02/01/2026
ኢትዮጵያ የ1 ቢሊዮን ዶላር የዩሮ ቦንድ ዕዳዋን ለማዋቀር በመርህ ደረጃ ስምምነት ላይ መድረሷ ተሰማ
የገንዘብ ሚኒስቴር፣ በፈረንጆቹ 2024 ሊከፈል የነበረውን 1 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር የዩሮ ቦንድ ዕዳ መልሶ ለማዋቀር ከባለዕዳዎች ኮሚቴ ጋር በመርህ ደረጃ ስምምነት ላይ መድረሱን አስታወቀ።
ባለፉት አስር ቀናት ሲካሄድ የነበረው ዝግ ድርድር ፍሬያማ በሆነ መልኩ መጠናቀቁን ሚኒስቴሩ ገልጿል። በድርድሩ ላይ ከጠቅላላው የቦንድ ዕዳ ከ45 በመቶ በላይ የሚወክሉ ዓለም አቀፍ ተቋማዊ የቦንድ ባለቤቶች የተሳተፉ ሲሆን፣ በሁለቱም ወገኖች በኩል ሕጋዊና የፋይናንስ አማካሪዎች ተገኝተዋል።
ይህ በመርህ ደረጃ የተደረሰው ስምምነት በዋናነት በፋይናንስ ውሎች ላይ ያተኮረ መሆኑ ተገልጿል።
የስምምነቱ ዝርዝር ሁኔታዎች ለዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) እና ለይፋዊ አበዳሪዎች ኮሚቴ የተላከ ሲሆን፣ ይህም የኢትዮጵያ የረጅም ጊዜ የዕዳ ዘላቂነት እንዲረጋገጥና የአበዳሪዎች ይሁንታ እንዲገኝ ለማድረግ መሆኑ ተጠቁሟል።
መንግስት ከባለዕዳዎቹ ኮሚቴ ጋር በመተባበር የፋይናንስ ነክ ያልሆኑ ሌሎች ዝርዝር ጉዳዮች ላይ መስማማት እንደሚጠበቅባቸው አመልክቷል። ይህ ሂደት እንደተጠናቀቀ በፈረንጆቹ 2026 መጀመሪያ ላይ የዕዳ ሽግሽግ ሂደቱን ተግባራዊ ለማድረግ ቁርጠኝነት እንዳለው ገልጿል።