Discover Amhara AMECO

Discover Amhara AMECO Contact information, map and directions, contact form, opening hours, services, ratings, photos, videos and announcements from Discover Amhara AMECO, Media/News Company, Bahir Dar.

ያለፈው ዓመት የአማራ ክልል የቱሪዝም እንቅስቃሴ እንዴት ነበር ?ባሕር ዳር: መስከረም 07/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል ዓለም አቀፍ ቅርሶችን ጨምሮ በርካታ ተፈጥሯዊ፣ ታሪካዊ፣ ሃይ...
17/09/2025

ያለፈው ዓመት የአማራ ክልል የቱሪዝም እንቅስቃሴ እንዴት ነበር ?

ባሕር ዳር: መስከረም 07/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል ዓለም አቀፍ ቅርሶችን ጨምሮ በርካታ ተፈጥሯዊ፣ ታሪካዊ፣ ሃይማኖታዊ እና ባሕላዊ የቱሪዝም መስህብ ሀብቶች የሚገኙበት ነው፡፡

በክልሉ በርካታ የኅብረተሰብ ክፍሎች በዘርፉ ተሰማርተው አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡ ለመኾኑ በ2017 ዓ.ም የአማራ ክልል የቱሪዝሙ ዘርፍ እንቅስቃሴው ምን ይመስል ነበር?

በጎንደር ከተማ የአንድ ሆቴል ሥራ አስኪያጅ የኾኑት አቶ ደሳለኝ ይልማ የጎንደር ከተማ በሺዎች የሚቆጠሩ ጎብኝዎችን የምታስተናግድ ከተማ ናት ብለዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በጸጥታ ችግር ምክንያት በቱሪዝም ዘርፉ ተቀዛቅዞ ነበር፤ በ2017 ዓ.ም በተወሰነ ደረጃ መነቃቃት መፈጠሩን አንስተዋል፡፡ የጥምቀት በዓል በደማቅ ሁኔታ መከበሩ፣ ክልላዊ የባሕልና ኪነ ጥበብ ፌስቲቫል እና ሌሎች ኮንፈረንሶች በጎንደር ከተማ መካሄዳቸው ቱሪዝሙ እንዲነቃቃ አድርገዋል ነው ያሉት።

የጎንደር ከተማ በርካታ የቱሪዝም ጸጋዎች ያለበት ነው ያሉት አቶ ደሳለኝ ለዘርፉ መቀዛቀዝ ዋናው ችግር የሰላሙ ሁኔታ ነው ብለዋል። መንግሥት እና ኅብረተሰቡ ለሰላም በጋራ መሥራት እንዳለባቸው ተናግረዋል።

የቅዱስ ላሊበላ እና አካባቢዋ የቱሪስት አስጎብኝዎች ማኅበር ሊቀ መንበር እስታሉ ቀለሙ የላሊበላ ከተማ ዓመቱን ሙሉ ጎብኝዎች የማይለዩት ነበር ብለዋል፡፡ በኮሮና ቫይረስ መከሰት፣ በሰሜኑ ጦርነት እና በአማራ ክልል በተፈጠረው የጸጥታ ችግር ምክንያት ዘርፉ ተጎድቶ ቆይቷል ነው ያሉት፡፡

የከተማዋ ዋናው የኢኮኖሚ ምንጭ ቱሪዝም በመኾኑ ከፍተኛ ጉዳት ገጥሟት እንደቆየም አንስተዋል፡፡ በ2017 ዓ.ም በክልሉ ቢሮ በኩል በቱሪዝም ዘርፍ ለተሰማሩ አካላት የማነቃቂያ ሥልጠና መሰጠቱን አንስተዋል፡፡ አልፎ አልፎ በአውሮፕላን የሚመጡ ጎብኝዎች ቢኖሩም የየብስ ትራንስፖርት ላይ ባለው ችግር ምክንያት የሃይማኖት ተጓዦች እንደበፊቱ ዓመቱን ሙሉ እንደማይመጡ ነው የተናገሩት።

ሰላም ለቱሪዝም መነሻ መሰረት በመኾኑ ችግሩን ለመፍታት መንግሥት እና የሚመለከታቸው አካላት ለሰላም ሊሠሩ ይገባል ብለዋል፡፡ በአከባቢው አንጻራዊ ሰላም በመኖሩ ጎብኝዎች ወደ አካባቢው እንዲሄዱ ጠይቀዋል።

የአማራ ክልል ባሕልና ቱሪዝም ቢሮ ምክትል ኀላፊ ዓባይ መንግሥቴ የክልሉ የጸጥታ ሁኔታ በቱሪዝም ዘርፉ ላይ ተጽዕኖ አሳድሮ መቆየቱን ገልጸዋል፡፡ ይሁንና በ2017 ዓ.ም በተፈጠረው አንጻራዊ ሰላም በቱሪዝም ዘርፍ በርካታ ሥራዎች መሠራታቸውን ተናግረዋል፡፡

በቅርስ ጥገና እና እንክብካቤ በኩል ከፌደራል መንግሥት ጋር በመተባበር የጎንደር አብያተ መንግሥታት እና የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ዓለም አቀፍ ቅርሶች ጥገና እየተከናወነ መኾኑን ገልጸዋል፡፡ በክልሉ መንግሥትም 80 ሚሊዮን ብር በመመደብ እና ከ59 ነጥብ 4 ሚሊዮን ብር በላይ ከማኅበረሰቡ እንዲያዋጣ በማድረግ 156 ቋሚ እና 604 ተንቀሳቃሽ ቅርሶች ላይ የጥገና እና እንክብካቤ ሥራ ተሠርቷል ብለዋል፡፡

የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርት ተገንብቶ መጠናቀቁን ያስታወሱት ምክትል ኀላፊው በደቡብ ወሎ ዞን የሚገኘው የሎጎ ሐይቅ የቱሪስት መዳረሻ ልማት ግንባታ እየተቀላጠፈ መኾኑን አንስተዋል፡፡ በጣና ሐይቅ በሚገኙ ገዳማት ለጎብኝዎች ምቹ የእግረኛ መንገድ እና የወደብ ግንባታ ሥራዎችም መሠራታቸውን ጠቅሰዋል፡፡

በ2017 በጀት ዓመት ከ12 ሚሊዮን በላይ የሀገር ውስጥ እና 27 ሺህ በላይ የውጭ ሀገር ቱሪስቶች ክልሉን መጎብኘታቸውንም ተናግረዋል፡፡ ይህም ከተያዘው ዕቅድ በላይ ነው። በክልሉ የቱሪስት ቁጥር ሳይኾን ፍሰት መረጃ የሚያዝ ሲኾን ይህም በየመዳረሻዎች ከአንድ ጊዜ በላይ የሚቆጠር ቱሪስት መኖሩን ታሳቢ ያደረገ ነው ብለዋል፡፡

ከዚህም ከ5 ነጥብ 83 ቢሊዮን ብር ገቢ መገኘቱን ገልጸዋል፡፡ በክልሉ የነበረው የጸጥታ ችግር ለቱሪዝም እንቅስቃሴው አሉታዊ ተጽዕኖ ያሳደረ ነበር ያሉት ምክትል ኀላፊው እነዚህ ቱሪስቶች በተንቀሳቀሱባቸው የክልሉ አካባቢዎች ጎብኝዎችን በተገቢው ሁኔታ በመቀበል እና ደኅንነታቸውን በማስጠበቅ በኩል የኅብረተሰቡ ድርሻ የጎላ እንደነበር ጠቁመዋል፡፡ በዘርፉ ከ38 ሺህ በላይ ዜጎች በቋሚ እና በጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፈጠሩንም ገልጸዋል፡፡ እነዚህን ተግባራት ለማከናወን የማርኬቲንግ እና ፕሮሞሽን ሥራዎች እንደተሠሩም ገልጸዋል፡፡

የሀገር ውስጥ ቱሪስት ፍሰትም ካለፈው በጀት ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ5 ሚሊዮን ብልጫ እንዳለው ተመላክቷል።

በተያዘው በ2018 ዓ.ም የሚከናወኑ መደበኛ ተግባራትን በተሻለ ከመፈጸም ባለፈ የክልሉን የቱሪዝም ጸጋዎችን በማስተዋወቅ ጎብኝዎችን ወደ ክልሉ ለመሳብ ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሠራ አመላክተዋል፡፡

በተለይም ደግሞ የክልሉን ሃይማኖታዊ እና ባሕላዊ ክብረ በዓላትን ታሪካዊ ይዘታቸውን እና ዕሴቶቻቸውን ጠብቆ በማክበር የጎብኝዎች መስህብ እንዲኾኑ ለማድረግ እንሠራለን ብለዋል፡፡ ቱሪዝም ሰላም ይፈልጋል ያሉት ምክትል ኀላፊው የክልሉን የመስህብ ሀብቶች በማልማት እና በማስጎብኘት ኅብረተሰቡን ከቱሪዝም ተጠቃሚ እንዲኾን ሁሉም ለሰላሙ ትኩረት ሰጥቶ እንዲሠራ ጥሪ አቅርበዋል።

ዘጋቢ፡- ፍሬሕይወት አዘዘው

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን

የታሪክ አምባ - መቅደላባሕር ዳር: መስከረም 07/2018 ዓ.ም (አሚኮ) መቅደላ አምባ ለመድረስ ከደሴ ከተማ በስተምሥራቅ 130 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከምትገኘው የተንታ ከተማ የሁለት ሰዓት...
17/09/2025

የታሪክ አምባ - መቅደላ

ባሕር ዳር: መስከረም 07/2018 ዓ.ም (አሚኮ) መቅደላ አምባ ለመድረስ ከደሴ ከተማ በስተምሥራቅ 130 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከምትገኘው የተንታ ከተማ የሁለት ሰዓት የእግር መንገድ መጓዝ ያስፈልጋል፡፡
ጥንት ከመቅደላ ደብረ ታቦር ከዚያም ወደ ጣና ሐይቅ ዳርቻ የሚያዘልቅ በሀገሬውም፣ በውጭ ሀገር ጎብኝዎችም የሚታወቅ የእግር መንገድ ነበር፡፡ አሁን ላይ ስለዚህ መንገድ በውል የሚያውቅ እምብዛም የለም፡፡

ስለ መቅደላ ሲነሳ አጼ ቴዎድሮስ ይታወሳሉ። የመቅደላ አምባ ዙሪያ ገባውን ከረጅም አድማሳዊ ርቀት ለመቆጣጠር የሚያስችል በመኾኑ እና በዘመኑ የፖለቲካ ጂኦግራፊ ሁነኛ ሥፍራ ላይ በመገኘቱ ከፍተኛ ስትራቴጂካዊ ጥቅም ነበረው፡፡

አጼ ቴዎድሮስ ከጎንደር በኋላ የሥልጣን ማዕከላቸውን ለጊዜው ወደ ደብረ ታቦር ከዚያም ወደ መቅደላ በማዞር ለተቀረው ግዛት አርዓያ ሊኾን የሚችል የአሥተዳደር ሥርዓት ለማቆም ጥረት የጀመሩት በዚሁ ሥፍራ ነበር፡፡

በርካታ እና የተለያዩ የጦር መሳሪያዎች፣ ብዛት ያላቸው ገድሎች፣ መጻሕፍት እና ድርሳናት፣ እንዲሁም የንጉሡ የግል የክብር ዕቃዎች በሥርዓት ተሰድረው ይቀመጡ የነበረው በመቅደላው ግምጃ ቤት ነበር፡፡
የመቅደላው አሥተዳደር ኀላፊም ከንጉሡ የቅርብ ባለሟሎች እና የረጅም ጊዜ ወዳጆች መካከል አንዱ የነበሩት ደጃች አለሜ ነበሩ፡፡

በዘመኑ 15 መድፎች፣ 7 ሞርታሮች፣ 11 ሺህ 63 የተለያዩ ጠመንጃዎች፣ 875 ሽጉጦች እና 481 ሳንጃዎች፣ ከ555 የመድፍ እና የሞርታር አረሮች እንዲሁም 83 ሺህ 563 የተለያዩ ጥይቶች ጋር በመቅደላ የንጉሥ ግምጃ ቤት እንደነበሩ የታሪክ መረጃዎች ያወሳሉ፡፡ አሁን ከእነኝህ የጦር መሳሪያዎች ለታሪክ መዘከርነት በሥፍራው የሚገኘው ሴባስቶፖል የተባለው የንጉሡ ትልቅ መድፍ ነው፡፡

መጻሕፍቱ፣ ድርሳናቱ፣ የወርቅ እና የብር ዋንጫዎች፣ አክሊሎች እንዲሁም ሌሎች የንጉሡ የግል ሀብቶች የነበሩ ቅርሶች ከመቅደላው ጦርነት እና ከአጼ ቴዎድሮስ እረፍት በኋላ በደላንታ ሜዳ ላይ ለጨረታ ተሰጥተው የጠላት ሠራዊት ተቀራምቷቸዋል፡፡ ከእነኝህ ቅርሶች ከፊሉ በእንግሊዝ ሀገር በሚገኙ የተለያዩ ሙዚየሞች ተቀምጠው ይገኛሉ፡፡

በመቅደላ አካባቢ ሊጎበኙ የሚችሉ ጥንታዊ እና ታሪካዊ ቅርሶች መካከል በአጼ ላሊበላ ዘመን ከአንድ አለት ተፈልፍሎ እንደተሠራ የሚነገርለት የፉል አምባ ጊዮርጊስ ውቅር ቤተ ክርስቲያን፣ በ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በአጼ ይስሃቅ ዘመነ መንግሥት እንደተተከለች የሚታመነው የመቅደላ ማርያም፣ በንጉሥ ሚካኤል የተሠራው እና የንጉሡ አጽም በክብር አርፎ የሚገኝበት ተንታ ሚካኤል ዋነኞቹ ናቸው፡፡

በውስጣቸውም የኢትዮጵያ ጥንታዊነት የሚዘክሩ እና የሚመሰክሩ በርካታ ተንቀሳቃሽ ቅርሶችን ይዘዋል፡፡

ምንጭ፡- የአማራ ክልል የቱሪስት መስህብ ሀብቶች አጭር ቅኝት መጽሐፍ

በሠናይት በየነ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን

በምሽት ጨረቃ የሚደምቀው ለውፈረ ለውፈ - ዋርዳ ሆየ ባሕር ዳር፡ መስከረም 03/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የአዲስ ዘመን ብስራትን ተከትሎ ጨለማውን መሸኛ አዲሱን መማፀኛ ቀለል ያሉ ደመራዎች በ...
13/09/2025

በምሽት ጨረቃ የሚደምቀው ለውፈረ ለውፈ - ዋርዳ ሆየ

ባሕር ዳር፡ መስከረም 03/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የአዲስ ዘመን ብስራትን ተከትሎ ጨለማውን መሸኛ አዲሱን መማፀኛ ቀለል ያሉ ደመራዎች በዋግ ኽምራ ነዋሪዎች መንደር ይጠበቃሉ፡፡

ጭሱ የክረምቱን ጭፍና ሽኝት እና ብርሃኑ የመፃዔ ጊዜው ተስፋ ምልክት ተደርጎም ይወሰዳል፡፡ ይህ ሕዝብ ለእያንዳንዱ የጊዜ ዑደት የራሱ መገለጫዎች ያሉት የባሕል ሀብታም ነው፡፡

ለውፈረ ለውፈ ከአዲስ ዘመን ጅማሮ እስከ መስከረም የመስቀል በዓል ማግሥት የሚጠናቀቅ የ17 ቀናት የምሽት ጨዋታ ነው፡፡

የክርስቶስን ግማደ መስቀል ለማግኘት የተደረገው ፍለጋ የተጀመረው በጭስ ነው፡፡ የዋግ ወጣቶች የሚጫወቱት ለውፈረ ለውፈ ጨዋታ መስከረም 16 ንግሥት እሌኒ መስቀሉን ለማግኘት ሥራ የጀመረችበትን ተምሳሌት ያደረገ ነው ያሉት የዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ቤተ ክህነት አስተዳዳሪ ሊቀ ኅሩያን ቀሲስ ኃይሌ ዓለሙ ናቸው፡፡

የመስቀሉ ፍለጋ የሰው ልጆች በአዲስ ዓመት የራሳቸውን ሕይዎት በአዲስ መልኩ እንዲፈልጉ የሚያነቃ ባሕላዊ ይዘት ያለው እየኾነ መምጣቱንም ነው ቀሲስ ኃይሌ የተናገሩት፡፡

መጋቢት 10 የተገኘው የክርስቶስ መስቀል ከእየሩሳሌም እስከ ቁንጥንጢንያ ተራሮች አማንያን ደመራ እየሠሩ እንዳከበሩ ሁሉ አሁንም ይህ ትውልድ በቅብብሎሽ ባሕላዊ ይዘትን ጨምሮ እያከበረው ነው ብለዋል ሊቀ ኅሩያን ቀሲስ ኃይሌ፡፡

ለውፈረ ለውፈ (ዋርዳ ሆየ) ጨዋታው ፀሐይ ወደ ማደርያዋ ስታመራ አካባቢው ለዐይን ያዝ ሲያደርግ ጀምሮ በኽምጠኛ ቋንቋ አርወ (አደባባይ) ተብሎ ከሚጠራ ሥፍራ ላይ ወጣት ወንዶች በትንሹ የሚንቀለቀል እሳት አቀጣጥለው የሚጫወቱት ሃይማኖታዊ ይዘት ያለው በጊዜ ሂደት ባሕላዊ ክዋኔ እየኾነ የመጣ ነው፡፡ የድንግዝግዙ ጨለማ ድባብ የሚደምቀው ቀድሞ በመጡ ተጫዋቾች ለውፈረ ለውፈ የግጥም ጥሪዎች ነው፡፡
ለውፈረ ለውፈ
ለውፈረ ለውፈ
እሆሆ ሽረሮ እሆሆ ሽረሮ
እሆሆ ሽረሮ እሆሆ ሽረሮ
የእኔማ እገሌ የምለው አይሰማማም ወይ
ሥራው አላልቅ ብሎት ጨለማው አስፈራህ ወይ
ኧረ ምን ዓይነት ነው ምን ዓይነቱ ፈሪ
አልቦ ያልጨረሰ፣ ጥጃ ያላሰረ፣ ያልታጠቀ ሱሪ
ለዛሬ ያልኾነ፣ ያልታጠቀ ቁምጣ
ጉልበቱ ይብረክረክ አንዳ'ይኑን ይጣ፡፡

እያሉ በሥራ ምክንያት የዘገዩ ጓደኞቻቸውን ጎንጦ በማያደማው ወግቶ በማይገድለው ወኔ ቀስቃሽ ግጥሞቻቸው ይጣራሉ፡፡

በተለይ በተራራዎች አካባቢ መንደሮቻቸውን ያደረጉት እነዚህ ሕዝቦች የገደል ማሚቶ እያስተጋባ የሚያጮኸው ድምፅ ወንድነታቸውን ይፈታተናል፡፡ የላሞች እና የጥጆዎች ጥሪ በቀነሰበት፣ የከብቶች ልፈፋ ፀጥ ረጭ ባለበት ወቅትማ አብዛኛው መንደርተኛ እራት እየበላ ወይም ሥራ ያዛለውን ሰውነታቸውን ለማሳረፍ ጥድፊያ የሚኾንበት ነው፡፡

አንዳንዴ በየመንደሩ ወጣቶቹ በሚያሰሙት ሩጫ ጋጣቸውን ለማስጠበቅ ከሚጮሁ ውሾች በቀር ከለውፈረ ለውፈ ተጫዋቾችን ድምፅ አልፎ የሚሰማ የለም፡፡ ፍየሎቻቸውን በየማታው እየበተነ የአመሉን የሚያደርሰው ነብር ሲመጣ ውሾች ጮኽ ብለው ሲጮኹ ባለቤቶች ወጥተው ‘‘ጅላው ጅላጉ …. ጅላው ጅላጉ’’ እያሉ ውሻውን የሚያደፋፍሩበት ድምፅ ጥሶ ሊደመጥ ይችላል፡፡

ታዲያ የለውፈረ ለውፈ ጉነጣው ለዘገዩ ወጣቶች ብቻ ሳይኾን ልጆቻቸውን ላዘገዩ ወላጆችም ይደርሳቸዋል፡፡ ያኔ ስማቸው እየተጠራ ሲሾመሩ … ‘‘አረ ተነስልን!’’ ወይም ‘‘ቶሎ በልተህ ሂድ!’’ ብለው ያጣድፉታል፡፡ ‘‘አሁን የእንትና ልጅ ተጠራ! አሁን ደግሞ እገሌን እንዲህ አሉት! ውይ እገሌንም እንዲህ አሉት’’ በማለት የዕለት በዕለት ግንኙነታቸው የሚያዩቸውን የሰዎችን ባሕሪ እያነሱ እየተሳሳቁ ይጎሽሟቸዋል፡፡ ለዚህ ሁሉ ማረፍያው ግን ደርሶ መገላገል ነው፡፡

የእኛማ እገሌ መልካሙ መልካሙ
ልጅን ጉያ ይዞ ምነው አስታመሙ፡፡
የኛማ እገሌ በጣም ይገርማሉ
ነብር ጋር እንዳልዋሉ
አብረው እንዳልታገሉ
ዛሬ ፈርተው መሰል፤ ምነው እምቢ አሉ፡፡

በማለት ፍላጎቱ እንዲነሳሳ አቅል ያሳጣሉ፡፡ ከሞላ ጎደል አብዛኞቹ ከመጡ በኋላ በሚንቦገበገው መለስተኛ የደመራ እሳት ላይ በኽምጠኛ ‹‹ቕርጘ ብረው›› (የብርቱካን መጠን ያለው ትኩስ ድንጋይ) ይጨመራል፡፡

ከዚያማ ከለውፈረ ለውፈ (ናማ ኑማ) ወደ እሆሆ ሽረሮ ያመራል፡፡ በጋራ በለውፈረ ለውፈ ጥሪው በኋላ በትልቅ ግርማ ባላቸው ተምሳሌትነታቸው የትጋት የኾኑ እንስሳት ስም ሁለት ቡድን ፈጥረው ወደ ውድድር ሜዳ ይገባሉ፡፡ አብዛኛው ጊዜ አንበሳ እና ነብር የሚል ስያሜን የየቡድናቸው መጠሪያ ያደርጉታል፡፡

እሆሆ ሽረሮ ከመለስተኛ የደመራ እሳት ላይ የገባውን የሚለበልበውን ድቡልቡል ድንጋይ የተሰየመው ዳኛው በእንጨት ገፋ አድርጎ በሳር እየጠበጠበ ይወረውራል፡፡ በቃ ምን ታደርጉት ልክ እሳት ካለመኖሩ በቀር እንደአውሮፓውያኑ ራግቤ በሉት፡፡ ከዚያማ ዳኛው ‘‘እሆሆ ሽረሮ…’’ ብሎ ራቅ ብለው ከደመራው በወጣው የእሳት ነበልባል ውር ውር እያሉ ወደሚታዩት ተጫዋቾች በኃይል እያንከባለለ መሬት ለመሬት ያሾረዋል፡፡

የለውፈረ ለውፈ ተጫዋቾቹ አቋቋም መስመር የለውም ድንጋዩ ሊገኝ በሚችልበት ሁሉ ተዘበራርቀው ነው የሚፋለሙት፡፡

ይሄ ቀላል ጉዳይ አይደለም፤፡ የወንድነት ማረጋጋጫ በዘገዩ ጊዜ በሽሙጥ የተሰደቡበትን ተረክ ፉርሽ የሚያደርጉበት መልካም አጋጣሚ ነው፡፡ ማን ነው ያንን የሚፋጅ ድቡልቡል እሳት በመዳፉ ይዞ ከዚያ ሁሉ ወጠምሻ አምልጦ ከደመራው እሳት ላይ ጨምሮ ጮቤ የሚረግጠው? አጓጊ ነው፡፡ ብቻ ተቀባብለውም ቢሆን አለያም በፍትጊያ ውስጥ በስልትም ሆነ በጉልበት ልቆ ያ ነበልባል ውስጥ የሚፋጅ ድንጋይን የመጨመር ትግል ነው፡፡

ድቡልቡሏ ድንጋይ እሳቷን በወጣቶቹ እጆች እየተሻሸች አንዳንዴም ፍጅቷ ሲጠና መሬት ላይ በጉረምሶች እግር እየተረጋገጠች ነበልባልነቷ ይቀንሳል፡፡ በየትኛውም ዘዴ ከመጨወቻ ሜዳው ወደ ነበረችበት እሳት ድንጋዩን ለጨመረ ቡድን እና ግለሰብ የሚቀርብ ሙገሳ፣ ድልቂያ፣ ዘፈን እና ግጥም ያንጎማልላል፡፡

በእርግጥ የመጀመሪያዋ ድንጋይ እሳቱ ጋር ስትጨመር ማንም አያሸንፍም፤ የቅድስት ድንግል ማርያም ነው ተብሎ ይጣላል፡፡ (ጨዋታው ሃይማኖታዊ ይዘት አለው ብያችሁ የለ?)፡፡ የእሷን በረከት ይዞ የመታገል ዕድል ማግኘት የጨዋታውን አጠቃላይ አሸናፊ እንደሚሰማው ዓይነት ነው፡፡ ለአሸናፊዎቹ እንዲህ ተብሎ ሊገጠምላቸው ይችላል፡፡

እሆሆ ሽረሮ እሆሆ ሽረሮ
እሆሆ ሽረሮ እሆሆ ሽረሮ
የብርቱ ልጅ ብርቱ
አንድ ጋን አተላ አይደርስም ካንጀቱ
ከድንጋይ ላይ ድንጋይ ከዚያ ላይ እሳት
እገሌ መብረቁ፤ አንበሳ ጉልበት፡፡

በዚህ የሚያበቃ እንዳይመስላችሁ አሸናፊዎቹ ከተሸናፊዎቹ ወገብ ላይ ቁብ ብለው በመደዳ ‘‘ዝቋላ ደርሼ፣ ሰቆጣ ደርሼ፣ ኮረም ደርሼ፣ ጎንደር ደርሼ፣ ደሴ ደርሼ’’ እያሉ ይደልቃሉ፡፡ አቤት ያኔ ተሸናፊ አያድርገኝ፡፡ ምንኛ ያስችላል፡፡

ጨዋታው በዚህ መልክ ያለገደብ ሊጫወቱት ይችላሉ፡፡ አንዳንዴም እስከ ንጋት የሚዘልቁበት አጋጣሚ እንዳለ ንጉሴ በሪሁን የተባሉ የሰቆጣ ከተማ ነዋሪ ነግውኛል፡፡

ከመስከረም አንድ ቀን ጀምሮ እስከ መስቀል በዓል የሚዘልቀው ይህ ጨዋታ ከአደባባዩ ትዕይንት ባለፈ በየቤቱ በመዞር ወተት እና የወተት ተዋፅኦ፣ ጠላ፣ እንጀራ እና ሙክት ይሰጣል፡፡ በወቅቱ ስጦታ ያላዘጋጁት ደግሞ ‘‘የመስከረም ማርያም፣ የኅዳር ሚካኤል፣ የታኅሣስ ገብርኤል አንድ ጋን ጠላ፣ አንድ ሙክት፣ ይህን ያህል እንጀራ…’’ እያሉ ይሳላሉ፡፡

ወጣቶቹም ቀኑን ጠብቀው ቃል የተገባላቸውን ስለት ይጠይቃሉ:: ‘እምቢ’ ከተባሉ ይመካከሩና በየአቅጣጫው ተራርቀው በመቆም (ተራራ ላይ ሊሆን ይችላል) ከዚያም እርስ በራሳቸው እየተጠራሩ “እከሌ ኡኡ፣ ኧረ እገሌ.. አቤት ኡኡ…” በማለት አስደንጋጭ የሆነ ጥሪ ያደርጋሉ። ከዚያም ቃል ገብቶ አልሰጣቸው ያለውን ሰውየ ስም በመጥራት ‘‘አቶ እከሌ ሙቷል፤ ቀብር ድረሱ’’ ይላሉ። ሌሎችም የቡድኑ አባላት ሩቅ ቦታ ሆነው ልክ እንደሞተ ሁሉ ‘‘ዋይ፣ ዋይ፣ ዋይ፣ ዋይ…’’ እያሉ ለማሳቀቅ ያሳብቃሉ፤ ነገር ግን ይሄ ይደረጋል ከመባሉ ውጭ ብዙን ጊዜ አይከሰትም፡፡

ትውልድ ያላቋረጠ የሕይዎት ዥረት ፍለጋ በትኩስ ድንጋይ ታሽቶ ይፈተናል፡፡ ለአዲስ ዓመት የጥንካሬ መሠረት እና የበረከት ማግኛ መንገድ ሁኖ ይዘልቃል፤ ለውፈረ ለውፈ በምሽት ጨረቃ የደመቀው ባሕላዊ ጨዋታ፡፡

አብዛኛው ግጥም ከመገኛ ቋንቋው ኽምጠኛ ወደ አማርኛ ኪናዊ ሁኖ የተተረጎመ ነው፡፡

ዘጋቢ፡- ግርማ ተጫነ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

የጀማ ወንዝ ዳር የሎሚ ልማትመስከረም 02/2018 ዓ.ም (አሚኮ) "አንሄድም ወይ ጀማ፣ሎሚ ልናለማ" ተብሎ ተዘፍኖለታል። በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ከሚገኙ ወረዳዎች ውስጥ ሞረትና  ጅሩ ...
12/09/2025

የጀማ ወንዝ ዳር የሎሚ ልማት

መስከረም 02/2018 ዓ.ም (አሚኮ)
"አንሄድም ወይ ጀማ፣
ሎሚ ልናለማ" ተብሎ ተዘፍኖለታል። በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ከሚገኙ ወረዳዎች ውስጥ ሞረትና ጅሩ ወራዳ በሎሚ ምርት የታወቁ ቆላማ አካባቢዎች ባለቤት ነው። በወረዳው በተለይም ጀማ ወንዝን ተከትሎ የተትረፈረፈ የሎሚ ምርት እንደሚገኝ የወረዳው የኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት መረጃ ይጠቁማል።

አካባቢው በአትክልትና ፍራፍሬ ብቻ ሳይኾን በሰብል ምርትም ከትርፍ አምራች አካባቢዎች አንዱ ነው። በእንስሳት ልማትም ቢኾን በተለይም የጅሩ ሰንጋ እንደሀገርም ታዋቂ እና ከፍ ያለ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያለው ነው።

ሞረት እና ጅሩ የውብ መልክዓ ምድር ባለቤትም በመኾኑ በቱሪዝም ጸጋው ተጠቃሽ ነው።

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

10/09/2025

የእንግጫ ነቀላ እና ከሴ አጨዳ ዜማዎች

08/09/2025

የሕዳሴ ግድብ ምረቃ የዋዜማ ዝግጂት

በባሕር ዳር ከተማ የተካሄደው የአማራ ክልል የክረምት በዓላት የማጠቃለያ ዝግጅት በምስል 👇በአሚናዳብ አራጋው
07/09/2025

በባሕር ዳር ከተማ የተካሄደው የአማራ ክልል የክረምት በዓላት የማጠቃለያ ዝግጅት በምስል 👇

በአሚናዳብ አራጋው

07/09/2025

የአማራ ክልል የክረምት በዓላት ማጠቃለያ

"የላክህልኝ ድሪ ሰላላ መላላመልሰህ ውሰደው ጉዳዬም አልሞላ" ባሕር ዳር:  ጳጉሜን 01/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የክረምት ወቅት ሊያልቅ ሲቃረብ፣ ምድሪቱ ስታሸበርቅ፣ ሜዳ እና ተራራዎች በአበ...
06/09/2025

"የላክህልኝ ድሪ ሰላላ መላላ
መልሰህ ውሰደው ጉዳዬም አልሞላ"

ባሕር ዳር: ጳጉሜን 01/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የክረምት ወቅት ሊያልቅ ሲቃረብ፣ ምድሪቱ ስታሸበርቅ፣ ሜዳ እና ተራራዎች በአበቦች ሲያጌጡ፣ አዲስ ዓመት መዳረሻ ላይ የምሥራቅ ጎጃም ልጃገረዶች የሚያከብሩት ተወዳጅ ክብረ በዓል አላቸው። እሱም የእንግጫ ነቀላ እና ከሴ አጨዳ ነው።

በዓሉን ማክበር የተጀመረው በኖኅ ዘመን የጥፋት ውኃ ታሪክን መሠረት በማድረግ ነው ይባላል። በኖኅ ዘመን የጥፋት ውኃ ምድርን ሸፍኗት ነበር።

ኖኅም በመርከብ ነበር። የጥፋት ውኃም አቆመ። ኖኅም ውኃው መጉደሉን ለማጣራት እርግብን እንደላካት ይነገራል፡፡ እርግብም የውኃውን መጉደል እና የአካባቢውን መለምለም ለማሳየት በአፏ ቄጤማ ይዛ ወደ መርከቡ እንደተመለሰች ይነገራል፡፡

ይህም ውኃው ለመጉደሉ እና የጨለማው ዘመን የማለፉ የምስራች ምልክት ኾኖ ይወሰዳል፡፡ ከዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ጋር በማስተሳሰር የእንግጫ ነቀላ በዓል እንደተጀመረ ከአማራ ክልል ባሕል እና ቱሪዝም ቢሮ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

ልጃገረዶች ልክ እንደ እርግቧ ነጭ ለብሰው የክረምቱ ጨለማ ማለፍን እና የጋራ ሸንተረሩ መለምለም እና ማበብን ለማየት ወደ መስክ ይወጣሉ። እንግጫ ነቅለው እና በአደይ አበባ አስጊጠው ወደ አብያተ ክርስቲያናት እና ዘመድ አዝማድ እየሄዱ “አዲስ ዓመት ገብቷል፤ ክረምቱ አልፏል፤ እንኳን አደረሳችሁ” እያሉ የምስራች ስጦታ ያበረክታሉ፡፡

ልጃገረዶች በዝማሬያቸው የሚያወድሱት እና የበዓላቸው ስያሜ የኾነው እንግጫ ስሩ ነጭ የኾነ የሳር ዘር ነው። ከሴ ደግሞ ጥሩ መዓዛ ያለው ተክል ነው።

በዚህ በዓል ዋናዎቹ ተሳታፊዎች ያላገቡ ልጃገረዶች ናቸው። ወንዶችም በሆያ ሆዬ ጨዋታ ያጅባሉ ያሉን በአነደድ ወረዳ ነዋሪ የኾኑት ወይዘሮ ሙሉቀን አይተነው ናቸው። ልጃገረዶች የተለያዩ ባሕላዊ ዜማዎችን እያዜሙ ወደ መስክ በመሄድ ለስጦታ የሚኾን ከሴ ያጭዳሉ፤ እንግጫ ይነቅላሉ ነው ያሉት።

የሚነቅሉት እንግጫም እምቡጥ ነው። ይህም ገና እምቡጥ ነን የሚለውን የልጅነት ጊዜያቸውን የሚገልጹበት ነው ይላሉ።

በሚነቅሉበት ጊዜ:-
"እንግጫችን ደነፋ፣ ጋሻውን ደፋ
እንግጫችን የወሩ፣ የቦረቦሩ …. " እያሉም ያዜማሉ ብለውናል።

የነቀሉትን እንግጫ ከአደይ አበባ ጋር በመጎንጎን በመጀመሪያ ወደ ቤተክርስቲያን ሄደው አበባውን ያስራሉ ነው ያሉት። ከሃይማኖት አባቶችም ምርቃን ይቀበላሉ። ከዚያም ተመልሰው በየቤቱ እየዞሩ ዜማዎችን እያዜሙ እና ባሕላዊ ጭፈራ እጨፈሩ የሚያከብሩት ልዩ በዓል እንደኾነ ነው የገለጹት፡፡

በጭፈራቸውም ወንዶችም ደቦት (ከእንጨት የሚዘጋጅ መብራት) ይዘው ያጅቧቸዋል። በየቤቱ እየሄዱ እንጎሮጎባሽ እያሉ እንኳን አደረሳችሁ ይላሉ። ወጣት ወንዶች የሚፈልጓትን ቆንጆም የሚመርጡበት እና የሚያጩበት በዓል ነው። በቀጣዩ ጥር እና በሚያዚያ ወር ለሚደረጉ ጋብቻዎች የመተጫጫ ጊዜ ነው።

ይህ በዓል ልጃገረዶች ከቤት ሥራ ነጻ ኾነው አምረው እና አጊጠው ከእኩዮቻቸው ጋር የሚጫወቱበት እንደኾነም አንስተዋል። ከሚዋቡባቸው መካከል ነጭ የባሕል ልብስ ይለብሳሉ፤ በወገባቸው ላይ ምሪ ያስራሉ። ምሪ ማለት ከቆዳ የሚሠራ እና ጫፉ ላይ ዛጎል ያለበት ያላገባች ሴት የምትታጠቀው መቀነት ነው። በተለያዩ ጌጣጌጦች አምረው እና ደምቀው ለመታየት እንደ ክታብ፣ ድሪ፣ መስቀል፣ ጠገራ ብር፣ አምባር፣ አልቦ፣ የጆሮ ጉትቻ ጌጣጌጦችን በማድረግ ይዋባሉ ነው ያሉት።

ሌላኛዋ የአነደድ ወረዳ ነዋሪ እና የበዓሉ ተሳታፊ የኾነችው ወጣት ተጎዳን ንጉሤ የእንግጫ ነቀላ በዓል ከጳጉሜ 1 ጀምሮ ልጃገረዶች የሚያከብሩት በዓል መኾኑን ገልጻለች። በበዓሉ ወቅት ልጃገረዶች ነጭ ባሕላዊ ልብስ ለብሰው በተለያዩ ጌጦች አምረው በዓሉን እንደሚያከብሩት ተናግራለች።

በዚህ በዓል ልጃገረዶች ከሚወዷቸው የከንፈር ወዳጆች ስጦታ ይበረከትላቸዋል፡፡ ይሄንም በዘፈን ይቀባበሉታል ነው ያለችው።

"የላክህልኝ ድሪ ሰላላ መላላ
መልሰህ ውሰደው ጉዳዬም አልሞላ" ይላሉ።

ቀኑን በሙሉ በመሰል ዜማዎች ሲጨፍሩ እና ሲጫወቱ እንደሚውሉ ገልጻለች። ልጃገረዶቹ እጃቸውን እንሶስላ ሞቀው፤ ፀጉራቸውን አሳምረው፤ የባሕል ቀሚስ ለብሰው፤ ዝማሬ እያሰሙ ይወጣሉ፡፡ በዕለቱም ከሥራ ነጻ ኾነው ሲጫወቱ እና ሲጨፍሩ እንደሚውሉ ተናግራለች። ከሚያዜሙት ዜማ መካከል

እቴ አደይ አበባ ነሽ
ውብ ነሽ ውብ ነሽ

አበባስ ያብባል በየሁሉ ደጅ
ምነው እኔ የሌለኝ የከንፈር ወዳጅ

አንተ የከንፈር ወዳጅ በጊዜ ሳመኝ
ጤፍ አበጥራለሁ የሰው ግዙ ነኝ።

የሰው ግዙ ሆኖ የሰው ግዙ መውደድ
እሳት በገለባ እፍ ብሎ ማንድድ። እያሉ ያዜማሉ።

የአነደድ ወረዳ ባሕል አና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት ኀላፊ አየነው አበራ በዓሉ በአዲስ ዓመት መዳረሻ ላይ የሚከበር መኾኑን ተናግረዋል። የእንግጫ ነቀላ እና ከሴ አጨዳ ክረምት አልፎ የአዲስ ዓመት መምጣትን አስመልክቶ የሚከበር በዓል መኾኑን ነው የገለጹት።

በዓሉ በአረንጓዴው የጎጃም ምድር ልጃገረዶች ነጭ ለብሰው ድንቅ ዝማሬ እያሰሙ ከጳጉሜ አንድ ጀምሮ እስከ አዲስ ዓመት የሚያከብሩት ነው ብለዋል። ይህንን በዓል ይዘቱን ጠብቆ ለትውልድ እንዲተላለፍ እየተሠራ እንደኾነም አንስተዋል።

የምሥራቅ ጎጃም ዞን ባሕል እና ቱሪዝም መምሪያ ተወካይ ኀላፊ ሙሉ ዓለማየሁ የዘንድሮውን የእንግጫ ነቀላ እና ከሴ አጨዳ በዓል እንደ ዞን ጳጉሜን 3/2017 ዓ.ም ለማክበር እየተዘጋጀን ነው ብለዋል። በወረዳዎች ደረጃ ቀደም ብለው በተለያዩ ዝግጅቶች ማክበራቸውን ነው የተናገሩት።

‎በዓሉ በአደባባይ እና በመስክ ልጃገረዶች እንግጫ ነቅለው በአደይ እና ሶሪት በመጎንጎን በባሕላዊ አልባሳት ተውበው የሚያከብሩት እንደኾነ አንስተዋል። የተለያዩ ዜማዎችን በማሰማት፣ ባሕላዊ ጭፈራ እንደሚያቀርቡም ገልጸዋል።

በበዓሉ ላይ ከወረዳዎች የተውጣጡ ልጃገረዶች፣ ወጣት ወንዶች እና ሌሎች የማኅበረሰብ ክፍሎች እንደሚሳተፉም ተናግረዋል።

ዘጋቢ፦ ፍሬሕይወት አዘዘው

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

የከሴ አጨዳ እና የእንግጫ ነቀላ ባሕላዊ ክዋኔው መንፈሳዊ ይዘትም ያለው ነው።ባሕር ዳር: ጳጉሜ 01/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የእንግጫ ነቀላ እና ከሴ አጨዳ በዓል በምሥራቅ ጎጃም ዞን በሁሉም...
06/09/2025

የከሴ አጨዳ እና የእንግጫ ነቀላ ባሕላዊ ክዋኔው መንፈሳዊ ይዘትም ያለው ነው።

ባሕር ዳር: ጳጉሜ 01/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የእንግጫ ነቀላ እና ከሴ አጨዳ በዓል በምሥራቅ ጎጃም ዞን በሁሉም ወረዳዎች እና ከተማ አሥተዳደሮች በድምቀት ሲከበር የኖረ በዓል ነው፡፡

በያዝነው ዓመትም በዓሉን በድምቀት እያከበሩ መኾናቸውን የተናገሩት የባሶሊበን ወረዳ ባሕል እና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት የቋሚ ቅርስ ምዝገባ ባለሙያው ተስፋው ገበየሁ ናቸው፡፡

በዓሉን ለማክበር ቀደም ብለው የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ሲከናወኑ የቆዩ መኾኑን ነው የገለጹት። በዓሉ በየጁቤ ከተማም በድምቀት ይከበራል ነው ያሉ፡፡

ይህ በዓል በአብዛኛው ሕጻናት፣ ወጣቶች እና ልጃገረዶች የሚሳተፉባቸው እና የእነሱ የመጫዎቻ፣ የመደሰቻ፣ የማመስገኛ እና የነጻነት ጊዜያቸው እንደኾነ ነው የገለጹት፡፡ገ
በዓሉ በባሶሊበን ወረዳ የተለያዩ የሥራ ኀላፊዎች፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ ከተለያዩ አካባቢዎች የተውጣጡ የባሕል አምባሳደሮች፣ የሃይማኖት አባቶች እና የአካባቢው ነዋሪዎች በተገኙበት በድምቀት እየተከበረ ነው ብለዋል፡፡

መልዓከ ሰይፍ መልካም መንግሥት በምሥራቅ ጓጃም ዞን የባሶ ሊበን ወረዳ ቤተክህነት ሥራ አሥኪያጅ እና የየጁቤ ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን አሥተዳዳሪ ናቸው። የከሴ አጨዳ እና የእንግጫ ነቀላ ባሕላዊ ክዋኔው መንፈሳዊ ይዘት ያለው እንደኾነም ነው የገለጹት። በኖህ ዘመን ምድር በንፍር ውኃ ጠፍታ በነበረበት ወቅት ኖህ እርግብን ወደ ምድር ላከ ይላል ታሪኩ ብለዋል።

እርግቧም የጥፋት ውኃ መጉደሉን ለማብሰር ከመሬት የበቀለውን ለምለም ቄጤማ በመያዝ ወደ ኖህ በመመለስ የምስራች ማብሰሯን የምናስብበት ምሳሌ እንደኾነ ነው የገለጹት።

ይህንንም ምሳሌ በማድረግ እርግቧ ለምለም ቄጤማ በአፏ ይዛ የጥፋት ውኃ መጉደሉን እንዳበሰረች ሁሉ ልጃገረዶቹ እንግጫ በመንቀል እና ከሴ በማጨድ በየዘመዶቻቸው እና በየጎረቤቶቻቸው ቤት በመሄድ እንኳን አደረሳችሁ በማለት ያበስራሉ ነው ያሉት።

ይህም የክረምቱን ወቅት እና የጨለማውን ጊዜ ወጥተን ከበጋው ደረስን በማለት ዘመን መለወጡን፣ የጨለማው ጊዜ ማለፉን እና በአዲስ ዓመት አዲስ ተስፋ መኖሩን የሚያበስሩበት ምሳሌ ነው ብለውናል።

ባሕል በሰው ልጅ የረጅም ዘመን ታሪክ ውስጥ ተፈጥሮን ለመረዳት፣ ለመቆጣጠር፣ ለማሥተዳደር፣ ለማስቀጠል እና የራሱን ህልውና ለማረጋገጥ በሰው ልጆች እና በተፈጥሮ በሚደረገው ትግል ከሰው ወደ ሰው የሚሸጋገር እና እየተሸጋገረ ያለ፣ የሚኖር ቁሳዊ እና መንፈሳዊ የቅርሶች ስብስብ ነው ያሉት ደግሞ የአማራ ክልል ባሕል እና ቱሪዝም ቢሮ የቅርሶች ጥናት ባለሙያ ነህምያ አቤ ናቸው።

ኢትዮጵያ የተለያዩ ሃይማኖታዊ እና ባሕላዊ ትውፊቶች በስፋት የሚከወኑባት ሀገር ናት ብለዋል ባለሙያው።

ከእነዚህ ባሕላዊ ሃብቶቻችን መካከልም ቡሄ፣ አሸንድየ፣ ከሴ አጨዳ፣ እንግጫ ነቀላ እና በዓባይ ወንዝ ላይ የሚከበረው የዓባይ ሩፋኤል በዓላት ዋና ዋናዎቹ እንደኾኑም አብራርተዋል፡፡

በክልላችን ነሐሴን እና ጳጉሜን የማይዳሰሱ የበዓላት ወቅት በማለት ብንጠራቸው ማጋነን አይኾንም ነው ያሉት ባለሙያው። አንገታቸውን ደፍተው የሚኖሩ ልጃገረዶች በዓደባባይ ወጥተው ከከንፈር ወዳጆቻቸው እና ለትዳር አጋር ከሚኾናቸው ጋር የሚገናኙበት፣ የወደዱትን የሚያሞግሱበት፣ አምላካቸውን የሚያወድሱበት የነጻነት ጊዜያቶቻቸው ናቸው ብለዋል፡፡

በዓላቱ ትውፊታቸውን ይዘው እንዲከበሩ እና እንዳይጠፉ አክብሮ እና አስጠብቆ ለማቆየት ቢሮው ሰፊ ሥራ እያከናወነ መኾኑንም ባለሙያው ገልጸዋል።

ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር ጥናት በማካሄድ፣ የፓናል ውይይት በማድረግ እና ሲምፖዚየም በማዘጋጀት በዓደባባይ ጎልተው እንዲወጡ እና በትውልዱ ውስጥ እንዲሰርጹ የማድረግ ሥራ እየተሠራ መኾኑንም ተናግረዋል።

ዘጋቢ:- ሰናይት በየነ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

በዓመት አንድ ጊዜ  የሚከወነው  ገበያ እና  ታሪኮቹባሕር ዳር፡ ነሐሴ 30/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን መንዝ ጌራ ምድር ወረዳ የሚገኘው ምስሐለ ማርያም በጥንታዊ ታ...
05/09/2025

በዓመት አንድ ጊዜ የሚከወነው ገበያ እና ታሪኮቹ

ባሕር ዳር፡ ነሐሴ 30/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን መንዝ ጌራ ምድር ወረዳ የሚገኘው ምስሐለ ማርያም በጥንታዊ ታሪኩ፣ በባሕላዊ እሴቶቹ እና ልዩ በኾነው የቅዱስ ሩፋኤል ዓመታዊ የንግስ በዓል አከባበር የሚታወቅ ልዩ ስፍራ ነው።

ይህ ቦታ ከመሐል ሜዳ ከተማ በ13 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ ሲኾን የነገሥታት ታሪካዊ አሻራ ያረፈበት እንደኾነ ይነገራል።

👉ታሪካዊ አመጣጥ

የቦታው ታሪክ ከአጼ አምደ ጽዮን ዘመን ጋር የሚያያዝ ነው። ንጉሡ በዚህ ስፍራ ቤተ መቅደስ ገንብተው "ማርያምን የምለምንበት" የሚል ትርጉም ያለውን "ምስሐለ ማርያም" የሚል ስያሜ እንደሰጡት ይነገራል።

👉ልዩ የገበያ ሥርዓት እና ትንብያው
በየዓመቱ ጳጉሜ 3 ቀን በሚከበረው የቅዱስ ሩፋኤል ንግሥ በዓል ላይ አንድ ልዩ የገበያ ሥርዓት ይካሄዳል።

የመንዝ ጌራ ምድር ባሕል እና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት ኀላፊ ማህሌት ዓላማው ለአሚኮ እንዳሉት በዚህ ቀን ለገበያ የቀረቡ የቁም እንስሳት እና የተለያዩ ሸቀጣሸቀጦች ዋጋ ለቀጣዩ ዓመት የኑሮ ሁኔታ ትንብያ ያገለግላል።

የገበያ እቃ ዋጋ ከጨመረ ለቀጣዩ ዓመት የኑሮ ውድነት እንደሚኖር ይተነበያል፤ ከቀነሰ ደግሞ ዓመቱ የኑሮ ውድነቱ የተሻለ እንደሚኾን ይታመናል ነው ያሉት።

ይህንን ትንበያ ቀደምት ነገሥታት ለሁሉም የኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲያገለግል አድርገው ይጠቀሙበት እንደነበር ይነገራል።

👉ባሕላዊ የጋብቻ ሥርዓት

ቀደም ሲል በዚህ ዓመታዊ ገበያ ላይ ወጣት ወንዶች እና ልጃገረዶች ይተጫጩ እንደነበር የአካባቢው ነዋሪዎች ይገልጻሉ።

ሚስት የሚፈልግ ወጣት ራሱን አስውቦ ወደ ገበያው ይወጣል፤ ባል የምትፈልግ ሴት በእጅ የተሠሩ እንደ ሰፌድ፣ ሌማት፣ እንቅብ እና የሸክላ እቃዎችን ይዛ ትወጣለች።

ወጣቱ ሴቷን አይቶ ካጫወታት እና ከወደዳት ለትዳር ይጠይቃታል፤ ሴቷም ወጣቱን ከወደደችው ተስማምታ ትዳር እንደሚመሰርቱ ይስማማሉ።

👉የዝናቡ ጸበል

በበዓሉ ዕለት ዝናብ ቢዘንብ፣ ማንም ሰው ጃንጥላ ዘርግቶ ራሱን አይከላከልም፤ ይልቁንም ዝናቡ እንዲመታው ተስተካክሎ ይቆማል፤ ምክንያቱም ዝናቡ በዓመት አንድ ጊዜ የሚገኝ "ድንቅ ጸበል" እንደኾነ ስለሚታመን ነው።

ይህ ስፍራ ከሃይማኖታዊ ፋይዳው ባሻገር ታሪካዊ፣ ባሕላዊ እና ማራኪ ገጽታዎች ያሉት በመኾኑ ለጥናት እና ምርምር፣ ለቱሪዝም መስህብነት ከፍተኛ እምቅ አቅም እንዳለውም ተናግረዋል።

የመንዝ ጌራ ምድር ነዋሪው ዘበነ ግዛው በዚህ ታሪካዊ የገበያ ቦታ እየሄዱ እንደሚገበዩ ገልጸዋል።
ገበያው ላይ ይሄ ቀረ የሚባል አገልግሉት እንደሌለ ለአሚኮ ተናግረዋል።

ሁሉም ነገር በአንድ ላይ የሚገኝበት ውብ እና ማራኪ ስፍራ ነው ብለዋል። ይህን ታሪካዊ ገበያ ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል በጉጉት የሚጠብቀው መኾኑን ገልጸዋል።

በገበያው ላይ ያልታዩ አዳዲስ ነገሮችም ብቅ ብቅ እንደሚሉ እና ረዘም ላለ ጊዜ የተጠፋፉም ሰዎች ገበያው ላይ የሚገናኙበት በመኾኑ በጉጉት የሚጠበቅ ቀን ነው ብለዋል። የግብይት ሥርዓቱ ቢጠና የቀደመውን እሴት እና ታሪክ ለማጉላት እንደሚያስችል ተናግረዋል። በተለይም በገበያው የሚደረገው ትንቢያ አዲስ ነገር ነው ብለዋል።

ዘጋቢ፦ ሰመሀል ፍስሀ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን

በደቅ ደሴት የተገነባው ወደብ የጎብኝዎችን እንቅስቃሴም ያሳድጋል። ባሕር ዳር: ነሐሴ 28/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የጣና ሐይቅ የጥበብ፣ የእምነት እና የታሪክ ማኅደር ሲኾን አያሌ ተፈጥሯዊ እ...
03/09/2025

በደቅ ደሴት የተገነባው ወደብ የጎብኝዎችን እንቅስቃሴም ያሳድጋል።

ባሕር ዳር: ነሐሴ 28/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የጣና ሐይቅ የጥበብ፣ የእምነት እና የታሪክ ማኅደር ሲኾን አያሌ ተፈጥሯዊ እና ሰው ሠራሽ መዳረሻዎችም አሉት። በጣና ሐይቅ ውስጥ ከሚገኙት ደሴቶች መካከል ደግሞ ደቅ ደሴት አንዱ ነው።

በውኃ ለተከበበችው የደቅ ደሴት ብቸኛው የትራንፖርት አማራጯ የባሕር ላይ ትራንስፖርት ነው። ለደቅ ደሴት በቂ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጥ ወደብ ባለመኖሩ የደሴቲቷ ነዋሪዎች ለችግር ተዳርገው ቆይተዋል። ይህንን መነሻ በማድረግ ነዋሪዎች ወደብ እንዲገነባላቸው ለዘመናት ሲጠይቁ ቆይተዋል።

የአማራ ክልል ባሕል እና ቱሪዝም ቢሮ የአካባቢውን የቱሪዝም ጸጋ መሠረት በማድረግ ከ21 ሚሊዮን ብር በላይ በኾነ ወጭ የወደብ ግንባታ እና የመሸጋገሪያ ድልድይ መገንባቱን አስታውቋል።

የቢሮው የቱሪዝም ልማት ዳይሬክተር መልካሙ አዳም የተገነባው ወደብ 8 ሜትር ስፋት እና 37 ሜትር ርዝመት ያለው ደረጃውን የጠበቀ መኾኑን ገልጸዋል።

በአሁኑ ወቅትም ወደቡ ለነዋሪዎች አገልግሎት እየሰጠ ስለመኾኑም ተናግረዋል። ወደቡን ገንብቶ ወደ ሥራ ለማስገባት የኅብረተሰቡ ተሳትፎ የጎላ አስተዋጽኦ እንደነበረውም አመላክተዋል።

የወደቡ ግንባታ በ1337 ዓ.ም እንደተመሠረተች ለሚነገርላት ለፈለገ ሕይዎት ጣና ሐይቅ ቅድስት አርሴማ ገዳምን የጎብኝዎች መዳረሻ ለማድረግ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ ነው አቶ መልካሙ የገለጹት፡፡

በጣና ሐይቅ የሚገኙ የቱሪዝም መዳረሻዎችን ለማስተሳሰር ሚናው የጎላ መኾኑንም ጠቁመዋል። ለክልሉ የቱሪዝም እንቅስቃሴም ተጨማሪ አቅም እንደኾነ ነው ዳይሬክተሩ ያብራሩት።

በፈለገ ሕይዎት ጣና ሐይቅ ቅድስት አርሴማ ገዳም የሰበካ ጉባኤ ጸሐፊ ቄስ ደመቀ አስናቀው በፊት ጎብኝዎች በናርጋ ሥላሴ እና በጉረር ቀበሌ በሚገኙት ወደቦች ይጠቀሙ እንደነበር አንስተዋል። ይህም ከፍተኛ እንግልት ይፈጥር እንደነበር ነው የሚገልጹት።

የተገነባው ወደብ ለብዙ ዘመናት ሲጠየቅ የቆየውን ጥያቄ የመለሰ እና በጥሩ ኹኔታ የተሠራ ስለመኾኑም ተናግረዋል። ወደ ገዳሟ ለሚመጡ ምዕመናን እና ሌሎች ጎብኝዎች ተጨማሪ የጉብኝት እድል እንደሚፈጥር አመላክተዋል።

ለነዋሪዎቿ ደግሞ የትራንስፖርት እፎይታን የሰጠ ስለመኾኑም ነው የገለጹት። ገዳሟን ለሚጎበኙ ጎብኝዎች ምቹ ኹኔታን የሚፈጥር ነው ይላሉ። የቀረው የመዳረሻ መንገድ እንዲሠራም ጠይቀዋል።

በደሴቲቷ ነዋሪ የኾኑት ቄስ ካሳሁን ይስማው ወደቡ ከመገንባቱ በፊት ወደ ቤተ ክርስትያኗ ይመጡ የነበሩት ጎብኝዎች ይቸገሩ እንደነበር አስታውሰዋል። አማኞችም በሌላ ወደብ በመጠቀም እስከ አንድ ሰዓት የሚደርስ የእግር ጉዞ ተጉዘው ይመጡ እንደነበር አንስተዋል።

አሁን ላይ ወደቡ በመገንባቱ ለነዋሪዎቹ እፎይታ እንደፈጠረላቸው ነው የገለጹት። ከወደቡ እስከ ቤተ ክርስትያኗ ያለው የመዳረሻ መንገድ አሁንም ምቹ አለመኾኑን ጠቅሰው በቀጣይ መንገዱ እንዲሠራም ጠይቀዋል።

በዚሁ ጉዳይ ምላሽ የሰጡት አቶ መልካሙ የመዳረሻ ልማት ሥራ በአንድ ጊዜ ተሠርቶ የሚጠናቀቅ ባለመኾኑ በነዋሪዎች የተነሳው ተጨማሪ የመዳረሻ መንገድ ልማት ጥያቄ በቀጣይ ኅብረተሰቡን በማሳተፍ ለማሟላት ጥረት ይደረጋል ነው ያሉት።

ዘጋቢ፦ አሰፋ ልጥገበው

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን

Address

Bahir Dar

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Discover Amhara AMECO posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to Discover Amhara AMECO:

Share