕሮፋይል) አንጻር በቤተ ክርስቲያን ጸሐፍት ከሚጻፉ መጻሕፍት ውስጥ በርካሽ እያነበብን ያለነው ያረጋል አበጋዝን ይመስለኛል፡፡ በዚህ በኩል በአንባብያን ስም ‹‹ስለ በጎነትህ እግዚአብሔር ይስጥልን!›› ማለት እፈልጋለሁ፡፡
---
ለ . ያረጋል አበጋዝ ምላሽ የሰጠባቸው የተመረጡ ጭብጦች
---
1. ‹‹ ››፡- ያረጋል አበጋዝ አጥብቆ የሚሞግተው አነጋገር ‹‹ወደ ቃሉ መመለስ›› የሚለውን የተሐድሶዎች ሐሳብ ነው፡፡ የሐሳቡ መዳረሻ ወደ ቃሉ መመለስ ሳይሆን ‹‹ወደ እኛ አረዳድ፣ ወደ ፕሮቴስታንታዊ ትርጓሜ መመለስ›› ማለት ነው ይላል - ለዚያውም በሺህ ከሚቆጠሩ ቅርንጫፎቻቸ ወደ የትኛው ‹‹ተመለሱ›› እንደሚሉ እንኳ ግልጽ እንዳልሆነ ደጋግሞ ይሞግታል፡፡ ይህን ጭብጥ በመድሎተ ጽድቅ ፩ና ፪ ያስነበበን ሲሆን በዚህኛውም ቅጽ (ገጽ 21-23) ያነሳሳዋል፡፡ ለውጥን በሚመለከትም ለውጥ ሁሉ በጎ ነው ከሚል መነሻ መንጎድ ያለበትን ድክመትና በቤ/ክ ሊለወጥ የሚችለውን ሊለወጥ ከማይችለው አለመለየትን እያነሳሳ በተሐድሶዎች የሚቀነቀነው ‹‹ለውጥ›› ማባሪያ የሌለው መበጣጠስ መሆኑን ያለፉትን የ500 ዓመታት ተሞክሮዎች እያነሳ ይሞግታል (ገ.281-311)፡፡
2. ፡- ያረጋል አበጋዝ ሁለት የሃይማኖት ብይኖችን ይተቻል፡፡ አንደኛው ‹‹ሁሉም ሃይማኖት ትክክል ነው›› የሚል ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ‹‹ሌሎች ሃይማኖትም እውነት አላቸው›› የሚል ነው፡፡ ሁለቱንም ይነቅፋል (ገ.31-33)፡፡ ርቱዕና መጽሐፋዊ አካሄድ የሚለው ‹‹ትክክለኛ ሃይማኖት አንዲት ብቻ ናት›› የሚለውን ነው፡፡ እንዲህ ማለት የሌሎችን እምነት መጋፋት ማለት አይደለም፤ ሁሉም የማመን መብት እንዳለው እንደዚህ ብሎ ማመንም መብት ነው፤ ይህን መቃወም በራሱም ፀረ ብዝኃነት ነው፤ ሌሎችን ከማስገደድ ጋር አይያያዝም፡፡ ሌላውን በሰውነቱ ከማክበርም አይከለክልም ይለናል፡፡ ‹‹የሌሎችን የእምነት በጻነት ለማክበር የራሳችንን እውነት መጣል የግድ አይደለም፡፡››(ገ.34)፡፡ ጌታም ‹‹… አውነትን በፍቅር እየያዝን … እንደግ›› አለን እንጂ ‹‹እውነትን ጥለን እንፋቀር አላለንም›› - የያረጋል ማሰሪያ ነው (ገ.92)፡፡ ሁሉም ሃይማኖት ትክክል ነው፤ ዋናው እምነት ነው የሚል አካሄድ ባራኪ አምላክን ፍለጋ ነው ይላል ያረጋል (ገ.35)፡፡ አያይዞም አካሄዱ ‹ፍጹም አውነት የለም፤ እውነት አንጻራዊት ናት› ከሚለው ድኅረ ዘመናዊነት (post modernism) ጋር የተገናኘ መሆኑን በመጥቀስ ‹‹እውነት አንጻራዊት ናት›› ከተባለ ይህ ዐረፍተ ነገር በራሱም ፍጹም አይደለም፤ ምክንያቱም አውነት አንጻራዊት ናት (እውነትን እኔ በሴት ጾታ አደረግኋት እንጂ ያረጋል በወንድ አንቀጽ ነው የሚጠራት) ተብሏል ሲል ይሞግታል (ገ.37)፡፡ ያረጋል አያመቻምችም!
3. ፡- እነዚህን ቃላት ይዘት ተኮር ትርጓሜ ይሰጥባቸዋል፡፡ ሃይማኖት የምንለው ይዘቱን፣ ምንነቱን፣ አጠቃላይ መለያየውን (ከሌሎች ሃይማኖቶች የሚለይበትን አስተምህሮ)፣ ሚዛኑን፣ ቁጥር ተሰጥቶት ‹‹አሐዱ/ አሐቲ/›› ሊባል የሚችል መሆኑን ከገጽ 39 እስከ 104 እየደጋገመ ያሳስበናል፡፡ በእነዚሁ ገጾች ውስጥ እምነትን፡- ውስጣዊና ግላዊ መታመን፣ በደረጃ ከሰው ሰው የሚለያይ እያለ ማሳያ ጥቅሶችን በርከት አድርጎ ያቀርባል፡፡ ብዙ ጊዜ በተሐድሶዎች የሚቀርበውን ‹‹ሃይማኖት በዛ እንጂ እምነት አንዲት ናት›› የሚል ማለዘቢያ ቃል ይገለብጠውና ‹‹ሃይማኖት አንዲት ናት፣ እንደየአማኙ ብርታትና ድክመት የሚለያይ እምነት ነው›› ወደማለት ይወስደናል፡፡ በአንዲት ሃይማኖት ውስጥ እንደየብርታታችን የተለያየ የትንካሬ ደረጃ ያለው እምነት ሊኖረን ይችላል፡፡ ይህ እይታ ‹‹እምነት እንጂ ሃይማኖት አያድንም›› የሚለውን ሃይማኖትን አስተሐቃሪ (ፀረ ዲኖሚኔሽን) መፈክር አጥብቆ ይወድራል፡፡ ጉዳዩ በመድሎተ ጽድቅ ቅጽ ፪ ‹‹መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ››ን በሚነቅፈው ርእስ ስር ቤተ ክርስቲያን በነገረ ድኅነት ያላትን ቦታ በስፋት ከተተነተነበት ነጥብ ጋር እየተገናኘ ቢነበብ ሸጋ ነው፡፡ ነገረ ድኅነትን ከነገረ ቤተ ክርስቲያን በማሰናሰል በኩል ያረጋል ብርቱ ነው፡፡
4. ፡- በሃይማኖት ጉዳይ የትክክል መሆንና አለመሆን ሲነሳ ‹‹ኧረ’ኔ በማንም አልፈርድም!›› የሚለውን ቸልተኛ አባባል ሲገሥጽ አትፍረድ ለምግባር እንጂ ለእምነት አይደለም ይለናል (ገ.98-104)፡፡ ‹‹በሃይማኖት ውስጥ ያለውን እውነት መናገር ማለት ራሱ ጌታ የተናገረውን መመስከር እንጂ በማንም ላይ ፍርድ መፍረድ አይደለም›› (ገ.99) - የያረጋል ቃል ነው፡፡ ይሄ ፍርድ አይደለም ምስክርነት ነው ይለናል (ገ.100)፡፡ ‹‹የሁሉም የሆነ የማንም አይደለም›› የሚለውን የፈረንጅ ብሂል በሚያዘክር መልኩ ሁሉም ሃይማኖት ትክክል ነው ማለት አንዱም ትክክል አይደለም ማለት ነው ይለናል (ገ.102)፡፡
5. ፡- ከገጽ 105 እስከ ገጽ 206 የተተነተነው ይህ ሐሳብ እጅጉን መሳጩና (ካለንበት ውዥንብር አንጻር) ወቅታዊው የመጽሐፉ ክፍል ሆኖብኛል፡፡ የኢትዮጵያን በቁሳዊ እድገት ወደ ኋላ መቅረት ሃይማኖታዊ ተሐድሶ ካለማድረግ ጋር ማገናኘትን፣ ቁሳዊ ስኬትንና ብልጽግናን የጽድቅና የአስተምህሮ ርቱዕነት ለማድረግ መሞከርን፣ የአሜሪካንና የደቡብ ኮርያን ኢኮኖሚያዊ ስኬት አምላካዊ ቡራኬ አድርጎ ማቅረብን ‹‹የልብ አድርስ›› በሆነ የፍሬ ነገር ትንተና፣ አመክንዮና ማስረጃ ይሞግታል፡፡ ሙያውም ለጉዳዩ ቅርበት ያለው መሆኑ ትንተናውን ምሉዕና የሥልጣን (authoritative) እንዳደረገው ይስሰማኛል፡፡ የያረጋል ወርቃማ ብርዕ እንዲህ ትላለች፡- ‹‹ … የክርስቲያን ዋና ዓላማ የእግዚአብሔርን መንግሥቱንና ጽድቁን መፈለግ እንጂ ምድራዊ የሆነውን ብልጽግናና ቁሳዊ ሀብትን መሻት አይደለም፤ ምክንያቱም እነዚህኞቹ እስከ ሠራን ድረስ ለሚያምኑት ብቻ ሳይሆን ለማያምኑትም እንኳ የሚሰጡ ተራ ነገሮች ናቸውና፡፡ በዚህ ዓለም ያሉ ነገሮች የእግዚአብሔር ልጆች በመሆናችን የሚሰጡን የሃይማኖት ዋጋዎች ሳይሆኑ ለሚሠራ ሁሉ ሊገኙ የሚችሉ ናቸው፤ ሰው በመሆናችን የሚሰጡ ናቸው›› (ገ.112)፡፡ እንዲያ ማለት ግን ብልጽግና ርኵሰት ነው ማለት አይደለም፡፡ ‹‹የኢኮኖሚ ብልጽግና እና ምድራዊ ሥልጣኔ የክርስትና ሃይማኖት ዋና ግቦች አይደሉም እንጂ፣ ክርስቲያኖች በዚህ ረገድ ጠንካራ ሥራ መሥራት የለባቸውም ማለት ግን አይደለም፡፡›› (ገ.134)
6.‹‹ ‹‹ና_የኢኮኖሚ_እድገት_የምክንያትና_ውጤት_ግንኙነት_አላቸውን? ጥያቄውን አሳጥሬ ያቀረብኩት እኔ ነኝ - ከገጽ 135 እስከ 160 ለሚደረደሩት የያረጋል የክርክር ነጥቦች ማንሻ እንዲመቸኝ፡፡ ‹‹የፕሮቴስታንት የሥራ ባህል ሥነ ምግባር /Protestant Work Ethic›› የሚለው የማክስ ዌበር ብሂል በምዕራቡ ዓለም የማኅበረ ኢኮኖሚና ፖለቲካዊ አስተሳሰብ የተንሰራፋ ነው፡፡ በየመማሪያ መጻሕፍቱ ነባራዊ ሀቅ የሆነ ያህል ይደጋገማል፡፡ ለጉዳዩ የቀረበ ሙያና ንባብ ያለው ያረጋል ይህን የተዘረጋ ሐሳብ እንዲህ ሲል እየጠቀለለ ያነሳዋል፡- (1) ከነባራዊ ሀቅ አንጻር በዚያ ዘመንም በጀርመን ሀገር ካቶሊክ የሚበዛባት ባቫሪያን የተባለች ግዛት ፕሮቴስታንታውያን ከሚበዙባቸው ግዛቶች ይልቅ እጅግ ሀብታሟ ግዛት ነበረች /ገ.136/፣ (2) የቅኝ ግዛት ዘረፋና ተቋማዊ ለውጦች የእድገቱ መሠረቶች ነበሩ /137/፣ (3)የካፒታሊዝም ዋና ዋና መደቦች የሆኑት ታላላቅ የመሬት ከበርቴዎች፣ ነጋዴዎችና ባንከሮች በዘመኑ እድገት ላይ ነበሩ፤ በኢኮኖሚው ላይ የአይሁዳውያን ሡታፌም አይሏል /ገ.138/፣ (4) ፈጠራዎች ጎልብተው ነበር፤ በተለይም ከ‹‹ጥቁር ሞት›› በኋላ የሰው ኃይል እጥረት መፈጠሩ ፈጠራንና ቴክኖሎጂን አበረታተዋል /ገ.139፣ ገ.142/፡፡ እነዚህ ሁሉ ምንጫቸውና መነሻቸው ከተሐድሶ በፊት ነበር፡፡ (5) አያሌ ጸሐፍት ይህን የዌበር ሐሳብ ሞግተዋል /ገ.143-47/፣ (6)በጂኦፖለቲካ ፍላጎትና በውስጥ አስተዳደር ዲሲፕሊን የመጣውን የደቡብ ኮርያ ኢኮኖሚያዊ እድገት ከአጎራባቾች ጃፓንና ቻይና ፈጣን እድገት እንኳ ሳያነጻጽሩ ለፕሮቴስታንታዊ ሥነ ምግባር በ‹‹በአንበሳ ድርሻ››ነት መስጠት አያስኬድም፣ (7) አጠቃላይ ታሪካዊ እይታው ‹‹ውኃን በሜትር ወይንም ጨርቅን በሊትር›› የሚለካ አውሮፓዊ የሥዕለ ሕሊና መር (euro-centric) የታሪክ አረዳድ ነው - ይላል ባለመገሥጽ ብርዑ ትሑቱ ወንድማችን ቁሳዊ እድገትን ከፕሮቴስታንታዊነት የሚያስተሳስረውን ተሐድሶአዊ ምኞት ሲመክት፡፡
7. ፡- ወደ ዝግመታዊ ለውጥ አውሮፓዊ ሥዕለ ሕሊና የሚያደላው ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ (ገ.165)፣ የ‹‹ሳይማር ያስተማረን›› አባትን ናቂ ራስን አድናቂ የ‹‹ምሩቁ›› ኢትዮጵያዊ መፈክር (ገ.183)፣ መጽልመ ደብተራው አንዳርጋቸው ጽጌ፣ ከሕወኃት እስከ ኢህአፓ ያሉ የ‹‹ያ ትውልድ›› አባላት ከገጽ 195 እስከ 206 በመድሎት እየተመዘኑ ይወቀሳሉ፡፡
8. ‹‹ #ሴኩላሪዝም››_በአውሮፓና_አሜሪካ፡- ያረጋል ወቅትንና የፍልስፍና የመደብ ጀርባን በጥልቀት ተረድቶ ትንታኔ ከሰጠባቸው ርእሶች አንዱ ይሄ ነው፡፡ በቅርቡ ወንድማችን ዳንኤል ክብረት ስለ መንግሥትና ሃይማኖት ግንኙነት ሲናገር የሁለቱን ተቋማት ግንኙነት በአሉታ ከሚመለከተው አውሮፓዊ እይታ ይልቅ ግንኙነቱን በአዎንታ የያዘው የአሜሪካ አካሄድ የተሻለ ነው የሚል ድምጸት ያለው ንግግር ሲናገር ሰምቼ አነበብታለሁ ብዬ ነበር፡፡ የያረጋል መድሎተ ጽደቅ ቅጽ ፫ አንዱ ንባቤ ሆነ ማለት ነው፡፡ ሆኖም የያረጋል ምንጮች የዳንኤል ክብረትን ሐሳብ ስለመደገፋቸው እጠራጠራለሁ፡፡ ያረጋል በማስረጃ ተደግፎ ይናገራል፡-
‹‹በአሜሪካ ቸርቾች ብዙ ሰው ለሚያይ ሰው አሜሪካ ከምዕራብ አውሮፓ በተሻለ በሴኩላሪዝም ያልተጠቃችና ክርስትና በደኅና ሁኔታ ያለባት አገር ልትመስለው ትችል ይሆናል፡፡ ልዩነቱ ግን በአውሮፓ በእግዚአብሔር አናምንም የሚሉ ሰዎች ቸርች አይሄዱም፤ በአሜሪካ ግን ብዙ ኤቴስቶች /በሀልዎተ እግዚአብሔር የማያምኑ ሰዎች/ ቸርች ይሄዳሉ፡፡ ለምን? ምክንያቱም የአሜሪካ ቸርቾች ራሳቸው ሴኩላር ስለሆኑ ነው፡፡ … ‹የአሜሪካ ቸርቾች ውስጣዊ ሴኩላራይዜሽን - internal secularization የተፈጸመባቸው ናቸው፡፡ አውሮፓ ሕዝቡ ከቸርቾቹ እየወጣ በመሄዱ ሴኩላር የሆነ ሲሆን የአሜሪካ ቸርቾች ግን ራሳቸው ሴኩላር በመሆናቸው አባላቶቻቸውን በውስጣቸው ለመያዝ ችለዋል፡፡›› (ገ.127)፡፡
ባጭሩ፡- በአውሮፓ ዓለማዊውና መንፈሳዊው ሕይወት በመስመር ተለይቶ ዓለማዊው እየበረከተ ቢሄድም በመንፈሳዊው ዓለም ያሉት እነዚያው ጥቂቶቹ ከአሜሪካ በተሻለ መንፈሳዊ ለዛና መጽሐፋዊ ስብከት ሲካሄድባቸው የአሜሪካውያኑ ግን ዓለማውያኑን ለመሳብ ሲባል ቸርቿን ዓለማዊት ያደረገ የሳይኮሎጂ፣ የቢስነስ ካውንስሊንግ፣ የስሜታዊነትና የምድራዊ ሕይወት ግልባጮች ሆነዋል፡፡ ዓለማውያንን ለመሳብ ሲባል የተጀመረው ‹‹ልምምድ›› መጨረሻው ዓለማዊት ቸርች መፍጠር ሆነ፡፡ ይህቺ ‹‹ልምምድ›› የምትል ቃል የፕሮቴስታንታውያን ወርቃማ ቃል ስትሆን ሰሞኑን ደግሞ በመሪዎቻችን በኩል ፖለቲካዊ ‹‹ጃርገን›› ሆና በጆሯችን ተሹማለች፡፡ በነገራችን ላይ የያረጋልን መጽሐፍ ካነበብኩ በኋላ የብልጽግና ፓርቲ መሪ የሆኑትን የጠ/ሚ/ር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) ‹‹መደመር›› መጽሐፍ ማንበብ ግድ ብሎኝ ነበር፡፡ እንደፈራሁት በ‹‹ቁሳዊነት›› የታጨቀ አይደለም፡፡ ለሀገራችን ጸሐፍት ቀላል በሆነው ደባትርን የማስተሐቅር ተግባርም አላገኘኋቸውም፡፡ ያዝልቅላቸው!
ሐ . ቢሆን ኖሮ
---
(1) በምንጭ ረገድ በተጠቀማቸው ያልኳቸው ሁለት ምንጮች አሉ፡፡ መጀመሪያ ብሔራውያን ምንጮች ከዚህም በላይ ቢጠቀሱ መልካም ነበር፡፡ ለምሳሌ፡- የፕሮቴስታንት የሥራ ትጋት ለሚለው መላምት የገዳማውያንን በሥራ ክፍፍል የተጋዘ ጥብቅ የሥራ ዲሲፒሊን እንደ መመከቻ መጠቀም ይቻል ነበር፡፡ በ‹‹ሶላ››ዎች - በተለይ ቅጽ ፪ ላይ - የሉተራን ተቺ እየሆነ የመጣውን The New Perspective on Paul /ጳውሎስን በአዲስ ንጻሬ/ በሚል የሚታወቅ እንቅስቃሴ መሰል አቀራረብ የተከተሉ ሥራዎችን ምነው ባያቸው አሰኝቶኛል፡፡
(2) መድሎተ ጽድቅ በሚል የወጡት ሦስት መጻሕፍት በቁጥር ብቻ ከሚለዩ በዐቢይ ርእስ ስር ንዑስ ርእስ ቢጨመር የበለጠ ገላጭ ይሆናል፡፡ ቅጽ ፩ ‹‹ነገረ ድኅነትና ምሥጢራት ላይ የተነሡ ጥቄዎች ሲፈተሹ››፣ ቅጽ ፪ ‹‹አምስቱ የሉተር ሶላዎች /ብቻዎች/ በመጽሐፍ ሚዛን››፣ ቅጽ ፫ ‹‹የተሐድሶዎች ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ታሪካዊ ሐተታዎች ሲመዘኑ›› በሚል ወይም ተቀራራቢ ሐረግ ንዑስ ርእስ ቢወጣላቸው ብያለሁ፡፡
(3) መጽሐፉ ከሚያነሣው ጭብጥና ከማጣቀሻው አንጻር ከማዕከላዊነት በላይ ላሉ ዘመናውያን አንባብያንን የሚደርስ ሆኖ ይታያል፡፡ የአብነት ቤቶቹ አበው ዘመናውያን ሐሳቦች ጋር እንዲተዋወቁ፣ በንባብ ያልጎለመሱ አንባቢዎችም የሚያነሳቸውን ሐሳቦች ተረድተው እንዲከተሉት አንዳንድ ጽንሰ ሐሳቦችን በዋናው መስመር ወይም በኅዳግ ማስታወሻ ቢያብራራ የሚያሰኙ ነጥቦች አሉ፡፡ ለምሳሌ፡- የአዲሱ ዘመን እንቅስቃሴ፣ ኢኩሜኒዝም፣ ሴኩላሪዝም፣ የፕሮቴስታንት የሥራ ሥነ ምግባር፣ የእውነትና የባህል አንጻራዊነት… ወደ ቲዎሪ ያደጉ ሐሳቦች በመሆናቸው ጽንሰ ሐሳባዊ ይዘታቸው አስቀድሞ እየተበየነ ሐተታው ቢቀጥል ለፍሰቱም ለቀጣይ የንባብ አነሳሽነትም ያግዝ ይመስለኛል፡፡
(4) በቃልና ጽንሰ ሐሳብ ብያኔ በኩል የሃይማኖት ትርጓሜ (ገ.39) የግእዙን አረዳድና ሶርያዊ መነሻውን መሠረት ቢያደርግ መልካም ነበር፤ ሃይማኖት ሶርያዊ ምንጭ ያለው የግእዝ ቃል ሲሆን ዋነኛ ትርጓሜውም እምነት (faith) ማለት መሆኑን የፊለክሲኖስ ዘማንቡግ ሥራዎችም ኢንሳይክሎፒዲያ ኢትዮፒካም ይጠቁማሉና፡፡
(5) የአውሮፓን አመለካከት በባህል አንጻራዊነት (cultural relativism) የሚመራ የሚያስመስለው ንባብ (ገ.167) ትክክል አይመስልም፤ የእነርሱ መርህ ዓለም አቀፋዊነት (universalism) ይመስለኛል፡፡ የአውሮፓ የባህል ብይንና የእውነት ብይን የተለያየ ሆኖ ይታየኛል፡፡ ከእውነት አንጻር እውነት አንጻራዊት ናት ወደማለት ያደላሉ፤ ከባህል አንጻር ግን የራሳቸውን አስተሳሰብ ‹‹ዓለም አቀፍ›› ብለው ይጠራሉ፣ የባህል አንጻራዊነትን የሚሰብኩ አፍሪካውያን፣ ኤስያና የመካከለኛው ምሥራቅ ሀገራት ይመስሉኛልና ዳግም ቢታይ፡፡
(6) የኅዳግ ማስታወሻዎች ከቁጥር 160 እስከ 164 እንዳሉ ጥቆማ ይሰጥና ይታለፋሉ (ገ.118)፤ ከታች ስንወርድ አናገኛቸውም፡፡ ችግሩ በእኔ እጅ ባለው ቅጅ ብቻ ካልሆነ ቢታረም፡፡
(7) የብልጽግና ወንጌልን ሰባኪዎችን ከ‹‹ሜይን ስትሪም ፕሮቴስታንት›› መለየት (ጸጋ ዘአብ በቀለ ብልጽግናዎችን እየወቀሰ መልሶ ያላደግነው በኦርቶዶክስ ችግር ነው እያለ ራሱን ቢቃረንም) ለይቶ ማየት ይገባ ነበር፡፡ የብልጽግና ወንጌልን የሚቃወሙ በርካታ ፕሮቴስታንታውያን መኖራቸውን አስታውሶ በዚያው ልክ ይህ አካሄድ ባገራችንም ያደረሰውን ጅምር ምስቅልቅል መጥቀስ ይቻል ነበር - ወቀሳው ጥቅል (hasty generalization) እንዳይሆን፡፡
(8) በተከታታይ በቀረቡት የመድሎተ ጽድቅ ቅጾች በአቀራረባቸው የሙግት መልክም ስላላቸው በተሐድሶዎች በኩል በተደጋጋሚ የሚፈጸሙ የክርክር ጸያፎችን /fallacies/ ከማሳያ ሐረጋት ጋር በዚህኛው ቅጽ ጠቅልሎ በሠንጠረዥ ማቅረብ ቢቻል ብዬ ተመኝቻለሁ፡፡
(9) ስለ ማርቲን ሉተር ሰብእና ለመናገር የዋለው ገጽ የበዛ ሆኖ ታይቶኛል፤ ክርክሩን ሳይሆን ተከራካሪውን ማጥቃት በሚል የሙግት ህፀፅ (fallacy of Ad Hominem) እንዳያሳማ እንደ መስጋት ብያለሁ፡፡ የሰውዬውን የምግባር ድኩምነት ደጋግሜ ሳላነብ አልቀርምና እንደ መታከት ብሎኝም ይሆናል፡፡
(10) ስለ ‹‹ሴኩላሪዝም›› አውሮፓዊና አሜሪካዊ ገጽታ በቀረቡት ነጥቦች ላይ መንግሥትና ሃይማኖት ሊኖራቸው የሚችል ግንኙነት በዐይነ ኦርቶዶክስ ምን መምሰል አለበት የምትል አመላካች መውጫ መንገድ ብትኖር ሸጋ ነበር ብያለሁ፡፡ ይህ ሁሉ ‹‹ቢሆን ኖሮ›› ይህም ቢታከል መጽሐፉ የበለጠ መልካም ይሆን ነበር ለማለት ነው፤ ሆኖም አለመሆኑ የመጽሐፉን ልዕልና አያጎድለውም፤ እንዲህ ማለቴ ፍጽምና ከመሻት ነው፡፡
---
#ሲጠቃለል፡- ኦርቶደክሳዊ አስተሳሰቦችን በአንጻረ ፕሮቴስታንት ለመፈተሸ የፈለገ ሁሉ የያረጋል መጻሕፍትን ቢያነብ መንገዱ ይቃናል፡፡ ኦርቶዶክሳዊ ወጣትማ ግዴታው ነው! ያረጋል አበጋዝ ኦርቶዶክሳዊ ሕይወትን በመጽሐፍም በገቢርም ከሚሰብኩ ወንድሞቻችን አንዱ ነው! ይጻፍ፤ እናነባለን! ያኑርልን ወንድማለም!
Reviewer : በአማን ነጸረ is a Lawyer, Deacon, Author and a Social Critic