26/12/2025
በክልሉ የሰብአዊ መብቶች አያያዝ ሁኔታ መሻሻል ያሳየ ቢሆንም ከተጠርጣሪዎችና ታራሚዎች ጋር በተያያዘ አሁንም ትኩረት የሚፈልጉ ጉዳዮች መኖራቸውን ኢሰመኮ ገለጸ
ዓርብ፣ ታኅሳስ 17 ቀን 2018 ዓ.ም ( )
የአፋር ክልል የነዋሪዎቹን ደህንነትና የሰብአዊ መብቶች አያያዝ ሁኔታን ለማሻሻል እያደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታ ቢሆንም ከተጠርጣሪዎችና ታራሚዎች ጋር በተያያዘ አሁንም ትኩረት የሚፈልጉ ጉዳዮች መኖራቸውን ኢሰመኮ ገለጸ። በዚህም ከሰብአዊ መብቶች አያያዝ ሁኔታ ጋር በተያያዘ በበርካታ ጉዳዮች መሻሻል የታየ ቢሆንም በተለይም የተጠርጣሪዎች ማደሪያ ክፍሎች ደረጃቸውን ያልጠበቁና የታራሚዎች ክፍሎች ደግሞ የተጨናነቁ መሆናቸው የአከባቢውን የአየር ሁኔታ ያላገናዘበ በመሆኑ ትኩረት የሚፈልግና ማስተካከያ የሚያሻው ጉዳይ መሆኑን ኮሚሽኑ ገልጿል።
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በአፋር ክልል ያለውን አጠቃላይ የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ በተመለከተ ከክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እና ሌሎች ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ጋር ታኅሣሥ 9 ቀን 2018 ዓ.ም በሰመራ ከተማ ውይይት ያካሄደ ሲሆን፤ የውይይቱ ዓላማም ኢሰመኮ በክልሉ በተለያዩ ጊዜያት ባካሄዳቸው የሰብአዊ መብቶች ክትትሎችና የምርመራ ግኝቶች መሰረት መሻሻል የታየባቸው ተጠናክረው እንዲቀጥሉና አሳሳቢ ጉዳዮች ላይ ደግሞ የእርምት እርምጃ እንዲወሰድ ያለመ መሆኑ ተገልጿል።
በዚህም በክልሉ የተጠርጣሪዎች ማደሪያ ክፍሎች ደረጃቸውን ያልጠበቁና የአከባቢውን የአየር ሁኔታ ያላገናዘቡ መሆናቸው፤ የታራሚዎች ክፍሎች ደግሞ የተጨናነቁ መሆናቸው እንዲሁም በፖሊስ ጣቢያዎች እና በማረሚያ ቤቶች ያለው የሕክምና፣ የምግብ፣ የአልጋ እና ፍራሽ አቅርቦት በቂ አለመሆን በቂ ትኩረት የሚፈልጉና ማስተካከያ የሚያሻቸው ጉዳዮች መሆናቸውን ኮሚሽኑ ባወጣው መግለጫ አመላክቷል።
በሰሜኑ ጦርነት የተጎዱ የትምህርት፣ ጤና፣ ባንክ እና መብራት አገልግሎቶች መሠረተ ልማቶችን ለመጠገን የተዋቀረው የመልሶ ማቋቋም ጽሕፈት ቤት እንቅስቃሴ፣ ተፈናቃዮችን በዘላቂነት ለማቋቋም የተደረጉ ጥረቶች፣ ሕግን ያልተከተለ እስር እንዳይኖር የተደረጉ ጥንቃቄዎች፣ ተጠርጣሪዎችን በ48 ሰዓት ውስጥ ፍርድ ቤት የማቅረብ ልምድ መሻሻሉ ደግሞ በክልሉ መልካም መሻሻል የታየባቸው ጉዳዮች ሆነዋል።
ከዚህ በተጨማሪም በፖሊስ አባላት የሥነ ምግባር ጉድለት ምክንያት ለሚደርሱ ጉዳቶች ተጠያቂነት እንዲረጋገጥ አመራሮች ቁርጠኝነት ማሳየታቸው፣ ለተጠርጣሪዎች የማደሪያ ክፍሎች፣ የመጠጥ እና የንጽሕና መጠበቂያ ውሃ አቅርቦት እንዲሁም የመጸዳጃ አገልግሎት መሻሻሉ እና የታራሚዎች ዕለታዊ የምግብ በጀት ከ50 ብር ወደ 100 ብር እንዲያድግ መደረጉን መልካም እመርታ የታየባቸው ሲል ኮሚሽኑ አበረታቷል።
በክልሉ ያለውን ሰላም በማስቀጠል፣ የሰብአዊ መብቶች መርሖዎችንና ድንጋጌዎችን በተከተለ መልኩ ባህላዊ የፍትሕ ሥርዓት ዕሴቶችን ከመደበኛው የፍትሕ አስተዳደር ጋር በማቀናጀት በክልሉ ያለውን የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ለማሻሻል ተጨማሪ ጥረቶችን ማድረግ እንደሚገባም የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ አሳስበዋል።
ለዚህም ኢሰመኮ በክልሉ የሚያከናውናቸውን የግንዛቤ ማሳደግ፣ የክትትል እና የውትወታ ሥራዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥል ዋና ኮሚሽነሩ አረጋግጠዋል።
የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሃጂ አወል አርባ በበኩላቸው ኢሰመኮ ያቀረባቸውን ግኝቶች በበጎ እንደሚቀበሏቸው ገልጸው፣ የክልሉ መንግሥት ጥንካሬዎችን ለማስቀጠልና ድክመቶችን ለማረም የሰብአዊ መብቶች ጉዳዮችን በሥራ ዕቅድና መርኃ ግብሮቹ ውስጥ አካቶ እንደሚሠራ ተናግረዋል።
በክልሉ በተለይም ወደመካከለኛው ምሥራቅ የሚደረገውን ሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር ለመከላከል እየተሠሩ የሚገኙ ተግባራትን የጠቀሱት ርእሰ መስተዳደሩ፤ ኢሰመኮ በዚህ ድርጊት ሰለባ በሚሆኑ ሰዎች ላይ የሚደርሱ የሰብአዊ መብቶች ጉዳቶችን እና የባለድርሻ አካላት ኃላፊነቶችን በተመለከተ የግንዛቤ ማሳደጊያ ተግባራትን በማከናወን ጭምር ክልሉ በሚያደርገው የሰብአዊ መብቶች ሁኔታን የማሻሻል ጥረት አበርክቶውን እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦
YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA