14/06/2026
በጋሞ ዞን ከ46 ሺህ በላይ ተማሪዎች የሚፈተኑበት የ2018 ዓ.ም ክልል አቀፍ ፈተና ዝግጅት መጠናቀቁ ተገለፀ
በጋሞ ዞን የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥና የፈተና ስርቆትን ለመከላከል የሚያስችሉ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ተጠናቀው የ2018 ዓ.ም የ6ኛ እና የ8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተናዎችን ለመስጠት ሙሉ ዝግጁነት መኖሩን የጋሞ ዞን ትምህርት መምሪያ አስታወቀ።
የጋሞ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ አዲሱ አዳሙ በሰጡት መግለጫ ዘንድሮ በዞኑ በሁለቱም ደረጃዎች በአጠቃላይ 46,354 ተማሪዎች ለክልል አቀፍ ፈተና እንደሚቀመጡ ገልጸዋል።
ፈተናው ፍፁም ሰላማዊ፣ ፍትሃዊና ስኬታማ በሆነ መንገድ እንዲጠናቀቅ ከዞን እስከ ወረዳ ካሉ ባለድርሻ አካላት ጋር ሰፊ የውይይትና የዝግጅት መድረኮች መካሄዳቸውንም ኃላፊው ጠቁመዋል።
እንደ ኃላፊው ገለፃ የፈተና ሂደቱ ተማሪዎች በተረጋጋ መንፈስ እውቀታቸውን እንዲመዝኑ ለማድረግ በሁለት ዙር ተከፍሎ የሚከናወን ሲሆን ፦
የ1ኛ ዙር የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና ከሰኔ 8 እስከ ሰኔ 9 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ የሚሰጥ ሲሆን፤ በዚህ ፈተና ላይ 26,637 ተማሪዎች ይሳተፋሉ። ለዚህም በዞኑ ስር የሚገኙ 543 ትምህርት ቤቶች የተለዩ ሲሆን፣ ሂደቱን በተሳለጠ መልኩ ለመምራት 198 የፈተና ማዕከላት ተደራጅተው ዝግጁ መደረጋቸውን ኃላፊው አብራርተዋል።
የ2ኛ ዙር የ8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና ደግሞ ከሰኔ 11 እስከ ሰኔ 12 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ የሚሰጥ ይሆናል። በዚህ ፈተና ላይ 19,717 ተማሪዎች የሚፈተኑ ሲሆን፤ ፈተናው በ446 ትምህርት ቤቶች ውስጥ ላሉ ተማሪዎች በ159 በተመረጡ የፈተና ማዕከላት ውስጥ እንደሚሰጥ አቶ አዲሱ አስታውቀዋል።
የመምሪያ ኃላፊው አቶ አዲሱ አዳሙ በመግለጫቸው ማጠቃለያ ላይ፤ “ፍትሃዊ እና ጥራት ያለው ትምህርት ለሁሉም!” የሚለውን መሪ ቃል በተግባር ለማዋል የፈተና ማዕከላትን ደህንነት ከማስጠበቅ ጀምሮ የፈተና አስፈጻሚዎችና ታዛቢዎችን ስምሪት የማስተካከል ስራ በልዩ ትኩረት መከናወኑን ገልጸዋል።
ተማሪዎችም በቀሩት ጥቂት ቀናት ራሳቸውን ለፈተናው ብቁ አድርገው እንዲያዘጋጁና ወላጆችም ለልጆቻቸው አስፈላጊውን የሞራልና የጥናት ጊዜ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።
ሰኔ 7/2018
(ጋሞ ዞን መ/ኮሙኒኬሽን)