19/04/2025
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ገ/መስቀል ጫላ የትንሳኤ በዓልን በማስመልከት የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።
የመልዕክቱ ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል፦
ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች በሙሉ እንኳን ለትንሳኤ በዓል በሠላምና ጤና አደረሳችሁ/አደረሰን !
የትንሳኤ በዓል በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ በየዓመቱ በድምቀት የሚከበር፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሰው ልጆች ፍቅር ሲል ክቡር ደሙን ያፈሰሰበት፣ በትንሳኤው ደግሞ ሠላምን ያበሰረበት ታላቅ በዓል ነው።
ህዝበ ክርስቲያኑ ላለፉት ሁለት ወራት በፆም፣ በስግደት፣ በይቅርታና ንሰሃ በመግባት ኢየሱስ ክርስቶስ ያለፈባቸውን የመከራ ቀናትና ትንሳኤ በማሰብ ለዛሬዉ የዋዜማ ቀን ደርሷል።
በዓሉ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰዉ ልጆች የከፈለውን የፍቅር ዋጋ የምናስብበት በመሆኑ እኛም በወንድማማችነት፣ በይቅርታ፣ በአንድነት፣ በመደጋገፍና ከቂምና ጥላቻ በመራቅ መንገዱን የምንከተልበት ሊሆን ይገባል።
ክልላችን ብዝሃ ባህል፣ ቋንቋ፣ እምቅ የመልማት ፀጋ፣ ያልተነኩ የገፀ ምድርና ከርሰ-ምድር ሀብቶች፣ ለኢንቨስትመንት ምቹና ሳቢ ከባቢ እንዲሁም በጋራ ለመልማትና ለመበልፀግ የቆረጡ ታታሪ ሕዝቦች የሚገኙበት ክልል ነዉ።
ፓርቲያችን የክልሉን ሕዝቦች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትና ብልጽግና ለማረጋገጥ በከተማና በገጠር ልዩ ልዩ ፕሮግራሞች ቀርጾ ተግባራዊ እያደረገ ይገኛል።
በክልላችን በሁሉም ዘርፎች የጀመርናቸው የልማት ዉጥኖች፣ መንግስታዊ ኢንሼቲቮች፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ መሻሻሎችና ተስፋ ሰጪ ዉጤቶች እያመጡ ነገን ይበልጥ እንድንናፍቅና እንድንተጋ አድርገዉናል።
ከተባበርንና ከተጋገዝን የክልላችን ብሎም የሀገራችን ብልጽግና ካቀድነዉ ባጠረ ጊዜ እንደሚሳካ አመላካች ዉጤቶች እየታዩ ሲሆን ክልላዊ አንድነታችንን በማጠናከር ለጋራ ራዕያችን ስኬት መትጋት ከሁላችንም ይጠበቃል።
በዓሉን ስናከብር የተቸገሩ ወገኖችን የመጠየቅ፣ የመደጋገፍና የመረዳዳት ኢትዮጵያዊ ባህላችንን በመጠበቅ እንዲሆን በዚህ አጋጣሚ አደራ ለማለት እወዳለሁ።
በድጋሜ ለመላዉ የክርስትና እምነት ተከታዮች በሙሉ መልካም የትንሳኤ በዓል እንዲሆን እመኛለሁ ።
አቶ ገ/መስቀል ጫላ
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ