05/11/2024
ኢትዮጵያ ለደቡብ ሱዳን የምታበድረውን ገንዘብ፤ በድፍድፍ ነዳጅ ለማስከፈል የሚያስችል አማራጭ የያዘ ስምምነት በፓርላማ ጸደቀ
ደቡብ ሱዳን ከኢትዮጵያ ለምትበደረው 738.26 ሚሊዮን ዶላር፤ ወደፊት የምትፈጽመውን ክፍያ በድፍድፍ ነዳጅ እንድትመልስ አማራጭ የሚሰጥ የብድር ስምምነት በፓርላማ ጸደቀ። በብድር ስምምነቱ የሚገኘው ገንዘብ፤ በደቡብ ሱዳን እና ኢትዮጵያ ድንበር ከምትገኘው ፓጋክ ከተማ በመነሳት እስከ ፓሎች ከተማ ድረስ ያለውን 220 ኪሎ ሜትር መንገድ ለመገንባት የሚያስችል ነው።
በሁለቱ ጎረቤት ሀገራት መካከል የተደረገው የብድር ስምምነት ዛሬ ማክሰኞ ጥቅምት 26፤ 2017 በተካሄደው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ስብሰባ ላይ በቀረበበት ወቅት፤ ማብራሪያውን በንባብ ያሰሙት በፓርላማ የመንግስት ዋና ተጠሪው ዶ/ር ተስፋዬ በልጅጌ ናቸው። ዶ/ር ተስፋዬ የብድር ስምምነቱ የሁለቱ ሀገራትን ፍላጎት መሰረት ያደረገ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለተግባራዊነቱም የተለያዩ የዝግጅት እና የትብብር ስራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸውን ለምክር ቤቱ አባላት ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ለደቡብ ሱዳን ብድር የምትሰጥበት የስምምነት ሰነድ በዛሬው ዕለት ለፓርላማ ይቀርብ እንጂ፤ ሁለቱ ሀገራት ስምምነቱን የተፈራረሙት በግንቦት 2015 ዓ.ም ነበር። የደቡብ ሱዳን ፕሬዝዳንት ሳልቫ ኪር ማያርዳት በተገኙበት በጁባ ከተማ በተካሄደው የፊርማ ስነ ስርዓት ላይ፤ ኢትዮጵያን በመወከል ፊርማቸውን ያኖሩት የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታው ዶ/ር እዮብ ነበሩ።
ደቡብ ሱዳን በብድር የምታገኘው ገንዘብ፤ በጋምቤላ በኩል ካለው የኢትዮጵያ ድንበር በመነሳት በነዳጅ ሀብት ወደ በለጸገው ፓሎች አካባቢ የሚዘረጋውን መንገድ ወደ አስፋልት ለማሳደግ የሚውል ነው። የመንገድ ፕሮጀክቱ የሲቪል እና የአማካሪ ስራዎች የሚከናወኑት በኢትዮጵያውያን ኮንትራክተሮች እንደሆነ በስምምነቱ ላይ ተጠቅሷል።
በኢትዮጵያ በኩል የመንገድ ፕሮጀክቱ የሚመራው በኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ነው። የደቡብ ሱዳን መንገዶች ባለስልጣን በደቡብ ሱዳን በኩል ተመሳሳይ ኃላፊነት እንደሚወስድ በስምምነቱ ላይ ሰፍሯል። ለፕሮጀከቱ ማስፈጸሚያ ይውል ዘንድ ከኢትዮጵያ መንግስት የሚሰጠው የ738.26 ሚሊዮን ዶላር ብድር፤ በውጪ ምንዛሬ ከሚፈለጉት የውጪ ስራዎች በስተቀር በብር የሚከፈል እንደሆነ ዶ/ር ተስፋዬ በዛሬው የፓርላማ ስብሰባ ላይ አስረድተዋል።
via
ዜና ኢትዮጵያ ለደቡብ ሱዳን የምታበድረውን ገንዘብ፤ በድፍድፍ ነዳጅ ለማስከፈል የሚያስችል አማራጭ የያዘ ስምምነት በፓርላማ ጸደቀ November 5, 2024 FacebookTwitterTelegramWhatsAppEmailCopy URL በቤርሳቤህ ገ...