Discover Amhara AMECO

Discover Amhara AMECO Contact information, map and directions, contact form, opening hours, services, ratings, photos, videos and announcements from Discover Amhara AMECO, Media/News Company, Bahir Dar.

ዘመናትን የተሻገረው የራያዎች ድምቀት-ሶለል ባሕር ዳር: ነሐሴ 16/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በጋው አልፎ ክረምት ሲተካ የገረጣው መሬት በአረንጓዴ ልምላሜ ይሸፈናል። ምድር ልብሷን ትለብሳለች።...
22/08/2025

ዘመናትን የተሻገረው የራያዎች ድምቀት-ሶለል

ባሕር ዳር: ነሐሴ 16/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በጋው አልፎ ክረምት ሲተካ የገረጣው መሬት በአረንጓዴ ልምላሜ ይሸፈናል። ምድር ልብሷን ትለብሳለች። ጋራው እና ሸንተረሩ በእጽዋት ያሸበርቃል።

ክረምት ገብቶ፣ ዝናቡም መሬቱን አጥግቦ ከሰነባበተ በኋላ ምድር በሳር በቅጠሉ ትሞሸራለች፣ ዕጽዋትም ማበብ ይጀምራሉ፣ ምድር በአበቦች ትዋባለች።

ዝናብ የከረመበት መሬትም ከነሐሴ አጋማሽ ጀምሮ ጠፈፍ እያለ ሲመጣ፣ ደመናው እየገፈፈ ሲሸሽ፣ ፀሐይም ሙሽራ መስላ ትገለጣለች። በዚህ ወቅትም ልጃገረዶች ዓመቱን ሙሉ ሲናፍቁት የከረሙትን ጨዋታ የሚጫወቱበት የአሸንድየ ቅጠልም ይለመልማል።

ከዛሬ ነሐሴ 16/2017 ጀምሮ የራያ ልጃገረዶች ተውበው፣ አምረው እና ደምቀው የሶለል በዓላቸውን ሊያከብሩም በአደባባይ ተከስተዋል።

👉 የሶለል በዓል መነሻ መሠረቱ

ሶለል በራያ አካባቢ በየዓመቱ ከነሐሴ 16 ጀምሮ እስከ ነሐሴ 21 ድረስ ልጃገረዶች የሚጫወቱት ባሕላዊ ክዋኔ ነው። ባሕሉ ሃይማኖታዊ መሠረት እንዳለውም ይነገራል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት የስብከተ ወንጌል ክፍልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ኀላፊ መምህር ኤርምያስ አዳነ የሶለል ባሕል መነሻው ሃይማኖታዊ ይዘት እንዳለው ይናገራሉ።

መምህር ኤርምያስ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በብሉይ ኪዳን እና በሀዲስ ኪዳን ሃይማኖታዊ መነሻ ጠቅሰው ያስረዳሉ። ይህም ከቅድስት ድንግል ማርያም እረፍት እና ዕርገት ጋር የሚያያዝ ሰፊ አስተምህሮ እንዳለውም ነው ያመላከቱት።

እንደ መምህር ኤርምያስ ገለጻ ልጃገረዶች በጨዋታቸው "አሸንዳ ሙሴ ፈስስ በይ በቀሚሴ" እያሉ የሚያዜሙት ዜማም ሙሴ በደብረ ሲና ያያት ዕጽን ወይም 'እጸ ሙሴ'ን ለማጠየቅ እንደኾነ ያብራራሉ።

ልጃገረዶች ክብ ሠርተው ሲጫወቱ ከመሀል ኾና የምታቀነቅነው ልጃገረድ የእመቤታችን ምሳሌ፣ ተቀባዮች የቅዱሳን መላዕክት፣ በወገባቸው የታጠቁት የአሸንድዬ ቅጠል ደግሞ የመላዕክት ክንፍ መኾኑን ነው መምህር ኤርምያስ ያብራሩት።

ወደ ግራና ወደ ቀኝ እያወዛወዙ የሚጫወቱት ደግሞ መላዕክት ክንፋቸውን ከክንፋቸው እያማቱ በፍጹም ደስታ እያመሰገኑ እመቤታችንን ያሳረጉበትን ምሳሌ የሚገልጽ መኾኑን አስረድተዋል።

ከዚህ በመነሳት የሶለል ባሕል ከጥንት ጀምሮ እየተከበረ ከዛሬው ትውልድ መድረሱን አመላክተዋል።
👉 የልጃገረዶች ዝግጅት ለሶለል

በቆቦ ከተማ ነዋሪ የኾነችውና የሶለል ተጫዋች ወጣት ሃይማኖት ኀይሌ የሶለል በዓል በየዓመቱ በናፍቆት የሚጠብቁት በዓል እንደኾነ ትገልጻለች።

እንደ ወጣቷ ገለጻ የሶለል በዓል ከመድረሱ በፊት ልጃገረዶች በቡድን እየተሰባሰቡ አለቃ በመምረጥ ዝግጅታቸውን ይጀመራሉ፡፡

ለአለቃነት የምትመረጠው ልጃገረድም እነሱን የምትቆጣጠር፣ ሲያጠፉ የምትመክርና የምትቆጣ፣ ግጥም የምታወጣ፣ የሚስብ የድምጽ ቅላጼ ያላት፣ ወደ ኋላ ሲቀሩ የምታበረታታ መኾን እንደሚኖርባት ታሳቢ ያደረገ ነው፡፡

በአለቃዋ ቤት በመሰባሰብም ግጥምና ዜማ እያጠኑ፣ የሚያስፈልጋቸውን ነገር እያዘጋጁ ይቆያሉ፡፡ የሶለል በዓልን ለመጫወት የሚጠቀሙት ቅጠል አሸንድዬ በመባል ይጠራል።

ለበዓሉ 2 ወይም 1 ቀን ሲቀረው ወንድ ወጣቶችን አሸንድዬ ከሚገኝበት ስፍራ በመላክ የአሸንድዬውን ቆርጠው እንዲያመጡላቸው ያደርጋሉ፡፡

ልጃገረዶችም የመጣላቸውን የአሸንድዬ ቅጠል በሚፈልጉት መልኩ እየጎነጎኑ ያዘጋጁታል፡፡ ከዚሁ ጋር ባሕላዊ የመዋቢያ ቁሳቁሶችን፣ ጌጣጌጦችን እና አልባሳትንም ጭምር እያዘጋጁ ይሰነባብታሉ።

👉 የሶለል ተጫዋቾች መዋቢያና ጌጣጌጦች

እንደ ወጣት ሃይማኖት ገለጻ የሶለል ተጫዋች ልጃገረዶች መዋቢያቸው ብዙ ነው። የፀጉር አሠራራቸውም በእድሜ ደረጃ እና በትዳር ሁኔታ ይለያያል።

ሕጻናት ልጆች በአካባቢው አጠራር "ጋሜ" እና "ቃሪ" የሚባሉትን የፀጉር ስሬት ይሠሩታል፡፡ "አሳስር" እና "አፈሳሶ" የሚባለው ደግሞ እድሜአቸው ከ14 እስከ 20 ዓመት ያሉት ልጃገረዶች የሚሠሩት ነው። “እጩኝ፤ ለትዳር ደርሻለሁ” እንደማለትም ነው።

ጊጫ፣ አለባሶ፣ ውስጠ ወይራ፣ ሹርባ፣ ጎበዝና ቆንጆ እና ሌሎች መጠሪያዎች ያሏቸው የፀጉር አሠራሮችንም ሌሎች ሴቶች በበዓሉ ሰሞን ተሠርተው ይዋባሉ፡፡

ከበዓሉ ቀደም ብሎ ፀጉራቸውን ቅቤ ይቀባሉ። ቆንጆ ውብ እንዲኾኑም ዐይናቸውን ይኳላሉ፤ ይዋባሉ። ትፍትፍ፣ አምሾ፣ ዋሾ ሸማ የሚባሉትንም አልባሳት ይለብሳሉ፡፡

በተለያዩ ክሮች ያሸበረቀ መቀነት ወገባቸው ላይ ሸብ ያደርጋሉ፡፡ የብር ድንብል ጌጥ ከደረታቸው ላይ ያደርጋሉ።

👉 የሶለል ጨዋታው ክዋኔ

ነሃሴ 16 በጠዋቱ ልጃገረዶች አምረውና ደምቀው ከየቤታቸው ይወጣሉ። የመጀመሪያ ተግባራቸውም ቤተ ክርስቲያን ሄደው ጸሎት ማድረስ እና ፈጣሪን ማመስገን ነው። ከዚያም ጨዋታቸውን የሚጀምሩትም በአካባቢያቸው ከሚገኝ ከዕድሜ ባለጸጋ አዛውንቶች ቤት ነው።

ልጃገረዶቹ የበዓሉ ድምቀት በኾነው በራያ ትፍትፍ ልብስ ደምቀው፣ የእግር አልቦ እና የፀጉር ሥሬት አምረው፣ ተውበው ጨዋታቸውን ይቀጥላሉ።

ወገባቸው ላይ የታጠቁትን የአሸንድዬ ቅጠል በማወዛወዝ ረዘም ብሎ በሚደመጠው ድምጻቸውም "ሶለል...ሶለል..." እያሉ የሚያስደምመውን ዜማ ያዜሙታል፡፡

የአሸንድዬውን በወገባቸው ታጥቀው በኅብረት እና በተረጋጋ ስሜት ከግራ ወደ ቀኝ፣ ከቀኝ ወደ ግራ፣ ደግሞም በዝግታ ወገባቸውን ሲያንቀሳቅሱት፣ አብሮ ወደ ግራ፣ ወደ ቀኝ እያወዛወዙ ይከውኑታል፡፡

በዚህ በዓል የተለያዩ ግጥሞችን ከዜማ ጋር በማዋሐድ ቤት ለቤት እየዞሩ ፈጣሪያቸውን ያመሰግኑበታል፡፡ የአካባቢውን ዕሴት፣ ትውፊት፣ፍቅርን፣ ተስፋን ይገልጹበታል፤ ውበትን፣ ጀግንነትን ያወድሱበታል።

👉የወንዶች ተሳትፎ በሶለል ጨዋታ

የሶለል በዓል ልጃገረዶች የሚጫወቱት ክዋኔ ቢኾንም ወጣት ወንዶችም ጭምር አምረውና ደምቀው የሚወጡበት ቀን ነው፡፡

ወንዶቹ እንደ እርቦ ወይም ጋቢ፣ ከታች ግልድም ያደርጋሉ። ጥርቅ የሚባለውን ከበሬ ቆዳ የተዘጋጀ ጫማ ይለብሳሉ።

በጥርሳቸው ላይም ሲዋክ (የጥርስ መፋቂያ)፣ ፀጉራቸው ላይ ሚዶ ሰክተው፣ በእጃቸው በትር በመያዝ ሶለል ከሚሉ ልጃገረዶች እየተከተሉ ይጨፍራሉ፡፡ ጅራፍ ይዘው እያጮሁ ከኋላቸው እየተከተሉ የሚያጅቡ ወንዶችም አሉ።

በዚህ አጋጣሚ ኮበሌው የሚፈልጋትን ቆንጆ ልጃገረድ ካለች ለፍቅር ያጫታል። ከኋላ በመኾን የአሸንድዬዋን ቅጠል በጥሶ በመውሰድ ፍቅሩን ይገልጽላታል፡፡ እሷም ዞር ብላ በአይኗ ትቃኘዋለች። በፈገግታ ስሜት ፈቃደኝነቷን ትገልጽለታለች ፡፡ በዚህ መልኩም ይተጫጫሉ፡፡

የሶለል ባሕላዊ ጨዋታን ከ10 ዓመት በላይ እየተጫወቱ ያሳለፉት ወይዘሮ አዝመራ ሞላ አሁን ላይ የሶለል ጨዋታ የሚጫወቱ ልጆች እንዳሏቸው ነግረውናል።

ባሕላዊ ትውፊቱ ከጥንት ጀምሮ የነበረ እና ከትውልድ ትውልድ እየተላለፈ የቀጠለ መኾኑን አንስተዋል። ልጆች በሶለል ባሕላዊ ጨዋታ ቁጥጥር እንደማይደረግባቸውም ነግረውናል።

የፈለጉትን ነገር የሚያደርጉበት ተናፋቂ ወቅት ስለመኾኑም ነው የጠቆሙት። ወላጆችም የመዋቢያ እና የሚያጌጡበትን ሁሉ የማሟላት ግዴታ አለባቸው ነው ያሉት። በሶለል በዓል የሚዜሙ ዜማዎችና ግጥሞች እንዳሉም ገልጸዋል።

👉በሶለል ጨዋታ የሚዜሙ የግጥም ስንኞች(ለቅምሻ)

በሶለል ጨዋታ ልጃገረዶች በስፋት ከሚጠቀሟቸው የግጥም ስንኞች የተወሰኑትን ለአብነት ለማንሳት ያክል:
በጋራ ኾነው ሲጫወቱ:-

"አሸንድዬ አሸንዳ አበባ፤ እርግፍ እንደ ወለባ፤
አሸንድዬ አሸንዳ ሙሴ፣ ፍስስ እንደ ቀሚሴ" ... እያሉ ይጨፍራሉ።
የሶለል ተጫዋቾች በየቤቱ እየሄዱ ደግሞ:-
“ሶለል ብየ መጣሁ
ሶለል ብዬ፣
ጌቶች አሉ ብዬ…
ይኼ የማን ነው ቤት፣ የጸዳ የኮራ፣
ከነ ባለቤቱ፣ ስሙ የተጠራ…" እያሉ ያዜማሉ።
ሶለለል ...ሶለለል...
ኧረ አበየ እገሌ የጌታው ልጅ ጌታ፣
ጠጠር አስመስሎ በብር የሚማታ።
"ሸሙናየ..."ሸሙናየ...
ሸሞንሟና ኩታ አሠርቼልህ፣
የማንን ድሪቶ ትጎትታለህ...
... ሸሙናየ" እያሉ አባዎራውን ያወድሳሉ።
“ሶለለል...ሶለለል
ከጎታ ላይ ኾና፣ ታሽካካለች ዶሮ፣
ኧረ እነየ እገሌ፣ ደልዳላ ወይዘሮ ...ሶለለል” እያሉ ደግሞ እማዎራዋን ያወድሳሉ፡፡

እነዚህን ለአብነት አነሳን እንጂ በእያንዳንዱ የጨዋታ ኹነት የራሱ ግጥምና ዜማ አለው። የሶለል ተጫዋቾችም በየቤቱ እየተዘዋወሩ በእናቶች፣ በአባቶች፣ በሽማግሌዎች ይመረቃሉ፤ ስጦታም ይበረከትላቸዋል፡፡

“ከብረው ይቆዩ ከብረው፣
በዓመት ወንድ ልጅ ወልደው፣
ሰላሳ ጥጆች አስረው፣
ሦስት አዳራሽ ቤት ሠርተው፣
ከብረው ይቆዩ ከብረው።” የሚለው ደግሞ የምስጋና እና የመሠነባበቻ ዜማቸው ነው፡፡

በየቤቱ ተዘዋውረው ሲጨፍሩ የሚሰጣቸውንም ገንዘብ ወይም ሌላ ስጦታ ሰብስበው በአለቃቸው ቤት ድግስ ያዘጋጃሉ፡፡ የአካባቢውን አዛውንቶች ጠርተው በመጋበዝ ይመረቃሉ፡፡

ሶለል የራያዎቹ ልዩ መልክ፣ ውበት፣ ድምቀት ነውና በዓላቸውን በራያ ምድር ተገኝታችሁ የሶለል ሙሽሮችን አድምቋቸው እንላለን፡፡

ዘጋቢ፡- አሰፋ ልጥገበው

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን

22/08/2025
 #አሚኮ30ተወዳጅ የራዲዮ ሥርጭቶችን ከአሚኮ ፖድካስት ይከታተሉ🎙አሚኮ ፖድካስት 📻📻የቀጥታ ሥርጭት አማራጮች፦🎙በድረገጽhttps://ameco.et/Podcast/🎙ቴሌግራምhttps://t.me/A...
21/08/2025

#አሚኮ30
ተወዳጅ የራዲዮ ሥርጭቶችን ከአሚኮ ፖድካስት ይከታተሉ
🎙አሚኮ ፖድካስት 📻
📻የቀጥታ ሥርጭት አማራጮች፦
🎙በድረገጽ
https://ameco.et/Podcast/
🎙ቴሌግራም
https://t.me/AmharaMassMedia?livestream
🎙ራዲዮ ጋርደን
https://radio.garden/visit/bahir-dar/aK2JS8Uh
🎙በዜኖ ኤፍኤም
https://zeno.fm/radio/fm-96-9/
https://zeno.fm/radio/amhara-radio/
🎙በፌስቡክ
https://www.facebook.com/share/1YBhu2GgT4/

ሻደይ ሃይማኖታዊ ሥርዓቱን በጠበቀ መልኩ እንዲከበር ዝግጅት ተደርጓል።ሰቆጣ: ነሐሴ 15/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የሻደይ በዓል ሃይማኖታዊ መሠረት ያለው የልጃገረዶቸ በዓል ነው። ይህንን በዓል...
21/08/2025

ሻደይ ሃይማኖታዊ ሥርዓቱን በጠበቀ መልኩ እንዲከበር ዝግጅት ተደርጓል።

ሰቆጣ: ነሐሴ 15/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የሻደይ በዓል ሃይማኖታዊ መሠረት ያለው የልጃገረዶቸ በዓል ነው።

ይህንን በዓል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሥርዓት መሠረት በሰቆጣ ከተማ ደብረ ፀሐይ ወይብላ ቅድስት ማርያም ካቴድራል በድምቀት ለማክበር መዘጋጀታቸውን የካቴድራሉ አሥተዳዳሪ መልአከ ፀሐይ ብርሃነ ሕይወት እንግዳ ገልጸዋል።

የሻደይ በዓል በሦስት የቤተ ክርስቲያኗ ታሪክ መነሻነት የሚከበር እንደኾነ መልአከ ፀሐይ ተናግረዋል። ቀዳሚው በኦሪት ዘፍጥረት ላይ የሚገኘ የድኅነት፣ የደስታ፣ የነጻ መውጣት ምሳሌ ከኾነው የውኃ ሙላት የመዳን ምሳሌ እንደኾነ ገልጸዋል።

ይሄውም እርግቧ የለመለመ ቅጠል በማምጣት የውኃ ሙላቱ መጉደሉን በመግለጿ ኖኅ ከነልጆቹ እግዚአብሔርን አመስግኗልና። ዛሬም ልጃገረዶች የደስታ፣ የድኅነት፣ የነጻነት ምሳሌ የኾነውን የሻደይን ቅጠል ይዘው ይዘምራሉ ብለዋል።

ሌላው መነሻ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክም በመጽሐፈ መሳፍንት የሚገኘው የዮፍታሔ ታሪክ ነው ይላሉ።

ሦስተኛው ማሳያ የቤተ ክርስቲያኗ መነሻ የቅድስት ድንግል ማርያም እርገትን መላዕክት በክንፋቸው እያሸበሸቡ ሲያሳርጓት ቶማስ በደመና ሰቨኗን ወይም መግነዟን ተረክቦ ተመልሷልና የዚህን ምሳሌ በመውሰድ እንደመላዕክት ክንፍ ከወገባቸው ሻደዩን አስረው እመቤታችንን ያመሰግኑበታል ብለዋል።

በዚህ ዓመትም በደብረ ፀሐይ ወይብላ ቅድስት ማርያም ካቴድራል በደናግላን ዘማሪያን በሻደይ ተውበው በዝማሬ እና በያሬዳዊ ወረብ ለማክበር መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።

ዘጋቢ: ደጀን ታምሩ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን

 #ይወዳጁን👍አሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ላለፉት 12 ዓመታት ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ዘገባዎችን ለተከታዮቹ በማድረስ የመረጃ ምንጭ ኾኗል። ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን! #አሚኮ30  #አሚ...
21/08/2025

#ይወዳጁን👍
አሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ላለፉት 12 ዓመታት ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ዘገባዎችን ለተከታዮቹ በማድረስ የመረጃ ምንጭ ኾኗል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
#አሚኮ30 #አሚኮኢትዮጵያ #አማራክልል

20/08/2025

አሚኮ 30 ዓመታትን በትጋት! #አሚኮ30

20/08/2025

#አሚኮ 30 ዓመታትን በትጋት!
ይምጡ አብረውን ይሥሩ!
አማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
#አሚኮ30

Address

Bahir Dar

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Discover Amhara AMECO posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to Discover Amhara AMECO:

Share