Addis Maleda - አዲስ ማለዳ

Addis Maleda - አዲስ ማለዳ አዲስ ማለዳ በቻምፒየን ኮምንኬሽንስ ተዘጋጅታ በሃገራችን ማኅበራዊ ለውጥ ለማምጣት ከሚዲያ የሚጠበቀውን ሚዛን የጠበቀ እና የተረጋገጠ መረጃ ለዜጎች የማድረስ ሚና ለመወጣት የምትሰራ ሚዲያ ነች።

በክልሉ የሰብአዊ መብቶች አያያዝ ሁኔታ መሻሻል ያሳየ ቢሆንም ከተጠርጣሪዎችና ታራሚዎች ጋር በተያያዘ አሁንም ትኩረት የሚፈልጉ ጉዳዮች መኖራቸውን ኢሰመኮ ገለጸ ዓርብ፣ ታኅሳስ 17 ቀን 201...
26/12/2025

በክልሉ የሰብአዊ መብቶች አያያዝ ሁኔታ መሻሻል ያሳየ ቢሆንም ከተጠርጣሪዎችና ታራሚዎች ጋር በተያያዘ አሁንም ትኩረት የሚፈልጉ ጉዳዮች መኖራቸውን ኢሰመኮ ገለጸ

ዓርብ፣ ታኅሳስ 17 ቀን 2018 ዓ.ም ( )

የአፋር ክልል የነዋሪዎቹን ደህንነትና የሰብአዊ መብቶች አያያዝ ሁኔታን ለማሻሻል እያደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታ ቢሆንም ከተጠርጣሪዎችና ታራሚዎች ጋር በተያያዘ አሁንም ትኩረት የሚፈልጉ ጉዳዮች መኖራቸውን ኢሰመኮ ገለጸ። በዚህም ከሰብአዊ መብቶች አያያዝ ሁኔታ ጋር በተያያዘ በበርካታ ጉዳዮች መሻሻል የታየ ቢሆንም በተለይም የተጠርጣሪዎች ማደሪያ ክፍሎች ደረጃቸውን ያልጠበቁና የታራሚዎች ክፍሎች ደግሞ የተጨናነቁ መሆናቸው የአከባቢውን የአየር ሁኔታ ያላገናዘበ በመሆኑ ትኩረት የሚፈልግና ማስተካከያ የሚያሻው ጉዳይ መሆኑን ኮሚሽኑ ገልጿል።

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በአፋር ክልል ያለውን አጠቃላይ የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ በተመለከተ ከክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እና ሌሎች ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ጋር ታኅሣሥ 9 ቀን 2018 ዓ.ም በሰመራ ከተማ ውይይት ያካሄደ ሲሆን፤ የውይይቱ ዓላማም ኢሰመኮ በክልሉ በተለያዩ ጊዜያት ባካሄዳቸው የሰብአዊ መብቶች ክትትሎችና የምርመራ ግኝቶች መሰረት መሻሻል የታየባቸው ተጠናክረው እንዲቀጥሉና አሳሳቢ ጉዳዮች ላይ ደግሞ የእርምት እርምጃ እንዲወሰድ ያለመ መሆኑ ተገልጿል።

በዚህም በክልሉ የተጠርጣሪዎች ማደሪያ ክፍሎች ደረጃቸውን ያልጠበቁና የአከባቢውን የአየር ሁኔታ ያላገናዘቡ መሆናቸው፤ የታራሚዎች ክፍሎች ደግሞ የተጨናነቁ መሆናቸው እንዲሁም በፖሊስ ጣቢያዎች እና በማረሚያ ቤቶች ያለው የሕክምና፣ የምግብ፣ የአልጋ እና ፍራሽ አቅርቦት በቂ አለመሆን በቂ ትኩረት የሚፈልጉና ማስተካከያ የሚያሻቸው ጉዳዮች መሆናቸውን ኮሚሽኑ ባወጣው መግለጫ አመላክቷል።

በሰሜኑ ጦርነት የተጎዱ የትምህርት፣ ጤና፣ ባንክ እና መብራት አገልግሎቶች መሠረተ ልማቶችን ለመጠገን የተዋቀረው የመልሶ ማቋቋም ጽሕፈት ቤት እንቅስቃሴ፣ ተፈናቃዮችን በዘላቂነት ለማቋቋም የተደረጉ ጥረቶች፣ ሕግን ያልተከተለ እስር እንዳይኖር የተደረጉ ጥንቃቄዎች፣ ተጠርጣሪዎችን በ48 ሰዓት ውስጥ ፍርድ ቤት የማቅረብ ልምድ መሻሻሉ ደግሞ በክልሉ መልካም መሻሻል የታየባቸው ጉዳዮች ሆነዋል።

ከዚህ በተጨማሪም በፖሊስ አባላት የሥነ ምግባር ጉድለት ምክንያት ለሚደርሱ ጉዳቶች ተጠያቂነት እንዲረጋገጥ አመራሮች ቁርጠኝነት ማሳየታቸው፣ ለተጠርጣሪዎች የማደሪያ ክፍሎች፣ የመጠጥ እና የንጽሕና መጠበቂያ ውሃ አቅርቦት እንዲሁም የመጸዳጃ አገልግሎት መሻሻሉ እና የታራሚዎች ዕለታዊ የምግብ በጀት ከ50 ብር ወደ 100 ብር እንዲያድግ መደረጉን መልካም እመርታ የታየባቸው ሲል ኮሚሽኑ አበረታቷል።

በክልሉ ያለውን ሰላም በማስቀጠል፣ የሰብአዊ መብቶች መርሖዎችንና ድንጋጌዎችን በተከተለ መልኩ ባህላዊ የፍትሕ ሥርዓት ዕሴቶችን ከመደበኛው የፍትሕ አስተዳደር ጋር በማቀናጀት በክልሉ ያለውን የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ለማሻሻል ተጨማሪ ጥረቶችን ማድረግ እንደሚገባም የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ አሳስበዋል።

ለዚህም ኢሰመኮ በክልሉ የሚያከናውናቸውን የግንዛቤ ማሳደግ፣ የክትትል እና የውትወታ ሥራዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥል ዋና ኮሚሽነሩ አረጋግጠዋል።

የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሃጂ አወል አርባ በበኩላቸው ኢሰመኮ ያቀረባቸውን ግኝቶች በበጎ እንደሚቀበሏቸው ገልጸው፣ የክልሉ መንግሥት ጥንካሬዎችን ለማስቀጠልና ድክመቶችን ለማረም የሰብአዊ መብቶች ጉዳዮችን በሥራ ዕቅድና መርኃ ግብሮቹ ውስጥ አካቶ እንደሚሠራ ተናግረዋል።

በክልሉ በተለይም ወደመካከለኛው ምሥራቅ የሚደረገውን ሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር ለመከላከል እየተሠሩ የሚገኙ ተግባራትን የጠቀሱት ርእሰ መስተዳደሩ፤ ኢሰመኮ በዚህ ድርጊት ሰለባ በሚሆኑ ሰዎች ላይ የሚደርሱ የሰብአዊ መብቶች ጉዳቶችን እና የባለድርሻ አካላት ኃላፊነቶችን በተመለከተ የግንዛቤ ማሳደጊያ ተግባራትን በማከናወን ጭምር ክልሉ በሚያደርገው የሰብአዊ መብቶች ሁኔታን የማሻሻል ጥረት አበርክቶውን እንዲቀጥል ጠይቀዋል።

ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦

YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA

የአልሸባብ የሽብር ቡድን ለሶማሊያና ለቀጠናው ሀገራት ትልቁ አሁናዊ የደህንነት ስጋት ሆኖ መቀጠሉን የተባበሩት መንግሥታት የባለሙያዎች ቡድን አስታወቀዓርብ፣ ታኅሳስ 17 ቀን 2018 ዓ.ም (...
26/12/2025

የአልሸባብ የሽብር ቡድን ለሶማሊያና ለቀጠናው ሀገራት ትልቁ አሁናዊ የደህንነት ስጋት ሆኖ መቀጠሉን የተባበሩት መንግሥታት የባለሙያዎች ቡድን አስታወቀ

ዓርብ፣ ታኅሳስ 17 ቀን 2018 ዓ.ም ( )

የአልሸባብ የሽብር ቡድን ለሶማሊያና ለቀጠናው ሀገራት ትልቁ አሁናዊ የደህንነት ስጋት ሆኖ መቀጠሉን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ባሙያዎች ቡድን ከትናንትና ወዲያ ረቡእ ዕለት ባወጣው ሪፖርት ላይ ገልጿል።

በዚህም አልሸባብ በቀጠናው ደህንነት ላይ፤ በተለይም ደግሞ በኬንያ ደህንነት ላይ ትልቅ አሁናዊ ስጋትን የደገነ መሆኑን ሪፖርቱ አመልክቷል።

ምክንያቱ ደግሞ ቡድኑ ራሱ ያመረታቸውን ተቀጣጣይና ተተኳሾች ጭምር በመጠቀም በኬንያ ላይ ተደጋጋሚ ጥቃቶችን እየፈጸመ የሚገኝ በመሆኑ ነው።

በዚህ ዓመት ብቻ አልሸባብ የሶማሊያ አዋሳኝ በሆኑት ማንዴራና ላሙ የተባሉ የኬንያ ግዛቶች ላይ በአማካኝ በወር ስድስት ጥቃቶችን ፈጽሟል።

“በመሆኑም አልሸባብ በኬንያ የደህንነት ኃይሎች ላይ ያነጣጠሩ ጥቃትቶችን በመፈጸም፣ መሰረተ ልማቶችን በማውደም፣ ከብቶችን በመስረቅ፣ ሴቶችን አፍኖ በመውሰድና በመድፈር ለኬንያ ትልቅ የደህንነት ስጋት ሆኗል” ሲል የተባበሩት መንግስታት የባለሙያዎች ቡድን በሪፖርቱ ገልጿል።

የአልሸባብ የሽብር ቡድን በቀጠናው ላይ የሚፈጥረው የደህንነት ስጋት የሚመነጨው በዋና ከተማዋ ሞቃዲሾ በሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ላይ ግድያ እስከመሞከር የዘለቀ ጥቃት የመፈጸም አቅሙ ብቻ ሳይሆን የቡድኑ ከፍተኛ የሆነ ፕሮፓጋንዳ የመስራት አቅም፣ የተራቀቀ የዝርፊየና ገንዘብ የማግኛ ስልቱ እንዲሁም አደገኛ የአስገድዶ ምልመላ ስልቱ ጭምር መሆኑንም የመንግስታቱ ድርጅት የባለሙያዎች ቡድን አመልክቷል።

የተባበሩት መንግስታት ደርጅት የባለሙያዎች ቡድን ሪፖርት ይህንን ይበል እንጂ የሶማሊያ መንግስት በአልሸባብ ላይ የሚያካሂደውን ጥቃት አጠናክሮ መቀጠሉንና ድልም እየተቀዳጀ መሆኑን ፕሬዚዳንት ሀሰን ሸክ መሀመድ በተደጋገሚ ሲገልጹ መሰማታቸው አይዘነጋም።

ባለፈው ጥቅምት ወር ላይ የሶማሊያ ብሔራዊ ጦርና አጋሮቹ በማዕከላዊ ጁባ ቡአሊ ከተማ ባካሄዱት ዘመቻ የአልሸባብን ተባባሪ መስራችና የቡድኑ የደህንነት መሪ የነበረውን መሀመድ አብዲ ሀሙድ ወይንም በቅፅል ስሙ ጃክፋር ጉሬይ የሚባለውን የአልሸባብ ዋነኛ ሰው መገደሉን መግለጻቸው ይታወሳል።

ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦

YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA

የፌደራሉ መንግስት ‛ በረሃብ ለተጠቁት ’ ሰዎች የሚደረጉ የድጋፍ ማሰባሰብ ዘመቻዎች “ ህገወጥ ናቸው ” ሲል ፈረጀህወሓትንም “ ሰብዓዊ እርዳታ በመስረቅ ” ወንጅሏልሐሙስ፣ ታህሳስ 16 ቀን...
25/12/2025

የፌደራሉ መንግስት ‛ በረሃብ ለተጠቁት ’ ሰዎች የሚደረጉ የድጋፍ ማሰባሰብ ዘመቻዎች “ ህገወጥ ናቸው ” ሲል ፈረጀ

ህወሓትንም “ ሰብዓዊ እርዳታ በመስረቅ ” ወንጅሏል

ሐሙስ፣ ታህሳስ 16 ቀን 2018 ዓ.ም ( )

የፌደራሉ መንግስት “ በማህበራዊ ሚዲያ አማራጮች በቡድንም ሆነ በተናጠል የሚደረጉ የድጋፍ ማሰባሰብ ዘመቻ የአሰራር ስርዓትን የጣሱ ህገ-ወጥ አካሄዶች ” ናቸው ሲል በይኗል።

የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽነር ሽፈራው ተ/ማርያም(ዶ/ር) ‛ ትህነግ ’ እያሉ የጠሩት ህወሓት “ ሕዝብን በረሃብ በመቅጣት ለፖለቲካ መሣሪያነት የመጠቀም ተግባሩን ዳግም በትግራይ ሕዝብ ላይ እያሳየ ነው ” ሲሉ በብርቱ ወንጅለዋል።

‛ የትህነግ ቡድን ’ እያሉ የጠሩት ህወሓት “ የፌደራል መንግስት በትግራይ ክልል በመጠለያ ማዕከላትና በልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር የሚያቀርበውን ሰብዓዊ ድጋፍ ለተፈለገው ዓላማ እንዳይወል እያደረገ እንደሚገኝ ” የጠቀሱት ኮሚሽነሩ፣ የሰሞኑ የሕጻጽ መጠለያ ጣቢያ ማስረጃ መሆኑን ለኢዜአ ነግረውታል።

ህወሓት ይህን ያደርግበታል ያሉትን ምክንያት አስረድተዋል። እሱም “ በትግራይ ክልል በመጠለያ ጣቢያዎች ለሚገኙ ወገኖች የሚቀርብን ሰብዓዊ ድጋፍ በመንጠቅ ” ድራማዊ ፕሮፓጋንዳ ማስተጋባት መሆኑን አመልክተዋል።

ዓለም አቀፉ ማህበረሰብም የፌደራል መንግስት በግልጽ መረጃና ማስረጃ የሚልከው ሰብዓዊ ድጋፍ የት እንደገባ መጠየቅ አለበት ያሉት ሽፈራው “ በቡድኑ የሃሰት ፕሮፓጋንዳ መደናገር እንደሌለበትም ” አሳስበዋል።

የፌደራሉ መንግስት አስተማማኝ ድጋፍ እያደረገ ነው ሲሉ የሚከራከሩት ኮሚሽነሩ ሙግታቸውንም በአሐዝ አስደግፈዋል።

በዚህም በትግራይ ክልል ከባለፈው ጥር 2017 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ታኅሳስ ወር 2018 ዓ.ም ድረስ ሁለት ሚሊየን ኩንታል በገንዘብ ሲተምን 32 ቢሊዮን ብር የሚገመት ሰብዓዊ ድጋፍ መሰራጨቱን አስታውቀዋል።

ይሁንና ህወሓት “ በትግራይ ክልል ሰብዓዊ ድጋፉ ተደራሽ እንዳይሆን በማስተጓጎል፣ ድጋፉን ከችግረኛ ዜጎች በመንጠቅ ዳግም የሕዝብ ጠላትነቱን እያረጋገጠ እንደሚገኝም ” ጠቅሰው ኮንነዋል።

ህወሓትን በብርቱ የወነጀሉት የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽነር ሽፈራው፣ በተናጠልም ሆነ በቡድን የሚደረጉ የድጋፍ ማሰባሰብ ዘመቻዎችም “ የአሰራር ሥርዓትን የጣሱ ህገወጥ አካሄዶች ናቸው ” ሲሉ ተናግረዋል።

“የተለያዩ የማህበራዊ ሚዲያ አማራጮችን በመጠቀም ሰብዓዊ ድጋፍ በማሰባሰብ ላልተገባ ዓላማ እያዋሉ የሚገኙ አካላት ከድርጊታቸው ሊታቀቡ እንደሚገባም ” አሳስበዋል።

ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦

YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA

ዝቅተኛ የደመወዝ ወለልን ለመወሰን ጉዳዩን የሚያጠና ቦርድ ለማቋቋም የሚያስችል ረቂቅ ተዘጋጅቶ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት መላኩ ተገለጸሐሙስ፣ ታኅሳስ 16 ቀን 2018 ዓ.ም ( )በኢትዮጵያ ለረ...
25/12/2025

ዝቅተኛ የደመወዝ ወለልን ለመወሰን ጉዳዩን የሚያጠና ቦርድ ለማቋቋም የሚያስችል ረቂቅ ተዘጋጅቶ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት መላኩ ተገለጸ

ሐሙስ፣ ታኅሳስ 16 ቀን 2018 ዓ.ም ( )

በኢትዮጵያ ለረጅም ጊዜ ሲጠየቅ የቆየውን የሠራተኞችን ዝቅተኛ የደመወዝ ወለልን ለመወሰን ጉዳዩን የሚያጠና ቦርድ ለማቋቋም የሚያስችል ረቂቅ ደንብ ተዘጋጅቶ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት መላኩን የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማሕበራት ኮንፌደሬሽን ለአዲስ ማለዳ አስታወቀ።

የኮንፌደሬሽኑ የሕዝብና የውጭ ግንኙነት መምሪያ ኃላፊ አያሌው አሕመድ ለአዲስ ማለዳ እንደገለጹት የሠራተኛውን ዝቅተኛ የደመወዝ ወለልን የመወሰን ጉዳይ በአንድ ወገን ብቻ የሚወሰን አለመሆኑን አመላክተው፤ በአሠሪ፣ ሠራተኛና መንግሥት ስምምነት መሠረት የሚወሰን መሆኑን ተናግረዋል።

ከዚህ በተጨማሪም ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል በቀጥታ የሚወሰን ጉዳይ አለመሆኑን ያስታወሱት ኃላፊው፤ በቅድሚያ ሦስቱ አካላት ማለትም፤ አሠሪ፣ ሠራተኛና መንግሥት ተስማምተውበት ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል ላይ ጥናት የሚያደርግ ቦርድ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ጸድቆ ከተቋቋመ በኋላ ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል የሚወሰነው ቦርዱ በሚያጠናው ጥናት መሠረት መሆኑንም አስገንዝበዋል።

በአሠሪና ሠራተኛ ሕጉ ላይም “የሀገሪቷን የኢኮኖሚ ሁኔታ እያዬ የሠራተኛውን ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል የሚወስን ቦርድ ይቋቋማል” የሚል ሕግ መኖሩን የተናገሩት ኃላፊው፤ ይሁን እንጂ በተለያዩ ምክንያቶች እስካሁን ድረስ ዝቅተኛ የደመወዝ ወለልን የሚያጠናው ቦርድ ሳይቋቋም መቆየቱን ገልጸዋል።

“እኛም ስንጠይቅ የቆየነው በአሠሪና ሠራተኛ ሕጉ መሠረት ይሄ ቦርድ ተቋቁሞ ሥራውን እንዲሠራ የሚል ነው” ያሉት የሕዝብና ውጭ ግንኙነት መምሪያ ኃላፊው፤ በዚህ መሠረት መንግሥትም ጥያቄውን አምኖበት ዝቅተኛ የደመወዝ ወለልን ለመወሰን ጉዳዩን የሚያጠናው ቦርድ ለማቋቋም የሚያስችሉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ሲሰሩ መቆየታቸውን ተናግረዋል።

በዚህም ሠራተኛውን፣ አሠሪውንና መንግሥትን ያካተተው የሦስትዮሽ አማካሪ ቦርድ በጉዳዩ ላይ በጋራ ሲመክርበት ከቆየ በኋላ ዝቅተኛ የደመወዝ ወለልን የሚያጠናውን ቦርድ ለማቋቋም የሚያስችለው ረቂቅ ሰነድ ደንብ ሆኖ እንዲወጣ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት መላኩን የኮንፌደሬሽኑ የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምሪያ ኃላፊ ለአዲስ ማለዳ ነግረዋታል።

ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦
YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA

ፕሬዝደንት ጣሂብ ኤርዶጋን እስራኤል “ቃሏን አላከበረችም” ሲሉ ወቀሱሐሙስ፣ ታኅሳስ 16 ቀን 2018 ዓ.ም ( )የቱርኩ ፕሬዝደንት ረሲብ ጣሂብ ኤርዶጋን “እስራኤል የገባችውን ቃል አላከበረች...
25/12/2025

ፕሬዝደንት ጣሂብ ኤርዶጋን እስራኤል “ቃሏን አላከበረችም” ሲሉ ወቀሱ

ሐሙስ፣ ታኅሳስ 16 ቀን 2018 ዓ.ም ( )

የቱርኩ ፕሬዝደንት ረሲብ ጣሂብ ኤርዶጋን “እስራኤል የገባችውን ቃል አላከበረችም፤ ሰብዓዊ እርዳታ ወደጋዛ እንዳይደርስ ሆን ብላ እንቅፋት እየፈጠረች ነው” ሲሉ እስራኤልን ወቅሰዋል።

ፕሬዚዳንት ኤርዶጋን ይህን ያሉት ትናንት ረቡዕ እርሳቸው የሚመሩት የፍትሕና ዕድገት ፓርቲ የግዛት አስተዳዳሪዎች ስብሰባ በአንካረ በተካሄደበት ወቅት ሲሆን፤ “እስራኤል የገባችውን ቃል እያከበረች አይደለም፤ የተፈበረኩ ማስተባበያዎችን በማቅረብ ሰብዓዊ እርዳታ ወደጋዛ እንዳይገባ ሆን ብላ ችግር እየፈጠረች፤ የሰብዓዊ እርዳታ ሂደቱንም በተደጋጋሚ እያስተጓጎለች ነው” ሲሉ እስራኤልን ወንጅለዋል።

“በእነዚህ አስደሳች ሦስት ወራት ለፍልስጤም የምናደርገውን ድጋፍ አጠናክረን እንቀጥላለን፤ እንደቱርክ የገባነውን ቃል አናጥፍም፤ ዝም አንልም፤ አንረሳትም፤ መቼም ቢሆን ጋዛን ብቻዋን አንተዋትም” ሲሉም አክለዋል።

“ከካውካስ እስከ ባልካን፣ ከአፍሪካ እስከ እስያ፣ ማንም ቢሆን በችግር ላይ ሆኖ እርዳታ በሚፈልግበት ጊዜ እኛ ቀድመን እዚያ እንገኛለን። ይህ ትናንት የነበረ፤ ዛሬም ያለ ነገም የማይቀየር የእኛ አቋም ነው” ያሉት ፕሬዚዳንት ኤርዶጋን ቱርክ ለፍልስጤም የምታደርገው ድጋፍ ሀገሪቱ በዓለም አቀፉ ደረጃ የምታራምደው የሰብዓዊ እርዳታ ፖሊሲዋ አንድ አካል መሆኑንም አመልክተዋል።

ቱርክ ሰላምን የምትደግፍ ብትሆንም ኢ-ፍትሐዊነትን ግን እንደማትቀበልም ፕሬዚዳንት ኤርዶጋን አጽንኦት ሰጥተውበታል።

“ጥንት እንደምናደርገው ሁሉ ዛሬም ለሰላም ያለንን ፍላጎት ሁሉም ሊያውቀው ይገባል። ይህ ማለት ግን ከኢ-ፍትሐዊነት ጋር እናብራለን፤ ጭቆናንም እንታገሳለን ማለት አይደለም፤ ይህን ፈጽመን አናደርገውም” ሲሉም አቋማቸውን አስረግጠዋል።

ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦
YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA

የቀይ ባሕር አፋር ዲሞክራሲያዊ ድርጅት በቀይ ባሕር አፋር ሕዝቦች ላይ በኤርትራ መንግሥት እየተፈፀመ ያለው ‘የዘር ማጥፋት ወንጀል’ ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ እንዲያውቅለት እንደሚፈልግ አሳወቀ...
24/12/2025

የቀይ ባሕር አፋር ዲሞክራሲያዊ ድርጅት በቀይ ባሕር አፋር ሕዝቦች ላይ በኤርትራ መንግሥት እየተፈፀመ ያለው ‘የዘር ማጥፋት ወንጀል’ ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ እንዲያውቅለት እንደሚፈልግ አሳወቀ

ረቡዕ፣ ታኅሳስ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ( )

ድርጅቱ ጉዳዩን አስመልክቶ ዛሬ በአዲስ አበባ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የኤርትራ መንግሥት በቀይ ባሕር አፋር ሕዝቦች ላይ በኃይል የታገዘ የዘር ማጥፋት ወንጀል እየፈጸመ መሆኑን ገልጾ፤ “እየተፈፀመ ያለውን የዘር ማጥፋት ወንጀል ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ እንዲያውቅልን እንፈልጋለን” ብሏል።

የቀይ ባሕር አፋር ዲሞክራሲያዊ ድርጅት ሊቀመንበር አቶ ኢብራሂም ሀሩን፤ “ገደብ የሌለው ወታደራዊ ግዳጅ እንድንሰጥ እየተገደድን፣ ሴቶቻችን እየተደፈሩ፣ ያለፍርድ እየታሰርን፣ ወደአካባቢያችን ሰው እንዳይገባና ሁኔታውን እንዳያይ የጉዞ ማዕቀብ እየተደረገ፣ ከባሕር እየተገፋን፣ ለብዙ ሺሕ ዓመታት ከኖርንበት መሬታችን በኃይል እየተፈናቀልንና እየተሰደደን፤ ከ1993 ጀምሮ ሆን ተብሎ እየደረሰብን ያለውን የዘር ማጥፋት ዘመቻ ለማጋለጥ ነው እዚህ የተገኘነው” ብለዋል።

በዚህም በኤርትራ መንግስት በቀይ ባሕር አፋር ሕዝቦች ላይ በሚፈጸመው በኃይል የታገዘ የዘር ማጥፋት ዘመቻ ሕዝቡ ወደተለያዩ አካባቢዎች ማለትም ወደየመን፣ ጂቡቲና ሳኡዲ አረቢያ በገፍ ነቅሎ እየተሰደደ መሆኑን ያመለከቱት ሊቀ መንበሩ ለአብነት በኢትዮጵያ ብቻ ሶስት መቶ ሺሕ ተፈናቃዮች መኖራቸውን ተናግረዋል።

“ስለሆነም ሕዝባችን ወደመጥፋት ደረጃ ላይ እየደረሰ በመሆኑ ለአፍሪካም ሆነ ለዓለም ሕዝብ እንዲታወቅልን ሰለፈለግን ነው ዛሬ ይህንን መግለጫ የሰጠነው” ብለዋል።

ድርጅቱ የኤርትራ መንግስት በቀይ ባሕር አፋር ሕዝቦች ላይ እየፈጸመ ያለውን የዘር ማጥፋት ወንጀል በተመለከተ በጋምቢያ ባንጁል ለሚገኘው የአፍሪካ የሰብዓዊ እና ሕዝቦች መብቶች ኮሚሽን ባለ122 ገጽ ክስ ማቅረቡንም ሊቀ መንበሩ ገልጸዋል።

ክሱ የተላከው በአውሮፓውያኑ አቆጣጠር ሰኔ 24 ቀን 2025 መሆኑን ያስታወሱት ሊቀ መንበሩ፤ ክሱን የተቀበለው የአፍሪካ የሰብዓዊ እና ሕዝቦች መብቶች ኮሚሽንም በ60 ቀናት ውስጥ ምላሽ እንዲሰጥበት ክሱን ለኤርትራ መንግስት የላከለት መሆኑን ለድርጅታቸው እንዳሳወቃቸውም ተናግረዋል።

“የራስን ዕድል በራስ መወሰን እስከመገንጠል” የሚል ዓላማን ይዞ ለ28 ዓመታት ያህል በትጥቅ ትግል ላይ የሚገው የቀይ ባህር አፋር ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ሊቀ መንበር “ዋነኛው ትግላችን ኤርትራ ውስጥ ሆነን ራስን በራስ የማስተዳደር መብት እስከመገንጠል የሚለውን ለማስከበር ነው፤ ይህ ካልሆነ ነው ወደሌላ እርምጃ የምንገባው” ብለዋል።

ድርጅታቸው ከኢትዮጵያ መንግሥት “ድጋፍ ይደረግለታል ወይ?” በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄም፤ “የትግላችን ዋነኛው መሰረታችን የአፋር ሕዝብ ነው፤አፋር እስካለ ድረስ ኢትዮጵያ ውስጥ ለመገኘታችን አዎ ኢትዮጵያ ውስጥም አለን፤ ሌሎች ሀገራት ውስጥም አለን፤ እንጂ ከኢትዮጵያ መንግሥት የምናገኘው ምንም ዓይነት ድጋፍ የለም” ሲሉ መልሰዋል።

ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦
YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA

እናት ፓርቲ የፌዴራል መንግሥትና የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር በረሃብ የተጠቁ ወገኖችን “ የፖለቲካ ቁማር መያዣ ከማድረግ እንዲቆጠቡ ” አሳሰበ“ ዘገባው አጠቃላይ ሁኔታውን የማይገልጽ ...
24/12/2025

እናት ፓርቲ የፌዴራል መንግሥትና የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር በረሃብ የተጠቁ ወገኖችን “ የፖለቲካ ቁማር መያዣ ከማድረግ እንዲቆጠቡ ” አሳሰበ

“ ዘገባው አጠቃላይ ሁኔታውን የማይገልጽ ነው ” መንግስት

ረቡዕ፣ ታህሳስ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ( )

እናት ፓርቲ ይህንን ያለው “ረሃብና ጥሙ ጊዜ አይሰጥም ” ሲል ሰይሞ ዛሬ ባወጣውና ለአዲስ ማለዳ በላከላት መግለጫው ነው፡፡

ፓርቲው በትግራይ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች በድርቅና በእርዳታ አቅርቦት ችግር ከፍተኛ ረሃብ መከሰቱንና በመድኃኒት እጦት ዜጎች ለከፋ ችግር መጋለጣቸውን መገንዘብ መቻሉን በመግለጫው አመልክቷል።

“ ችግሩ ከሰሞኑ በይፋ ይነገር እንጂ በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች በተመሳሳይ ኹኔታ በሰቆቃ የሚያሳልፉ በርካታ ወገኖቻችን መኖራቸው ይታወቃል ” በማለት ለችግሩ መንስኤ ናቸው ብሎ ወዳ መላከታቸው ምክንያቶች ይሻገራል፡፡

“ በስደተኞች መጠለያ ያሉ፣ በድርቅ ምክንያት ማምረት ያልቻሉ፣ በአጠቃላይ ክልሉ እጅግ አውዳሚ ከኾነ ጦርነት ማግስት ውስጥ መገኘቱና መሰል ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ ምክንያቶች ችግሮች መፈጠራቸው አይቀሬ በመኾኑ ቅድመ ጥንቃቄና ሰብዓዊ ቀውሶች ሲከሰቱ አፋጣኝ መድረሻ የመፍትሔ አማራጮች ማስቀመጥና ከቁጥጥር ውጭ ከመኾናቸው በፊት መድረስ ይገባ ነበር ” ሲልም ወቅሷል፡፡

መግለጫው ሲቀጥል አሁን ላይ በተለይ በሕጻጽ መጠለያ ጣቢያ ያሉ ዜጎች በረሃብና መድኃኒት እጦት ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰባቸው መሆኑን ጠቅሶ፣ “ መላው ኢትዮጵያውያን ተረባርበው የዕለት ጉርሳቸውንና በዘላቂነት የሚቋቋሙበትን ኹኔታ መፍጠር የቅድሚያ ቅድሚያ የሚሰጠው ተግባር ኾኖ አግኝተነዋል ” ብሏል፡፡

በትግራይ ያለውን እጅግ የባሰበትና ጊዜ የማይሰጠውን ኹኔታ አነሳን እንጂ ችግሩ በአማራ ክልል ባሉ እንደ ደብረ ብርሃን፣ ጃራ፣ መጠለያ ያሉ ወገኖችም በመኖርና በመሞት መሐል ኾነው ቀናቸውን እንደሚገፉ አስታውቋል፡፡

ፓርቲው በመጨረሻም ምክረሃሳብ ያላቸውን ነጥቦች ዘርዝሯል፡፡

በውጭም በውስጥም ያሉ ኢትዮጵያውያን በሚቻለው አቅም ኹሉ ተረባርቦ በረሃብና መድኃኒት እጦት የሚሰቃዩ ወገኖቻችንን እንዲታደጋቸው፣ በዘላቂነትም እንዲያቋቁማቸው ጥሪ ያቀረበበት ነው፡፡

የፌዴራል መንግሥትና የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር እነዚኽን ወገኖች የፖለቲካ ቁማር መያዣ ከማድረግ እንዲቆጠቡ፣ እርዳታዎችን በቀናነት እንዲያሳልጡ እንዲኹም ወደዳግም ግጭት ከሚገፋ አባባሽ ምክንያቶች እንዲቆጠቡ በአደራ ጭምር አሳስቧል፡፡

የፌደራሉ መንግስት በበኩሉ ዛሬ ባወጣው መግለጫ በትግራይ ክልል ሰሜን ምዕራብ ዞን በህፃፅ ጊዜያዊ መጠለያ ጣቢያ የሚገኙ ዜጎች የሰብዓዊ ድጋፍ እንዳልደረሳቸው የሚገልጽ የተሳሳተና የመጠለያ ጣቢያውን አጠቃላይ ሁኔታ የማይገልጽ ነው ሲል ተችቷል፡፡

የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን በኩል የወጣው መግለጫ በሕጻጽ ጊዜያዊ መጠለያ ጣቢያም የሚገኙ ዜጎች ዓመቱን ሙሉ ተመሳሳይ ድጋፍ ሲደረግላቸው እንደነበረ አስታውሶ ከመስከረም ወር 2018 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ታህሳስ ወር 2018 ድረስ የተሟላና ያልተቆራረጠ የምግብ ስብአዊ ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑን መረጃዎች እንደሚያሳዩ ጠቁሟል።

በአሰገደ ወረዳ ህፃፅ ጊዜያዊ መጠለያ ጣቢያ ባለፉት አራት ወራት ለ14 ሺህ 413 ዜጎች ድጋፍ ሲደረግ ቆይቷል የሚለው መግለጫው በተጨማሪም ከአጎራባች መጠለያ ጣቢያ የሚገኙ ዜጎችን ጨምሮ በመስከረም ወር 16 ሺህ 775፣ በጥቅምት ወር 18 ሺህ 290፣ በህዳር ወር 17ሺህ 813 እንዲሁም በታህሳስ ወር የሚያስፈልገው ለ14 ሺህ 413 ዜጎች የሚያስፈልግ ምግብ ተሰራጭቷል ብሏል፡፡

በዚህም በድምሩ 11 ሺህ 406 ኩንታል ምግብ ማለተም ስንዴ፣ ማሽላ፣ ጥራጥሬና የምግብ ዘይት ባለፉት አራት ወራት እንዲዳርሳቸው መደረጉን ገልጾ በገንዘብ ሲተመን ከ257 ሚሊየን ብር በላይ ይሆናል ሲል አትቷል።

በሌላ በኩል በክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር የተለያዩ የሰብአዊ ድጋፍ ችግሮች መኖራቸውንና ተጨማሪ የፌዴራል ድጋፍ እንደሚያስፈልግ ቢጠየቅ ኖሮ በኮሚሽናችን በኩል አስፈላጊውን ድጋፍ ለመፈጸም የሚያስችል ዝግጁነት ያለን መሆኑን ለመግለጽ እወዳለሁ ብሏል፡፡

መንግስት ይን መግለጫ ከማውጣቱ አስቀድሞ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝደንት ሌ/ጄነራል ታደሠ ወረደ ለኢትዮጵያ ህዝቦች ሲሉ ባስተላለፉት መልዕክት የፌደራሉን መንግስት ጨምሮ ለተለያዩ አካላት ድጋፍ እንዲደረግ ጥሪ ማቅረባቸው አይዘነጋም፡፡

[ በዚህ ዘገባ ላይ ተጨማሪ መረጃዎች ታከለውበታል ]

ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦
YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA

ሊቢያ በቱርክ ዋና ከተማ አንካራ አቅራቢያ በደረሰ የአውሮፕላን አደጋ ሕይወታቸውን ላጡት የጦር ኃይል አዛዧና ሌሎች አራት ከፍተኛ ወታደራዊ ባለስልጣናት የሦስት ቀናት ብሔራዊ ኀዘን አወጀችረቡ...
24/12/2025

ሊቢያ በቱርክ ዋና ከተማ አንካራ አቅራቢያ በደረሰ የአውሮፕላን አደጋ ሕይወታቸውን ላጡት የጦር ኃይል አዛዧና ሌሎች አራት ከፍተኛ ወታደራዊ ባለስልጣናት የሦስት ቀናት ብሔራዊ ኀዘን አወጀች

ረቡእ፣ ታኅሳስ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ( )

ትላንና ማክሰኞ እለት በቱርክ ዋና ከተማ አንካራ አቅራቢያ በደረሰ የአውሮፕላን መከስከስ አደጋ የሊቢያ ጦር ኃይል አዛዥ መሀመድ አሊ አህመድ አል ሃዳድ ሕይወታቸው ማለፉ ታውቋል።

ከጦር ኃይል አዛዡ መሀመድ አሊ አህመድ አል ሃዳድ በተጨማሪ ሌሎች ተጨማሪ አራት የሊቢያ ከፍተኛ ወታደራዊ ባለስልጣናት እና ሦስት የበረራ ሰራተኞች በአውሮፕላን አደጋው ሕይወታቸው ማለፉን ዘገባዎች አመልክተዋል።

ይህን ተከትሎም የሊቢያ ብሔራዊ አንድነት መንግሥት የሦስት ቀናት ብሔራዊ ኀዘን አውጇል።

ብሔራዊ ኃዘን በታወጀባቸው ሦስት ቀናት ውስጥ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች ሰንደቅ ዓላማዎች ዝቅ ብለው እንዲውለበለቡ የተወሰነ ሲሆን፤ ሁሉም ክብረ በዓላትና ሌሎች የአደባባይ ትዕይንቶችም ለጊዜው እንዲቆሙ ተወስኗል።

መንግሥት በጦር ኃይል አዛዡና በሌሎች የጦር ኃይል አበላት ሞት የተሰማውን ጥልቅ ኃዘን ገልጾ ለሟች ቤተሰቦችና የሊቢያ ጦር ኃይል አባላት መጽናናትን ተመኝቷል።

የሊቢያ ፕሬዚዳንታዊ መማክርት ኃላፊ መሀመድ መንፊ በኤክስ ገጻቸው ባስተላለፉት መልእክት በበሊቢያው የጦር ኃይል አዛዥ መሀመድ አሊ አህመድ አል ሃዳድ እና ሌሎች ተጨማሪ አራት የሊቢያ ከፍተኛ ወታደራዊ ባለስልጣናት ሞት በእጅጉ ማዘናቸውን ገልጸው፤ “የጦር መሪዎቹ ሞት ለሊቢያ ጦር ሰራዊትና መላው ሊቢያውያን ትልቅ ኪሳራ ነው” ብለዋል። ለቤተሰቦቻቸውና ለመላው ሊቢያውያንም መጽናናትን ተመኝተዋል።

የሊቢያው ጠቅላይ ሚኒስትር አብዱልሃሚድ ዲቤባ በበኩላቸው በፌስቡክ ገጻቸው ባስተላለፉት የሃዘን መግለጫ የጦር አዛዡ ሕልፈት የተከሰተው የልዑካን ቡድኑ ወደ አገራቸው ሲመለሱ በነበሩበት ወቅት መሆኑን ገልጸው፤ “የደረሰው አደጋ ለሀገር፣ ለወታደራዊ ተቋሙ እና ለመላው የሊቢያ ሕዝብ ትልቅ ኪሳራ ነው” ብለዋል።

“ሀገራቸውን በቅንነትና በትጋት ያገለገሉ የዲሲፕሊን፣ የኃላፊነት እና የብሔራዊ ቁርጠኝነት ምሳሌ የሆኑ ወታደራዊ ጀግኖችን አጥተናል” ሲሉም በቁጭት ሃዘናቸውን ገልጸዋል።

የቱርክ ባለስልጣናት በበኩላቸው በአደጋው ዙሪየ ምርመራ መጀመሩን ገልፀው፤ “የአደጋው መንስኤ ሴራ ወይንም የቴክኒክ ብልሽት መሆኑን እናጣራለን” ብለዋል።

ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦
YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA

ኢትዮ ቴሌኮምንና ሳፋሪኮምን ለመደገፍ ተስማምተናል ሲሉ የኬንያው ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ ገለጹማክሰኞ፣ ታህሳስ 14 ቀን 2018 ዓ.ም ( )የኬንያና የኢትዮጵያ መንግሥት ኢትዮ ቴሌኮምንና ሳፋ...
23/12/2025

ኢትዮ ቴሌኮምንና ሳፋሪኮምን ለመደገፍ ተስማምተናል ሲሉ የኬንያው ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ ገለጹ

ማክሰኞ፣ ታህሳስ 14 ቀን 2018 ዓ.ም ( )

የኬንያና የኢትዮጵያ መንግሥት ኢትዮ ቴሌኮምንና ሳፋሪኮምን በጋራ ለመደገፍ መስማማታቸውን ለአንድ ቀን ይፋዊ ሥራ ጉብኝት ወደኢትዮጵያ የመጡት የኬንያው ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ ገልጸዋል።

የአፍሪካ ቀንድ ሰላም እና ፀጥታ እንዲሻሻል ኬንያና ኢትዮጵያ የሚያደርጉትን ትብብር አጠናክረው እንደሚቀጥሉ የገለጹት ፕሬዚዳንት ሩቶ፤ “ለጠንካራ ኢኮኖሚያዊ ትስስር፣ ዲጂታል ዕድገትና የጋራ ብልጽግና ባለን የጋራ ርዕይ ላይ ተመስርተን ለቀጣናው መረጋጋት፣ ለንግግርና ለአፍሪካዊ መፍትሔዎች ያለንን የጋራ ቁርጠኝነት በድጋሚ አረጋግጠናል” ብለዋል።

በጉብኝታቸው ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ጋር ፍሬያማ ውይይት ማድረጋቸውን የጠቆሙት ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ፤ ሁለቱ መሪዎች ከተነጋገሩባቸው ቁልፍ ጉዳዮች መካከል አንደኛው ኢትዮ ቴሌኮምንና ሳፋሪኮምን በጋራ ለመደገፍ መስማማታቸው መሆኑንም አመልክተዋል።

ሁለቱ ተቋማት በቀጠናዊ ገበያው ውስጥ ያሉትን ስትራቴጀካዊ የጋራ ኢንቨስትመንት ዕድሎች በአግባቡ ለመጠቀም ወሳኝ ፋይዳ ያላቸው መሆኑን የገለጹት ፕሬዚዳንት ሩቶ በመሆኑም ኢትዮ ቴሌኮምና ሳፋሪኮም ከኬንያና ከኢትዮጵያ መንግስታት ሙሉ ድጋፍ በሚያገኙባቸው ጉዳዮች ላይ መስማማታቸውን በማሕበራዊ መገናኛ ዘዴ በጻፉት መልእክት መግለጻቸውን አዲስ ማለዳ ተመልክታለች።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ደግሞ ባሰራጩት መልዕክት “ በውይይታችን የሁለትዮሽ ግንኙነታችንን በሚጠናከርበት ሁኔታ ላይ እንዲሁም በአፍሪካ ቀንድ ሰላም እና ፀጥታ ጉዳዮች ላይ ሃሳብ የተለዋወጥን ሲሆን ይኽም በሰላም እና መረጋጋት፣ ንግግር ብሎም በአፍሪካ መር መፍትሔዎች ላይ ያለንን የወል ጽኑ አቋም የሚያሳይ ነበር ” ብለዋል፡፡

ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦
YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA

ብልጽግና ፓርቲ በአምሥት ቀናት ውስጥ ብቻ ለሕዝብ አገልግሎት የሚውሉ ከ37 ሺሕ 500 በላይ ሰዓታትን ማባከኑን ኢዜማ ገለጸማክሰኞ፣ ታህሳስ 14 ቀን 2018 ዓ.ም ( )ብልጽግና ፓርቲ በአም...
23/12/2025

ብልጽግና ፓርቲ በአምሥት ቀናት ውስጥ ብቻ ለሕዝብ አገልግሎት የሚውሉ ከ37 ሺሕ 500 በላይ ሰዓታትን ማባከኑን ኢዜማ ገለጸ

ማክሰኞ፣ ታህሳስ 14 ቀን 2018 ዓ.ም ( )

ብልጽግና ፓርቲ በአምሥት ቀናት ውስጥ ብቻ ለሕዝብ አገልግሎት የሚውሉ ከ 37 ሺሕ 500 በላይ ሰዓታትን ማባከኑን የኢትዮጵያ ዜጎች ለማሕበራዊ ፍትሕ ፓርቲ(ኢዜማ) ዛሬ ከሰዓት ባወጣው መግለጫ አስታወቀ።

“በመንግሥት የሥራ ሰዓት እና ሃብት የፓርቲ ስብሰባ የማድረግ አባዜ መሠረታዊ የሕግ የበላይነት ድንጋጌዎች ተጥሰዋል፤ ዜጎችም ዕለታዊ አገልግሎት ተነፍገው የመልካም አሥተዳደር በደል ደርሶባቸዋል” ብሏል ኢዜማ።

“በአንድ ወረዳ ውስጥ በአማካይ እስከ 300 የመንግሥት ሠራተኞች እንዳሉ ፓርቲያችን ባደረገው የመረጃ ማጣራት ተገንዝቧል” ያለው የኢዜማ መግለጫ፤ በዚህም መሠረት ፓርቲያችን አዲስ አበባ በሚገኙ አስር ወረዳዎች ባደረገው ምልከታ ሠራተኞቹ በሥራ ሰዓታቸው ሊያሳልፉት ከሚገባው ከግማሽ በላይ የሆነውን የሥራ ሰዓት ለፓርቲ ስብሰባ መዋሉን መመልከቱን ገልጿል።

በዚህ መሠረት በእነዚህ ወረዳዎች በአማካይ 150 የሚሆኑት ሠራተኞች ከ 37,500 በላይ ሰዓታትን በዐምስት ቀናት ብቻ እንዳባከኑ ለመረዳት መቻሉን ኢዜማ ባወጣው መግለጫ አመልክቷል።

“ይህ አይነት ስብሰባ በተለያዩ ደረጃዎች እንደሚደረጉ በገዢው ፓርቲ የተለያዩ የማኀበራዊ ትሥሥር ገጾችና ሚዲያዎች እየተገለጹ መሆኑን ወስደን ስሌቱን ከ5000 በላይ የመንግሥት ሠራተኞች ያሉባቸውን ተቋማት ከመረመርን ደግሞ የሚባክነው ሰዓት መጠን ብዙ መሆኑ እና አገልግሎት ማግኘት የሚገባው ማኅበረሰብ ምሬት ምን ያህል እንደሆነ መገመት አዳጋች አይደለም” ሲልም ኮንኗል።

“የመንግሥትን የሥራ ሰዓት ለፓርቲ ሥራ ማዋል ሳያንስ የተበደሉት የሥራ ሰዓታት እና የተጉላላው አገልግሎት ፈላጊው ማኅበረሰብ እንግልት አንፃር ስንመዝነው ጥፋቱን እጥፍ ድርብ ያደርገዋል” ያለው ኢዜማ በመግለጫው፤ ዜጎች በአመለካከት የሚመስላቸውን የፖለቲካ ድርጅት የመደገፍ መብታቸው ላይ ምንም ዓይነት ብዥታ የሌለበት ቢሆንም በሕዝብ ግብር የሚተዳደሩ የመንግሥት ተቋማት የአንድ ድርጅት ተቀጥላ እንዲኾኑ ጫና ማድረግ ግን በሕግም ሆነ በሞራል ፍጹም ተቀባይነት የሌለው መሆኑን አስገንዝቧል።

“ብልጽግና ፓርቲ ትምህርት ያልወሰደው ከኢሕአዴግ ብቻ አይደለም፤ ከአምስት ዓመታት በፊት በተመሳሳይ የምርጫ ወቅት መቃረብን ተከትሎ መንግሥታዊ መዋቅርን እና ሀብትን ባልተገባ መንገድ ለእራሱ ጥቅም በማዋል ሕገወጥ ስብሰባ ያደርግ የነበረ ሲሆን ከዚህ ተግባሩ ከመቆጠብ ይልቅ እንደውርስ ሃጢያት ይዞ መንጎዱን ያሳያል” ሲልም ብልጽግናን ከሷል።

“ይህም ብልጽግና ፓርቲ ለዴሞክራሲ፣ ለሕግ የበላይነትና ለዘላቂ የሕዝብ ጥቅም ደንታ እንደሌለው የሚያሳይ አሳፋሪ ድርጊት ነው” ያለው ኢዜማ፤ በታችኛው የመንግሥት መዋቅር ላለው ሕዝብ በአካባቢ ምርጫ ወኪሎችን ከመረጠ ከ 20 ዓመታት በላይ መቆጠራቸውንም አስታውሷል።

መሠረታዊ የፌደራሊዝም መገለጫ የኾነው የዜጎች በታችኛው መዋቅር የመወከል መብት ባልተጠበቀበት በዚህ ወቅት ብልጽግና ፓርቲ የሚያደርገውን ተጨማሪ በደል ቆም ብሎ እንኳን ለማሰብ አለመቻሉ የበለጠ ድርጊቱን አሳፋሪ ያደርገዋል ሲልም ፓርቲው በመግለጫው ብልጽግናን ኮንኗል።

“አሁንም በተለያየ ጊዜ በተደጋጋሚ እንዳሳወቅነው ሁሉ ፓርቲው ከዚህ እና መሰል ተግባሮቹ እንዲቆጠብ ጥሪ እናደርጋለን፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድም ይህንን ጉድይ በአንክሮ በመከታተል ከዚህ ድርጊቱ እንዲያስቆም እንጠይቃለን” ሲልም ኢዜማ ጥሪ አቅርቧል።

የሕዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም የዜጎች ከአገልግሎት ጋር የተገናኘ በደልን ከፍ ባለ ደረጃ በመከታተል ብልጽግናን ተጠያቂ እንዲያደርግም ኢዜማ በመግለጫው ጥሪ አቅርቧል።

ምንም እንኳን ኢዜማ ይህን ቢልም የገዢው ብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች ስብሰባዎቹ ከፍተኛ ጠቀሜታ ያላቸው መሆኑን በተለያዩ አማራጮች ሲገልጹ ሰንብተዋል፡፡

ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦
YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA

ቻይና ከአንድ መቶ በላይ አሕጉር አቋራጭ ባሊስቲክ ሚሳኤሎችን በሚሳኤል መተኮሻ ስፍራዎች አዘጋጅታ አስቀምጣ ልትሆን እንደምትችል ከፔንታጎን የወጣ ሪፖርት አመለከተማክሰኞ፣ ታህሳስ 14 ቀን 2...
23/12/2025

ቻይና ከአንድ መቶ በላይ አሕጉር አቋራጭ ባሊስቲክ ሚሳኤሎችን በሚሳኤል መተኮሻ ስፍራዎች አዘጋጅታ አስቀምጣ ልትሆን እንደምትችል ከፔንታጎን የወጣ ሪፖርት አመለከተ

ማክሰኞ፣ ታህሳስ 14 ቀን 2018 ዓ.ም ( )

ቻይና ከአንድ መቶ በላይ አሕጉር አቋራጭ ባሊስቲክ ሚሳኤሎችን በሦስት የሚሳኤል መተኮሻ ስፍራዎች ዝግጁ አድርጋ አስቀምጣ ልትሆን እንደምትችል ከአሜሪካው የመከላከያ መስሪያ ቤት ፔንታጎን የወጣ ረቂቅ ሪፖርት አመለከተ።

ቻይና የኒውክሊየር የጦር መሳሪያ ብዛትን ለመገደብ ለሚደረገው የጦር መሳሪያ ቁጥጥር ላይ ለመነጋገር ፍላጎት የሌላት መሆኑንም ፔንታጎን በሪፖርቱ ጠቁሟል።

በአሜሪካ ቺካጎ መሰረቱን ያደረገው “አቶሚክ ሳይንቲስትስ” የተባለ መጽሔት በበኩሉ ከምንጊዜውም በላይ የጦር መሳሪያዋን በዓይነትና በብዛት እየጨመረችና እያዘመነች የምትገኘው ቻይና የኑክሊየር ኃይል ከታጠቀ ማንኛውም ሀገር በላይ የኑክሊየር የጦር መሳሪያዎችን በማከማቸት ላይ የምትገኝ መሆኗን ገልጿል።

ቤጂንግ በበኩሏ ሪፖርቱን፤ “ሆን ብሎ የቻይናን ስም ለማጥፋትና የዓለም አቀፉን ማሕበረሰብ ለማሳሳት ያለመ” ስትል ውድቅ አድርጋዋለች።

ባለፈው ወር የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኒውክሊየር ጦር መሳሪያ ቅነሳ ላይ ከሩስያና ቻይና ጋር ተባብረው ለመስራት መዘጋጀታቸውን መግለጻቸው ይታወሳል።

ይሁን እንጂ ቻይና በዚህ የጦር መሳሪያ ቅነሳ ንግግር ላይ የመሳተፍ ፍላጎት እንደሌላት አሁን ላይ ፔንታጎን ይዞት የወጣውና ሮይተርስ ተመልክቸዋለሁ ያለው ሪፖርት አመላክቷል።

በአሁኑ ሰዓት ቻይና ከአንድ መቶ በላይ የሚሆኑ “ዲ.ኤፍ-31” በመባል የሚታወቁ አሕጉር አቋራጭ ሚሳየሎችን በሞንጎሊያ ድንበር አቅራቢያ በሚገኝ የኒውክሊየር ማከማቻና መተኮሻ ስፍራ ላይ ማስቀመጧን የገለጸው የፔንታጎን ሪፖርት፤ “አሁንም ቢሆን በጦር መሳሪያ ቅነሳ ላይ ለመነጋገር ቻይና ፍላጎት የሌላት መሆኑን ተረድተናል” ሲል ቻይናን ወንጅሏል።

ፔንታጎን ከዚህ ቀደም ባወጣው ሪፖርት የሚሳየል መተኮሻ ስፍራው መኖሩን ገልጾ የነበረ ሲሆን በስፍራው ምን ያህል ሚሳኤሎች እንዳሉ ግን አለመግለጹ ይታወሳል።

ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦
YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA

በትግራይ ክልል ሕጻጽ መጠሊያ ጣቢያ የተከሰተውን ረሃብ በተመለከተ ሁለት የፖለቲካ ፓርቲዎች አስቸኳይ ሰብዓዊ ድጋፍ እንዲደረግ ጥሪ አቀረቡሰኞ፣ ታህሳስ 13 ቀን 2018 ዓ.ም ( )ሁለቱ ፓር...
22/12/2025

በትግራይ ክልል ሕጻጽ መጠሊያ ጣቢያ የተከሰተውን ረሃብ በተመለከተ ሁለት የፖለቲካ ፓርቲዎች አስቸኳይ ሰብዓዊ ድጋፍ እንዲደረግ ጥሪ አቀረቡ

ሰኞ፣ ታህሳስ 13 ቀን 2018 ዓ.ም ( )

ሁለቱ ፓርቲዎች ኢሕአፓና ስምረት ሲሆን ያወጡትን መግለጫም ለአዲስ ማለዳ ልከውላታል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) ባወጣው መግለጫ አሰቃቂውን ጦርነት ተከትሎ ከቤታቸው ተፈናቅለው በየመጠለያ ጣቢያው ያሉ ንጹሀን ዜጎች ዘርፈ ብዙ ችግሮች ሲደርስባቸው መቆየቱን አስታውሷል፡፡

ችግሮቻቸውን የሚፈታላቸው ብቻ ሳይሆን ጉዳዬ የሚላቸውም አካል ባለመኖሩ ለከፋ አደጋ ከተጋለጡ ዓመታት አልፈዋል የሚለው መግለጫው በሕፃፅ የተፈናቃዮች መጠለያ ካምፕ ላይ የደረሰውም ይሄው ነው ብሏል።

ነገር ግን ረሃብ በፍጹም ጊዜ አይሰጥምና ለእነዚህ ወገኖች በአስቸኳይ የሰብዓዊ እርዳታ እንዲደርሳቸውና ጉዳያቸውም በዘላቂነት እንዲፈታ ኢሕአፓ ጠይቋል፡፡

የኢሕአፓ መግለጫ ሲቀጥል ልጆቻቸው በጦርነት ለተማገዱባቸው፤ ጥቂቶች ለስልጣናቸው ሲሉ ከቀያቸው ላፈናቀሏቸው ለእነዚህ ዜጎች የሚደረግ ማንኛውም ድጋፍ እርዳታ ሳይሆን የዜግነት ግዴታ እንደሆነም ሊሰመርበት ይገባል ሲል አሳስቧል፡፡

የጌታቸው ረዳ ስምረት ፓርቲም በተመሳሳይ ያወጣውን መግለጫ ለአዲስ ማለዳ ልኮላታል፡፡

ስምረት በምዕራብ ትግራይ ዞን አስገደ ወረዳ ሕጻጽ የተፈናቃዮች መጠለያ ነዋሪዎች ረሃቡን ለማስቆም እና ወዲያውኑ ለመድረስ ሰብአዊ እና ሞራላዊ ኃላፊነታቸውን መወጣት አለባቸው ብሏል።

ኋላ ቀር ቡድን እያለ የጠራው ህወሓትን ከሕዝቡ በፊት የማዳን መዝሙር በሰብዓዊነት፣ በህሊና፣ በሥነ ምግባር እና በሕግ ተቀባይነት የሌለው ሲሆን ሕዝባችን በዚህ ጽንሰ ሐሳብ እየሞተ ነው ሲልም አክሏል።

ስምረት ሁሉም የሰብአዊ ድርጅቶች ይህንን አሳዛኝ ሁኔታ በአስቸኳይ እንዲፈቱት ጥሪ አቅርቧል፡፡

ይህ ሁኔታ ከሚዲያ ካልተደበቀ በስተቀር በሌሎች አካባቢዎች የተፈናቀሉና የተሰደዱ ወገኖቻችንም የመሰቃየትና የመሞት ኣደጋ እንደተጋረጠባቸዎ ምንም ጥርጥር የለውም ሲልም አትቷል፡፡

“ ህዝባችንን በተሳሳተ መንገድ በመንቀሳቀስ ወደዚህ ደረጃ ያደረሱት ኋላቀር ቡድን እና ተባባሪዎቹ አሁንም የፕሪቶሪያን ስምምነት ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ለማድረግ እና የተፈናቀሉ ወገኖቻችንን ወደ ቤታቸው ለመመለስ ዘላቂ መፍትሄ የሆነውን ህገ መንግስት ለማክበር እየተቸገሩ ነው፤ የትግራይን ህዝብ "በእስር" ውስጥ አስገብቶ ሁሉንም ነገር በስልጣን እና በቡድን ጥቅም ላይ በማዋል የፖለቲካ ቁማር ተጫውቷል፤ እየተጫወተም ይገኛል ” ሲል ወንጅሏል፡፡

በዓለም ዙሪያ የሚገኙ የትግራይ ተወላጆች እና የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት፣ ክልሎች፣ የኢትዮጵያ መንግስት እና ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለተፈናቀሉ እና በአጠቃላይ ለስደተኞች እና በተለይም በህፃፅ ላይ ለደረሰው ከባድ ረሃብ ድጋፍ እንዲያደርጉም ጥሪ አቅርቧል፡፡

ተጨማሪ ዜናዎችንና አዳዲስ መረጃዎችን ለማግኘት የማሕበራዊ ሚዲያ ገጾቻችን ይጎብኙ፦
YouTube ➲ t.ly/vSgS
Telegram ➲ t.ly/SOXU
Facebook ➲ t.ly/flx8
Twitter ➲ t.ly/mxA

Address

Tsehay Messay Bldg, 4th Floor Near Bambis Supermarket
Addis Ababa
63000

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Addis Maleda - አዲስ ማለዳ posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to Addis Maleda - አዲስ ማለዳ:

Share