Discover Amhara AMECO

Discover Amhara AMECO Contact information, map and directions, contact form, opening hours, services, ratings, photos, videos and announcements from Discover Amhara AMECO, Media/News Company, Bahir Dar.

ሻደይ እና የወጣቶች ዝግጅትሰቆጣ: ሐምሌ 18/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ሻደይ በዋግ ኽምራ ልዩ ትኩረት ተሰጥቷቸው ከሚከበሩ ባሕላዊ ጨዋታዎች መካከል ቀዳሚው ነው። በየዓመቱ ከነሐሴ 16-21 ባ...
25/07/2025

ሻደይ እና የወጣቶች ዝግጅት

ሰቆጣ: ሐምሌ 18/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ሻደይ በዋግ ኽምራ ልዩ ትኩረት ተሰጥቷቸው ከሚከበሩ ባሕላዊ ጨዋታዎች መካከል ቀዳሚው ነው። በየዓመቱ ከነሐሴ 16-21 ባሉ የማርያም በዓላት ተብለው በሚጠሩት ቀናት ልጃገረዶች በነጻነት ያለከልካይ
"ሻደይ አበባየ ሻደይ
አሽከር ይሙት ይሙት ይላሉ የኔታ
አሽከር አይደለም ወይ የሚኾነው ጌታ
ሻደይ አበባየ ሻደይ"..እያሉ ያዜማሉ።

ወጣቶቹም የትዳር አጋርን ከመምረጥ ጀምሮ የሻደይ ተጫዋች ቆነጃጅትን በማጀብ በኩል ትልቅ ድርሻ አላቸው። በመኾኑም የሰቆጣ ከተማ ወጣቶች የሻደይን በዓል በምን መልኩ እየጠበቁት ይገኛሉ ብለን ጠይቀናቸዋል።

ወጣት ዝናቡ በየነ የሰቆጣ ከተማ ነዋሪ ሲኾን ሻደይን በድምቀት ለማክበር ከወዲሁ አስፈላጊ ባሕላዊ አልባሳት እና ጌጣጌጦችን አሟልቶ እየጠበቀ እንደሚገኝ አጫውቶናል።

ወጣቱ ትውልድ የውጭ ሀገር ፋሽን ተከታይ እየኾነ በመምጣቱ ለባሕላዊ አልባሳት ያላቸው ግምት እየቀነሰ መጥቷል ያለው ወጣት ዝናቡ የዋግ ሹሞቹን አለባበስ በጠበቀ መልኩ ሻደይን ለማክበር ወጣቶች ከወዲሁ አስፈላጊውን ቁሳቁስ እንዲያሟሉ አሳስቧል።

ሌላኛው በባሕላዊ የዋግ አለባበስ አሸብርቆ ያገኘነው ወጣት ዓለማየሁ ጥላሁን ሻደይን በአንድ አይነት አለባበስ እና በባሕላዊ አልባሳት ደምቀው ለመዋል በሰፈር ተደራጅተው አልባሳቱን እንዳሟሉ ጠቅሷል።

ሌሎችም ወጣቶች ለባሕሉ ቅድሚያ ሰጥተው መዘጋጀት እንደሚገባቸው የጠቆመው ወጣት ዓለማየሁ ሴቶቹ ላይ ያለው የባሕል ወዳድነት በአዎንታ የሚታይ ነው ብሏል።

በዓሉንም የዋግ ወጣቶች እና ቆነጃጅት በጉጉት እየጠበቁት እንደሚገኙ ነው የነገረን።

ሃይማኖታዊ እና ባሕላዊ መሰረት ያለው የሻደይ ጨዋታ ለዋግ ኽምራ ማኅበረሰብ የተለየ እንድምታ ያለው በዓል መኾኑን የብሔረሰብ አሥተዳደሩ ባሕልና ቱሪዝም መምሪያ ኀላፊ ኢዮብ ዘውዴ ገልጸዋል።

ይህ ሕዝባዊ የኾነውን የነጻነት በዓል በድምቀት እና በሰላማዊ መንገድ ለማክበር አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ሥራ ከወረዳ እስከ ቀበሌ በአግባቡ እየተሠራ እንደኾነ ነው ኀላፊው የገለጹት።

የአካባቢው ወጣቶች፣ ቆነጃጅት፣ ሕጻናት እና እናቶች ባሕሉ የፈቀደውን የባሕል አልባሳት አሟልተው በዓሉን እየጠበቁት እንደኾነ የተናገሩት አቶ ኢዮብ ሰቆጣ ከተማም እንግዶቿን ለመቀበል ተዘጋጅታለች ብለዋል።

ዘጋቢ:- ደጀን ታምሩ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

ማን እንደ አባ - ድንጋይን እንደ ጀልባባሕር ዳር: ሐምሌ 17/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በጎርጎራ አካባቢ ከሚገኙ ጥንታዊ ገዳማት መካከል የማን እንደ አባ አቡነ ያሳይ መድኃኔዓለም አንድነት ገ...
24/07/2025

ማን እንደ አባ - ድንጋይን እንደ ጀልባ

ባሕር ዳር: ሐምሌ 17/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በጎርጎራ አካባቢ ከሚገኙ ጥንታዊ ገዳማት መካከል የማን እንደ አባ አቡነ ያሳይ መድኃኔዓለም አንድነት ገዳም አንዱ ነው። ይህ ገዳም በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በምዕራብ ደንቢያ ወረዳ ከጎርጎራ ከተማ በስተምዕራብ በኩል አምስት ኪሎሜትር ርቀት ከተንጣለለው የጣና ሐይቅ ዳርቻ ይገኛል።

ገዳሙ በ1 ሺህ 326 ዓ.ም በቀዳማዊ አምደ ጽዮን ልጅ በጻዲቁ አቡነ ያሳይ እንደተመሠረተ የገዳሙ አበምኔት አባ ዮሐንስ አፈወርቅ ያሳይ ያስረዳሉ፡፡

ወደዚሁ ጥንታዊ ገዳም ለመሄድ ከጎርጎራ በጀልባ 25 ደቂቃ፣ በመኪና ደግሞ 30 ደቂቃ ይወስዳል፡፡

በተንጣለለው የጣና ሐይቅ ዳርቻ ላይ የተመሠረተው ይህ ገዳም ስያሜውን ያገኘው አቡነ ያሳይ በመድኃኔዓለም ተዓምራዊ ጥበብ በሰፊ ድንጋይ ላይ ተቀምጠው እንደ ጀልባ በመጠቀም በጣና ሐይቅ ሲመላለሱ በወቅቱ ይመለከቱ የነበሩ ሰዎች በመደነቅ ማን እንደ አባ አሉ። በደንጋይ ላይ ሲሄዱ አይተው ማን እንደ አባ ብለዋልና ገዳሙም ማን እንደ አባ የሚል ስያሜ እንደተሰጠው ይነገራል።

ገዳሙ የእነ አጼ ዮሐንስ (ጻድቁ ዮሐንስ)፣ የእነ አጼ ባካፋ እና የእነ እቴጌ ምንትዋብ አሻራ መገኛም ነው፡፡ የገዳሙን መቅደስ እና ቅድስት አጼ ፋሲል እንደሠሩት የሚነገርለት ይህ ገዳም የነገሥታት ዘውዶች፣ ብዛት ያላቸው የብራና መጻሕፍት፣ የተለያዩ መስቀሎች፣ የገበታ ስዕሎች፣ ማን እንደ አባ በጣና ላይ እንደ ጀልባ ይጠቀሙባት የነበረች ድንጋይ እና ሌሎችም በርካታ ቅርሶች ይገኙበታል፡፡

ማን እንደ አባ አቡነ ያሳይ መድኃኔዓለም አንድነት ገዳም ማራኪ ውበት እና አስደሳች በኾነ 150 ሄክታር በሚሸፍን መሬት በሀገር በቀል እፅዋት በተከበበው ግቢ፣ ጎንበስ ቀና እያሉ ለአምላካቸው ምስጋናን የሚያቀርቡ በሚመስሉ ዛፎች ተከቦ፣ በአእዋፍ ዝማሬ ታጅቦ በስተምሥራቅ የተንጣለለው ሐይቅ ማዕበሉን እያፏጨ ግርማ ሞገስን አላብሶት የሚኖር ገዳም ነው።
በገዳሙ ውስጥ ከ227 በላይ አባቶች እና ዘጠና የሚደርሱ የጉባኤ ተማሪዎችም ይገኙበታል፡፡

አበው መነኮሳት "ስጋዬን ለመነኩሴ ነብሴን ለሥላሴ" ብለው ሳይታክቱ በአገልግሎት የሚታትሩበት ይህ ገዳም ከሚተዳደርበት ደንብ አንዱ "መለመን ክልክል ነው" የሚለው ሕግ መኾኑን የገዳሙ አበምኔት ይናገራሉ፡፡

በዚህ በተፈጥሮ በታደለ ገዳም መነኮሳቱ አንድ ሺህ ሄክታር በሚደርስ ቦታ ላይ የተለያዩ ሰብሎችን በማልማት፣ ከብት በማርባት እና ንብ በማነብ ሥራ በመሰማራት ገዳሙ ራሱን ችሎ የሚተዳደር እንዲኾን አድርገውታል ነው ያሉት፡፡

ከአስር ያላነሱ የእህል ወፍጮዎችንም ከቅርብ ርቀት በሚገኙ ሁለት ከተሞች በመትከል ለማኅበረሰቡ ግልጋሎት በመስጠት የውስጥ ገቢያቸውን በማሳደግ ተጠቃሚ እንደኾኑም ተናግረዋል፡፡

ይህ የተፈጥሮ ውበቱ አስደማሚ የኾነ እድሜ ጠገቡ ገዳም የብዙ ቅርሶች ባለቤት የመንገድ መሠረተ ልማት እና ራሱን የቻለ የቅርሶች መጠበቂያ ሙዚየም አለመኖሩን የገዳሙ አበምኔት አባ ዮሐንስ አፈወርቅ ያሳይ ጠቁመዋል፡፡

የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ባሕልና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ አቤል መብት በገዳሙ የተነሡ የመሠረተ ልማት ችግሮች እና የሙዚየም ቤት አለመኖር ለመቅረፍ የተጀመሩ ሥራዎች መኖራቸውን ተናግረዋል፡፡

ከጎርጎራ ወደ ገዳሙ የሚወስደው መንገድ እንደተሠራ እና ቀጣይ የኮንክሪት አስፋልት የማድረግ እቅድ መያዙንም ነው የገለጹት።

ከማን እንደአባ ገዳም ወደ ሱሲኒዮስ ቤተ መንግሥት እና በቅርብ ርቀት የሚገኙ ገዳማትን በየብስ እና በጣና ላይ ለማገናኘት የሚያስችል የቱሪስት ፍኖተ ካርታ እየተሠራ መኾኑንም አንስተዋል።

ገዳሙ ካሉት እድሜ ጠገብ እና ብዛት ያላቸው ቅርሶች አንጻር ሙዚየም እንደሚያስፈልገው በመታመኑ ከሚመለከተው አካል ጋር በመወያየት እንዴት መሠራት አለበት በሚለው ዙሪያ ጥናት ላይ መኾናቸውንም ተናግረዋል፡፡

ዘጋቢ:- ሰናይት በየነ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

የባሕር ዳር ጌጦችባሕር ዳር: ሐምሌ 16/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የጣና ሐይቅ ዳርቻዋ ባሕር ዳር ከተማ በስፋት ከምትታወቅባቸው መልኮቿ መካከል የእደ ጥበብ ሥራዎች ዋነኞቹ ናቸው።ከነዚህም መካ...
23/07/2025

የባሕር ዳር ጌጦች

ባሕር ዳር: ሐምሌ 16/2017 ዓ.ም (አሚኮ)
የጣና ሐይቅ ዳርቻዋ ባሕር ዳር ከተማ በስፋት ከምትታወቅባቸው መልኮቿ መካከል የእደ ጥበብ ሥራዎች ዋነኞቹ ናቸው።

ከነዚህም መካከል በደንገል እና ሠበዝ ተሠርተው ያጌጡ መሰቦች፣ አገልግሎች እና ከእንስሳት ቆዳ የሚሠሩት ልዩ ልዩ ባሕላዊ መገልገያዎች የበርካቶችን ቀልብ የሚስቡ የጥበብ ሥራዎች ናቸው።

እኒህን ባሕላዊ ቁሶች በመሥራት አራት ልጆቻቸውን የሚያሥተዳድሩት ወይዘሮ የሺፋና አዲስ በዚህ ሥራ ላይ የተሰማሩት ገና የ12 ዓመት ልጅ እያሉ እንደነበር አጫውተውናል። ለ35 ዓመታትም በዚህ ሥራ ላይ ቆይተዋል። ለበርካታ ዓመታት እየሠሩት ያለው የእጅ ሥራ የቤተሰባቸውን የእለት ፍላጎት ከመሸፈን ውጪ ይህ ነው የሚባል ለውጥ እንዳላስገኘላቸው ተናግረዋል።

ወይዘሮ የሺፋና እንዳሉት ሙያው ዕውቀት እና ክህሎት ይፈልግ ነበር። የእየሠራን ያለነው ግን በተለምዶ በነባሩ ዕውቀት ብቻ ነው ብለዋል።

ይባስ ብሎ እንግልቱ እየጨመረ ነው ይላሉ ወይዘሮ የሺፋና። ደንብ አስከባሪዎች ከዚህ ቦታ ተነሱ በሚል ንግግር ከነሱ ጋር በእሰጣ ገባ ነው የምንውለው ብለዋል። አንድም አካል መጥቶ ለመፍትሔው እስኪ ምን ብናደርግ ይሻላል የሚል የለም ነው ያሉት።

ሥልጠና እና የመሥሪያ ቦታ ቢመቻች የተለያዩ ፈጠራዎችን እና ጌጣጌጦችን በመጨመር በጥራት ሳቢና ማራኪ አድርገን መሥራት እንችል ነበር ብለዋል።

ይህ እንዲኾን ግን መንግሥት ለጥበብ ሥራው ትኩረት በመስጠት በእጅ ብቻ ሳይኾን በማሽኖች በመታገዝ ሥራው ቢከናወን ሁሉም ተጠቃሚ ሊኾን ይችላል ነው ያሉት።

የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ባሕልና ቱሪዝም መምሪያ ኀላፊ ጋሻው እንዳለው እንደተናገሩት ከተማዋ ከሌሎች አካባቢዎች በተለየ ጎልተው የሚታዩ የእደ ጥበብ ሥራዎች ባለቤት ናት ብለዋል።

እነዚህን መሰል የእደ ጥበብ ሥራዎች ጥንታዊነታቸውን ሳይለቁ ለአገልግሎት አሰጣጥ በሚያመች መልኩ በተለያዩ ዲዛይን በማቅረብ ለማኅበረሰቡ እና ለጎብኝዎች መስህብነት እየዋሉ መኾናቸውን ገልጸዋል።

የሀገር በቀል ዕውቀት ያላቸውን ሰዎች እና ገፅታ ያስተዋውቅልናል ብለን ያመንባቸውን የእደ ጥበብ ባለሙያዎች ከፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ጋር በጋራ በመነጋገር ተጨማሪ ዕውቀት እንዲገበዩ ሥልጠናዎችን እንዲወስዱ አድርገናል ነው ያሉት።

በከተማዋ በጣና ክፍለ ከተማ አካባቢ ቦታ እንዲያገኙ በማድረግም የጌጠኛ አገልግል መንደር በመባል እንዲጠራም ሥራ ተሠርቷል ነው ያሉት።

ዘጋቢ:- ሰመሀል ፍስሀ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

ኢትዮጵያዊነት በተርክዬ ደምቋል።   ባሕርዳር:ሐምሌ 14/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በዓለምአቀፍ የባሕል ፌስቲቫል ለመሳተፍ ወደ ተርክዬ  የተጓዘው  የአማራ ክልል የሙሉዓለም ባሕል ማዕከል ኢትዮ...
21/07/2025

ኢትዮጵያዊነት በተርክዬ ደምቋል።

ባሕርዳር:ሐምሌ 14/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በዓለምአቀፍ የባሕል ፌስቲቫል ለመሳተፍ ወደ ተርክዬ የተጓዘው የአማራ ክልል የሙሉዓለም ባሕል ማዕከል ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነትን የሚሰብኩ የባሕል ጥበባዊ ሥራዎቹን አቅርቧል።

በአውሮፓ ተርክዬ ትራባዞን አክሻባት ከተማ ዓለምአቀፍ የአውሮፓ ፌስቲቫል የኢትዮጵያን ባሕል፣ ኪነ ጥበብ እና እሴቶች የማስተዋወቅ ሥራ ሢሠራ ቆይቷል። ትናንት ሐምሌ 13/2017 ዓ.ም ምሽት በተካሄደው መድረክ የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦችን ባሕላዊ ሙዚቃ፣ የኢትዮጵያን ባሕል እና የኪነ ጥበብ ሥራዎችን አቅርቧል፡፡

ቡድኑ ሥራዎቹን ያቀረበው ከአውሮፓ እና ከኢሲያ ሀገራት ሀገራቸውን ወክለው የተለያዩ የልዑካን ቡድኖች በተገኙበት መድረክ ነው። ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያዊነትንም በዓለም አደባባይ ሲያስተዋውቁ አምሽተዋል።

የኪነ ጥበብ ልዑኩ ባቀረባቸው ኢትዮጵያዊ የጥበብ ሥራዎች አድናቆት እና ምሥጋናም ተችሮታል። ከተለያዩ ዓለም አቀፍ የዘርፉ መሪዎች እና ባለሙያዎች ጋርም ትውውቅ የተደረገበት መድረክ መኾኑን የአማራ ክልል የሙሉዓለም የባሕል ማዕከል ዋና ዳይሬክተር ገብረማርያም ይርጋ ተናግረዋል፡፡

የሙሉዓለም ባሕል ማዕከል ከዚህ በፊት በሕንድ እና ሩሲያ ዓለም አቀፍ መድረኮች ላይ ከተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት እና ሀገራት ጋር በኪነ ጥበቡ ዘርፍ ጠንካራ ግንኙነት በመፍጠር የተሻለ የባሕል ዲፕሎማሲ ሥራዎችን እየፈጸመ የመጣ ነው ብለዋል።

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!

https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

ከ4 መቶ ዓመታት በላይ አጽማቸው  ያልፈረሰ ፍየሎች የሚገኙበት ገዳም። ባሕር ዳር: ሐምሌ 12/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ጩጊ ማርያም ወአቡነ ምዕመነ ድንግል አንድነት ገዳም በማዕከላዊ ጎንደር ...
19/07/2025

ከ4 መቶ ዓመታት በላይ አጽማቸው ያልፈረሰ ፍየሎች የሚገኙበት ገዳም።

ባሕር ዳር: ሐምሌ 12/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ጩጊ ማርያም ወአቡነ ምዕመነ ድንግል አንድነት ገዳም በማዕከላዊ ጎንደር ዞን ወገራ ወረዳ ጉንዳ ጩጊ ቀበሌ ትገኛለች።

ገዳሟ ከጎንደር ከተማ 37 ኪሎ ሜትር፣ ከወረዳው ዋና ከተማ አምባጊዮርጊስ ምዕራብ አቅጣጫ በ18 ኪሎ ሜትር ርቀት፣ እንዲኹም ከኮሶዬ ከ2 ሰዓት የእግር ጉዞ በኋላ የምትገኝ ገዳም ናት፡፡

ገዳሟ በ1 ሺህ 632 ዓ.ም አባ ምዕመነ ድንግል በተባሉ አባት እንደተመሰረተች ይነገራል፡፡ በወገራ ወረዳ ከሚገኙ ጥንታዊ ገዳማት እና የጎብኝዎች መዳረሻ መካከልም አንዷ ናት፡፡

በወገራ ወረዳ ባሕልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ቡድን መሪ እንዳልክ ተቀባ በጩጊ ማርያም አንድነት ገዳም ጥንታዊ የብራና መጻሕፍት፣ ጥንታዊ መስቀሎች እና ሌሎችም ሰው ሠራሽ እና ተፈጥሯዊ ቅርሶች የሚገኙባት መኾኑን አስረድተዋል።

በገዳሟ ውስጥ ጥልቀቱ በውል የማይታወቅ፣ ካህናት እና ዲያቆናት ብቻ እየገቡ የሚቀዱት የዋሻ ውስጥ ጸበል ይገኛል ነው ያሉት። "የዋሻ ውስጥ ጸበሉ መፍሰሻ የለውም፤ ልክ እንደኩሬ ኾኖ ጥርት ያለ ነው፤ መጠኑ አይቀንስም፤ አይጨምርም" በማለት የጸበሉን የተለየ ገጽታ ይናገራሉ።

ወድቆ የተነሳ ችብሃ ዛፍ፣ የኢትዮጵያ ካርታ ቅርጽ ያለው ዋሻ፣ ከተራራ መካከል ብርሃን የሚያሳይ ልዩ ቦታና ሌሎችም ጎብኝዎችን የሚያስደንቁ መስህቦች በገዳሟ ይገኛሉ ነው ያሉት።

በገዳሟ ውስጥ ከ4 መቶ ዓመት በላይ የቆዩ አጽማቸው ያልፈረሱ 16 ፍየሎች ይገኛሉ ብለዋል። እነዚህ ፍየሎች በገዳሟ የሚገኘውን የዮርዳኖስ ጸበል (ማይ ዮርዳኖስ) ጠጥተው እንደኾነ ገልጸዋል።

ይህም ጸበሉን የጠጣ አካሉ ሳይፈርስ ለብዙ ዘመን እንዲቆይ ለቦታው የተሰጠ ቃል ኪዳን እንደኾነ የገዳሙን የታሪክ ድርሳናትን ጠቅሰው ያብራራሉ። በቦታውም ላይ የብዙ ቅዱሳን አፅም እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡

ሌላው በዚህ አካባቢ ከሚገኙ ሳቢና ማራኪ ተራሮች መካከል ኑር እምባ ተራራ ይገኛል፡፡ ይህም ስያሜውን ያገኘው አፄ ሱስንዮስ አባ ምዕመነ ድንግልን "ይኑሩ አባ" ብለው እንዲቀመጡ አደረጓቸው፤ በዚህም ተራራው ይኑሩ የሚለውን ቃል በመጠቀም ኑሩ አምባ የሚለውን ስያሜ እንዳገኘ ይነገራል፡፡

በተራራው መካከል አባ ምዕመነ ድንግል ከገዳሟ ወደ ዋሻው በሚመጡበት ጊዜ ደክሟቸው በትረ መስቀላቸውን ተደግፈው ከተራራው ስር ሲቆሙ መሀል ላይ እንደተከፈተላቸው ይገለፃል፡፡

ገዳሟ በየዓመቱ ሰኔ 21፣ ጥር 21 እና ጳጉሜ 3 የንግሥ በዓሏ እንደሚከበርም ነው የተናገሩት፡፡ ከነዚህ ውስጥ ሰኔ 21 ቀን ከፍተኛ የኾነ የሀገር ውስጥ ቱሪስት ፍሰት ይገኝበታል፡፡

ጩጊ ማርያም ከታሪካዊና ሃይማኖታዊ መስህቦች በተጨማሪ እጅግ አስደማሚ በኾኑት የኮሶዬና ውናንያ የተራራ ሰንሰለቶች ግርጌ የምትገኝ በመኾኗ አስደናቂ የመልክዓ ምድር ገጽታዎችንም ለማየት ዕድል የምትሰጥ ልዩ ቦታ ናት፡፡

አካባቢው የመሠረተ ልማት ችግር ያለበት መኾኑን ጠቁመዋል። የገዳሟን የቱሪዝም ፀጋ በሚገባ ለማስተዋወቅ እና ጎብኝዎች ወደ አካባቢው እንዲመጡ ለማድረግ የመንገድ ግንባታ እና ሰፊ የማስተዋወቅ ሥራዎችን መሥራት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል።

ዘጋቢ: አሰፋ ልጥገበው

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን

የዓባይ ወንዝ ዳር የታሪክ ሰገነት!ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 11/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ውጥኑ የተጀመረው በ1995 ዓ.ም ነበር። በወቅቱ የነበሩ አንቱ የተባሉ የሀገሪቱ የኪነ ቅርጽ እጆች፣ አርክቴ...
18/07/2025

የዓባይ ወንዝ ዳር የታሪክ ሰገነት!

ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 11/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ውጥኑ የተጀመረው በ1995 ዓ.ም ነበር። በወቅቱ የነበሩ አንቱ የተባሉ የሀገሪቱ የኪነ ቅርጽ እጆች፣ አርክቴክቶች እና ሰዓሊያን ለሥራው ውበት እና ዘመን ተሻጋሪነት እጃቸውን እንዲያሳርፉ ታጩ።

እነዚህ የሕንጻው ዓለም ጠቢባን በጀ አሉና ጥሪውን ተቀብለው እንደየመክሊታቸው መትጋት ጀመሩ። በ1994 ዓ.ም ግንባታው ተጀምሮ በ1998 ዓ.ም ተጠናቀቀ።

ይህ የዓባይ ወንዝ ዳር የታሪክ ማማ ሲጀመር ከ1973 እስከ 1983 ዓ.ም ብቻ ያለውን የኢህዴን/ብአዴን ታሪክ ብቻ ቀንብቦ በመሰነድ ለታጋዮች መታሰቢያ ይኾን ዘንድ ነበር።

ስሙም፣ ግብሩ፣ የታሪክ ምዕራፍ አካታችነቱም ውስን የፖለቲካ እሳቤ የተጫነው ኾነ። በመኾኑም ከሕዝቡ ጥያቄዎች እየተነሱበት ትችቶችንም ማስተናገድ ጀመረ።

የሕዝብን ጥያቄ ተቀብሎ እና ውስንነቶቹን አስተካክሎ የክልሉን ባሕል፣ እሴት እና ረጅም ታሪክ የሚሰንድ ሁነኛ የሕዝብ ሃብት ለመኾን ወሰነ።

በ2013 ዓ.ም በጀመረው ተቋማዊ ማሻሻያ ፖለቲካ የተጫነው እና አካታች ያልኾነውን ስሙን በመቀየር "የአማራ ሕዝብ ዝክረ ታሪክ ማዕከል" ተብሎ እንደገና ተደራጀ።

ሕዝቡን የማይወክሉ ኪነ ቅርሶችን እና የሙዚየም አደረጃጀቱንም በሕዝብ አስተያየት መሠረት እና በጥናት ተመስርቶ እንደገና አረመ።

የአማራ ሕዝብ ዝክረ ታሪክ ማዕከል የሕዝብ ግንኙነት ኀላፊ በላይ ስማቸው ማዕከሉ አሁን የአማራ ክልል ሕዝብ ለሀገረ መንግሥት ግንባታ ያበረከተውን አስተዋጽኦ፣ ባሕሉን፣ እሴቱን እና ጉልህ ታሪኩን ሰንዶ ለትውልድ ለማስተላለፍ የሚሠራ የታሪክ ማማ ነው።

ማዕከሉ የሕዝቡን ጥንታዊ፣ መካከለኛ እና የዘመናዊ ዘመን ታሪክ በማደራጀት እና በማስረጽ ታሪኩን የሚያውቅ፣ በቀደመ ታሪኩ የሚኮራ እና አዳዲስ ታሪኮችንም የሚሠራ ትውልድ ይፈጠር ዘንድ አቅዶ የሚሠራ ስለመኾኑም አቶ በላይ ተናግረዋል።

ለታሪክ ምርምሮች የመረጃ ምንጭ ኾኖ ያግዛል፣ በተንጣለለው የቤተ መጻሕፍት አገልግሎቱም የንባብ እና የዕውቀት ምንጭ ኾኗል፣ በውብ ምድረ ግቢው ሰርግ እና መሠል የተለያዩ ኹነቶችን ለማዘጋጀት የከተማው ነዋሪዎች ይጠቀሙበታል ብለዋል ኀላፊው።

ዝክረ ታሪክ ማዕከሉ የተደራጀ ሙዚየም ያለው ነው። ሁሉንም የታሪክ አንጓዎች የሚነግር የኪነ ሕንጻ እና ኪነ ቅርስ፣ የዕውቅ ሰዓሊያን እጅ የተፈተነበት የሥዕል ጋለሪ፣ በየዘመኑ ለክልሉ ሕዝብ እና ለሀገርም ረብ ያለው ሥራ በመሥራት እንደ ዕንቁ ያበሩ ጀግኖች ታሪክ እና ምስል፣ እንደነ እትጌ ጣይቱ እና አምሳለ ጓሉ አይነት ሀገርን በብልሃት ሲያሻግሩ እና አይቻልም የተባለውን በመቻል ያሳዩ ተምሳሌት ሴቶችንም የሚዘክር ነው ሙዚየሙ።

ሕዝቡ በየዘመኑ ሲገለገልባቸው የነበሩ ባሕላዊ ቁሳቁሶች፣ ደምቆ የሚታይባቸው የእጁ ውጤት የኾኑ ባሕላዊ አልባሳት በዚሁ ሙዚየም በክብር ተሰንደው ይታያሉ።

ዓለም ገና ስለቴክኖሎጅ ሳያስብ የቀደሙ የክልሉ ሕዝብ የቴክኖሎጅ ጅምሮች፣ ከሀገራትም ቀድሞ ፊደል በመቅረጽ፣ ቀለም በመበጥበጥ እና ዘመን በመቀመር የተተለመ የዕውቀት አሻራ በዚሁ ዝክረ ታሪክ ማዕከል ውስጥ ነፍስ ዘርቶ ይታያል።

ዘመናዊ አንፊ ትያትር፣ መሠብሠቢያ አዳራሽ፣ ከ31 ሺህ በላይ መጻሕፍትን የያዘ ቤተ ንባብ፣ ለተማሪዎች የሚያግዝ የኢንተርኔት አገልግሎት፣ ፋውንቴን እና ሌሎች በርካታ የቱሪዝም አገልግሎቶችንም ይሰጣል ማዕከሉ።

አቶ በላይ ማዕከሉ ከ2013 ዓ.ም የለውጥ ሥራዎቹ ወዲህ በክልሉ ሲቪል ሰርቪስ የሚተዳደር የሕዝብ ተቋም ነው። ከለውጡ በፊት በነበረው የቀደመ አሠራሩ ብቻ በመረዳት ማዕከሉን በፖለቲካ መነጽር ብቻ የሚመለከቱ እና በትችት ብቻ የተጠመዱ ሰዎች አኹንም ድረስ ስለመኖራቸውም አንስተዋል።

"የአማራ ሕዝብ ዝክረ ታሪክ የክልሉ ባሕል፣ እሴት፣ ቋንቋ፣ እና ሌሎችም የቱሪዝም ሃብቶች የተሰነዱበት የሕዝብ ሃብት ነው" መኾኑን ማወቅ ይገባል ብለዋል።

ዝክረ ታሪክ ማዕከሉ በባሕር ዳር ከተማ በታላቁ የዓባይ ወንዝ ዳር በ27 ሺህ 300 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ተንጣልሎ ያረፈ ነው። ይህንን ቦታ የበለጠ በማልማት የክልሉን የቱሪዝም ሃብቶች እንደማስተዋወቂያ እና መጠበቂያነት ከመገልገል ባለፈ ራሱንም አንዱ የጉብኝዎች መዳረሻ ሁነኛ ቦታ ለማድረግ እየተሠራ ነው ብለዋል አቶ በላይ።

የዓባይ ወንዝ ከጣና ሐይቅ ወጥቶ በጎኑ የሚያልፍ ልዩ ቦታ ነው፣ ከወንዙ ጋር የተሰናሰለ የፋውንቴን እና የአረንጓዴ ልማት ሥራ በዘመናዊ መልኩ ለመገንባት የዲዛይን ሥራው ስለመጠናቀቁም ኀላፊው ገልጸዋል።

የታቀደው የልማት ሥራ ከነባሩ የዓባይ ድልድይ ውብ ኾኖ እስከተገነባው አዲሱ ድልድይ ድረስ የሚያስተሳስር ነው ብለዋል።

በአዲስ የተሠራው ዲዛይን በመንግሥት በጀት፣ በባለሃብቶች ቅንጅት እና በልማታዊ ድርጅቶች ተሳትፎ ዕውን እንዲኾንም ታቅዶ እየተሠራ እንጀኾነም ጠቁመዋል።

ሕዝቡም ይህንን ዝክረ ታሪክ ማዕከል በውል በመገንዘብ እና ወደ ቦታው በመግባትም በውስጡ የያዘውን የቱሪዝም ሃብት በመመልከት ታሪክን ማስቀጠል ይገባዋል፤ ማዕከሉ ያቀደውን ተጨማሪ የልማት ሥራም በባለቤትነት መውሰድ እና የበኩልን ድርሻ እንዲወጣም ጥሪ አስተላልፈዋል።

ዘጋቢ:- አሚናዳብ አራጋው

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!

https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን

ጥንታዊው ባህሪ ግንብ ደብረ ገነት ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያንባሕር ዳር፡ ሐምሌ 09/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በኪነ ሕንፃ ጥበብ የተዋበው እና 486 ዓመታት ዕድሜ ያስቆጠረው ባህሪ ግንብ ደብ...
17/07/2025

ጥንታዊው ባህሪ ግንብ ደብረ ገነት ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን

ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 09/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በኪነ ሕንፃ ጥበብ የተዋበው እና 486 ዓመታት ዕድሜ ያስቆጠረው ባህሪ ግንብ ደብረ ገነት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ከማክሰኝት ከተማ በሰሜን አቅጣጫ አምስት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው ጀጃ ባህሪ ግንብ ቀበሌ ላይ ከፍ ባለ ቦታ በዛፎች ተከቦ በግርማ ሞገስ ይገኛል።

ቤተክርስቲያኑ ከባሕር ዳር ጎንደር በሚወስደው ዋና መንገድ ዳር የሚገኝ በመኾኑ ለጎብኝዎች ምቹ ነው።

የአካባቢው ነዋሪዎች እና የደብሩ ካህናት እንደሚናገሩት ይህ ታሪካዊ ሕንፃ በ16ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በ1531 ዓ.ም ደጃች ባህሪ በተባሉ ሰው የተገነባ ነው።

የቤተክርስቲያኑ አሥተዳዳሪ መላከ ገነት ጋሻው አያሌው እንደነገሩን ባህሪ ግንብ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን በአጼ ልብነ ድንግል ዘመነ መንግሥት እንደተገነባ ይታመናል።

የባህሪ ግንብ ሕንፃ ረጅም ዘመንን ያስቆጠረ እና ለአካባቢው ቀበሌም መጠሪያ ኾኖ የሚያገለገል ጥንታዊ ሥፍራ ነው።

በቤተክርስቲያኑ ውስጥ ዕድሜ ጠገብ ካባዎች፣ ጽናዎች እና በብራና የተፃፉ የተለያዩ መጽሐፍት ይገኛሉ፡፡

በቅርብ ርቀትም በወቅቱ ጀኔራል ነጋ ኃይለስላሴ የተባሉ ሰው ያሠሩት የእንቁላል ግንብ እንደሚገኝ የቤተክርስቲያኑ አሥተዳዳሪ ነግረውናል።

የባህሪ ግንብ ቅዱስ ሚካኤል ሕንፃ ረዥም ዘመን ያስቆጠረ በመኾኑ የኪነ ሕንፃ ጥበቡን እንደጠበቀ ለትውልድ ለማስተላለፍ እና ለቱሪስቶች ምቹ ለማድረግ ጥገና እየተደረገለት እንደሚገኝ የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ባሕል እና ቱሪዝም መምሪያ ኀላፊ አቤል መብት ተናግረዋል።

ለጥገና ሥራው ከመንግሥት 4 ነጥብ 6 ሚሊዮን ብር መበጀቱን ነው የጠቆሙት።

በጥገና ሥራው ላይ ኅብረተሰቡ በገንዘብ፣ በሙያ፣ በአይነት እና በጉልበት ንቁ ተሳትፎ እያደረገ እንደሚገኝም አብራርተዋል፡፡

አሁን ላይ የቅርሱ ጥገና 83 በመቶ መድረሱንም መምሪያ ኀላፊ አቤል መብት ለአሚኮ ተናግረዋል፡፡

በሰናይት በየነ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!

https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን

ዳጋ እስጢፋኖስ ገዳም፦ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 09/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ዳጋ እስጢፋኖስ ገዳም በጣና ሐይቅ ውስጥ ከሚገኙ ገዳማት መካከል አንዱ ነው።ከባሕር ዳር ከተማ በስተሰሜን አቅጣጫ 44 ኪ...
16/07/2025

ዳጋ እስጢፋኖስ ገዳም፦

ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 09/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ዳጋ እስጢፋኖስ ገዳም በጣና ሐይቅ ውስጥ ከሚገኙ ገዳማት መካከል አንዱ ነው።

ከባሕር ዳር ከተማ በስተሰሜን አቅጣጫ 44 ኪሎ ሜትር ርቀት በአማካኝ ከሦስት ሰዓት የጀልባ ጉዞ በኋላ ይገኛል።

ገዳሙ በጣና ሐይቅ ውስጥ ከተገደሙ ገዳማት መካከል የመጀመሪያው ነው። በ13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በአፄ ይኩኑ አምላክ ዘመነ መንግሥት አቡነ ሂሩተ አምላክ በተባሉ አባት እንደተመሠረተ ከአማራ ክልል ባሕልና ቱሪዝም ቢሮ የተገኘ መረጃ ያስረዳል፡፡

የኪነ ሕንጻ ጥበብ እና ፍልስፍና ያረፈበት ታሪካዊው የዳጋ እስጢፋኖስ ገዳም ገዳሙን በገደሙት ጻድቁ አቡነ ሂሩተ አምላክ ከሐይቅ ገዳም በመነሳት የእስጢፋኖስ ታቦተ ጽላት በመያዝ በድንጋይ ታንኳ ጣናን በመስቀላቸው እየቀዘፉ ወደ ዳጋ እስጢፋኖስ ገዳም የገቡበትን ታንኳ ቅርፅ ይዞ እንደተሠራ ይነገራል፡፡

ዳጋን ከመካከለኛው ዘመን አንሥቶ ነገሥታቱ፣ መኳንንቱ፣ ጳጳሳቱ እና ምዕመኑ የሀገሪቱ ታሪክ ባለ አደራ አድርገውታል፡፡ በሀገሪቱ የደረሱ የእርስ በእርስ ጦርነቶች እና ወረራዎች ወደ ገዳሙ ባለመዝለቃቸውም ከ800 ዓመታት በላይ የተጠበቁ ቅርሶችን አቅፎ ይዟል፡፡

በዳጋ እስጢፋኖስ ከአፄ ይኩኑ አምላክ እስከ ቀዳማዊ ኀይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት ድረስ የነበሩ አራት ነገሥታት ማለትም አጼ ዳዊት (1382-1430)፣ አጼ ዘርዓ ያዕቆብ (1334-1468)፣ አጼ ፋሲል (1632-1667)፣ የአጼ ወድንግል (1603-1604)፣ የአጼ ሱስንዮስ (1606-1632) ዐጽሞች ዛሬም በክብር ይገኛል፡፡

የመስቀሉን ክፋይ ጨምሮ አያሌ ንዋየተ ቅድሳት፣ የነገሥታት መገልገያ ዕቃዎች፣ ካባዎች እና አክሊሎች፣ የገዳሙ መስራች አቡነ ሂሩተ ወደ ገዳሙ የመጡበት የድንጋይ ታንኳ እና በርካታ የብራና መጻሕፍት ይገኛሉ፡፡

ገዳሙ በታሪክ እና ቅርስ ማኅደርነቱ እንዲኹም ዓመቱን በሙሉ ልምላሜ በማይለየው ጥቅጥቅ ደን የተሸፈነ በመኾኑ በቱሪስቶች ከፍተኛ አድናቆትን ያተረፈ ገዳም ነው።

ከካህናቱ ጸሎት፣ ከአዕዋፋቱ ዝማሬ፣ ከእድሜ ጠገብ ዛፎች የእርስ በእርስ ቁርኝት፣ ከጣና ውኃ መገማሸር ያለፈ ድምጽ የሚፈልግ አይመስልም፡፡ ይህን ተከትሎም አንዳንዶች ዝምተኛው ገዳም በሚል ቅፅል ስም ይጠሩታል።

እሱ ባይቀሰቅስም በዝምታው መንፈስን የሚያድስ ሰማያዊ የኾነ መንፈሳዊ የሥነ ልቦና ሐኪምነቱ ተገደው እና በፍቅሩ ተማርከው የሚሄዱበትን ወዳጆቹን ግን ደጁን አልከለከላቸውም ቀጣይም አይከለክላቸውም፡፡

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን ዳጋ ደጁ ጭር ብሏል። ዝምታውን ሰብሮ ጠያቂ ወዳጆቹን ኑልኝ የሚል ይመስላል ይላሉ ከ1999 ዓ.ም ጀምሮ ገዳሙን በተደጋጋሚ የጎበኙት የባሕር ዳር ከተማ ነዋሪ ዘማሪ አብርሃም ድረስ።

እስከ 2010 ዓ.ም አካባቢ ዳጋ ብዙ ጎብኝ ነበረው፡፡ በተለይ ነጮች በጣም ይጎበኙት ነበር፡፡ ከዛ በኋላ ግን የኮሮና ቫይረስ ሲከሰት በኋላም በሰሜን ኢትዮጵያ በነበረው ጦርነት እና አማራ ክልል ላይ በተፈጠረው ወቅታዊ ጉዳይ ምክንያት ጎብኝዎች እየጎበኙት አይደለም፡፡ የሀገር ውስጥ ጎብኝዎችም እየሄዱ አይደለም፡፡

እኔ እስከማውቀው ድረስ የበፊቱ እና የአሁኑ ጎብኝ ቁጥር አይገናኝም፡፡ ወደ ባሕር ዳር የመጣ ማንኛውም ሰው ገዳሙን መጎብኘት ቢፈልግ ቦታው ላይ ያለው አኹናዊ ኹኔታ ሰላማዊ ነው። ገዳሙ ያለበትን ኹኔታ እና ታሪካዊነት የማስተዋወቅ ሥራ ግን ያስፈልጋል ሲሉ ትዝብታቸውን ለአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ አጋርተዋል።

ሌላኛው የዳጋ እስጢፋኖስ የወንዶች አንድነት ገዳምን በተደጋጋሚ የጎበኙት ወልደ ተክለሃይማኖት አብርሃም ደግሞ ቀደም ባሉት ጊዜያት ዳጋ እስጢፋኖስ ገዳምን በተደጋጋሚ ጎብኝቻለሁ፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ወደ ገዳሙ ሄጄ አላውቅም፡፡ የሰላሙ ኹኔታ ለጉብኝት ምቹ አይደለም፡፡ ሰዎች ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሰው ልዩ ልዩ ተግባሮቻቸውን የሚያከናውኑበት ኹኔታ ላይ አይደለንም አሉን።

እንኳንስ የውጭ ሀገር ጎብኝ የሀገር ውስጥ ጎብኝም እየሄደ አይደለም፡፡ ይህ መኾኑ ደግሞ እንደ ሀገርም ኾነ እንደ ክልል ጉዳት ይኖረዋል፡፡

ሰላም ሲኖር ጎብኝዎች ብቻ ሳይኾኑ ከትናንሽ የንግድ ተቋማት ጀምሮ እስከ ትላልቅ የንግድ ተቋማት ተጠቃሚ መኾን ይችላሉ። ስለዚህ ሰላም የሁሉም ነገር መሰረት ነውና ለሰላም መሥራት ያስፈልጋል ነው ያሉት፡፡

የገዳሙ ልዩ ልዩ ሥራዎች ጉዳይ አስፈጻሚ አባ ሐብተማርያም ዮሐንስ በዳጋ እስጢፋኖስ ዓለምን ንቀው ፈጣሪያቸውን እያመሰገኑ የሚኖሩ ከ180 በላይ ወንድ መነኩሳት ይገኛሉ።

አባቶች ስለ ሰው ልጆች እና ስለሀገር ሰላም በጾምና በጸሎት ከመለመን ባሻገር በገዳሙ የተለያዩ የእደ ጥበብ (የሸማ ሥራ) እና የመስኖ ልማት (ብርቱካን፣ ሸንኮራ አገዳና ሌሎች ፍራፍሬ) ሥራዎችን ይሠራሉ ብለዋል።

እነዚህ የልማት እና የእደ ጥበብ ሥራዎችን ወደ ባሕር ዳር ከተማ በማምጣት ለነጋዴዎች ያስረክባሉ እንጂ ወደ ገዳሙ የሚመጣ ጎብኝ ስለቀነሰ በገዳሙ አካባቢ መሸጥ የሚቻልበት ኹኔታ የለም ነው ያሉት።

ክልሉ ላይ ባለው የጸጥታ ችግር ምክንያትም ጎብኝ የለም። ገዳሙ ራቅ ያለ ከመኾኑ የተነሳ ጎብኝዎች ስጋት ስላለባቸው በቅርብ ወደ ሚገኙ ተቋማት ነው የሚሄዱ። አልፎ አልፎ የሀገር ውስጥ ጎብኝዎች ይመጣሉ ሲሉ አባ ሐብተማርያም ተናግረዋል።

በተለይም ደግሞ መንግሥት ሠራተኞች፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች እና የሰንበት ት/ቤት አገልጋዮች ናቸው የሚመጡት። አኹን ላይ የገዳሙን ትውፊት ጠብቆ በገዳሙ እየተገነባ የሚገኘው ትልቅ ሙዚየም በመጠናቀቅ ላይ ነውም ብለዋል።

በክልሉ ባሕልና ቱሪዝም ቢሮ አማካኝነት የገዳሙ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች እና ሌሎችም ሥራዎች እየተሠሩ ናቸው።

የገዳሙ ቅርሶችም ደኅንነታቸው ተጠብቆ ከ300 ዓመት በላይ ሲያገለግል በቆየው ነባር ሙዚየም ደኅንነታቸው ተጠብቆ ይገኛል።

ገዳሙ እንደቀደመው ጊዜ ጎብኝዎች እንዲጎበኙት ግን የአካባቢው ሰላም አስፈላጊ ነው፣ እግዚአብሔር የሀገሪቱን ሰላም እንዲያስተካክልልን በጸሎት እየጠየቅን ነው ያሉት።

መልካሙ አዳም የአማራ ክልል ባሕልና ቱሪዝም ቢሮ የቱሪዝም ልማት ዳይሬክተር ናቸው። አማራ ክልል ላይ ከፍተኛ የቱሪስት ፍሰት የሚኖርበት ወቅት ከመስከረም እስከ የካቲት ወር ድረስ ነው ይላሉ።

ዳይሬክተሩ ከመጋቢት ወር በኋላ ግን የቱሪስት ፍሰቱ የሚቀንስበት ጊዜ ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ባለው የክልሉ ቱሪዝም ፍሰት ልምድ መሰረት እየሄደ እንዳለ የሚያስረዳ ነው ብለዋል። ነገር ግን አሁን ላይ ቱሪስት የለም እና አለ ማለት አይቻልም፡፡ በጥናትና ምርምር ማረጋገጥ ያስፈልጋልም ነው ያሉት።

በዳጋ እስጢፋኖስ በፌደራል መንግሥት አስተባባሪነት፣ በክልሉ መንግሥት ድጎማ እና በማኅበረሰብ ተሳትፎ የገዳሙን የቀደመ ትውፊት ጠብቆ ሙዚየም እየተገነባ ነው ብለዋል።

የማጠናቀቂያ ምዕራፍ ላይ ይገኛል። በቅርቡ ይመረቃል፤ በውላችን መሰረት እስከ መጪው የኅዳር ወር መጨረሻ ያልቃል ነው ያሉት፡፡

ከዚሁ ጋር ተያይዞም የጉብኝት ትስስር የሚፈጥሩ የተለያዩ መሰረተ ልማቶችን ሠርተን አብረን ለማስመረቅ እየሠራን ነው ሲሉም ተናግረዋል፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞ በዚህ በጀት ዓመት በእቅድ ተይዞ እየተሠራ ያለ ከቱሪዝም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር የዳጋ እስጢፋኖስ የጉብኝት ማዕከል እና ወደ ገዳሙ ለሚመጡ ቱሪስቶች ማረፊያ ክፍሎች፣ ሻወር እና መጸዳጃ ቤቶች ግንባታ በጨረታ ለኮንትራክተሮች ሠጥተን ሥራው ተጀምሯል ብለዋል፡፡

ደጋ እስጢፋኖስ በአኹኑ ሰዓት ከፀጥታ ችግር ስጋት ነጻ ኾኖ የክረምቱን ቅዝቃዜ መርሻ እና ዝምታውን የሚሰብሩ ታሪክ ነጋሪ ጎብኝዎችን ይሻል።

ለዚህ ደግሞ በጎብኝዎች አማካኝነት ተጠቃሚ የሚኾኑ የአካባቢው ማኅበረሰብ እና የመንግሥት አሥተዳደር አካላትን የጋራ ጥረት ይጠይቃል ነው ያሉት።

ዘጋቢ:-ሮዛ የሻነህ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

ከጥንት እስከ ዛሬ ጸንቶ የቆመ ታሪክ - ቆማ ፋሲለደስባሕር ዳር: ሐምሌ 08/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ቆማ ቅዱስ ፋሲለደስ ገዳም በደቡብ ጎንደር ዞን በእስቴ ወረዳ በደብር ቀበሌ የሚገኝ ጥንታ...
15/07/2025

ከጥንት እስከ ዛሬ ጸንቶ የቆመ ታሪክ - ቆማ ፋሲለደስ

ባሕር ዳር: ሐምሌ 08/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ቆማ ቅዱስ ፋሲለደስ ገዳም በደቡብ ጎንደር ዞን በእስቴ ወረዳ በደብር ቀበሌ የሚገኝ ጥንታዊ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያኑን በ1597 ዓ.ም የአጼ ፋሲል እናት እና የንጉሥ ሱሲንዮስ ሚስት ንግሥት ወልደ ሳህላ ናቸው የመሰረቱት፡፡

ንግሥት ወልደ ሳህላ አፄ ሱሲንዮስ ሃይማኖታቸውን ሲቀይሩ ሃይማኖቴን አልቀይርም፤ ገዳም መስርቼ ሃይማኖቴን አጸናለሁ ብለው ብራደጌ (ብሩ አደጌ) ወደ ተባለ ቦታ በመሄድ ቤተ ክርስቲያን ሠርተው እንደነበር ይነገራል።

የስያሜው እና አመሰራረቱም የብራደጌው ቤተ ክርስቲያን ተሠርቶ ከመጠናቀቅ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ ተሠርቶ ከተጠናቀቀ በኋላ ለክብረ በዓሉ የሚታረደው በሬ ተነስቶ አመለጠ፤ ሕዝቡም በሬውን ለመያዝ ሲሮጥ ንግሥቲቱ በሬውን አትያዙት፤ ብቻ ተከትላችሁ የሚቆምበትን ቦታ እዩ በማለት አዘዙ፡፡ ሕዝቡም የታዘዘውን አደረገ፡፡ ንግሥቲቱም በሬው የት ደረሰ ብለው ሲጠይቁ ቆመ የሚል መልስ ተሰጣቸው፡፡ በዚህ ምክንያትም በሬው የቆመበት ቦታ ስያሜ ቆማ እንደተባለ በአፈ ታሪክ ይነገራል።

ንግሥቲቱ በሬው የቆመበት ሥፍራ በአጋጣሚ ሳይኾን የቤተ ክርስቲያኑ ቦታ እዚያ ላይ እንዲኾን የእግዚአብሔር ፈቃድ ስለኾነ ነው ብለው አመኑ። ቤተ ክርስቲያኑም በዚያ ቦታ እንዲገነባ አደረጉ ይባላል፡፡

በመጀመሪያ እድሞ እና እቃ ቤት በድንጋይ እና በኖራ አሠሩ። በመቀጠልም ቤተ መቅደሱን አሳነጹ። ስለ አሠራሩ የሚናገሩት አባቶች ቤተ መቅደሱ ሕንጻ በድንጋይ እና በኖራ መጀመሩን ይናገራሉ፡፡ "የበቁ አባቶች" ለንግሥቷ 'እድሜሽ አጭር ነው' ስላሏቸው ሞትን ለመቅደም በጭቃ እንዲጠናቀቅ ማድረጋቸው ይነገራል፡፡

“ቆማ ፋሲለደስ ክበቡ ክበቡ
እንኳን ዲያቆኖቹ ያታልላል ካቡ" ተብሎ የተዜመለት ቆማ ፋሲለደስ ከወረዳው ዋና ከተማ ከመካነ ኢየሱስ 48 ኪሎ ሜትር፣ ከደብረ ታቦር ከተማ 104 ኪሎ ሜትር እና ከባሕር ዳር ከተማ 160 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል፡፡

በቆማ ፋሲለደስ መምህር የኾኑት አባ አውስጣጢዎስ ስለገዳሙ በሰጡን መረጃ አፄ ፋሲል በ1624 ዓ.ም የደብር እና የገዳም ሥርዓት እንዲፈፀምበት ርእሰ አድባራት ወገዳማት ቆማ ቅዱስ ፋሲለደስ ብለው ሰይመውታል፡፡

ቤተ ክርስቲያኑ የተሰየመው በሰማዕቱ ቅዱስ ፋሲለደስ ሥም ነው። ንግሥት ወልደ ሳህላ ለሰማዕቱ ካላቸው ክብር የተነሳ ልጃቸውን አጼ ፋሲልን በሰማዕቱ መሰየማቸው እና ቆማ ፋሲለደስንም እንደዚያው ማድረጋቸው ገልጸውልናል፡፡

ታቦቱም ከሰማዕቱ ፋሲለደስ ትውልድ ሀገር ከአንፆኪያ እንደመጣ ይነገራል። ክብረ በዓሉም መስከረም እና ታኅሣሥ 11 ቀናት ናቸው፡፡

እንደ አባ አውስጣጢዎስ ገለጻ ቤተ ክርስቲያኑ 16 አምደ ወርቅ አሉት፡፡ በቁመቱ ረጂም እና የውስጥ አሠራሩ እና የውጪ ግቢው ከእድሞው ጋር ሲታይ ግርማ ሞገሱ ጥንታዊነት ብቻ ሳይኾን አሁናዊ ክብሩ እና ውበቱ እንደተላበሰ ነው፡፡

ቆማ ፋሲለደስ በቀድሞ ዘመን የነበሩ መንፈሳዊ እሳቤዎች እና ተዓምራት የተገለጡበት በመኾኑም ታሪኩን ታላቅ ያደርገዋል፡፡

በ1928 ዓ.ም ጣሊያን ኢትዮጵያን በወረረ ጊዜ ቤተ ክርስቲያኑን ከአየር ላይ በቦንብ ለመምታት ያደረገውን ሙከራ በማክሸፍ ቦንቦቹ ሌላ ቦታ እንዲወድቁ እና እንዳይፈነዱ ማድረጉ ይነገራል፡፡

ነጮች ጫማቸውን ሳያወልቁ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ሊገቡ በመሞከራቸው እባብ እግራቸው ላይ ተጠምጥሞ ሳይገቡ መቅረታቸው የሚነገሩ ተዓምራት ናቸው፡፡

በቤተ ክርስቲያኑ ጥንታዊ የኾኑ ከአፄ ፋሲል፣ ከንግሥት ወልደ ሳህላ እና ከሌሎች ነገሥታት የተበረከቱ የብራና መጻሕፍት፣ የብረት ደወል፣ የብር ከበሮ፣ ነጋሪት፣ የወርቅ መስቀል እና ልዩ ልዩ ጥንታዊ ቅርሶች ይገኛሉ።

በቤተ ክርስቲያኑ የሚገኙ ጥንታዊ እና የማይንቀሳቀሱ ቅርሶች አብዛኞቹ ሕንጻዎቹ በኖራ የተገነቡ ናቸው። የግድግዳ ላይ ሥዕሎች፣ በጎንደር ዘመነ መንግሥት የግንባታ ጥበብ የተሠሩት የቤተ ክርስቲያኑ አጥር፣ እቃ ቤት እና ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ ጥንታዊነትን ይገልጻሉ።

ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ለመድረስ የበጋ የመኪና መንገድ ያለው አለው። ጥንታዊው ቤተክርስቲያን ጎብኝዎች ሊጎበኙት እና ሊያዩ የሚገባ የታሪክ እና የሃይማኖት ማሕደር ነው።

በዋሴ ባዬ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን

ሰቆጣ ለሻደይ በዓል ዝግጅት ጀምራለች።ሰቆጣ: ሐምሌ 05/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ሻደይ በዋግ ኽምራ ልዩ ትርጉም ያለው የልጃገረዶች ጨዋታ ነው። ሻደይ ከነሃሴ 16 እስከ 21 ድረስ በየዓመቱ ...
15/07/2025

ሰቆጣ ለሻደይ በዓል ዝግጅት ጀምራለች።

ሰቆጣ: ሐምሌ 05/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ሻደይ በዋግ ኽምራ ልዩ ትርጉም ያለው የልጃገረዶች ጨዋታ ነው። ሻደይ ከነሃሴ 16 እስከ 21 ድረስ በየዓመቱ በልዩ ልዩ የባሕል አልባሳትና ጌጣጌጦች የተዋቡ ልጃገረዶች በድምቀት የሚያከብሩት በዓል ነው።

በመኾኑም የሻደይን በዓል በልዩ ኹኔታ ለማክበር የቅድመ ዝግጅት ሥራ መጀመሩን የሰቆጣ ከተማ አሥተዳደር ባሕልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ካሳ ከበደ ገልጸዋል።

የሻደይ ባሕላዊ ጨዋታ ከኦሪት ጀምሮ ሲከበር እንደመጣ ይነገራል። በዓሉን በዞን ደረጃ ከ20ዐዐ ዓ.ም ጀምሮ በሰቆጣ ከተማ ከየወረዳው የተውጣጡ ልጃገረዶች የሚያከብሩት በዓል እንደኾነ ኀላፊው ተናግረዋል።

ሰቆጣ ከተማም በዓሉን በድምቀት ለማክበር ከወጣቱ፣ ከነጋዴው ማኅበረሰብ እና ከአመራሩ ጋር የጋራ ሥራ መጀመራቸውንም ጠቁመዋል።

የብሔረሰብ አሥተዳደሩ ባሕልና ቱሪዝም መሥሪያ ኃላፊ ኢዮብ ዘውዴ የሻደይ ባሕላዊ ጨዋታ በታዳጊዎች፣ በአዋቂ ልጃገረዶች እና በእናቶች ተከፍሎ የሚከበርና የዋግ ሕዝብ ልዩ መገለጫ ነው።

ወጣቶችም የሰቆጣ ከተማን ለእንግዶች ምቹ እንድትኾን ለማድረግ በበጎ ፈቃድ አገልግሎት በእቅድ በማካተት ወደ ተግባር ተገብቷል። በአካባቢው ያለውን ሰላም በማጽናት ለእንግዶች የተመቼ ከባቢ ለመፍጠር በጋራ መሥራት ይገባል ነው ያሉት አቶ ኢዮብ።

ሻደይን ከነሃሴ 01 ጀምረው ልጃገረዶች አልባሳት በማሟላት፣ እንሶስላ በመሞቅ እና ሻደይ በመንቀል፣ ባሕላዊ ጨዋታዎችንም በቡድን መለማመድ ይጀምራሉ።

መምሪያ ኀላፊው እንዳሉት እንደ ዞን በዓሉን በድምቀት ለማክበር ኮሚቴ በማዋቀር እና ተልዕኮ በመሥጠት ወደ ሥራ ተገብቷል።

ወጣቶችም የአካባቢውን ሰላም ከመጠበቅ ባሻገር ውብና ጽዱ ከተማን ለመፍጠር በበጎ ፈቃድ አገልግሎት የበኩላቸውን ሚና እንዲወጡ ጠይቀዋል።

ዘጋቢ:- ደጀን ታምሩ

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

 #አሚኮየአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን የመረጃ አማራጮችን በቀላሉ ያግኙ። QR ኮዱን ስካን ያርጉ ወይንም ቀጣይን ሊንክ ይጎብኙ👇https://linktr.ee/AmharaMediaCorporationየአሚ...
15/07/2025

#አሚኮ
የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን የመረጃ አማራጮችን በቀላሉ ያግኙ።
QR ኮዱን ስካን ያርጉ ወይንም ቀጣይን ሊንክ ይጎብኙ👇

https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

የዓባይ ወንዝ ዳር የውበት ሰገነትባሕር ዳር: ሐምሌ 08/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በባሕር ዳር ከተማ ውስጥ ታላቁ የዓባይ ወንዝ ከጣና ሐይቅ ተለያይቶ ከሚወጣበት ውብ ቦታ ወረድ ብሎ ሌላ የተን...
15/07/2025

የዓባይ ወንዝ ዳር የውበት ሰገነት

ባሕር ዳር: ሐምሌ 08/2017 ዓ.ም (አሚኮ) በባሕር ዳር ከተማ ውስጥ ታላቁ የዓባይ ወንዝ ከጣና ሐይቅ ተለያይቶ ከሚወጣበት ውብ ቦታ ወረድ ብሎ ሌላ የተንጣለለ የውበት ሰገነት አለ - የአማራ ሕዝብ ዝክረ ታሪክ ማዕከል።

ይህ ማዕከል የአማራ ክልልን ሕዝብ ታሪክ፣ ባሕል እና እሴት አደራጅቶ የያዘ ማዕከል ነው። የአማራ ሕዝብ ዝክረ ታሪክ ማዕከል በእድሜ ጠገቡ የዓባይ ወንዝ ድልድይ እና ውብ ኾኖ በተገነባው አዲሱ ድልድይ መካከል ያረፈ፣ የውብ ኪነ ሕንጻ፣ ሥዕል እና ቅርጻ ቅርጾችን የያዘም ነው።

በአሚናዳብ አራጋው

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Address

Bahir Dar

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Discover Amhara AMECO posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to Discover Amhara AMECO:

Share