30/05/2026
''የሰው ልጅ ድካም፣ የእናት እምባ! የጋዜጠኛ ሶፎንያስ መጨረሻ''
በእውነት ልብ ይነካል፣ ያሳዝናል! ቪዲዮውን ስመለከተው ውስጤ እርብሽ ነው ያለው ።እኛ ሰዎች ስንያዝ እንዲህ ነን? አቅም አለን፣ ጉልበት አለን፣ ሁሉን ማድረግ እንችላለን ብለን የምንፎክርበት የጉልበታችን ቀን አልፎ፣ አቅም አጥተን የምንወድቅበት ቀን ግን ሌላ ፍጡር እንሆናለን። ይህ ድክመት የሁላችንም ነው !
እውነቱን ለመነጋገር፣ ከጋዜጠኛ ሶፎንያስ ጋር በተያያዘ ከዚህ ቀደም በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በተለቀቁ ፣ ከባህላችንም ሆነ ከሃይማኖታችን ያፈነገጠውን ተግባር በተመለከተ፣ ሁላችንም አዝነናል፣ "ለምን?" ብለን ጠይቀናል፣ ተቆጥተናልም። ምክንያቱም ያ ያየነው ህይወት ፍጹም የሚገባና የማይመጥን ስለነበረ ነው።
ነገር ግን፣ ያ ጊዜ አልፎ ዛሬ ቪዲዮው ላይ እንደምናየው ሌላ እጅግ አሳዛኝ ታሪክ ይዞ መጥቷል። በቅርቡ በማህበራዊ ሚዲያ፣ በተለይም በፌስቡክ ገጹ ላይ "ከህመሜ ተፈወስኩኝ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ይቅርታ አድርግልኝ" በማለት ሁላችንንም ያስደሰተ መልዕክት አጋርቶ የነበረው ሶፎንያስ፣ ዛሬ በከፋ ፈተና ውስጥ ይገኛል። በተለይ ደግሞ የወላጅ እናቱ ንግግር ልብ የሚሰብር ነው።
ይህቺ ምስኪን እናት ልጇ ባለትዳር ሆኖ፣ የልጅ ልጅ አሳይቷቸው በጥሩ ህይወት ውስጥ ለማየት እንጂ፣ እንዲህ አይነቱ አስከፊ መከራና ፈተና ላይ ይወድቃል ብለው መቼም አልጠበቁም። ሶፎንያስን ብቻዋን፣ በብዙ መከራ፣ ሊስትሮ ጠርጋ እና ፓርኪንግ ሰርታ ለቁም ነገር ያበቃች ጀግና እናት ናት! ዛሬ ግን የኢትዮጵያ ህዝብ ልጇን ከዚህ የከፋ ስቃይና ህመም እንዲታደግላት በሸገር ኢንፎ ቃለ-መጠይቅ ላይ በዕንባ ስትማጸን ትታያለች።
እናትየው በከፍተኛ ሃዘን፦ "እኔ ከልጄ ህይወት መትረፍ በፊት እዛ ቤት አልመለስም፣ ልጄ መጀመሪያ ህክምና አግኝቶ ይዳንልኝ፣ አድኑልኝ!" እያሉ መላውን የኢትዮጵያን ህዝብ እየለመኑ ነው።
የሚመለከታችሁ የጤና ተቋማት፣ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች እና መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ፤ ይህቺ ምስኪን እናትም ከስጋት ወጥታ፣ የፈሰሰው እምባዋ ታብሶ በሰላም እንድትኖር ሁላችንም የበኩላችንን እንወጣ ።
ፈጣሪ ለወላጅ እናት ብርታትን፣ ለጋዜጠኛ ሶፎንያስ ደግሞ አፋጣኝ ምህረትንና ሙሉ ፈውስን ይላክላቸው! አሜን🙏
በይድነቃቸው ከበደ