
13/09/2025
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን።
መስከረም 4 ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ በዓለ ልደቱ ነው፡፡
🔥 ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ
አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቅዱስ ወንጌሉ እንደነገረን በመንግስተ ሰማያት ታላቁ ሰው ወንጌላዊው ዮሐንስ ነው።
ቅዱሱ ሐዋርያ ከዘብዴዎስና ከማርያም ባውፍልያ ተወልዶ በገሊላ አካባቢ አድጐ ገና በወጣትነቱ መድኃኔ ዓለምን ተከትሎታል። ቅዱስ ዮሐንስ ከሐዋርያት ቀድሞ ጌታን ከመከተሉ ባሻገር በምንም ምክንያት ከጐኑ አይጠፋም ነበር። ስለ ንጽሕናውና በጐ የፍቅር ሕሊናው ሕጻን ሳለ በወንድሞቹ ሐዋርያት ዘንድ ሞገሱ ከፍ ያለ ነው።
ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌልን ለመስበክ ዕጣ የደረሰው እስያ ስለነበር ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስን አስከትሎ ሄደ፡፡ ይኽችውም ኤፌሶን በጥንቱ በታናሽ እስያ በዛሬው የቱርክ ግዛት ውስጥ ከተማ ናት፡፡ ዛሬ ኢያዞሎክ ተብላ የጥንት ታሪኳ ጠፍቷል፡፡ አስቀድሞ ቅዱስ ጳውሎስ ወንጌልን ሰብኮባታል፡፡ ደቀ መዝሙሩን ቅዱስ ጢሞቴዎስንም በከተማዋ ላይ ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾሞት ነበር፡፡ እርሱም በግፍ እስከተገደለበት ጊዜ ድረስ ቅዱስ ዮሐንስን እየረዳው በከተማዋ ብዙ አገልግሏል፡፡ በኋላ ግን በግፍ ገድለውታል፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ኤፌሶን ለመሄድ በመርከብ ሲሳፈር መርከቡ በማዕበል ተሰበረ፡፡ ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስን መዕበሉ ወደ አንዲት ደሴት አደረሰው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን በመርከቡ ስባሪ ተንጠልጥሎ በባሕሩ ማዕበል መካከል 40 ቀንና 40 ሌሊት ከኖረ በኋላ ማዕበሉ ተፍቶ አብሮኮሮስ ካለበት ደሴት አደረሰውና ተያይዘው ኤፌሶን ከተማ ገቡ፡፡ የከተማይቱም ሰዎች እጅግ ክፉዎች ስለነበሩ መጀመሪያ ላይ ቅዱስ ወንጌልን መስበክ አልቻሉም ነበር፡፡ እነርሱም እጅግ ክፉዎች መሆናቸውን ስላወቀ ቅዱስ ዮሐንስ ገና ዕጣው ሲደርሰው በሀዘን አልቅሶ ነበር፡፡ አሁንም ከተማው በገቡ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ ምክንያት በመፍጠር ሮምና ለምትባል ሴት የውሽባ ቤቷ እሳት አንዳጅ ሆኖ አብሮኮሮስም ዕቃ አጣቢ ሆነው ተቀጠሩ፡፡ የቀጠረቻቸው ሴትም እጅግ ታሠቃያቸው ጀመር፡፡ ባሮቿ እንደሆኑ ተስማምተው ስለጻፉላት ትደበድባቸውም ነበር፡፡
እነርሱም በታላቅ ጉስቁልና ውስጥ እየኖሩ እያለ በአንዲት ዕለት የአገረ ገዥው ልጅ ለመታጠብ ወደ ውሽባው ቤት ገባ፡፡ በውሽባ ቤቱም የሰይጣን ኃይል ስለነበረበት የመኰንኑን ልጅ አንቆ ገደለው፡፡ የአገሪቱም ሰዎች ሁሉ ለሞተው የመኰንን ልጅ ሊያለቅሱ ሲሰበሰቡ ቅዱስ ዮሐንስም አብሮ ቆሞ ሲመለከት ሮምና መጥታ ‹‹በጌታዬ ልጅ ሞት ልትደሰት መጣህን›› እያለች ረገመችው፡፡ እርሱም ‹‹አይዞሽ አትዘኚ›› አላትና ወደ ሞተው ልጅ ቀርቦ በመስቀል ምልክት ካማተበበት በኋላ በፊቱ እፍ አለበት፡፡ የሞተውም ልጅ ድኖ ተነሣ፡፡ የሀገሪቱም ሰዎች እጅግ ደነገጡ፡፡ ሮምናም ደንግጣ ‹‹እግዚአብሔር የሚሉት አምላክ አንተ ነህን›› ብላ ጠየቀችው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ‹‹በፍጹም እኔ አምላክ አይደለሁም፣ እኔ የእርሱ አገልጋዩና ሐዋርያው ነኝ እንጂ›› አላት፡፡ ሮምናም ስለበደለቻቸው በደል ሁሉ መሪር ዕንባን እያለቀሰች ይቅር እንዲሏት ለመነቻቸው፡፡ እነርሱም አረጋጉዋት፡፡ ከሕዝቡም ውስጥ ብዙዎቹ በጌታችን አመኑ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ሌሎች ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን እያደረገ ወንጌልን እየሰበከ ከጣዖት አገልጋዮች በቀር ሁሉንም አሳምኖ አጠመቃቸው፡፡ አገልጋዮችን ኤጲስቆጶሳትን፣ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ከሾመላቸው በኋላ ወደ ሌሎች አቅራቢያ አገሮች ሄደ፡፡ በመጨረሻም በከሃዲውና በጨካኙ በድምጥያኖስ ዘመን በጣዖት አምላኪዎች ተከሶ ለፍርድ ቀረበ፡፡ በፈላ ውኃ ካሠቃዩት በኋለ በፍጥሞ ደሴት አጋዙት፡፡ በዚያም ሳለ ራእዩን ተመልክቶ ጻፈው፡፡ ድምጥያኖስም ከተገደለ በኋላ ከግዞቱ ተመልሶ ሦስቱን መልእክታቱንና ቅዱስ ወንጌሉን ጽፏል፡፡ ጌታችንም አስቀድሞ ሞትን እንደማይቀምስ ለዮሐንስ ቃል ገብቶለት ነበርና (ዮሐ 21፡22) ጥር 4 ቀን እንደ ኤልያስና ሄኖክ ሞትን እንዳያይ ወደ ብሔረ ሕያዋን ወስዶታል፡፡
ጌታችን ለዮሐንስ ያልነገረው እርሱም ያላስተማረው ምሥጢር የለም፡፡ ወንጌሉን መጻፍ ሲጀምር ‹‹በመጀመሪያ ቃል ነበረ፣ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ…›› ብሎ የጌታችን ነገር ተመራምሮ ለመድረስ ሲል በመሀል መልአኩን በዮርዳኖስ ባሕር ላይ ሲሄድ አገኘው፡፡ መልአኩም የዮርዳኖስን ባሕር በእንቁላል ቅርፊት እየጨለፈ ወደ ውጭ ሲያፈስ ተመለከተው፡፡ ዮሐንስም ተገርሞ ‹‹ምን ማድረግህ ነው›› አለው፡፡ መልአኩም ‹‹የዮርዳኖስን ባሕር ቀድቼ እየደፋሁ ልጨርሰው ነው›› ሲለው ዮሐንስም መልሶ ‹‹ታዲያ በእንቁላል ስባሪ ነውን?›› አለው፡፡ መልአኩም ‹‹አዎን›› አለው፡፡ ዮሐንስም ‹‹በከንቱ ደከምክ›› አለው፡፡ ይህን ጊዜ መልአኩም መልሶ ‹‹አንተስ እንጂ ደግሞ የአምላክን መገኘት፣ አኗኗሩንም ተመራምረህ በጥበብ ለማግኘት ብለህ ‹በመጀመሪያ ቃል ነበረ፣ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ..› ብለህ ጀምረህ የለምን? አንተ ጌታን ተመራምረህ ካገኘህና ከደረስክበት እኔም የዮርዳኖስን ወንዝ በዚህ እንቁላል ቅርፊት ቀድቼ እጨርሰዋለሁ›› አለው፡፡ ዮሐንስም ይህን ጊዜ ደንግጦ ዝቅ ብሎ ‹‹ስሙ ዮሐንስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ…›› ብሎ ሀሳቡን ለወጠና ሌላ ታሪክ ቀጠለ፡፡
እናቱም በሕፃንነቱ ስለሞተች እመቤታችን ናት እየተንከባከበች ያሳደገችው፡፡
ጌታችንን እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ በመከተሉ ክርስቲያኖችን ሁሉ ወክሎ በአደራ ድንግል እመቤታችንን ተቀብሏል። ከእርሷ ጋር ለ15 ዓመታት እየተንከባከበ ቢቀመጥ መዝገበ ምሥጢር ሆነ። ስንኩዋን ከሰው ልጆች ይቅርና ከልዑላኑ መላዕክትም ማዕረጉ ከፍ አለ። ሰው ቢበቃ መላእክትን ሊያይ ይቻለዋል። ቅዱስ ዮሐንስን ግን መላእክት ሊያዩት ይከብዳቸዋል። ከፍጥረት ወገን ከእመ ብርሃን ቀጥሎ ክቡር እርሱ ነው።
ቅዱስ ዮሐንስ በመልኩም ከጌታችን ጋር ይመሳሰል ነበር፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ሥዕል የመሳል ተሰጥኦም ነበረው፡፡ ጌታችን በተሰቀለበት ዘመን የነበረው ጢባርዮስ ቄሳር ልጁ በሽተኛ ነበር፡፡ የጌታችንን የማዳን ሥራ እየሰማ እነ ጲላጦስም ስለጌታችን የሚጽፉለትን ይሰማ ስለነበር ልጁን ከጌታችን መቃብር ላይ እንዲያኖሩለት ላከው፡፡ ልጁም ፈጥኖ ተፈወሰለት፡፡ ጢባርዮስ ቄሳርም በልጁ መዳን ምክንያት የጌታችንን ውለታ ማስቀመጥ ፈልጎ የጌታችንን ሥዕሉን የሚሥልለትን ሲያጠያይቅ ዮሐንስን አገናኙት፡፡ ዮሐንስም ጌታችንን ልክ በዕለተ ዓርብ እንደተሰቀለ አድርጎ በመሣል ለጢባርዮስ ቄሳር ሰጠው፡፡ ሲሥለውም በመጀመሪያ ጌታችንን ልክ እንደተሰቀለ አድርጎ ራቁቱን ነበር የሳለው፡፡ ዮሐንስ የሳለው የጌታችን ሥዕልም አፍ አውጥቶ ‹‹በመጀመሪያ አይሁድ በኢየሩሳሌም ራቁቴን ሰቀሉኝ፣ አሁን ደግሞ አንተ ድጋሚ በሮም ራቁቴን ትሰቅለኝን?›› ብሎ ተናገረው፡፡ ዮሐንስም እጅግ ደንግጦ ‹‹እንዴት አድርጌ ልሳልህ?›› ብሎ የሳለውን ሥዕል ቢጠይቀው ሥዕሉም ‹‹ከለሜዳ አልብሰህ ሳለኝ›› አለው፡፡ ዮሐንስም እንዳለው ከለሜዳ አልብሶ ከሳለው በኋላ ሥዕሉን ትኩር ብሎ ተመልክቶ ቢስመው ከንፈሩ አንድ ቀን ተኩል ያህል ተጣብቆ ቆይቷል፡፡ ዛሬም ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የምትጠቀምባቸውን የጌታችንን ስነ ስቅለት የሚያሳዩ ሥዕሎች መገኛቸው ይህ ወንጌላዊው ዮሐንስ የሳለው ሥዕል ነው፡፡
ቅዱሱ ከጌታችን ዕርገት በሁዋላ ለ70 ዓመታት በዚህ ምድር ሲኖር አብዛኛውን ጊዜውን ያሳለፈው በኤፌሶን አካባቢ ነው። ሕዝቡን ወደ ክርስትና ለማምጣት በአፍም በመጽሐፍም ደክሟል።
ሶስት መልዕክታት ፣ ራዕዩንና ወንጌልን ጽፎላቸዋል። ሕይወትን ስለ ሰበከላቸው በፈንታው ብዙ አሰቃይተውታል። ከእሳት እስከ ስለት: እስከ መጋዝም በስተእርጅና ደርሶበታል። እርሱ ግን በትእግስቱ ገንዘብ አድርጉዋቸዋል።
ቅዱስ ዮሐንስ በእናት ቤተ ክርስቲያን በተለያዩ ስሞች ይጠራል፡፡
➛ ፍቁረ እግዚእ
በሕይወቱና በኑሮው ሁሉ ጌታችንን ለመምሰል ይጥር ነበርና ጌታችንም እጅግ ይወደው ስለነበር "ፍቁረ እግዚእ" ተብሎ ይጠራል።
➛ ዮሐንስ ወልደ ዘብድዮስ
የታላቁ ያዕቆብ ታናሽ ወንድም ስለሆነና አባቱም ዘብድዮስ ስለሚባል ዮሐንስ ወልደ ዘብድዮስ ይባላል።
➛ ወልደ ነጎድጓድ
ለጌታችን ባለው ቅናትና ከወንድሙ ጋር ሆነው ባሳዩት የኃይል ሥራ እንዲሁም የጌታችንን አምላክነት በመግለጡ "ወልደ ነጎድጓድ" ተብሏል።
➛ ታኦሎጐስ (ነባቤ መለኮት)
ነገረ መለኮትን ከሌሎቹ በበለጠ ሁኔታ አስፍቶና አምልቶ በማስተማሩ "ነባቤ መነኮት ወይም ታኦሎጎስ" ተብሏል
➛ አቡቀለምሲስ (ምሥጢራትን ያየ)
ኃላፊውንና መጻዒውን ጊዜ በራእዩ ስለገለጠ "አቡቀለምሲስ" ይባላል። ይህም በግሪክኛ ባለራእይ ማለት ነው።
➛ ቁጹረ ገጽ
የጌታችንን መከራ መስቀሉን እያስታወሰ 70 ዘመን ሙሉ እያለቀሰ ስለኖረና ፊቱም በሀዘን ስለተቋጠረ "ቁጹረ ገጽ" ተብሏል፡፡
➛ ወንጌላዊ
➛ ሐዋርያ
➛ ሰማዕት ዘእንበለ ደም
➛ ደቀ መለኮት ወምሥጢር
➛ ርዕሰ ደናግል (የደናግል አለቃ)
➛ ዘረፈቀ ውስተ ሕጽኑ ለኢየሱስ (ከጌታ ጎን የሚቀመጥ)
➛ ንስር ሠራሪ
➛ ልዑለ ስብከት
➛ ምድራዊው መልዐክ
➛ ዓምደ ብርሃን
➛ ሐዋርያ ትንቢት
➛ ቀርነ ቤተ ክርስቲያን
➛ ኮከበ ከዋክብት
በዚህች ዕለት ቅዱሱ ሐዋርያ ከእናቱ ማርያም ባውፍልያ ፤ ከአባቱ ዘብዴዎስ መወለዱን ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች።
በቅዱስ ዮሐንስ ላይ ያደረ የእመቤታችን ድንግል ማርያምና የአንድ ልጇ ፍቅር በእኛም ላይ ይደር። ቸሩ ጌታ ስም አጠራራቸው ካማረና ከከበረ ወዳጆቹ በረከትን ያሳትፈን::
➛ መስከረም 4 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ ኢያሱ ወልደ ነዌ (ነቢይና መስፍን)
2.ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ (ልደቱ)
3.ቅዱሳን ዘብዴዎስና ማርያም ባውፍልያ
4.አባ መቃርስ ሊቀ ዻዻሳት
5.አባ ሙሴ ዻዻስ
➛ ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ እንድርያስ ሐዋርያ
2.ቅድስት ሶፍያ ሰማዕት
3.ቅዱስ ዮሐንስ ዘሐራቅሊ (ሰማዕት)
"አሁንም እግዚአብሔርን ፍሩ። በእውነተኛም ልብ አምልኩት . . . እግዚአብሔርን ማምለክ ክፉ መስሎ ቢታያችሁ . . . የአሞራውያንን አማልክት ታመልኩ እንደ ሆነ: የምታመልኩትን ዛሬ ምረጡ። እኔና ቤቴ ግን እግዚአብሔርን እናመልካለን።"
(ኢያሱ. 24:14)
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአማላጅነታቸው የምንታመን የተዋሕዶ ልጆች የሆንን ሁላችንን የድባውን የአቡነ ሙሴን፣ የወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስንና የነቢዩን የቅዱስ ኢያሱን ረድኤት በረከታቸውን ያሳድርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን፡፡
ምንጭ፦ የመስከረም ➍ እና የጥር ወር ስንክሳር ፣
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ጸሎት ይማረን። አሜን።
⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼
ከታች ያለውን ማስፈንጠሪያ በመጫን ቤተሰብ ይሁኑ
Tᴇʟᴇɢʀᴀᴍ - https://t.me/Synaxarium
Fᴀᴄᴇʙᴏᴏᴋ
🔸https://m.facebook.com/MeseleNigatuDek0
መስከረም ❸ 🀄️ን 2011 ዓ.ም