ስንክሳር

ስንክሳር Ethiopian Synaxarium

"ፍቅር ያጌብረኒ ከመ እንግር ዜናሆሙ ለቅዱሳን"

"የቅዱሳንን ዜና(ታሪክ) እንድመሰክር ፍቅር ያስገድደኛል"
(አባ ጊዮርጊስ) ከሁሉ በላይ በምትሆን ሐዋርያት በሰበሰቧት በአንድት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን።

ታኅሣሥ 4 ጌታችን 5 እንጀራና ሁለቱን ዓሣ አበርክቶ ሕዝቡን ሲመግብ እንጀራውንና ዓሣዎቹን የያዘውን ወጣት ወደ ጌታችን ወስዶ እንዲባረክ ያደረገው የወጣቶች ሐዋርያ ፤ ሐዋርያው ቅዱስ እንድር...
12/12/2025

ታኅሣሥ 4 ጌታችን 5 እንጀራና ሁለቱን ዓሣ አበርክቶ ሕዝቡን ሲመግብ እንጀራውንና ዓሣዎቹን የያዘውን ወጣት ወደ ጌታችን ወስዶ እንዲባረክ ያደረገው የወጣቶች ሐዋርያ ፤ ሐዋርያው ቅዱስ እንድርያስ እረፍቱ ነው።

በሀገራችን በስሙ የተሰየመ ቤተክርስቲያን መኖሩን አላውቅም እንጂ፤ ሐዋርያው በሩሲያ፣ በቢታንያ፣ በገላቲያና በሩማንያ ወንጌልን ሰብኮ ብዙ ክርስቲያኖችን አፍርቷል፡፡ የቍስጥንጥንያ የመጀመሪያው ሊቀ ጳጳስ ነው፡፡ በግሪክ ሲያስተምር ከሃዲያን ይዘው በ60 ዓ.ም ታኅሣሥ 4 ቀን ሰቅለው ገድ.ለው,ታል፡፡

ሊሰቅሉት ሲወስዱትም ‹‹ጌታዬ በተሰቀለበት ዓይነት መስቀል አትስቀሉኝ›› በማለት ሲለምናቸው እነርሱም ፍቃዱን ፈጽመውለት የእንግሊዝኛውን ኤክስ (X) ፊደል ቅርጽ ባለው መስቀል ላይ ሰቅለውታል፡፡

ስኮትላንዶች የቀኝ የእጆቹን ጣቶች በአንድ መነኩሴ አማካኝነት ስላገኙ ሐዋርያው እንድርያስን ‹‹ጠባቂያችን›› ነው እያሉ ይመኩበታል፡፡

በሌሎች ሀገራት የሚከበረውን የሐዋርያው ቅዱስ እንድርያስ መታሰቢያ በዓል ድባብ ከዛሬ ማታ ጀምሮ አጋራችኋለሁ።

እስከዚያው ከዕለቱ ስንክሳር ስለ ተጋድሎው አንብቡ

https://www.facebook.com/share/p/1AHRp4agUX/
ᴍᴇsᴇʟᴇ ɴɪɢᴀᴛᴜ ᴅᴇᴋᴏ

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን። ታኅሣሥ 4 ሐዋርያው ቅዱስ እንድርያስ ዕረፍቱ ነው፡፡ እንድርያስ ማለት ‹‹ጽኑ በኩር›› ማለት ነው፡፡ ሐዋርያው እንድርያስ የ...
12/12/2025

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን።
ታኅሣሥ 4 ሐዋርያው ቅዱስ እንድርያስ ዕረፍቱ ነው፡፡

እንድርያስ ማለት ‹‹ጽኑ በኩር›› ማለት ነው፡፡ ሐዋርያው እንድርያስ የሐዋርያው የቅዱስ ጴጥሮስ ወንድም ሲሆን በመጀመሪያ የተጠራ ሐዋርያ ነው፡፡ በመጀመሪያ የመጥምቁ ዮሐንስ ደቀ መዝሙር የነበረ ቢሆንም መጥምቁ የጌታችንን መንገድ ሲጠርግና ስለ ክርስቶስም ሲሰብክ ስለሰማው በዚያው የጌታችን ደቀ መዝሙር ሆኗል፡፡ ከሰው ጋር ፈጥኖ የመግባባት ችሎታ ስለነበረው በሐዋርያትም ዘንድ እንደ አስተባባሪ ይቆጠር ነበር፡፡ ጌታችን 5 እንጀራና ሁለቱን ዓሣ አበርክቶ ሕዝቡን ሲመግብ እንጀራውንና ዓሣዎቹን የያዘውን ወጣት ወደ ጌታችን ወስዶ እንዲባረክ ያደረገው እንድርያስ ነው፡፡ በዚህም የወጣቶች ሐዋርያ እየተባለ ይጠራል፡፡

ሐዋርያው በሩሲያ፣ በቢታንያ፣ በገላቲያና በሩማንያ ወንጌልን ሰብኮ ብዙ ክርስቲያኖችን አፍርቷል፡፡ የቍስጥንጥንያ የመጀመሪያው ሊቀ ጳጳስ ነው፡፡ በግሪክ ሲያስተምር ከሃዲያን ይዘው በ60 ዓ.ም ታኅሣሥ 4 ቀን ሰቅለው ገድለውታል፡፡ ሊሰቅሉት ሲወስዱትም ‹‹ጌታዬ በተሰቀለበት ዓይነት መስቀል አትስቀሉኝ›› በማለት ሲለምናቸው እነርሱም ፍቃዱን ፈጽመውለት የእንግሊዝኛውን ኤክስ (X) ፊደል ቅርጽ ባለው መስቀል ላይ ሰቅለውታል፡፡

ስኮትላንዶች የቀኝ የእጆቹን ጣቶች በአንድ መነኩሴ አማካኝነት ስላገኙ ሐዋርያው እንድርያስን ‹‹ጠባቂያችን›› ነው እያሉ ይመኩበታል፡፡
ሐዋርያው ቅዱስ እንድርያስ ወንጌልን እየሰበከ በጽርዕ አገር ሳለ ክብር ይጋበውና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠለትና እንዲህ አለው፡- ‹‹ሰውን የሚበሉ ሰዎች ማትያስን ይዘው አሥረውታል፣ ከሦስት ቀንም በኋላ ሊበሉት ከእሥር ቤታቸው ያወጡታልና አንተ አሁን ወደ እነዚያ ሰውን ወደሚበሉት ሰዎች አገር ሂድ›› አለው፡፡ እነዚህም ሰውን ስለሚበሉት ሰዎች ለማወቅ ካስፈለገ የሐዋርያውን የማትያስን ገድል መመልከቱ ተገቢ ነው፡፡ ወይም በቅድስት ‹‹ፍቅርተ ክርስቶስ›› ገድል ላይም በስፋት ተጠቅሷል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ማትያስ በአስቆሮቱ ይሁዳ ምትክ ከተተካ በኋላ ሰውን ወደሚበሉ ሰዎች አገር ሄዶ ወንጌልን ይሰብክ ዘንድ ዕጣ ደረሰው፡፡ ይህችም ሀገር እስኩቴስ የተባለች የሩሲያ ክፍል እንደሆነች የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊዎች ተናግረዋል፡፡ ማትያስም እነዚህ ሰውን የሚበሉ ሰዎች አገራቸው እንደደረሰ ዓይኑን አውጥተው አሠሩት፡፡ ምግባቸውም የመጻተኛ ሰው ሥጋ ነው፡፡ በልማዳቸው መሠረት መጻተኛን ሰው ገና እንደያዙት ዓይኖቹን አውጥተው በእሥር ቤት ያኖሩታል፡፡ እስከ 30 ቀንም ድረስ ሳር እያበሉ ያስቀምጡትና በ30ኛው ቀን ከእሥር ቤታቸው አውጥተው አርደው ይበሉታል፡፡ ሐዋርያው ማትያስንም እንደ ሥርዓታቸው ዓይኖቹን አውጥተው አሥረውት ሳለ 30ኛው ቀን ሳይፈጸም ነው ጌታችን ለሐዋርያው እንድርያስ ተገልጦለት ሄዶ ማትያስን እንዲያድነው የነገረው፡፡ ጌታችን ለእንድርያስ ተገልጦለት ‹‹ሰውን የሚበሉ ሰዎች ማትያስን ይዘው አሥረውታል፣ ከሦስት ቀንም በኋላ ሊበሉት ከእሥር ቤታቸው ያወጡታልና አንተ አሁን ወደ እነዚያ ሰውን ወደሚበሉት ሰዎች አገር ሂድ›› ባለው ጊዜ እንድርያስም መልሶ ጌታችንን ‹‹ጌታዬ ፈጣሪዬ የቀረው ሦስት ቀን ከሆነ እንዴት እደርሳለሁ? ነገር ግን ፈጥኖ የሚያወጣውን ከመላእክት አንዱን ላክ እንጂ›› አለው፡፡ ጌታችንም ‹‹እኔ ሀገሪቱን ራሷን ወደዚህ ነይ ካልኳት በውስጧ ከሚኖሩት ሁሉ ጋር ትመጣለች፤ አሁን ግን ፈቃዴ አንተና ደቀ መዝሙሮችህ እንድትሄዱ ነውና ነገ በጠዋት ተነሥታችሁ ወደ ባሕሩ ሂዱ የተዘጋጀች መርከብም ታገኛላችሁ›› አለው፡፡ ጌታችን ለእንድርያስ ይህንን ከነገረው በኋላ በክብር ዐረገ፡፡

በነጋም ጊዜ እንድርያስ ከቀደ መዝሙሮቹ ጋር ተነሥቶ ወደ ወደቡ ደረሰ፡፡ ጥሩ የተዘጋጀች መርከብንም አገኘ፡፡ ጌታችንም በሊቀ ሐመር አምሳል ተገለጠለት ነገር ግን እንድርያስ አላወቀውም ነበርና ‹‹ሊቀ ሐመር ሆይ ሰላም ለአንተ ይሁን›› አለው፡፡ ጌታችንም ‹‹የእግዚአብሔር ሰላም ይደርብህ›› አለው፡፡ እንድርያስም ‹‹በዚህ መርከብ ወዴት ትሄዳለህ?›› ሲለው ጌታችንም ‹‹ሰውን ወደሚበሉ ሰዎች አገር እሄዳለሁ›› አለው፡፡ እንደርያስም ‹‹ወንድሜ ሆይ! ከአንተ ጋራ ትጭነኝ ዘንድ እለምንሃለሁ›› አለው፡፡ በሊቀ ሐመር አምሳል የተገለጠው ጌታችንም ወደ መርከቡ ካወጣቸው በኋላ ሲጓዙ እንድርያስን ‹‹ጌታህ ምን ኃይል አደረገ?›› አለው፡፡ እንድርያስም ‹‹ጌታችን ያደረጋቸውን ተአምራቶች ሊነግረው ጀመረ የሚያናግረው ራሱ ጌታችን መሆኑን አላወቀም ነበርና፡፡ ከዚህም በኋላ ሊቀ ሐመሩ እንደሚያንቀላፋ ሰው ሆነ፣ ያንጊዜም እንድርያስና ደቀ መዝሙሮቹ ተኙ፡፡ ወዲያውም ጌታችን እንድርያስንና ደቀ መዝሙሮቹን ይሸከሟቸው ዘንድ መላእክትን አዘዛቸውና ወስደው በባሕሩ ዳርቻ አስቀመጧቸው፡፡ ከእንቅልፋቸውም በነቁ ጊዜ መርከብን አላገኙም፡፡ እንድርያስም የመርከቡ ሊቀ ሐመር ጌታችን መሆኑን አሁን ዐወቀና ለልጆቹ ነገራቸው፡፡
እንድርያስም ወዲያው መጸለይ ሲጀምር አሁንም ጌታችን ተገለጠለትና ‹‹ወዳጄ እንድርያስ ሆይ አትፍራ እኔ ይህን አድርጌያለሁና ምንም የሚሳነኝ ነገር እንደሌለ ታውቃለህ፤ አሁንም ወደ እሥር ቤቱ ሄደህ ማትያስንና ከእርሱ ጋር ያሉትን ሁሉ አውጣቸው›› አለው፡፡ እንድርያስም ልጆቹን ይዞ ወደ ከተማው በመግባት ማትያስ ወደታሰረበት ወኅኒ ቤት ሲሄድ የወኅኒ ቤቱ በሯ ራሷ ተከፈተችለት፡፡ ማትያስንና ደቀ መዝሙሮቹንም በወኅኒ ቤቱ ውስጥ አገኛቸውና ሰላምታ ከተሰጣጡ በኋላ ብዙ አወሩ፡፡

እንድርያስም ማትያስን ‹‹ከ2 ቀን በኋላ አውጥተው እንደ እንስሳ አርደው ይበሉኛል አልክ፣ አንተ በጌታችን ዘንድ ያየናትን ያችን ምሥጢር ረሳሃትን? በምናገራት ጊዜ ሰማይና ምድር ይናወጣሉኮ›› አለው፡፡ ማትያስም ‹‹ጌታችንም እንደበጎች በተኩላዎች መካከል እልካችኋለሁ ብሏልና ወደዚህ እሥር ቤት በጨመሩኝ ጊዜ ጌታችን ተገልጦልኝ አንተ መጥተህ እንደምታደነኝ ገልጦልኛልና አሁንም የምታደርገውን አስተውል›› አለው፡፡ እንድርያስም ወደ እሥረኞቹ በተመለከተ ጊዜ እንደ እንስሳ ሣር ሲበሉ አይቶ እጅግ በማዘን አለቀሰ፣ ሰይጣንንም ከሠራዊቱ ጋር አሠረው፡፡
ከዚህም በኋላ ሁለቱ ሐዋርያት ተነነሥተው ከጸለዩ በኋላ እጆቻቸውን በእሥረኞቹ ላይ ጫኑባቸውና ወደ አእምሮአቸው መለሷቸው፡፡ ከከተማውም ወጥተው በዚያ በአንድነት እንዲቀመጡ አዘዟቸውና ወጥተው በከተማው ጎዳና ዳር ተቀምጠው የሚሆነውን መከታታል ጀመሩ፡፡ ሰውን የሚበሉት የሀገሪቱ ሰዎችም እንደልማዳቸው የሚበሉትን ተረኛ ሰው ከእሥር ቤቱ ሊያወጡ ሲመጡ የእሥር ቤቱ በር ተከፍቶ እሥረኞቹም አምልጠው መውጣታቸውን ተመለከቱ፡፡

በዚህም ጊዜ ሰይጣን ሰውን መስሎ ተገለጠላቸውና ‹‹ይህንን ያደረጉት ሐዋርያት ናቸው›› አላቸው፡፡ እነርሱም ሁለቱን ሐዋርያት ይዘው በማሠር በከተማ እየጎተቱ አዞሯቸው፡፡ በእሥር ቤትም እያሳደሩ እስከ ሦስት ቀን እንዲሁ አደረጉባቸው፡፡ ደማቸውም በምድር ላይ እንደውኃ ፈሰሰ፡፡ እንድርያስና ማትያስም ጸሎት ካደረጉ በኋላ አንድን የእምነ በረድ ምሰሶን ከሥሩ የጥፋት ውኃን አፍልቆ ከተማዋን ያጥለቀልቃት ዘንድ አዘዙት፡፡ እንዳዘዙትም ከእምነ በረዱ ምሰሶው ሥር ብዙ ውኃ ፈልቆ የከተማዋን ሰዎች ያሰጥማቸው ዘንድ ገነፈለ፡፡ የአገሪቱም ሰዎች ሸሽተው ከከተማው ለመውጣት ቢሞክሩም ውኃ እስከ አንገታቸው ድረስ አስጥሞ ያዛቸው፡፡ ብዙዎቹም ሞቱ፡፡ ከዚህም በኋላ ‹‹ወዮልን ወዮታ አለብን፣ ይሄ ሁሉ የደረሰብን በእነዚያ በተመረጡ ሰዎች ላይ በፈጸምነው በደል ምክንያት ነው እኛም በአምላካቸው እናምናለን›› አሉ፡፡
እንድርያስም ከዚህ በኋላ ውኃውን እንዲጎድል አዘዘውና እንዳዘዘው ጎድሎ ጠፋ፡፡ የአገሪቱም ሰዎች ወደ ሐዋርያት ቢመጡ ሐዋርያቱን ቆመው ሲጸልዩ አገኟቸውና ‹‹ይቅር በሉን›› ብለው ለመኗቸው፡፡ ሐዋርያትም ‹‹በሕያው እግዚአብሔር እመኑ እንጂ አትፍሩ›› አሏቸው፡፡ እንድርያስና ማትያስም ዳግመኛ ወደ ጌታችን ጸልየው በውኃው ስጥመት የሞቱትን በርካታ ሰዎች ከሞት እንዲነሡ አደረጓቸው፡፡ ሰውን የሚበሉትን የአገሪቱንም ሰዎች ሁሉ አእምሮአቸውንና የቀድሞ አርያቸውን መለሱላቸው፡፡ አስቀድሞ ሰይጣን አድሮባቸው ነበርና፡፡ አሁን ግን የቀድሞው የአራዊት ጸባያቸውም ርቆላቸው ሰው የሚበላውን ምግብ የሚመገቡ የዋሆች ሆኑ፡፡ ከዚህም በኋላ ሁለቱ ቅዱሳን ሐዋርያት ሁሉንም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቋቸው፡፡ ሥጋ ወደሙንም አቀበሏቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሠርተውላቸው ሕግና ሥርዓትን ሁሉ አስተምረው ከትእዛዛቸው እንዳይናወጹ መክረዋቸው የቀናች ሃይማኖትን አጸኑላቸው፡፡ ሐዋርያትም ሃይማኖትን እያስተማሯቸው 30 ቀን አብረዋቸው ከተቀመጡ በኋላ አገልጋይ ኤጲስ ቆጶሳትን፣ ካህናትንና ዲያቆናትን ሾሙላቸው፡፡ የከበሩ ቅዱሳን ሐዋርያት ብዙ ተአምራትን አደረጉ፣ ሕሙማንን ሁሉ ፈወሱ፡፡ ከዚህም በኋላ እንድርያስ ከደቀ መዝሙሮቹ ጋር ወደ ግሪክ አገር ተመለሰ፡፡
የሐዋርያው የቅዱስ እንድርያስ ረድኤት በረከቱ ይደርብን በጸሎቱ ይማረን።

ምንጭ፦ የታኅሣሥ ➍ ስንክሳር

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

🍃🍃🍃 🍃🍃🍃 🍃🍃🍃 🍃🍃

ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ
እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ
ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ
እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀ መበለት ውኩፈ
እም እለ አብዑ ብዑላን ዘተርፈ።

ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን
ሰማዕታት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን
ደናግል ዓዲ ወመነኮሳት ኄራን
ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን
እስከ አረጋዊ ልሒቅ እምንዑስ ሕፃን።

ለዘጸሐፎ በክርታስ
ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ
ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ
ወለዘሰምዐ ቃሎ በእዝነ መንፈስ
በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኲሉ እምባእስ
ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ
ወይፈኑ ለነ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ
እምይዜ ወእስከ ለዓለም አሜን።

ጌታ ሆይ ከብልጽግናቸው ብዛት የተነሳ ብዙ መባ ካገቡት ይልቅ የደሀይቱን አነስተኛ መባ እንደተቀበልህ ለሁል ጊዜ የሚያገለግሉህ አእላፍ መላእክትን እያሳሰብሁ በችግሬ ጊዜ የማቀርብልህን ምስጋና ተቀበል።

እናንተም ቅዱሳን ነቢያት የወንጌል ሰባኪያን ሐዋርያት ሰማዕታትና ጻድቃን ትጉሃን መላእክት ፍጹማን ደናግል እንዲሁም ደጋጎች መነኰሳት ሆይ ልጅ አዋቂ ሳይለይ የምንሰበሰብበትን የጉባኤ ቦታ ባርኩ።

ይህን መጽሐፍ ወረቀት አዘጋጅቶ ብራና ደምጦ የጻፈውንና ያጻፈውንም የተረጐመውን ቃለ ንባቡን በእርጋታ መንፈስ እና በተመስጦ ሕሊና ያዳመጠ በደለኛን ሁሉ የምታስምር የጌታ እናቱ በማርያም ጸሎት ኢየሱስ ክርስቶስ በአንድነት ይማረን። አሜን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼
ከታች ያለውን ማስፈንጠሪያ በመጫን ቤተሰብ ይሁኑ
Tᴇʟᴇɢʀᴀᴍ - https://t.me/Synaxarium

Fᴀᴄᴇʙᴏᴏᴋ
🔹https://www.facebook.com/MeseleNigatuDek0

🔸https://www.facebook.com/Mesele.Nigatu.Deko

ታኅሣሥ ❸ ቀን 2011 ዓ.ም

ታኅሣሥ 3  መልአኩ ቅዱስ ፋኑኤልም እመቤታችንን ሰማያዊ ኅብስት የመገበበትና የተሾመበት ዕለት ነው፡፡የመልአኩ ቅዱስ ፋኑኤል ጥበቃው አይለየን !!ምንጭ፦  የታኅሣሥ ❸ ስንክሳር         ...
12/12/2025

ታኅሣሥ 3 መልአኩ ቅዱስ ፋኑኤልም እመቤታችንን ሰማያዊ ኅብስት የመገበበትና የተሾመበት ዕለት ነው፡፡

የመልአኩ ቅዱስ ፋኑኤል ጥበቃው አይለየን !!

ምንጭ፦ የታኅሣሥ ❸ ስንክሳር

ከታች ያለውን ማስፈንጠሪያ በመጫን ቤተሰብ ይሁኑ
Tᴇʟᴇɢʀᴀᴍ - https://t.me/Synaxarium

Fᴀᴄᴇʙᴏᴏᴋ
🔹https://www.facebook.com/MeseleNigatuDek0

🔸https://www.facebook.com/Mesele.Nigatu.Deko


ታኅሣሥ ➋ ቀን 2011 ዓ.ም

ታኅሣሥ 3 ባዕታ ለማርያም እምቤታችን ቤተ መቅደስ የገባችበት ዕለት ነው፡፡ 🔥 በዓታ ለማርያም ቅዱሳን ኢያቄምና ሐና በአንድነት ተጋብተው ሲኖሩ ልጅ አጡ፡፡ እነርሱም እጅግ ደጋግ ሰዎች ነበሩ...
12/12/2025

ታኅሣሥ 3 ባዕታ ለማርያም እምቤታችን ቤተ መቅደስ የገባችበት ዕለት ነው፡፡

🔥 በዓታ ለማርያም

ቅዱሳን ኢያቄምና ሐና በአንድነት ተጋብተው ሲኖሩ ልጅ አጡ፡፡ እነርሱም እጅግ ደጋግ ሰዎች ነበሩ፡፡ አንድ ልጅ እንኳ ስላልነበራቸው እጅግ ያዝኑ ነበር፡፡ ወደ ቤተመቅደስ እየሄዱ እግዚአብሔር ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ አጥብቀው ይለምኑት ነበር፡፡ መብዓ ይዘው ለሊቀ ካህኑ ሲሰጡት ሊቀ ካህኑም እንኳ ሳይቀር ‹‹እግዚአብሔር ብዙ ተባዙ ያለውን ሕግ በእናንተ ላይ እንዳይፈጸም አድርጎ ልጅ የከለከላችሁ ኃጢአተኛ ብትሆኑ ነውና መብዓችሁን አልቀበልም›› ብሎ በእጅጉ አሳዝኗቸዋል፡፡ በሊቀ ካህኑ እያዘኑና እየተከዙ ሲመለሱ ከድካማቸው ያርፉ ዘንድ ዛፍ ሥር ተቀመጠው ሳለ እርግቦች ጫጩቶቻቸውን ሲያጫውቱ ተመልክተው ‹‹ለእነዚህ ወፎች እንኳ ልጆችን የሰጠህ አምላክ ለእኛስ መች ይሆን ልጅ የምትሰጠን?›› ብለው እጅግ አምርረው አለቀሱ፡፡

ሲያዝኑ ሲጸልዩ ውለው ወደቤታቸው ሲመለሱ ርግብ ከልጆቿ ጋር ስትጫወት አይታ ‹‹አቤቱ ጌታዬ ለዚች እንስሳ ልጅ የሰጠህ አምላክ ምነው ለኔ ልጅ ነሳኸኝ?›› እያለች ምርር ብላ አለቀሰች፡፡ እንዲህ ብለው ሲያዝኑ ሲጸልዩ ውለው ከዘካርያስ ከሊቀ ካህናቱ ሄደው ‹‹አቤቱ ጌታችን ሆይ ወንድ ልጅ ብንወልድ ተምሮ ቤተ እግዚአብሔርን አገልግሎ እንዲኖር እንሰጣለን፤ ሴት ልጅም ብንወልድ ውኃ ቀድታ መሶብ ወርቅ ሰፍታ መጋረጃ ፈትላ ካህናትን አገልግላ እንድትኖር እንሰጣለን›› ብለው ስዕለት ገቡ፡፡ ዘካርያስም ‹‹እግዚአብሔር ጸሎታችሁን ይስማችሁ ስዕለታችሁን ይቀበልላችሁ የልቦናችሁን ሀሳብ ይፈጽምላችሁ›› ብሎ አሳረገላቸው።

ከዚህም በኋላ ቅድስት ሐና እና ቅዱስ ኢያቄም ዕለቱን ራእይ አይተው ነገር አግኝተው አደሩ፡፡ ራእዩስ እንዴት ነው ቢሉ ኢያቄም ‹‹7ቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ›› አላት፡፡ ‹‹ወፍ›› የተባለው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ነጭነቱ ንጽሐ ባህሪው ነው፤ ‹‹ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ›› ማለቱ የኢያቄምን (የሰውን) ባህርይ ባህርይ እንዳደረገው ዕወቅ ሲል ነው፡፡ 7ቱ ሰማያት የተባሉ የጌታችን ልዩ ልዩ ባሕርይው ምልአቱ ስፋቱ ርቀቱ ልዕልናው ናቸው፡፡ ሐናም ‹‹እኔም ደግሞ አየሁ እንጂ›› አለችው፡፡ ‹‹ምን አየሽ?›› ቢላት ‹‹ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማህጸኔ ስትተኛ አየሁ›› አለችው፡፡ ‹‹ርግብ›› የተባለች እመቤታችን ድንግል ማርያም ናት፤ ነጭነቱ ንጽህናዋ ቅድስናዋ ድንግልናዋ ነው፡፡ ‹‹ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማኅፀኔ ስትተኛ አየሁ›› ማለቷ ብሥራተ ገብርኤልን በጆሮዋ ሰምታ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጌታችንን መፀነሷን ነው፡፡ ይህንኑም ራእይ ያዩት ሐምሌ 30 ዕለት ነው፡፡

እነርሱም እንዲህ ያለ ራእይ ካየን ነገር ካገኘን ብለው ዕለቱን በሩካቤ ሥጋ አልተገናኙም ይልቁንም ፈቃደ እግዚአብሔር ቢሆን ብለው አዳምንና ሔዋንን ‹‹‹ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሉአት›› ብሎ ያበሰረ አምላክ ለእኛስ ይልክልን የለምን?›› ብለው ዕለቱን አልጋ ምንጣፍ ለይተው እስከ 7 ቀን ድረስ ለየብቻቸው ሰነበቱ፡፡ ነሐሴ በባተ በሰባተኛው ቀን ‹‹‹ከሰው የበለጠች ከመላእክት የከበረች ደግ ፍጥረት ትወልዳላቹህ ብሎሏችኀል ጌታ›› ብሎ መልአኩ ገብርኤል ለቅድስት ሐና ነገራት፡፡

እግዚአብሔር አምላክ አብርሃምን እና ሳራን የተመለከተ አምላክ በኢያቄምና ሐና አማካኝነት ለዓለም ድኅነት ምክንያት የሆነችውን እና ዓለም ሳይፈጠር በአምላክ ልቦና ታስባ ትኖር የነበረች የተነገረላት ትንቢት ሊፈጸም የአባት የእናቷ የቅድመ አያቶቿ ራእይ ሊተረጎም ጌታ የፈቀደበት ጊዜ ሲደርስ እመቤታችን እግዝእትነ ማርያም እሁድ እለት ነሐሴ 7 ቀን በ16 ዓ.ዓ ተፀነሰች፡፡

እመቤታችንም በተፀነሰች በ9 ወር ከአምስት ቀን የግንቦት መባቻ ዕለት ግንቦት 1 ተወለደች፡፡ ሦስት ዓመትም በሆናት ጊዜ እናትና አባቷ ቅዱስ ኢያቄምና ቅድስት ሐና ስዕለታቸውን አስበው የአምላክ እናት ብፅዓት አድርገው ለእግዚአብሔር ይሰጧት ዘንድ በዚህች ዕለት ወደ ቤተ መቅደስ ወሰዷት፡፡

የብርሃን እናቱ ክብርት እመቤታችን ቃል ኪዳኗ ይጠብቀን። ተወዳጅ ልጇ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከበዓሏ ረድኤት በረከት ይክፈለን።

ምንጭ፦ የታኅሣሥ ❸ ስንክሳር

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼
ከታች ያለውን ማስፈንጠሪያ በመጫን ቤተሰብ ይሁኑ
Tᴇʟᴇɢʀᴀᴍ - https://t.me/Synaxarium

Fᴀᴄᴇʙᴏᴏᴋ
🔹https://www.facebook.com/MeseleNigatuDek0

🔸https://www.facebook.com/Mesele.Nigatu.Deko

ታኅሣሥ ➋ ቀን 2011 ዓ.ም

[ታኅሣሥ 3 የእመቤታችን ወደ ቤተ መቅደስ መግባት ድንቅ ታሪክና የ8 ሊቃውንት ትምህርት]✍(  በመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ )♥❖♥ ኢያቄምና ሐና ቃል ኪዳናቸውን ለመፈጸም ዘመዶቻቸውን ...
11/12/2025

[ታኅሣሥ 3 የእመቤታችን ወደ ቤተ መቅደስ መግባት ድንቅ ታሪክና የ8 ሊቃውንት ትምህርት]
✍( በመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ )
♥❖♥ ኢያቄምና ሐና ቃል ኪዳናቸውን ለመፈጸም ዘመዶቻቸውን ባልንጀሮቻቸውን ከነልጆቻቸው በመጥራት ሕፃን ልጃቸውን እመቤታችንን ልዩና ንጹሕ ልብስን አልብሰው በመንፈሳዊ ዝማሬ እግዚአብሔርን እያመሰገኑ መብራትን በእጆቻቸው ይዘው እያበሩ ኢየሩሳሌም ወዳለው ቤተ መቅደስ ወሰዷት፤ ያን ጊዜም ሊቀ ካህናቱ ዘካርያስ በካህናቱ ታጅቦ የምስጋና ዝማሬን ከልኡካኑ ጋር እያሰማ እነርሱን ለመገናኘት ከመቅደስ ወጣ።

♥❖♥ በዚያም ሊቀ ካህናቱ ብቻ ወደሚገባበት ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ የሚያስወጡ ፲፭ ደረጃዎች ሲኖሩ በየደረጃዎቹም መዝሙረ ዳዊት ተደጋግሞ ሲደረስባቸው ከሚጸለዩት የዳዊት መዝሙራት ውስጥ መዝ ፻፲፰(፻፲፱)-፻፴፪ (፻፴፫) የሚገኙ ሲኾኑ እነዚኽንም የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት አጥኚዎች “Psalms of Ascent” (የመውጣት መዝሙራት) ይሏቸዋል::

♥❖♥ እናትና አባቷም ሊቀ ካህናቱን ካለበት ቅዱስ ቦታ ወደነርሱ እስኪመጣ ለመቆየት ልጃቸው ማርያምን ከአንደኛው ደረጃ ላይ ቢያኖሯትም ርሷ ግን በድንቅ አምላካዊ ሥራ መንፈሳዊ ኀይልን ተመልታ የሦስት ዓመቷ እመቤታችን ያለምንም ረዳት ብቻዋን ደረጃዎቹን በመውጣት በእጅጉ ወደተቀደሰው ሊቀ ካህናቱ ብቻ ወዳለበት ስፍራ ኼደች ርሱም በእጅጉ ተደንቆ ባረካት።

♥❖♥ያን ጊዜ መንፈስ ቅዱስ ለሊቀ ካህናቱ የሰው ዘርን በመላ ወደ ገነት የሚያስገባ ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት የእግዚአብሔር ልጅን የምትወልደው ርሷ እንደኾነች ገልጾለት ቦታዋም በጣም የተቀደሰውና ርሱ መሥዋዕት ለማቅረብ በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ የሚገባበት ከርሱ በቀር ማንም ሰው የማይገባበት ቅድስት ቅዱሳን ውስጥ መኾኑን ገልጾለታል ፡፡

♥❖♥ ርሱም ይኽነን የእግዚአብሔር ድንቅ ሥራን በማድነቅ ይኽቺን የመሰለች ልጅ ምን እናደርጋታለን? ምን እናበላታለን? ምንስ እናጠጣታለን? ምን እናነጥፍላታለን? ብሎ ሲጨነቅ ለእስራኤል ደመና ጋርዶ መናን አውርዶ የመገበ፤ ለኤልያስም በመልአኩ እጅ በመሶበ ወርቅ ኅብስት የመገበ፤ ለዕዝራ ሱቱኤልም በመልአኩ በቅዱስ ዑራኤል እጅ መልኩ እሳት የሚመስል ጽዋዐ ልቡና ያጠጣው ልዑል እግዚአብሔር ለእናትነት ወደ መረጣት ወደ እናቱ መልአኩ ፋኑኤልን ላከላት (ዘፀ ፲፮፥፴፩፤ ፩ነገ ፲፱፥፮፤ ዕዝ. ሱቱ. ፲፫፥፴፰-፵፩)::

♥❖♥ ከዚያም “ወሶቤሃ ወረደ ፋኑኤል ሊቀ መላእክት ወጸለላ በአክናፊሁ ወተለዐለ ላዕለ መጠነ ቆመ ብእሲ ወወሀባ ወመጠዋ ወዐርገ ውስተ ሰማይ” ይላል በዚያን ጊዜ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ፋኑኤል ኅብስት ሰማያዊን፤ በብርሃን ጽዋዕ ስቴ ሕይወትን ይዞ ረብቦ በመውረድ አንድ ክንፉን አንጽፎ አንዱን ክንፉን አጐናጽፎ ከመሬት የሰው ቁመት ያኽል ከፍ አድርጓት ኅብስቱን መግቧት ጽዋውን አጠጥቷት ወደ ሰማይ ዐርጓል፡፡

♥❖♥ ስላዩትና ስለተደረገው ነገር ኹሉ እግዚአብሔርን እያመሰገኑ አማናዊት የአምላክ መቅደስ የአካላዊ ቃል ታቦት እመቤታችንን ምሳሌዋ ወደሚኾነው ቤተ መቅደስ ታኅሣሥ ፫ በሦስት ዓመቷ አስገብተዋታል፤ ከዚያም ኢያቄምና ሐና ወደ ቤታቸው ተመልሰዋል፡፡

♥♥♥ የቅድስት ድንግል ማርያም የቤተ መቅደስ ሕይወት በእጅጉ አስደናቂ ሲኾን የቤተ ክርስቲያናችን ቅዱስ ትውፊት (Holy Tradition) እንደሚያስረዳን ቤተ መቅደስ በኖረችባቸው 12 ዓመታት የእግዚአብሔርን ሕግ በማጥናት ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ ለቤተ መቅደስ የሚያስፈልገውን ነገር በእጆቿ እየሠራች በፍጹም ንጽሕና ቅድስና ኾና እግዚአብሔርን በማመስገን መላእክት እያገለገሏት ኖራለች፡፡

ይኽነን በቤተ መቅደስ የነበራትን ቆይታ ቀደምት የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት በጥልቀት ጽፈዋል እነሆ የሊቃውንቱ ቃል፦

፩) [አባ ጽጌ ድንግልና አባ ገብረ ማርያም ዘደብረ ሐንታ በማሕሌተ ጽጌ]
“የሐዝነኒ ማርያም ዘረከበኪ ድክትምና
አመ ቤተ መቅደስ ቦእኪ እንዘ ትጠብዊ ሐሊበ ሐና
ወያስተፌሥሐኒ ካዕበ ትእምርተ ልህቀትኪ በቅድስና
ምስለ አብያጺሁ ከመ አብ እንዘ ይሴስየኪ መና
ፋኑኤል ጽጌ ነድ ዘይከይድ ደመና”

(ማርያም የሐናን ወተት እየጠባሽ ወደ ቤተ መቅደስ በገባሽ ጊዜ ያገኘሽ ብቸኝነት ያሳዝነኛል፤ ዳግመኛም በደመና የሚመላለስ ደመናን የሚረግጥ የእሳት አበባ ፋኑኤል ከጓደኞቹ መላእክት ጋር መናን እየመገበሽ በንጽሕና የማደግሽ ተአምር ደስ ያሰኘኛል)♥

♥“ከመ ታቦት ሥርጉት በወርቀ ዐረብ ወተርሴስ
በድንግልና ማርያም ስርጉተ ሥጋ ወነፍስ
ተአምረ ነቢር አርአይኪ በቤተ መቅደስ
ኢያቄም ወሐና ቀንሞስ ቀናንሞስ
እምዘጸገዩኪ ለጳጦስ በዓመት ሠላስ”

(በዐረብና በተርሴስ ወርቅ እንዳጌጠች ታቦት በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ ያጌጥሽ ማርያም፤ ቀንሞስ ቀናንሞስ የሚባሉ ሽቱዎች ኢያቄምና ሐና ለጳጦስ ምሳሌ የኾንሽ አንቺን ከአስገኙሽ ዘንድ በሦስት ዓመት በቤተ መቅደስ የመኖር ተአምርን አሳየሽ)
++++++++++++++
፪) [ሊቁ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴ ማርያም]
♥♥♥ “ኦ ድንግል አኮ በተላህዮ ዘልሕቂ ከመ አዋልደ ዕብራውያን እለ ያገዝፋ ክሣዶን አላ በቅድስና ወበንጽሕ ውስተ ቤተ መቅደስ ነበርኪ…” (ድንግል ሆይ አንገታቸውን እንደሚያገዝፉ እንደ ዕብራውያን ሴቶች ልጆች በዋዛ ያደግሽ አይደለም፤ በንጽሕና በቅድስና በቤተ መቅደስ ኖርሽ እንጂ፤ ድንግል ሆይ ምድራዊ ኅብስትን የተመገብሽ አይደለም፤ ከሰማየ ሰማያት የበሰለ ሰማያዊ ኅብስትን ነው እንጂ፤ ድንግል ሆይ ምድራዊ መጠጥን የጠጣሽ አይደለም፤ ከሰማየ ሰማያት የተቀዳ ሰማያዊ መጠጥን ነው እንጂ፤ ድንግል ሆይ ከአንቺ አስቀድሞ ከአንቺም በኋላ እንዳሉ ሴቶች መተዳደፍን የምታውቂ አይደለም፤ በንጽሕና በቅድስና ያጌጥሽ ነሽ እንጂ፤ ድንግል ሆይ የሚያታልሉ ጐልማሶች ያረጋጉሽ አይደለም የሰማይ መላእክት ጐበኙሽ እንጂ እንደተነገረ ካህናትና የካህናት አለቆች አመሰገኑሽ እንጂ)
+++++++++++++++++++
፫) [በ፭፻፭ (505) ዓ.ም የተወለደው ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ያሬድም በአንቀጸ ብርሃን]

♥“አንቲ ውእቱ ንጽሕት እም ንጹሓን ድንግል ኅሪት ዘነበርኪ ውስተ ቤተ መቅደስ ከመ ታቦት ዘግቡር እምዕፅ ዘኢይነቅዝ…” (ከንጹሓን ይልቅ ንጽሕት የኾንሽ አንቺ ነሽ፤ ከማይነቅዝ ዕንጨት እንደተሠራ በወርቅ እንደተጌጠና ዋጋው ብዙ በኾነ በሚያበራ ዕንቊ እንደተለበጠ ታቦት በቤተ መቅደስ ውስጥ የኖርሽ የተመረጥሽ ድንግል ነሽ፤ እንዲኽ ኾነሽ በቤተ መቅደስ ውስጥ ኖርሽ፤ መላእክት ዘወትር ምግብሽን ያመጡ ነበር፤ መላእክት እየጐበኙሽ እንዲኽ ዐሥራ ኹለት ዓመት ኖርሽ፤ መጠጥሽም የሕይወት መጠጥ ነበር፤ ምግብሽም የሰማይ ኅብስት ነበር)

♥ “እኅትነ ይብልዋ ወይኬልልዋ ነያ ሐዳስዩ ጣዕዋ፤ ጸቃውዕ ይውሕዝ እምከናፍሪሃ ከመ ቅርፍተ ሮማን መላትሒሃ፤ ልዑል ሠምራ ዳዊት ዘመራ በቤተ መቅደስ ተወክፍዋ”
(መላእክት እመቤታችንን እኅታችን ይሏታል፤ በክንፋቸው ይጋርዷታል፤ በማር ወለላ የተመሰለ የእግዚአብሔር ቃል ከከንፈሮቿ ይፈስሳል፤ ጒንጮቿ እንደ ሮማን ቅርፍት ናቸው፤ ልዑል ወደዳት፤ ዳዊት በመዝሙሩ አመሰገናት፤ በቤተ መቅደስ ተቀበሏት) (ቅዱስ ያሬድ፤ መጽሐፈ ድጓ)

♥ “ሰአሊ ለነ ማርያም እንተ እግዝእ ኀረያ ዕፀ ጳጦስ ሰመያ በቤተ መቅደስ ተወክፋ ዘካርያስ ወኲሎሙ ቅዱሳን ይብልዋ ሐዳስዩ ጣዕዋ”
(ጌታ የመረጠሽ ማርያም ሆይ ለምኝልን፤ ዕፀ ጳጦስ ተብላ የተጠራችውን እመቤታችን ዘካርያስ በቤተ መቅደስ ተቀበላት፤ ኹላቸውም ቅዱሳን ዐዲሲቱ እንቦሳ ይሏታል)

♥ “ጠባብ ወትሕት በቤተ መቅደስ ዘልህቀት ወለተ ዳዊት ቀጸበቶ በትእምርት ለዘወረደ እመልዕልት”
(ብልኅና ትሕትናን የተላበሰችው በቤተ መቅደስ ያደገችው የዳዊት ልጅ እመቤታችን ከላይ የወረደውን በምልክት ጠራችው) ይላል
++++++++++++++
፬) [ከ፫፻፳-፬፻፫ (320-403) ዓ.ም የነበረው የቆጵሮሱ ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ]
♥ “She was brave and dignifified in all her action…” (ርሷ በኹሉም ርምጃዎቿ ጐበዝና የተከበረች ነበረች፤ የምትናገረው በጣም ጥቂት ሲኾን ርሱም ለማድረግ አስፈላጊ በሚኾንበት ብቻ ነበር፤ በጣም ዝግጁ ኾና የምትሰማና በቀላሉ ንግግር ለማድረግ የምትችል ናት፤ ለእያንዳንዱ ሰው አክብሮትና ክብር (ሰላምታ) ትሰጣለች፤ ቁመቷ መኻከለኛ ሲኾን አንዳንዶች ግን ቁመቷ ከፍ ያለ እንደነበር ይናገራሉ፤ ከእያንዳንዱ ሰው ጋር ያለምንም ፍርሀት በግልጽነት ያለምንም ሳቅና መጯጯኽ ትናገራለች፤ በተለይ ፈጽማ ለቁጣ የምትጋበዝ አልነበረችም፤ መልኳ እንደ ደረሰ የስንዴ አዝመራ ያማረ ጸጒሯ ቀይማ ነው፤ ዐይኖቿ ብሩሃትና የዋህ የኾኑ ቀለማቸውም ፈዘዝ ያለ ቡናማ ኾኖ የዐይኖቿ ብሌኖች የዘይት-አረንጓዴ ይመስላል፤ የዐይኖቿ ቅንድብ (ሽፋሽፍት) ከፊል ክብና ደማቅ ጥቁር ናቸው፤ አፍንጫዋም ረዥም፣ ከናፍሮቿ ቀይና ምሉእ ሲኾኑ በቃሎቿ ጣፋጭነት የተመላባቸው ነበሩ፤ ፊቷ ክብ ሳይኾን ግን እንቁላልማ ዐይነት ቅርጽ ነበረው፤ እጆቿ ረዥምና ጣቶቿም በጣም ረዣዥም ነበሩ፤ ከማንኛውም ያልተገባ ኩራት ሙሉ በሙሉ የነጻች ስትኾን ግድ የለሽነት ፈጽሞ ጨርሶ የለባትም ነበር፤ የሚመጡትን ነገራት በፍጹም ትሕትና ትቀበል ነበር፤ ተፈጥሯዊ ቀለማት ያላቸው (ማለትም በቤት ድር የተሠሩ) ልብሶችን ትለብስ ነበር፤ ይኽም በእጅጉ አብሯት የሚኼደው አለባበስና ይኽ እውነታ በራሷ ላይ በምታደርገው ቅዱስ ልብስ አኹን ቅሉ ሊረጋገጥ የሚችል እውነታ ነው፤ ለማጠቃለል ያኽል በመንገዶቿ ኹሉ በጌታ ስጦታ የተመላች ነበረች)
+++++++++++
፭) [ከ፫፻፲፭-፫፻፹፮ (315-386) ዓ.ም ድረስ የነበረው የኢየሩሳሌሙ ጳጳስ ቅዱስ ቄርሎስ]
♥♥♥ “They (Joachim and Anna) were in the habit of visiting their daughter once each month,…’’ (እነርሱ (ኢያቄምና ሐና) በወር አንድ ጊዜ ልጃቸውን የመጐብኘት ልምድ ነበራቸው፤ ለርሷ የሚያስፈልጋትን ነገር ይዘው ይመጡ ነበር፤ እናም ትንሿ ድንግል ልጃቸው ከርሷ በዕድሜ ከፍ ከሚሉ ደናግል ጋር በቤተ መቅደስ ታገለግል ነበር፤ እነርሱም በእጆቿ እንዴት መሥራት እንደምትችል ያስተምሯት ነበር፤ ርሷም ዐዋቂ በኾነች ጊዜ በራሷ ወደ ቤተ መቅደሱ ዐደባባይ ስትኼድ ከካህናትና ከአባቷ በቀር ማንም ወንድ ከቶ አይቷት አያውቅም…ትንሿ ድንግል ማርያም በቤተ መቅደስ ነበረች፤ የመላእክት አለቃው ገብርኤል በጣፋጭ መዐዛው ወደ ርሷ ቀረባት…የርሷ ውበቷ ምንም ወሰን አልነበረውም፤ ቤተ መቅደሱም ከጣፋጭ መዐዛዋ የተነሣ በመላእክት ይመላ ነበር፤ ለንግግሯ ሲሉ ብቻ ይጐበኟት ነበረ)
++++++++++++++++
፮) [በ፪፻፶፮ (256) ዓ.ም የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ የነበረው ዲሜጥሮስ]
♥♥♥ “At the moment when her mother Anna set her upon her feet, inside the door of the temple…” (እናቷ ሐና በካህናቱ ፊት በቤተ መቅደሱ በር ላይ ርሷን በእግሯ ባኖረቻት ጊዜ በራሷ ለጌታ መሥዋዕት ወደሚቀርብበት ወደ መሠዊያዉ መጋረጃ ወደ ቤተ መቅደስ እስክትደርስ ድረስ ኼደች፤ ከገባችም በኋላ ለመውጣት አልተመለሰችም በልቡናዋም የቤተሰቦቿ ሐሳብና ምድራዊ ነገራትን ከቶ አላሰበችም…እናም ባደገችና ስምንትና ዐሥር ዓመት በመላትም ጊዜ ለካህናቱ ኹሉ አብነት (ምሳሌ) ነበረች ርሷንም ለማየት ይፈሩ ነበር፤ መላ ሰውነቷ ንጹሕ ነበር ልቡናዋም በጌታ የጸና ነው፤በሥጋዋም በነፍሷም ንጽሕት ናት፤ ፊቷንም ከቤተ መቅደሱ በር ውጪ በፍጹም አላዞረችም፤ እንግዳ ሰውንም ከቶ አላየችም የወጣት ሰው ፊትን ለመመልከት ፊቷን ከቶ አላዞረችም፤ በቅድስና እግዚአብሔርን በማገልገል ለቤተ መቅደስ በመላላክ ኖረች እንጂ፤ ልብሷ ያማረ ዕጥፋቱ በማኅተሟ ላይ ወደ ታች የወረደ ሲኾን የራሷ መሸፈኛም እስከ ዐይኖቿ ይደርሳል…በዐይኖቿ ላይ በጭራሽ መዋቢያ ቀለም አልተጠቀመችም፤ በጉንጮቿ ላይ ምንም ዐይነት የማጌጫ አበባ አላኖረችም፤ በእግሮቿ ላይ መጫሚያ ሰንደሎች አላደረገችም፤ በክንዶቿና በእጆቿ ላይ አልቦ ወይም አንባር ወይም ጌጣጌጥ አላደረገችም ነበር፤ ከልክ ያለፈ ምግብ በጭራሽ ፈልጋ አታውቅም፤ በከተማው የገበያ ስፍራ ውስጥ በጭራሽ ተጉዛ አታውቅም፤ ለዚኽ ዓለም ሥራዎች በጭራሽ ጉጉት ዐድሮባት አያውቅም)
+++++++++++++
፯) [ከ፫፻፸፮-፬፻፵፬ (376-444) ዓ.ም የነበረው እስክንድርያዊዉ ቅዱስ ቄርሎስ]

♥♥♥ “Come, O all ye women who desire virginity…” (ድንግልናን የምትፈልጉ ሴቶች በሙሉ የጌታችን እናት የኾነችውን የድንግል ማርያምን ምሳሌ ተከተሉ፤ የርሷንም መንገድ መናኛ ምግብ መብላቷንና መሬት ላይ መተኛቷን ዐስቡ፤ ለዚኽ ዓለም ነገሮች ምንም ዐይነት ጉጉት የላትምና የርሷ ስምም ኹልጊዜም በካህናት አፍ ውስጥ ነበር፤ ሰውነቷን በጭራሽ በሕዝብ መታጠቢያ ውስጥ ታጥባ አታውቅም፤ ራሷን በፍጹም በመዋቢያ የፊት ቀለም፣ በዐይን ኩልና በቅባት በጭራሽ አስውባ አታውቅም፤ በጣም ያጌጠ ልብስ እንደሚወድዱ ኹሉም በዘመኗ የነበሩ ሴቶች በደማቅ ባለቀለም ልብስ በጭራሽ አስጌጣ አታውቅም፤ በጭራሽ የወይንን ጣዕም ቀምሳ አታውቅም፤ ኹልጊዜም ዓለማትን የፈጠረ ፈጣሪዋን ትጠብቅ ስለነበር ፊቷን ወደ ምሥራቅ አዙራ ትቀመጥ ነበር፤ ከእናቷና ከአባቷ በስተቀር ከማንም ጋር ተገናኝታና አውርታ አታውቅም)
+++++++++++++++++++

፰) [ ከ፪፻፺፮-፫፻፸፫ (296-373) ዓ.ም የነበረው ቅዱስ አትናቴዎስ]
♥♥♥ “Mary was pure virgin, with a harmonius disposition…” (ማርያም ንጽሕት ድንግል ስትኾን በጣም ጥሩ አቋም የነበራትና መልካም ሥራዎችን የምትወድድ ነበረች፤ በወንዶች መታየትን ፈጽማ አትፈልግም ነበር፤ ግን እግዚአብሔርን እንዲመረምራት ጠይቃዋለች፤ ያለማቋረጥ በቤቱ ውስጥ ቆይታለች፤ ከጨዋታ የራቀ (የመናኝ) ሰውን ኑሮ ትኖር የነበረ ሲኾን ማር ከምትሰጥ ንብ ጋር ትመሳሰላለች፤ በእጆቿ ከሠራቻቸው ሥራዎች የምታገኘውን ገንዘብ ለድኾች ታከፋፍላለች፤ በብቸኝነት ኹለት ነገራትን እንዲያደርግላት ወደ እግዚአብሔር ትጸልያለች፤ ይኸውም መጥፎ ሐሳብ በልቧ ውስጥ እንዳይሠርጽና ልቧ በጭራሽ ከፍቅር አምላካዊ እየቀዘቀዘ እንዳይኼድ ነበረ፤ ንግግሯ የተረጋጋ እና ድምፆቿም ዝግ ያሉ ናቸው፤ በየቀኑም መንፈሳዊ ርምጃ (ብቃታዊ መሻሻል ዕድገት) ማድረግ ትፈልጋለች፤ በየቀኑም ያነን ታደርጋለች፤ በጠዋት ስትነሣም ከዚኽ በፊት አስቀድማ ከሠራቻቸው አስበልጣ ሥራዎቿን ለመሥራት ትፈልጋለች፤ ሞትን ፈጽማ አትፈራም ነበር ይልቁኑ በሐዘን ኹና የመንግሥተ ሰማያት መዠመሪያ (መግቢያ) እንዳላቋረጠች በየቀኑ እያየች በጸሎቷ ታነሣለች) በማለት የደናግል መመኪያነቷን በስፋት ገልጾታል፡፡

ምንጭ፡-
✍️ ነገረ ማርያም በብሉይ ኪዳን (500 ገጾች)
✍️ ነገረ ማርያም በሐዲስ ኪዳን (402 ገጾች)
✍️ ነገረ ማርያም በሊቃውንት ክፍል 1 (290 ገጾች)
✍️ ነገረ ማርያም በሊቃውንት ክፍል 2 (242 ገጾች)
ከሚባሉት ያሳተምኳቸው መጻሕፍት የተወሰደ [በድጋሚ ፓስት የተደረገ)

[የአማናዊት መቅደስ የቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ይደርብን፤ መልካም በዓል፡፡]
[ጸሎቷ እንዲጠብቀን በረከቷ እንዲትረፈረፍልን ወደ ቤተ መቅደስ መግባቷን አስመልክታችሁ እጅግ አብዝተን የምንወዳት የፈጣሪያችን የክርስቶስ እናትን አመስግኗት]

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን።ታኅሣሥ 3 ባዕታ ለማርያም እምቤታችን ቤተ መቅደስ የገባችበት ዕለት ነው፡፡ ➛ መልአኩ ቅዱስ ፋኑኤልም እመቤታችንን ሰማያዊ ኅብ...
11/12/2025

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን።
ታኅሣሥ 3 ባዕታ ለማርያም እምቤታችን ቤተ መቅደስ የገባችበት ዕለት ነው፡፡

➛ መልአኩ ቅዱስ ፋኑኤልም እመቤታችንን ሰማያዊ ኅብስት የመገበበትና የተሾመበት ዕለት ነው፡፡

➛ ዳግመኛም በዚኽች ዕለት ቀድሰው ሕዝቡን ሁሉ ሲያቆርቡ ቢመሽባቸው ፀሐይን እንደ ኢያሱ ገዝተው ያቆሟት እና 8 እንጀራን አበርክተው 8ሺህ ሕዝብ በመመገብ ጌታችንን የመሰሉት አቡነ ዜና ማርቆስ ዕረፍታቸው ነው፡፡

🔥 በዓታ ለማርያም

የብርሃን እናቱ የድንግል ወላዲተ አምላክን የትውልዷን ነገር እንዲህ ነው፡- ጴጥርቃ እና ቴክታ የሚባሉ የከበሩ ደጋግ ሰዎች በኢየሩሳሌም በአንድነት ተጋብተው በሕገ እግዚአብሔር ይኖሩ ነበር፡፡ እነዚህም በእግዚአብሔር የሚያምኑ የተወደዱ ጻድቃን ደግ ሰዎች ናቸው፡፡ እነርሱም በእግዚአብሄርም በሰውም ዘንድ የተመሰከረለላቸው ባለጸጎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን መካን ስለነነበሩ የሚወርሳቸው ልጅ አልነበራቸውም፡፡
አንድ ቀን ጴጥርቃ ቴክታን እንዲህ አላት፡- ‹‹እህቴ ሆይ! ይህን ሁሉ የሰበሰብነውን ገንዘባችንን ምን እናደርገዋለን? ልጅ የለን የሚወርሰን፣ አንቺም መካን ነሽ እኔም ካንቺ በቀር ሌላ ሴት አላውቅም›› አላት፡፡ እርሷም ‹‹ወንድሜ ሆይ! አምላከ እስራኤል ለእኔ ልጅ ቢነሳኝ አንተም እንደኔው ሆነህ ትቀራለህን? ከሌላ ደርሰህ ውለድ እንጂ›› ብላ ብታሰናብተው እንደዚህ ያለ ነገር እንኳንስ ላደርገው በልቦናዬም እንዳላስበው አምላከ እስራኤል ያውቃል›› አላት፡፡ እርሷም ‹‹አምላከ እስራኤል የሚያደርገውን የሚያውቅ የለም፣ ትላንትና ማታ በህልሜ ነጭ ጥጃ ከማኅፀኔ ስትወጣ ያችም ነጭ ጥጃ ሌላ ነጭ ጥጃ ስትወልድ እንዲሁ እስከ 7ት ትውልድ ሲዋለድ ሰባተኛይቱ ጨረቃን ስትወልድ፣ ጨረቃዋም ፀሐይን ስትወልድ አየሁ›› አለችው፡፡ እርሱም በጠዋት ከህልም ፈቺ ዘንድ ሔዶ የነገረችውን ሁሉ ነገረው፡፡ ያም ህልም ፈቺ ‹‹እግዚአብሔር በምሕረቱ አይቷችኋል፣ በሳህሉ መግቧአችኀል፣ 7 አንስት ጥጆች መውለዳችሁ 7 ሴቶች ልጆች እና የልጅ ልጆች ትወልዳላችሁ፤ ከቤታችሁ ሰባተኛይቱ ጨረቃ መውለዷ ከሰው የበለጠች ከመላእክትም የከበረች ደግ ፍጥረት ትወልዳላችሁ የፀሐይ ነገር ግን አልታወቀኝም›› አለው፡፡
ጴጥርቃም ሕልም ፈቺው የነገረውን ሁሉ ሔዶ ለሚስቱ ነገራት፡፡ እርሷም ‹‹እንጃ አምላከ እስራኤል የሚያደርገውን ማን ያውቃል!?›› ብላ ዝም አለች፡፡ ከዚያም ፀንሳ ሴት ልጅ ወለደች፡፡ ስሟንም ሄሜን ብለው አወጡላት፤ ሄሜንም አድጋ ለአካለ መጠን ስትደርስ አጋብተዋት ሴት ልጅ ወለደች፣ በስምንተኛ ቀኗም ዴርዲ ብለው ስም አወጡላት፡፡ ዴርዲም አድጋ እንዲሁ ሴት ወለደችና ቶና አለቻት፣ ቶናም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ሲካር አለቻት፣ ሲካርም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ሴትና አለቻት፣ ሴትናም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ሄርሜላ አለቻት፣ ሄርሜላም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ንጽህት ቅድስት ክብርት የምትሆን እመቤታችንን የምትወልደውን ሐናን ወለደች፡፡
ይህቺም ሐና በሥርዓት አድጋ ለአእምሮ ስትበቃ አካለ መጠን ስትደርስ ከቤተ መንግስት ወገን ከነቅዱስ ዳዊት ወገን ከሆነው ከቅዱስ ኢያቄም ጋር አጋቧት፡፡ እነዚህ ቅዱሳን ኢያቄምና ሐና በአንድነት ተጋብተው ሲኖሩ ልጅ አጡ፡፡ እነርሱም እጅግ ደጋግ ሰዎች ነበሩ፡፡ አንድ ልጅ እንኳ ስላልነበራቸው እጅግ ያዝኑ ነበር፡፡ ወደ ቤተመቅደስ እየሄዱ እግዚአብሔር ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ አጥብቀው ይለምኑት ነበር፡፡ መብዓ ይዘው ለሊቀ ካህኑ ሲሰጡት ሊቀ ካህኑም እንኳ ሳይቀር ‹‹እግዚአብሔር ብዙ ተባዙ ያለውን ሕግ በእናንተ ላይ እንዳይፈጸም አድርጎ ልጅ የከለከላችሁ ኃጢአተኛ ብትሆኑ ነውና መብዓችሁን አልቀበልም›› ብሎ በእጅጉ አሳዝኗቸዋል፡፡ በሊቀ ካህኑ እያዘኑና እየተከዙ ሲመለሱ ከድካማቸው ያርፉ ዘንድ ዛፍ ሥር ተቀመጠው ሳለ እርግቦች ጫጩቶቻቸውን ሲያጫውቱ ተመልክተው ‹‹ለእነዚህ ወፎች እንኳ ልጆችን የሰጠህ አምላክ ለእኛስ መች ይሆን ልጅ የምትሰጠን?›› ብለው እጅግ አምርረው አለቀሱ፡፡
ሲያዝኑ ሲጸልዩ ውለው ወደቤታቸው ሲመለሱ ርግብ ከልጆቿ ጋር ስትጫወት አይታ ‹‹አቤቱ ጌታዬ ለዚች እንስሳ ልጅ የሰጠህ አምላክ ምነው ለኔ ልጅ ነሳኸኝ?›› እያለች ምርር ብላ አለቀሰች፡፡ እንዲህ ብለው ሲያዝኑ ሲጸልዩ ውለው ከዘካርያስ ከሊቀ ካህናቱ ሄደው ‹‹አቤቱ ጌታችን ሆይ ወንድ ልጅ ብንወልድ ተምሮ ቤተ እግዚአብሔርን አገልግሎ እንዲኖር እንሰጣለን፤ ሴት ልጅም ብንወልድ ውኃ ቀድታ መሶብ ወርቅ ሰፍታ መጋረጃ ፈትላ ካህናትን አገልግላ እንድትኖር እንሰጣለን›› ብለው ስዕለት ገቡ፡፡ ዘካርያስም ‹‹እግዚአብሔር ጸሎታችሁን ይስማችሁ ስዕለታችሁን ይቀበልላችሁ የልቦናችሁን ሀሳብ ይፈጽምላችሁ›› ብሎ አሳረገላቸው።
ከዚህም በኋላ ቅድስት ሐና እና ቅዱስ ኢያቄም ዕለቱን ራእይ አይተው ነገር አግኝተው አደሩ፡፡ ራእዩስ እንዴት ነው ቢሉ ኢያቄም ‹‹7ቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ›› አላት፡፡ ‹‹ወፍ›› የተባለው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ነጭነቱ ንጽሐ ባህሪው ነው፤ ‹‹ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ›› ማለቱ የኢያቄምን (የሰውን) ባህርይ ባህርይ እንዳደረገው ዕወቅ ሲል ነው፡፡ 7ቱ ሰማያት የተባሉ የጌታችን ልዩ ልዩ ባሕርይው ምልአቱ ስፋቱ ርቀቱ ልዕልናው ናቸው፡፡ ሐናም ‹‹እኔም ደግሞ አየሁ እንጂ›› አለችው፡፡ ‹‹ምን አየሽ?›› ቢላት ‹‹ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማህጸኔ ስትተኛ አየሁ›› አለችው፡፡ ‹‹ርግብ›› የተባለች እመቤታችን ድንግል ማርያም ናት፤ ነጭነቱ ንጽህናዋ ቅድስናዋ ድንግልናዋ ነው፡፡ ‹‹ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማኅፀኔ ስትተኛ አየሁ›› ማለቷ ብሥራተ ገብርኤልን በጆሮዋ ሰምታ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጌታችንን መፀነሷን ነው፡፡ ይህንኑም ራእይ ያዩት ሐምሌ 30 ዕለት ነው፡፡
እነርሱም እንዲህ ያለ ራእይ ካየን ነገር ካገኘን ብለው ዕለቱን በሩካቤ ሥጋ አልተገናኙም ይልቁንም ፈቃደ እግዚአብሔር ቢሆን ብለው አዳምንና ሔዋንን ‹‹‹ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሉአት›› ብሎ ያበሰረ አምላክ ለእኛስ ይልክልን የለምን?›› ብለው ዕለቱን አልጋ ምንጣፍ ለይተው እስከ 7 ቀን ድረስ ለየብቻቸው ሰነበቱ፡፡ ነሐሴ በባተ በሰባተኛው ቀን ‹‹‹ከሰው የበለጠች ከመላእክት የከበረች ደግ ፍጥረት ትወልዳላቹህና ዛሬ በሩካቤ ሥጋ ተገናኙ› ብሎሏችኀል ጌታ›› ብሎ መልአኩ ለቅድስት ሐና ነገራት፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አብርሃምን እና ሳራን የተመለከተ አምላክ በኢያቄምና ሐና አማካኝነት ለዓለም ድኅነት ምክንያት የሆነችውን እና ዓለም ሳይፈጠር በአምላክ ልቦና ታስባ ትኖር የነበረች የተነገረላት ትንቢት ሊፈጸም የአባት የእናቷ የቅድመ አያቶቿ ራእይ ሊተረጎም ጌታ የፈቀደበት ጊዜ ሲደርስ እመቤታችን እግዝእትነ ማርያም እሁድ እለት ነሐሴ 7 ቀን በ16 ዓ.ዓ ተፀነሰች፡፡
እመቤታችን ከተፀነሰች በኋላ አይሁድ ቀንተው ተነሱባቸው ቅናቱ እንዴት ነው ቢሉ ሳሚናስ የሚባል የጦሊቅ ልጅ ከኤዶቅ ካጎቱ ቤት ሄዶ ሞተ፤ እነርሱም እንቀብራለን ብለው ባልጋ ይዘው ሲሄዱ ከመንገድ አሳረፉት፡፡ ቅድስት ሐናም የአጎቷ ልጅ ነበርና ለማልቀስ ብትደርስ ዘመዶቿ ሁሉ ተሰብስበው ሲላቀሱ ቆዯአት፤ እርሷም አብራ እየዞረች ስታለቅስ ጥላዋ ቢያርፍበት መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ብድግ ብሎ ተነሥቶ "ስብሃት ለኪ ማርያም እሙ ለፀሐየ ጽድቅ ለአብ ሙሽራው ለወልድ ወላዲቱ ለመንፈስ ቅዱስ ጽርሃ ቤቱ ተፈስሂ ደስ ይበልሽ" ብሎ ሰገደላት፡፡ አይሁድም ይህ ተአምር ሲደረግ ከዚያው ነበሩና "ምነው ሳሚናስ ምን አየህ? ምን ትላለህ?" ቢሉት "ከዚች ከሐና ማኅፀን የምትወለደው ሕፃን ሰማይ ምድርን አየርን የፈጠረ አምላክን ትወልዳለች እያሉ መላእክት ሁሉ ሲያመሰግኗት ሰማሁ" አላቸው፡፡ ዳግመኛም "እኔንም ያነሣችኝ የፈወሰችኝ ያዳነችኝ እርሷ ናት" አላቸው፡፡ አይሁድም "በል ተወው ሰማንህ" ብለው ቅናት ጀመሩ፡፡ ሐና በእርጅናዋ ጊዜ መፀነሷን የተመለከቱ ዘመዶቿና ያገሯ ሰዎች ተገርመው እየመጡ ይጠይቋት ነበር፡፡ እመቤታችን ማርያም በፅንስ እያለች ብዙ ታምራትን አድርጋለች። ከእነዚህም መካከል ዐይነ ስውር የነበረችው የአርሳባን ልጅ ወደ ሐና መጥታ እውነትም ሐና መጸነሷን ለማረጋገጥ ሆዷን ዳሰሰቻት፡፡ እርሷም ሳታስበው ዐይኗን ስትነካ ዐይኗ በራላት፡፡ እመቤታችንም በተፀነሰች በ9 ወር ከአምስት ቀን የግንቦት መባቻ ዕለት ግንቦት 1 ተወለደች፡፡ ሦስት ዓመትም በሆናት ጊዜ እናትና አባቷ ቅዱስ ኢያቄምና ቅድስት ሐና ስዕለታቸውን አስበው የአምላክ እናት ብፅዓት አድርገው ለእግዚአብሔር ይሰጧት ዘንድ በዚህች ዕለት ወደ ቤተ መቅደስ ወሰዷት፡፡
የብርሃን እናቱ ክብርት እመቤታችን ከበዓሏ ረድኤት በረከት ትክፈለን።

🔥 አቡነ ዜና ማርቆስ

አባታችን ዜና ማርቆስ ሀገራቸው ጽላልሽ አውራጃ ምድረ ዞረሬ ስትሆን ትውልዳቸው ከነገደ ሌዊና ከእስራኤል ነገሥት ወገን ነው፡፡ ወላጆቻቸው ልጅ በማጣት ሲያዝኑ አንድ ዕለት ሐዋርያውና ወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ ወደ እናታቸው ማርያም ዘመዳ ሌሊት መጥቶ ገድሉና ትሩፋቱ በዓለም ሁሉ የመላ ጻዲቅ ልጅ እንደምትወልድ ነገራት፡፡ ለአባቱ ለቀሲስ ዮሐንስም እንዲሁ ተገልጦለት ‹‹ሚስትህ ማርያም ዘመዳ የካቲት 24 ፀንሳ ኅዳር 24 ቀን ይኸውም በካህናተ ሰማይ በዓል ቀን ትወልዳለች፣ ስሙም ዜና ማርቆስ ይባላል›› በማለት ብስራቱን ነግሮታል፡፡
በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ ብሥራት መሠረት አባታችን በተወለዱም ዕለት ቅዱስ ዑራኤልና ቅዱስ ሩፋኤል የብርሃን ልብስ አልብሰው በክንፋቸው ሲጋርዱአቸው ለሰዎችም ሁሉ ታይቷል፡፡ በወቅቱም የአባ ሳሙኤል ዘወገግ አባት እንድርያስና የአቡነ ተክለሃይማኖት አባት ቅዱስ ጸጋ ዘአብ እስኪደነቁ ድረስ ይህን በዓይናቸው ተመልክተዋል፡፡ ሁለቱ መላእክትም ከእናታቸው ዕቅፍ ወስደው ወደ ሐዋርያው ማርቆስ መቃብር ወስደው ለማርቆስና ለቅዱሳን ጳጳሳት አስባርከዋቸው መልሰው ለእናቱ ሰጧቸው፣ እናቱ ግን ይህን አታውቅም ነበር፡፡ አቡነ ዜና ማርቆስም በተወለዱ በሦስተኛው ቀን በእግራቸው ቆመው ‹‹አንድ አምላክ ለሆኑ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ እሰግዳለሁ›› ብለው ሦስት ጊዜ አምላካቸውን አመስግነው ሰግደዋል፡፡ በ40 ቀኑ ሲጠመቅ የሚያጠምቀው ካህን የአባቱ ወንድም እንድርያስ ውኃው ሲፈላ አይቶ ሸሽቷል፡፡ መልአኩም እንዳይፈራ ነግሮት ለእርሱም ተአምር እንደሚደረግለት አስረዳው፡፡ እንድርያስም ዕድሜው 72 ነበርና ራሰ በራ ስለነበር በውኃውም ራሱን ቢታጠብበት ጸጉር አብቅሏል፡፡ ሕዝቡም ሁሉ ይህን አይቶ አደነቀ፡፡ ያችም ውኃ ሌሎች በጣም ብዙ ተአምራትን አደረገች፡፡
አንድ ዓመት በሆነውም ጊዜ ቤተክርስቲያን ውስጥ እየዳኸ ሲሄድ መልአክ በክንፎቹ አቅፎ ወስዶ ጌታችንና እመቤታችን ጋር አቅርቦት አስባርኮታል፡፡ እንዲሁም የ15ቱን ነቢያት፣ የ12ቱን ሐዋርያት የ72ቱን አርድእት፣ ሃይማኖታቸው የቀና የ318ቱን ሊቃውንት፣ የጻድቃንን፣ የሰማዕታትን የእነዚህን ሁሉ በረከት እንዲቀበል ካደረገው በኋላ ወደዚያች ቤተክርስቲያን መለሰው፡፡ ከጳጳሱ ከአቡነ ጌርሎስ ድቁናን ተቀብሎ ከአባቱ ጋር ወደ ሀገሩ ሲመለስ ዘራፊዎች ደብድበው በትራቸውንም ሳያስቀሩ ዘረፏቸው፡፡ አቡነ ዜና ማርቆስም ወደ ፈጣሪው በጸለየ ጊዜ በትራቸው እባብ ሆና ነድፋ ገደለቻቸው፡፡ በኋላም ወደ አምላካቸው ጸልየው ከሞት እንዲነሱ በማድረግ በአካባቢውም ያሉ ሰዎች ሁሉ በእርሱ አምላክ እንዲያምኑ አድርጓቸዋል፡፡
ከዚህም በኋላ ብሉያትንና ሐዲሳትን ጠንቅቆ ከተማረና ካደገ በኋላ ሚስት አጭተው አጋቡት፡፡ እርሱ ግን በዚያው በሠርጉ ዕለት ማታ ጌታ ‹‹እናትና አባቱን ሚስቱን ቤቱን ንብረቱን ያልተወ ሊያገለግለኝ አይችልም›› ያለውን ቃል አስቦ ሚስቱን እንዲህ አላት፡- ‹‹እኅት ሆይ! የዚህ ዓለም ኑሮ ምን ይጠቅመናል፣ ዓለሙም ፍላጎቱም ያልፋል፡፡ ስለዚህ የነፍሴን ድኅነት ለመሻት እሄድ ዘንድ አሰናብችኝ›› ሲላት እርሷም ‹‹አንተ የተውከው ዓለም ለእኔስ ምን ይጠቅመኛል?›› በማለት ሁለቱም ሰው ሳያያቸው ከጫጉላ ቤታቸው በሌሊት ወጥተው ሄዱ፡፡ ቅዱስ ዑራኤልና ቅዱስ ሩፋኤልም እየመራቸው ዜና ማርቆስን ምሁር ገዳመ ኢየሱስ እርሷን ደግሞ ወደ ቤተ ደናግል ማማስ ደብር አደረሷቸው፡፡ እርሷም ሙትን እስከማስነሣት ድረስ ታላላቅ ተአምራትን እያደረገች ቆይታ ተጋድሎዋን ፈጽማ በጥር 21 ቀን በክብር ዐርፋለች፡፡ ዐርፋ የተቀበችውም በደመና ተነጥቃ ኢየሩሳሌም ከሄደች በኋላ እመቤታችን በተቀበረችበት በጌቴሴማኒ ሲሆን ሁለት አንበሶች ጉድጓድ ቆፍረው ቀብረዋታል፡፡
አባታችንም በምሁር ሀገር ይመለክ የነበረውን ማኮስ የተባለውን ጣዖት በመሬት ውስጥ ቀበረውታል፡፡ ገዥውም ተቆጥቶ በአባታችን ላይ ክፉ ሲያደርግ ‹‹ካላመንክ አንተም እንደ አምላክህ እንደ ማኮስ መሬት ተከፍታ ትውጥሃለች›› ብሎ በተናገረበት ቅጽበት ገዥውን ከነሠራዊቱ መሬት ተከፍታ ዋጠቻቸው፡፡ ከዚያም ፈጥነውና በደመና ተነጥቀው ወደ ግብፅ በመሄድ ከአባ ብንያሚን ቅስና ተቀብለው መጡና መሬት ተከፍታ የዋጠችውን የገዥውን ቤተሰቦች ጨምሮ ብዙ ሺህ የምሁር ሕዝቦችን አስተምረው አጠመቋቸው፡፡ ያንን ገዥም ስለ ተጠመቁ ልጆቹና ሚስቱ ብለው ከ5 ዓመት በኋላ በጸሎታቸው ኃይል ከሞት አስነስተውታል፡፡ በዚሁ ሀገር ከአባ ዜና ማርቆስ ጋር ሳሉ የኢትዮጵያው ጳጳስ አባ ጌርሎስ በድንገት ዐርፈው ሳለ ጻዲቁ ዜና ማርቆስ ጸሎት አድርገው ከሞት አስነሥተዋቸዋል፡፡ ሌላም እንዲሁ በጉራጌ ሀገር ገርዳን የሚባለውን ጣዖት ሰባብረው በውስጡ የነበረውን ሰይጣንን እንደ ትቢያ በኖ እስኪጠፋ ድረስ አስጨንቀውታል፡፡ ሕፃናቱን ጨምሮ ከ124 ሺህ በላይ የሚሆኑትን ሕዝቦችም አስተምረው አጥምቀዋቸዋል፡፡ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤልም ሁልጊዜ እንደ ጓደኛ እያናገራቸው ይረዳቸው ነበር፡፡
አባታችን ዜና ማርቆስ የሚያደርጓቸው እጅግ ድንቅ የሆኑ ተአምራት በሕዝብ ዘንድ ውዳሴን እያመጣ እንዳያስቸግራቸው ብለው ይህን ተአምር የማድረግ ሥራ እግዚአብሔር እንዲያርቅላቸው ይለምኑት ነበር፡፡ ወግዳ በምትባል ሀገር ሄደው በዋሻ ውስጥ ሳሉ አቡነ ተክለሃይማኖት ወደ እርሳቸው መጥተው አብረው በዋሻው ብዙ ተአምራትን እያደረጉ ቆይተዋል፡፡ ለአባ ዜና ማርቆስና ለሌሎች ለብዙ አባቶች የምንኩስና አባት የሆኑት አቡነ ተክለሃይማኖት ትሕትናቸውን ያሳዩ ዘንድ አቡነ ዜና ማርቆስን ያገለግሏቸው ነበር፡፡ ወደ ሞረት ሀገር እንዲሄዱ መልአክ ነግሯቸው ሁለቱም ሄደው በዚያም አብረው ተቀምጠዋል፡፡ ጣዖት አምላኪውን የሞረቱ ገዥ ሊገድላቸው ፊልጎ ከነሠራዊቱ ወዳሉበት ዋሻ ሄደ፡፡ አቡነ ዜና ማርቆስም ተራራዋን በሥላሴ ስም ባርከው ቢያዟት የገዥውን ጭፍሮች አፏን ከፍታ ዋጠቻቸው፡፡ ገዥውን ድል አሰግድንም በተአምራቸው አሳምነውት አስተምረው አጠመቁት፡፡
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ገብርኤል ለአቡነ ተክለሃይማኖት ተገልጦላቸው ወደ ግራርያ ሀገር እንዲሄዱ ስለነገራቸው አቡነ ተክለሃይማኖት የመላእክትን አስኬማ ለአቡነ ዜና ማርቆስ አልብሰዋቸው ዜና ማርቆስንም በደብረ ብስራት እንዲጸኑ ነግረዋቸው ወደ ግራርያ ሄዱ፡፡ ሲሄዱም የደብረ ብስራት ዛፎቹ እንጨቶቹና ደንጊያዮቹ ሁሉ አቡነ ተክለሃይማኖትን እንደ ንጉሥ ሠራዊት ከፊት ከኋላ ሆነው ሸኝተዋቸዋል፡፡ አባታችንም ‹‹የወንድሜን የዜና ማርቆስን ቦታ ትታችሁ ከዚህች ምድር ትሄዱ ዘንድ አልፈቅድምና ሁላችሁ በየቦታችሁ ቁሙ›› ብለዋቸዋል፡፡ ‹‹ሰውም እንኳ ቢሆን ለምንኩስና ወደ እኔ ዘንድ ወደ ግራርያ ከመምጣቱ በፊት ይህን ምድር ሳይሳለም ወደ እኔ አይምጣ›› በማለት ቃልኪዳናቸውን ከደብረ ብስራት ጋር አድርገዋል፡፡
አባታችን ዜና ማርቆስ በኤልያስ ሠረገላ ሆነው እግዚአብሔርን ወደማያውቁት ወደ አዳል ሕዝቦች ሄደው ከጣዖት አምላኪው ንጉሥ ከአብደልማል ፊት ወንጌልን ሲያስተምሩ ንጉሡ በጦር ወግቶ ገድሏቸዋል፣ ነገር ግን መልአኩ ሩፋኤል መጥቶ ከሞት አሥተስቷቸዋል፡፡ የንጉሡን ጣዖትና አገልጋዮቹን መብረቅ ከሰማይ ወርዶ ሲያጠፋቸው ንጉሡ ሠራዊታቸው ደግሞ በመሬት ላይ ወድቀው ቀርተዋል፡፡ ከዓርብ እስከ ሰኞም ድረስ ጨለማ ሆኖ ከቆየ በኋላ ከአባታችን ከተወጋ ጎናቸው የፀሐይ ብርሃን ወጥቶ ለንጉሡ አብደልማል አብርቶለታል፡፡ እርሱም አምኖ ከነቤተሰቡ የተጠመቀ ሲሆን ሚስቱም በአረማውያን ዘንድ ለክርስቶስ ምስክር ሆና አንገቷን ተሰይፋ ሰማዕትነትን ተቀብላለች፡፡ በሀገሪቱም የተጠመቁት ሰዎች ቁጥር ከስምንት መቶ ሺህ በላይ ናቸው፡፡
ከዚህም በኋላ አቡነ ዜና ማርቆስ እንደ ሐዋርያትም ደመና በመጥቀስ ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ሄደው ሁሉንም የተቀደሱ ቦታዎችን ተሳልሟዋል፡፡ ከጌታችን መቃብር ላይ አፈር ዘግነው ከዮርዳኖስም ወንዝ ውኃ ቀድተው ለንስር አሞራዎች አሸክመው ወደ ገዳማቸው በማምጣት በደብረ ብስራት ምድር ካለው አፈርና ውኃ ጋር ጨምረውታል፡፡ ጌታችም ‹‹ይህችን ምድርህን እንደ ኢየሩሳሌም አድርጌልሃለሁ›› የሚል ቃልኪዳን ሰጥቷቸዋል፡፡ አባታችን ከደብረ ሊባኖስ አውራጃ ራሱን ያስመልክ የነበረን ሰይጣን ገዝተው ይዘው እስከ ደብረ ብስራት ድረስ የቤተክርስቲያን መሥሪያ እንጨት አሸክመውታል፡፡ በዚያም እንጨት በመሸከም ሲያገለግላቸው ኖሯል፡፡
አባታችን ዜና ማርቆስ ወደ ዋልድባ በመሄድ ከአባ ሳሙኤል ጋር ተገናኝተው እንዲሁም ከሌሎች በርካታ አባቶች በየቦታው እየሄዱ በረከት ተቀብለዋል፡፡ ወደ ትግራይም በመሄድ የተሰዓቱ ቅዱሳንን ገዳማት ተሳልመው ወደ ሰሜንም ሄደው ዜማውን ሲያዜም ያሳያቸው ዘንድ ወደ ቅዱስ ያሬድ መቃብር ሄደው ሰባት ቀን ሲማጸኑ ከቆዩ በኋላ ወደ አክሱም ጽዮን ሄደው በዚያ ከቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱስ ኤፍሬምና ከቅዱስ አባ ሕርያቆስ ጋር ሆኖ እነርሱ ድርሰታቸውን ሲያነቡ ያሬድ ደግሞ ድርሰታቸውን እያዜመው ተገልጠውላቸዋል፡፡ አባታችን ወደ ላሊበላም ሄደው ከቅዱስ ላሊበላ በረከትን ተቀብለዋል፡፡ ወደ ጣና ደሴትም ሄደው በዚያ ካሉ ቅዱሳን ተባርከዋል፡፡ ሐይቅ እስጢፋኖስም አባ ኢየሱስ ሞዐ ጋር በመሄድ እንዲሁ ተባርከዋል፡፡ በታናሽ ደመናም ወደ ብሔረ ሕያዋን ተነጥቀው ሞትን ካልቀመሱት ከሄኖክ፣ ከኤልያስና ከዕዝራ በረከትን ተቀብለዋል፡፡ ወደ እስላም ሀገርም በመሄድ ለአንድ ዓመት ቆይተው በዚያ ያሉ ሕዝቦችን በተአምራቸውና በትምህርታቸው አሳምነው አጥምቀዋቸዋል፡፡ ጌታችን በምድር ላይ ብዙ ቃልኪዳን ከሰጣቸው በኋላ ወደ ሰማይ አውጥቶ ገነትንና ሲኦልን ሁሉን አሳይቷቸዋል፡፡
አቡነ ዜና ማርቆስ 8 እንጀራን አበርክተው 8ሺህ ሰዎችን በመመገብ ጌታችንን መስለውታል፡፡ ቀድሰው ሕዝቡን ሁሉ ሲያቆርቡ ቢመሽባቸው ፀሐይን እንደ ኢያሱ ገዝተው አቁመዋታል፡፡ በታኅሣሥ ወር መባቻ አባታችን በገዳመ ደንስ በረሃ ያገኛት ተአምረኛዋ ሥዕለ ማርያም ወዳለችበት ቤተክርስቲያን ሄደና ለመቀደስ ሠራዒ ካህን ሆኖ ተሠየመና እንደሚገባ የቅዳሴውን ሥርዓት ጀመረ፡፡ ማዕጠንት ይዞ እየዞረ የቤተ ክርስቲያኑን በሮች በሚያጥንበት ጊዜ ሥጋ ወደሙን ለመቀበል እርስ በእርሳቸው ሲጨናነቁ የልጆቹ መነኮሳትን ብዛት ተመለከተ፡፡ ያን ጊዜም በልቡ አሰበ፣ እንዲህም አለ፡- ‹ይህን ያህል ያለውን ሰው ቅዱስ ቊርባን ማቀበል እንዴት ይቻላል? ይህ ሁሉ ሰው በተራ እስከሚቀበል ድረስ ፀሐይ ይገባል፣ መሽቶ ሌሊትም ይሆናል› አለ፡፡ ከዚህም በኋላ ዐይነ ልቡናውን ወደ ሰማይ አቅንቶ ‹አቤቱ ጠላቶቹን እስከደመሰሰና ለእስራኤል ልጆች ርስታቸውን እስካካፈለ ድረስ ለኢያሱ ፀሐይን በገባዖን ያቆምክ አንተ ነህ፤ ዛሬም ቅዱስ ሥጋህን ክቡር ደምህን ለእነዚህ ባሮችህ ቅዱሳን መነኮሳትና ለሕዝቦችህ እስከማቀብላቸው ድረስ እንዲሁ በቸርነትህ ብዛት ፀሐይን አቁማት› ብሎ በጸለየ ጊዜ ፀሐይዋ ወዲያውኑ ቆመች፡፡ ከዚህም በኋላ ቅዳሴውን ጨርሶ ሕዝቡን ሁሉ አቆረባቸው፡፡››
ቅዱስ አባታችን በምሁር ኢየሱስ ገዳም ከሬብ በሚባል ዋሻ ውስጥ 40 ዓመት ዘግተው ተጋድለዋል፡፡ በዚህም ሳሉ መልአክ የዕረፍታቸውን ዕለት ታኅሣሥ ሦስት ቀን እንደሚሆን ስለነገራቸው ታኅሣሥ አንድ ቀን ወደ ገዳማቸው በመሄድ ቀድሰው ሕዝቡን ሁሉ ሲያቆርቡ ቢመሽባቸው ፀሐይን ለሁለተኛ ጊዜ እንደ ኢያሱ ገዝተው አቁመዋታል፡፡ አባታችን ዜና ማርቆስ የዕረፍታቸውን ዕለት ከመልአኩ ከተረዱ በኋላ ለደቀ መዛሙርቱን እንዲህ አሏቸው፡- ‹‹ከዚህ ዓለም የምለይበት ጊዜ ደርሷልና ወደ ፈጣሩዬ እሄዳለሁ፣ እኔ ሽማግሌ አባታችሁ የምመክራችሁን ስሙ፣ ከበጎ ሥራ ሁሉ አስቀድማችሁ እርስ በእርሳችሁ ተዋደዱ፣ ፍቅር ሰማያዊ መንግሥትን ለማግኘት በባለሟልነት ወደ እግዚአብሔር ፊት ያደርሳልና›› ብለው መከሯቸው፡፡ ዳግመኛም ጾመኛ ነኝ አትበሉ አሏቸው፡፡ ‹‹ስለ ነፍሳችሁ ድኅነት፣ ከመከራና ከጥፋትም ሁሉ ለማምለጥ በምትጾሙ ጊዜ እንዲህ እየጾማችሁ ሳላችሁ ስለምትሹት ግብር ወደ ዓለም ሰዎች ብትደርሱና በጾም ቀን ሲበሉና ሲጠጡ ብታዩአቸው መብልና መጠጥን በሚወዱ ሰዎች ፊት በውጭ በአደባባይ ‹ዛሬ የጾም ቀን ስለሆነ እኛ እንጾማለን› አትበሉ፡፡ ስለ እናንተ መጾምና ስለ እነርሱም አለመጾም አንዳች አትናገሩ፣ ባለመጾማቸውም አትንቀፏቸው፡፡ ስለ ሌላ ሥራ ወደማይጾሙ ሰዎች ብትደርሱ ግን በጾም ዕለት ወንድሞቻችን ‹ኑ አብረን እንብላ› ቢሏችሁ እኛ እንጾማለን አትበሉ፣ እንዲህ በሉ እንጂ፡- ‹ወደ እናንተ ከመምጣታችን በፊት ከቤት በልተናል፣ ጠግበናል› ስትሏቸው እናንተ እንደምትጾሙ ያውቃሉ፡፡›››
ከዚህም በኋላ አቡነ ዜና ማርቆስ ታኅሣሥ ሁለት ቀን የደቀ መዛሙርቶቻቸውን እግር ሲያጥቡ ውለው አስቀድሞ መልአኩ እንደነገራቸው ታኅሣሥ ሦስት ቀን በ140 ዓመታቸው ነቢይም፣ ሐዋርያም፣ ካህንም፣ ባለራእይም፣ የሀገራችንም ብርሃን የሆኑት ጻዲቁ አባታችን በክብር ዐርፈዋል፡፡
የአቡነ ዜና ማርቆስ ረድኤት በረከታቸው ይደረርብን በጸሎታቸው ይማረን።

ምንጭ፦ የታኅሣሥ ❸ ስንክሳር

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

🍃🍃🍃 🍃🍃🍃 🍃🍃🍃 🍃🍃

ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ
እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ
ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ
እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀ መበለት ውኩፈ
እም እለ አብዑ ብዑላን ዘተርፈ።

ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን
ሰማዕታት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን
ደናግል ዓዲ ወመነኮሳት ኄራን
ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን
እስከ አረጋዊ ልሒቅ እምንዑስ ሕፃን።

ለዘጸሐፎ በክርታስ
ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ
ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ
ወለዘሰምዐ ቃሎ በእዝነ መንፈስ
በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኲሉ እምባእስ
ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ
ወይፈኑ ለነ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ
እምይዜ ወእስከ ለዓለም አሜን።

ጌታ ሆይ ከብልጽግናቸው ብዛት የተነሳ ብዙ መባ ካገቡት ይልቅ የደሀይቱን አነስተኛ መባ እንደተቀበልህ ለሁል ጊዜ የሚያገለግሉህ አእላፍ መላእክትን እያሳሰብሁ በችግሬ ጊዜ የማቀርብልህን ምስጋና ተቀበል።

እናንተም ቅዱሳን ነቢያት የወንጌል ሰባኪያን ሐዋርያት ሰማዕታትና ጻድቃን ትጉሃን መላእክት ፍጹማን ደናግል እንዲሁም ደጋጎች መነኰሳት ሆይ ልጅ አዋቂ ሳይለይ የምንሰበሰብበትን የጉባኤ ቦታ ባርኩ።

ይህን መጽሐፍ ወረቀት አዘጋጅቶ ብራና ደምጦ የጻፈውንና ያጻፈውንም የተረጐመውን ቃለ ንባቡን በእርጋታ መንፈስ እና በተመስጦ ሕሊና ያዳመጠ በደለኛን ሁሉ የምታስምር የጌታ እናቱ በማርያም ጸሎት ኢየሱስ ክርስቶስ በአንድነት ይማረን። አሜን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼⁼
ከታች ያለውን ማስፈንጠሪያ በመጫን ቤተሰብ ይሁኑ
Tᴇʟᴇɢʀᴀᴍ - https://t.me/Synaxarium

Fᴀᴄᴇʙᴏᴏᴋ
🔹https://www.facebook.com/MeseleNigatuDek0

🔸https://www.facebook.com/Mesele.Nigatu.Deko


ታኅሣሥ ➋ ቀን 2011 ዓ.ም

Address

Awassa

Telephone

+251926265782

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ስንክሳር posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to ስንክሳር:

Share