አሚኮ በኲር/AMECO BEKUR

አሚኮ በኲር/AMECO BEKUR በኲር
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን የምትዘጋጅ ሳምንታዊ የቤተሰብ ጋዜጣ

21/07/2025
ፆታዊ ጥቃት ለምን?የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም  በዓለም አቀፍ ደረጃ የዓለም ጤና ድርጅት ይፋ ያደረገው ጥናት ከ2019 እ.አ.አ በኋላ ያለው መረጃ እንዳመለከተው ከሦስት ሴቶች አን...
21/07/2025

ፆታዊ ጥቃት ለምን?
የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

በዓለም አቀፍ ደረጃ የዓለም ጤና ድርጅት ይፋ ያደረገው ጥናት ከ2019 እ.አ.አ በኋላ ያለው መረጃ እንዳመለከተው ከሦስት ሴቶች አንዷ ፆታዊ ጥቃት ይደርስባታል፤ ይህም በመቶኛ ሲሰላ 34 ከመቶ የሚሆኑ ሴቶች ላይ ፆታን መሠረት ያደረገ ጥቃት ይደርስባቸዋል እንደ ማለት ነው::
በአማራ ክልል ሴቶች ሕፃናት እና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ የሴቶች ንቅናቄ ተሳታፎ ማስፋፊያ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ወ/ሮ ደስታ ፈንታ የሴቶችን ጥቃት አስመልክቶ ሰሞኑን በባሕር ዳር ከተማ ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሑፍ ጾታን መሠረት ያደረገ ጥቃት ተብሎ የሚገለፀው ከሰዎች ፍላጐት ውጭ ኃይልን በመጠቀም የሚፈፀም ማንኛውም ዓይነት ጥቃት እንደሆነ አመላክተዋል::

ጥናት አቅራቢዋ ጾታን መሸረት ያደረገ ጥቃት በተለይ በጦርነት ወቅት የከፋ ስለመሆኑ ጠቁመዋል:: ለአብነትም በሰሜኑ ጦርነት ወቅት ሕጻናት፣ ወጣቶች፣ መነኩሴዎች፣ የአልጋ ቁራኛዎች እና የአዕምሮ ችግር ያለባቸው… ዜጎች ተገዶ የመደፈር ጥቃቱ ሰለባ እንደሆኑ አመላክተዋል::
የጥቃቱ መንስኤ በዋናነነት ማኅበረሰቡ በሴቶች እና በወንዶች መካከል የፈጠረው የተዛባ ማኅበራዊ አመለካከት ወይም ሥርዓተ ፆታ ነው:: ታዲያ ይህንን ጥቃት ግለሰቦች፣ ማኅበረሰቡ እና በቡድን የተደራጁ አካላት በቀላሉ መብታቸውን ማስከበር በማይችሉ ሴቶች ላይ በብዛት ሲፈጽሙ ይስተዋላል::
ወ/ሮ ደስታ ፈንታ በጥናታቸው ፆታዊ ጥቃትን በሦስት ከፍለውታል፤ የመጀመሪያው አካላዊ ጥቃትን /ድብደባ/፣ ግርፋትን፣ በአሲድ መቃጠልን እና ሲከፍ ደግሞ ግድያን ያካትታል::
ሁለተኛው የሥነ ልቦና ጥቃት የሚባለው ደግሞ ስድብ፣ ዛቻ፣ ማሸማቀቅ እና የመሳሰሉት ናቸው:: ሌላው (ሦስተኛው) ደግሞ ኢኮኖሚያዊ ጥቃት የሚባለው ሲሆን ሀብትን እና መሬትን መንጠቅ፣ ንብረትን መከልከል፣ ከምርት እና ከሥራ ውጭ ማድረግ፣ ንብረት ማንቀሳቀስ መከልከልን … ያካተተ ነው::

ጥናቱ እንደሚያሳየው የጾታዊ ጥቃት ሰለባ ከሚሆኑት ሕጻናት፣ ወጣቶች፣ መነኩሴዎች፣ የአልጋ ቁራኛዎች እና የአዕምሮ ችግር ያለባቸው… ዜጎች ውስጥ 10 ከመቶው ወሲባዊ ጥቃት፣ 21 ነጥብ ስድስት ከመቶ ደግሞ ሥነ ልቦናዊ እንዲሁም 27 ከመቶ ያህሉ አካላዊ ጥቃቶች ይደርስባቸዋል:: በጠቅላላው ዕድሜ ክልላቸው ከ15 እስከ 49 በሚገኙ ሴቶች 25 ከመቶ አካላዊ፣ 24 ከመቶ ሥነ ልቦናዊ ፣ 12 ከመቶ ወሲባዊ (ተገዶ መደፈር) ጥቃት እንዲሁም ስምንት ከመቶ ደግሞ አካላዊ ድብደባ እና ወሲባዊ ጥቃት ተደጋግሞ ይፈፀምባቸዋል::
ፆታን መሠረት ያደረገ ጥቃት መንስኤ ምንድን ነው? ተብሎ ሲጠየቅ በዋናነት የሚነሳው ማኅበረሰቡ ስለ ፆታ ያለው የተዛባ አመለካከት ተንሰራፍቶ መቆየቱ እንደሆነ ወ/ሮ ደስታ ያነሳሉ:: ለአብነትም መጥፎ ድርጊት የፈፀመን ወንድ ጀግና፣ ተጎድታ የመጣችን ሴት አስጠቂ፣ ከፍ ብለው ሲወጡ (አለባበስን ጨምሮ ራሳቸውን ጠብቀው) ደግሞ ማንቋሸሽ የተለመደ ድርጊት ነው::

የተዛባ የማኅበረሰብ እሳቤ መኖር በተለይም “ሴት ብታውቅ በወንድ ያልቅ” እየተባለ ሴቶች ምንም ነገር ሲሠሩ ማንቋሸሽ ዛሬም ድረስ የዘለቀ ችግር መሆኑ በጥናቱ ተመላክቷል:: በአሁኑ ወቅት ደግሞ ሴቶችን በከፍተኛ ደረጃ ለጥቃት ተጋላጭ ያደረጋቸው በየአካባቢው ያለውን የሠላም እጦት እና ድህነት (የኢኮኖሚ ጥገኝነት) በምክንያትነት ይነሳሉ::
በሰሜኑ ጦርነት ወቅት በርካታ ሪፖርት ያልተደረጉ ጥቃቶች ቢኖሩም ከአምስት ሺህ በላይ ሴቶች ፆታዊ (አስገድዶ መድፈር) ጥቃት ደርሶባቸዋል:: ከ2016 እስከ 2017 ዓ.ም የተደረጉ ጥናቶች እንደሚያመላክቱት ደግሞ ከአንድ ሺህ 324 በላይ ሕጻናትን ጨምሮ አዋቂ ሴቶች ጾታዊ ጥቃት ደርሶባቸዋል:: ከነዚህ ውስጥ አንድ ሺህ 159 አዋቂ ሴቶች፣ 745 ሕጻናት 22 ደግሞ ወንድ ሕጻናት ጥቃት እንደተፈፀመባቸው በዋን ስቶፕ ሴንተር ተቋማት የተደረገው ሪፖርት ያመላክታል::

በአማራ ክልል ጥቃት ለሚደርስባቸው ሰዎች ጊዜያዊ የመጠለያ፣ የምገባ፣ የሥነ ልቦና፣ … አገልግሎት የሚሰጥ 17 የዋን ስቶፕ ሴንተር መኖሩን ያነሱት ወ/ሮ ደስታ ጥቃት ደርሶባቸው በማዕከሉ ከተቀመጡት ውስጥ 466 ሴቶች ተጠርጣሪ ጥቃት ፈፃሚዎች ላይ ክስ መሥርተዋል፤ 183 አጥፊዎች ደግሞ ውሳኔ አግኝተዋል:: ከነዚህ ውስጥ 111 አጥፊዎች በፅኑ እስራት፣ 38ቱ እስከ ሦስት ዓመት በሚደርስ እስራት ስምንቱ ደግሞ በገንዘብ የተቀጡ ሲሆን 12ቱ ነፃ ወጥተዋል:: የቀሪዎቹ ክስ በሂደት ላይ መሆኑን ነው ወ/ሮ ደስታ ያመላከቱት::
በግጭቱ መደፈራቸውን ሪፖርት ያላደረጉ መምህራንን ጨምሮ በርካታ የመንግሥት ሠራተኞች እንዳሉ ታውቆ ክስ እንዲመሠርቱ ቢጠየቁም “ዳግም ጥቃት ይደርስብናል” በሚል ስጋት ክስ መመሥረት አለመፈለጋቸው ደግሞ ፊደል ቆጥረዋል የሚባሉት ሴቶችም ጭምር በስጋት ውስጥ እንደሚኖሩ ማሳያ እንደሆነ ነው ባለሙያዋ የገለፁት::

በሕጉ በኩልም የላላ ውሳኔ መኖር፣ ምርመራ ለማድረግ መረጃ የሚሰበሰብበት እና የሕክምና ውጤት የሚገኝበት ተቋም ተገቢውን መረጃ አለመስጠት፣ የመጨረሻ የፍርድ ውሳኔው ሌሎችን የማያስተምር (ውሃ የማያነሳ) መሆኑ በጥናቱ ተለይቷል:: በዚህም ለአጥፊዎች የሚሰጠው ፍርድ የጥቃት ሰለባ ለሆኑት አካላት ችግራቸውን በአግባቡ የሚያካክስ እንዳልሆነ ነው የተገለጸው::
ቢሮውም አስፈላጊውን አካላዊም፣ ሆነ ሥነ ልቦናዊ ሕክምና ካገኙ በኋላ ኢኮኖሚያዊ ችግር ላለባቸው ከረጅ ድርጀቶች ጋር በመተባበር ወደ ገቢ ማስገኛ ሥራ ለማስገባት እንደየ አካባቢው ሁኔታ ከ10 ሺህ እስከ 100 ሺህ ብር በመስጠት ሥራ እንዲጀምሩ እያደረገ መሆኑን ባለሙያዋ ጠቁመዋል:: ችግሩ አሁን ባለው ፍጥነት እንዳይቀጥል ደግሞ ኅብረተሰቡም ቢሆን ጥቃት አድራሹን ተገቢውን ቅጣት እንዲያገኝ፣ ለሴቶች መብት መከበር ለቆመ አካል በመተባበር እና ተገቢውን ማስረጃ በማቅረብ አስፈላጊውን ትብብር ሊያደርግ እንደሚገባ ነው ባለሙያዋ የጠየቁት::
በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ባሕር ዳር እና ደሴ ጽ/ቤት ሴቶች እና ወጣቶች ዴስክ ካርዲኔተር ወ/ሮ ሃና ጆርጅ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች እና ጾታዊ ጥቃት በአማራ ክልል ወደ መጥፋት አቅራቢያ ደርሶ እንደነበር አስታውሰዋል:: አሁን ባለው ግጭት እና ወቅታዊ ችግር ምክንያት ግን በጣም መሥፋፋት እንደጀመረ ነው የጠቆሙት::

በተለይም ፆታዊ ጥቃት እየጨመረ መምጣቱን ወ/ሮ ሃና አስታውሰዋል:: ለዚህም ምክንያቱ ተማሪዎች ከትምህርት ገበታ ርቀው በቤት በመቀመጣቸው የተነሳ በአካባቢያቸው ለጥቃት በቀላሉ ተጋላጭ መሆናቸው ነው:: የሴቶች እና ሕጻናት ጥቃት እንዲስፋፋ ካደረጉት ውስጥ አደንዛዥ ዕፅ፣ መጤ ልማዳዊ ድርጊት (ግብረ ሰዶምን ጨምሮ)፣ በታዳጊዎች እየተለመደ የመጣውና አላግባብ የተስፋፋው የማሕበራዊ ሚዲያ (የሶሻል ሚዲያ) አጠቃቀም እንደሆኑ ጠቁመዋል:: የወላጆች ልጆችን አዋዋል በአግባቡ መከታተል አለመቻል ደግሞ ችግሩ ይበልጥ እንዲስፋፋ ማድረጉን ገልፀዋል::
በቀጣይ ወላጆች ልጆቻቸውን በየሃይማኖታቸው በሚገባ በማስተማር ሰብዕና ግንባታ ላይ መሥራት እንደሚገባቸው ነው ወ/ሮ ሃና ያስገነዘቡት:: ከፆታዊ ጥቃት ጋር በተያያዘ የሚወሰነው የፍትሕ ውሳኔ ሂደት እና ቅጣቱ አስተማሪ እንዲሆንም ከተጎጂዎች የዕድሜ ልክ ጉዳት አንፃር ተመጣጣኝ ሆኖ መታየት እንዳለበት አስገንዝበዋል:: በዚህ ላይ ኅብረተሰቡ በንቅናቄ ሊሠራ ይገባል ያሉት ወ/ሮ ሃና፤ ሁሉም በየእምነቱ ከመሰባሰብ ጀምሮ በስብከት ወቅት በተለይ ለወጣቶች በአግባቡ ባሕርይን ሊለውጥ የሚችል ትምህርት እንዲሰጥም ጠይቀዋል::

ማናት
የሸዋሉል መንግሥቱ
የሸዋሉል መንግሥቱ ገጣሚ እና ዜማ ደራሲ ጋዜጠኛ እንዲሁም ፀሐፌ ተውኔት ነበረች::
ውልደቷ በያኔው አጠራር ምሥራቅ ሃረርጌ ጃርሶ (ኤጀርሳ ጎሮ) አካባቢ በ1937 ዓ.ም ነው:: ብዙዎች በስሟ አጠራር ዙሪያ ጥያቄዎችን ያነሱ ነበር። ምክንያቱ ደግሞ አንድም ሴት በወቅቱ በዚህ ስም የማትጠራ በመሆኑ ነው:: ልዑል የሚለው ስያሜ የሚሰጠው ለወንድ እንጂ ለሴት ባለመሆኑ ነው ብዙዎች ሲጠሯት ‹‹የሸዋልዑል መንግሥቱ›› እያሉ ሲሆን እርሷ ግን ስሟን በፅሑፍ በምታሰፍርበት ጊዜ ‹‹የሸዋሉል መንግሥቱ›› በማለት ነበር።
ትምህርቷን ተወልዳ ባደገችበት ምሥራቅ ሀረርጌ ጃርሶ (ኤጀርሳ ጎሮ) አካባቢ ሲሆን ከሥነ-ፅሁፍ ጋር የነበራት ትውውቅም ገና በ10 ዓመቷ ነበር:: የመጀመሪያው የድርሰት ሥራዋም “የኢዮብ ትዕግስት›› የተሰኘ ድርሰቷ ሲሆን ከ 9 ዓመታት በኋላ ማለትም በ19 ዓመት እድሜዋ ጥቂት መሻሻያ ተደርጎበት በኢትዮጵያ ሬዲዮ ‹‹የትያትር ጊዜ›› በተባለ ፕሮግራም ላይ ተላልፎላታል:: ይህ ሥራም በድርሰት ዓለም የመጀመሪያው ሥራዋ ነው:: “ወይ ሆቢ ሆቢ” ለድምፃዊ አሊ ቢራ ያበረከተችው ብዙዎች የወደዱላት አይረሴ የሙዚቃ የግጥም ሥራዎቿ ነው:: የሸዋሉል መንግሥቱ ሙዚቃ “ዘሃረር” የተባለ መፅሔትንም በማዘጋጀት ትታወቃለች። በጊዜውም የ27 ዓመት ወጣት ነበረች::
ሸዋሉል መንግሥቱ ብዙ ጊዜዋን ያሳለፈችው በሀረርጌ ፖሊስ ማስታወቂያ ክፍል በየሁለት ወሩ የሚታተመውን “የምስራቅ በረኛ” መፅሄትን በማዘጋጀት ነበር::በዚህ ክፍል ለሀረር ምሥራቃዊ ሰጎን ኦርኬስትራ አያሌ ግጥሞች እና ዜማዎችን ቲያትሮች እና ዝማሬዎችን ታዘጋጅ ነበር:: የሸዋሉል መንግሥቱ የመፅሐፍ ደራሲም ነበረች። በ1962 ዓ.ም ተፅፎ በ1968 ዓ.ም የታተመው ‹‹እስከመቼ ወንደላጤ›› የተሰኘ ሥራዋ በዚህ ዘመን እምብዛም የሚታወቅ ባይሆንም በዘመኑ ብዙ የተነበበ ነው:: በ32 ዓመቷ አዲስ አበባ ከተማ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየችው የሸዋሉል በአዲስ አበባ በቆየችባቸው ጥቂት ጊዜያት ውስጥ በርካታ ሥራዎችን ሠርታለች። በኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን በዜና አንባቢነት፣ በፕሮግራም አዘጋጅነት እና በሬዲዮ ድራማ ፀሐፊነት ሠርታለች::
በደርግ ዘመን በቀበሌ ሊቀ መንበርነት ያገለገለች ሲሆን በወቅቱም የመኢሶን አባል ነበረች:: የሸዋሉል መንግሥቱ የአምስት ልጆች እናት ስትሆን ግንቦት 1969 ዓ.ም ነው ከዚህ ዓለም በሞት የተለየችው።
ምንጭ - የኢትዮጵያ ታሪክና ቱሪዝም

(ማራኪ ሰውነት)
በኲር የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

የሕዳሴው ግድብ- የኢትዮጵያውያን ቁጭት ማሳያየሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም “ዓባይ ጉደል ብለው አለኝ በታህሣሥየማን ሆድ ይችላል እስከዚያው ድረስ”ለተረት የታደለ፤ ለአፍ የጣፈጠ ወንዝ...
21/07/2025

የሕዳሴው ግድብ- የኢትዮጵያውያን ቁጭት ማሳያ
የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

“ዓባይ ጉደል ብለው አለኝ በታህሣሥ
የማን ሆድ ይችላል እስከዚያው ድረስ”
ለተረት የታደለ፤ ለአፍ የጣፈጠ ወንዝ እንደ ዓባይ የለም:: አንዳንድ ሰው ምንም ዓይነት ተረትና ምሳሌ ባይችል ቢያንስ “አባይ ማደሪያ የለው ግንድ ይዞ ይዞራል” የሚለው ተረትና ምሳሌ ከአፉ አይታጣም:: እርግጥ ነው፤ አባይ መንገደኛ ነው፤ብዙ ርቆ ይሄዳል:: በእርግጥም የግዝፈቱንና የገናናነቱ እና ያህል ጥቅም ላይ አልዋለም ::

ክረምት አልፎ የዓባይ ውሃ ሙላት ጎድሎ ታህሣሥ ድረስ መታገስ አቅቶት የናፍቆት ግጥም እና እንጉርጉሮ ለመግጠም የታተረ፣ እስከዚያ መታገስ ያቃተው ትውልድ ዓባይን ጥቅም ላይ ለማዋል ለምን ገደደው? ነው ጥያቄው::

አንዳንድ አባባሎች ለስንፍና፣ ለሰበብ በር ይከፍታሉ:: እነዚህን አባባሎች ላለመቻል እንደሰበብ ወስደን ላልተሳካልን ነገር እንደ ምክንያት በመቁጠር ራስን ለማሳመን እንጠቀምባቸዋለን::
ዓባይን ላለመጠቀማችን ተረቱን እንደ ምክንያት፤ ምሳሌያዊ ንግግሩን እንደአይነኬ በማየት ዓባይ መንገደኛ እንዲሆን እድል ሰጥተነው ኖረናል::

ከዚህ ሁሉ ተረት ውጭ ሁሉም የማይናገረው እና በውስጡ የያዘው ቁጭት እንዳለ ማሳያው ግን የሕዳሴው ግድብ የመሰረት ድንጋይ መጣል ነው::
የሕዳሴው ግድብ የመሰረት ድንጋይ ብስራት ለዘመናት በተረት ሸንግለን እንዲጓዝ እድል የሰጠነው እና መንገድ የከፈትንለትዓባይ ከልባችን እንዳልነበረ በዚሁም በሁሉም ሰው ልብ ውስጥ ቁጭት እንደነበረ ማሳያ ነው::

አቅሙ የፈቀደ ሁሉ ያለውን ሳይሰስት እየሰጠ እዚህ ደርሷል:: በዚህ ግድብ ግንባታ ሂደት መላ ኢትዮጵያውያን እውቀታቸውን፣ ጉልበታቸውን እና ገንዛባቸውን አስተባብረው በጋራ ለመቆ እንዲሁም በጋራ ለመስራት እንደምክንያት የሆነ ብሎም ግድቡ የሁሉም መሆኑን ያሳየ ተግባር ፈጽመዋል::
ግንባታው ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ሕዝቡ ከ23 ቢሊዮን ብር በላይ ድጋፍ አድርጓል:: ይህን ያህል ገንዘብ መሰብሰብ የተቻለው ደግሞ ከቦንድ ሽያጭ እና ስጦታ፣ በ8100 አጭር የጽሑፍ መልዕክት እና ከኢትዮጵያ ነጻ አካውንት እንዲሁም ከውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን /ከዳያስፖራዎች/ ነው::

የሕዳሴ ግድብ ተጠናቆ በመጭው መስከረም በድምቀት ለማስመረቅ ዝግጅት እየተደረገ ነው:: የሕዳሴ ግድቡ ግንባታ ተጠናቆ ወደ ልማት ሲሸጋገርም የተፋሰሱን ሀገራት ተጎጂ የሚያደርግ ሳይሆን ለቀጣናዊ የጋራ ልማት በረከት በጋራ ለመልማት የሚያስችል እና የሁሉንም ተጠቃሚነት ባረጋገጠ መልኩ ነው:: ለእኛ ለኢትዮጵያውያን በአንድ የመቆምና በጋራ የመፈጸም ማሳያና የቁጭታችንም መገለጫ ነው::

በኲር የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

“ሁሉም ሙዚቃዎች በዘመናቸዉ ጥሩ ናቸው”የሐምሌ 14  ቀን 2017 ዓ.ም  ዕትምሙዚቃን አጥብቆ ይወዳል፤ ትውልድ እና እድገቱ  ባሕር ዳር ከተማ  ነው:: ማንኛውም ሰው ለሚወደው ሙያ እስትንፋ...
21/07/2025

“ሁሉም ሙዚቃዎች በዘመናቸዉ ጥሩ ናቸው”
የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

ሙዚቃን አጥብቆ ይወዳል፤ ትውልድ እና እድገቱ ባሕር ዳር ከተማ ነው:: ማንኛውም ሰው ለሚወደው ሙያ እስትንፋሱ እስኪወጣ መታገል እና መስዋዕት መክፈል አለበት ብሎ ያስባል፤ ሙዚቃ አቀናባሪዉ አበበ ኪሮስ:: የበኩር እንግዳ አድርገነዋል፤
መልካም ንባብ!

ትውልድና እድገትህ ምን ይመስላል?
ተወልጄ ያደኩት ባሕር ዳር ከተማ ነው:: የአንደኛ ደረጃ ትምህርቴን ከአንደኛ እስከ ስድስተኛ በጠይማ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት፣ ሰባት እና የስምንተኛ ክፍልን ደግሞ በቀድሞው በድልችቦ አንደኛ እና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ነው የተከታተልኩት:: ከዘጠነኛ እስከ 12ኛ ክፍል ደግሞ በግዮን ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ነው የተማርኩት:: ከ12ኛ ክፍል በኋላ በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ በማታው የትምህርት ክፍለ ጊዜ በጋዜጠኝነት (ጆርናሊዝም) በ10+3 ተምሪያለሁ:: “ጆርናሊዝምን’’ የመረጥኩት ጋዜጠኛ እሆናለሁ በሚል ሳይሆን በወቅቱ በዩኒቨርሲቲው ከሚሰጡ ትምህርቶች ለሙዚቃ ይቀርባል በሚል ነው:: ግን ወደ ሙያው አልገባሁም::

ወደ ሙዚቃው እንዴት ልትገባ ቻልክ?
ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሙዚቃው ዓለም እንድገባ ያደረገኝ ያኔ አንደኛ ደረጃ ተማሪ እያለሁ የሙዚቃ ትምህርት ራሱን ችሎ እንደ አንድ የትምህርት አይነት ይሰጥ ስለነበር ከሌሎቹ ትምርቶች የበለጠ ትኩረት እሰጠው ነበር:: ክፍለጊዜው ሲደርስም በጣም ደስ ይለኝ ነበር:: ከዚያም በ1989 ዓ.ም በባህልና ቱሪዝም አማካኝነት በአጼ ሠርጸ ድንግል ትምህርት ቤት በክረምት ወቅት ለሁለት ወራት ስለሙዚቃ ትምህርት እንደሚሰጥ ሰው ነገረኝ:: እኔም ጊዜ ሳላባክን ከሰልጣኞች አንዱ ሆንኩ:: በስልጠናውም ሙዚቃ ምን እንደሆነ ለመጀመሪያ ጊዜ ተረዳሁ:: ከዛ በፊት ከእኔ በዕድሜ ይበልጡ የነበሩ የሰፈር ልጆች ክራር ሲጫዎቱ ከስራቸው ቁጭ ብዬ እመለከት፤ አዳምጥም ነበር:: ከዛ ራሴ ከወዳደቁ ጣውላዎች ክራር አዘጋጅቼ እንደነገሩ አድርጌ መሞከር ጀመርኩ:: ያኔ ምንም አይነት እውቀት አልነበረኝም፤ ክራሩን ከማየት ውጪ በእጄ እንኳ ነክቼ አላውቅም ነበር:: እያንዳንዱ የክራር ክር ምን አይነት ድምጽ እንዳለው አላውቅም ነበር:: በስልጠናውም ሙዚቃ፣ ቅኝት፣ ኖታ እና ሪትም ምን እንደሆኑ ተረዳሁ:: የነበረኝ ልምድም በሥልጠናው ዳበረ ግንዛቤየም ሰፋ:: የተሻለ መሞከር ጀመርኩ:: ከዛ ፍላጎቴን የሚያውቅ አንድ የሠፈር ልጅ ጥራቱን የጠበቀ የራሱን ክራር በስጦታ ሰጠኝ:: ሌት ተቀን እያልኩ መለማመድ ጀመርኩ፤ በሂደትም ክራር መጫዎት ቻልኩ::

ሰርከስ አልማን እንዴት ነበር የተቀላቀልከው?
ያኔ ለሙዚቃ ስልጠናው ስንሄድ ሰርከስ አልማ ከሚሠሩ ልጆች ጋር እንገናኝ ነበር:: ልጆቹም ያለኝን ችሎታ በማየት ሰርከስ አልማ መግባት እንደምችል ነገሩኝ:: ከዚያም በ1994 ሰርከስ አልማ ገባሁ:: በወቅቱ አልማ የባህል ቡድን እንጅ ሰርከስ አልነበረውም:: ሰርከስ ትግራይ እና ሰርከስ ጅማ በወቅቱ በጣም ታዋቂ ነበሩ:: ከነሱ በማየት እኛም ተግባራዊ ማድረግ ጀመርን:: ሰርከሰኞች ሰርከሱን የሚያሳዩት በሙዚቃ በመታጀብ ነበር:: በሰርከሱም ለኪስ 120 ብር በወር እየተከፈለኝ ክራር መጫዎት ጀመርኩ::
አልማ እየሠራሁ ቤዝ የሚባል የሙዚቃ መሳሪያ የመጫዎት እድሉን አገኘሁ:: ቤዝ የጊታር አይነት ነው:: ድምጹ ለሙዚቃ መሠረታዊ የሚባል እና በጣም ወሳኝ ነው:: ከዚያም ክራር የሚጫዎት ሌላ ሰው ሲመጣ እኔ ወደ ቤዝ ጊታር ዞርኩ:: ልምድ የለኝም፤ ግን እጄ አያርፍም፤ መነካካት ስለምወድ ድምጹ ማረከኝ እና ወደ ቤዙ ተሳብኩ:: ባንዱን ሙሉ ለማድረግ እኔ ቤዙን ያዝኩ ሌላ ሰው ክራሩን ያዘ::

ሙዚቃ ማቀናበሩንስ እንዴት ለመድክ?
ትምህርቴን 1990 ዓ.ም ላይ አጠናቅቄ ሙሉ ስዓቴን ሙዚቃ ላይ ማዋል ጀመርኩ:: ኦሳ የሚባል ድርጅት በየቀበሌው ያቋቋመው የጸረ - ኤድስ ክበብ ነበር:: እኔም ቀበሌ 10 በሚገኘው እፀ-ሕይዎት የሚባል ክበብ ገባሁ:: ክበቡ በሙዚቃ ጭምር ነበር ለሕብረተሰቡ ግንዛቤ የሚፈጥረው እኔም ክራር እጫዎት ነበር:: ከጠዋት ጀምሮ እስከ 10 ስዓት ድረስ ልምምድ እናደርግ ነበር:: ከዚያም በ1996 ዓ.ም ኪቦርድ ለመጫዎት ሙከራ ማድረግ ጀመርኩ:: ኪቦርድ በባህሪው እንደሙሉ ባንድ አድርጎ ስለሚያጫውት ሌት ተቀን በራሴ ማንዋሉን በማንበብ ተለማምጄ መጫዎት ቻልኩኝ:: ክራሩንም ተውኩት:: ሙዚቃ ማቀነባበር የጀመርኩትም ያኔ ነው:: ከዚያም በ1998 ዓ.ም ሙሉዓለም የባሕል ማዕከል በባሕል መሳሪያ ተጫዋችነት ተወዳድሬ ተቀጠርኩ:: ኪቦርድ ብጫዎትም ብዙ የሚጎድለኝ ነገር ስለነበር ያን ጉድለቴን እስክሞላ ክራር ለመጫዎት በመወሰን ነበር በክራር ተጫዋችነት የተቀጠርኩት:: ሁለት ዓመት ክራር ከተጫዎትኩ በኋላ አሁንም የሙዚቃ መሳሪያ ሳይ መነካካት ስለምወድ የተቀመጠ ኪቦርድ ነበር እሱን መጫዎት ጀመርኩ፤ በባህል ማዕከሉ የሚሠሩ መዝሙሮች ሲኖሩም በኪቦርዱ እቀርጽ ነበር:: ምድቤ ግን የባህል መሳሪያ መጫዎት ነበር:: ይህን ማደርገው ፍላጎት ስላለኝ ነው:: 2000 ዓ.ም አካባቢ ሚሊኒዬም ባንድ የሚባል ዘመናዊ ባንድ ተቋቁሞ ነበር:: ከዚያም ባንዱ ሙሉ በሙሉ ወደ ሙሉዓለም የባህል ማዕከል ሲጠቃለል ወደዛው ገባሁ:: በ2010 ዓ.ም የሲቪል ሰርቪስ መዋቅር ሲመጣም ኪቦርድ ተጫዋች ሆንኩ::
ለመጀመሪያ ጊዜ ስቱዲዮ ኮምፒዩተር ያየሁት በለጠ የሚባል ልጅ ከአዲስ አበባ መጥቶ ሙሉዓለም ሲቀጠር ‘መሳሪያው አለኝ፤ ለምን አብረን አንሠራም’ ሲለኝ ተስማምቼ አብሬው መሥራት ስጀምር ነው:: ለመጀመሪያ ጊዜ ኪቦርድ ላይ የምቀርጸው ሙዚቃ እንዴት ኮምፒዩተር ላይ እንደሚቀረጽ አወቅኹኝ:: የባህል ማዕከሉ የሚሠራቸውን ሕብረ ዝማሬዎች ማቀናበር ጀመርኩ:: በተለይም የኮረና ሕብረ ዝማሬን አቀናብሬያለሁ:: የኦሮሚኛ የዘይኑ ሙሃባውን ስለኮሮና የታጫዎተውን፣ የመለሰ ካሳሁንን፡- ናፈቀኝ ሀገሬን፣ ያኢስ ራያ፣ አጄልጂል፣ ሰንደልዬን፤ የአበበ ሰማኸኝን ሰናድሬ፣ የገብርየን ቢተው አደቡን ላስገዛው፤ የአሸናፊ ተክለኃይማኖትን አቻም የለሽ የሚለውን፣ የሙሉዓለም የባሕል ማዕከሉ ድምጻዊያን ያወጡት የጋራ አልበም ውስጥ ጎንደርኛውን አቀናብሬያለሁ:: እንዲሁም ጎጃምኛውንም በጋራ ሠርተናል:: ሌሎች ስማቸውን በደንብ ማስታወስ አልቻልኩም እንጂ የበርካታ ጀማሪ ድምጻዊያንን ሙዚቃ አቀናብሬያለሁ::

ሙዚቃ ከማቀናበር በተጨማሪ ሌላ የምትሞክረው ችሎታህ ምንድን ነው ?
አሁን ከሙዚቃ በተጨማሪም ዜማ መስጠት ለምጃለሁ:: ዜማ መሥራት የጀመርኩት ከሙዚቃ ማቀናበር በመጣ ልምድ ነው:: ድምጻዊያን ሙዚቃ ቀርጸው ሲመጡ ያኔ ዜማውን አስተካክላለሁ:: የት ላይ ቢስተካከል ቆንጆ እንደሚሆን አቀናባሪው ያውቀዋል:: ሙዚቃው ለጆሮዬ ካልጣመኝ ላቀናብረው አልችልም:: ስለዚህ ያን ዜማ አስተካክላለሁ:: ለመጀመሪያም ጊዜ የጎጃምኛ ዜማ ሰርቼ ቢያድጌ ለሚባል ጀማሪ ሙዚቀኛ ሰጥቻለሁ:: የሙዚቃ መሳሪያ በመነካካት ዜማ ይመጣልኛል::

ሙዚቃ ከባድ ነው ወይስ ቀላል? ለማቀናበርስ የትኛውን ሰዓት ትመርጣለህ?
ሙዚቃ ከባድ ነው:: የአምስት ደቂቃ ሙዚቃ ለመሥራት የረጅም ጊዜ ድካም እና ልፋት ይጠይቃል:: ሪኮርዲንግ (ቀረጻ) አለ፤ ስልተምት አለ፤ የሚያስፈልጉ ድምጾች አሉ፤ ድምጻዊው ጋር ይሄዳል ወይስ አይሄድም የሚለውን ማረጋገጥ አለ:: ሙዚቃ ሰውን የማሳመን ሥራ በመሆኑ ከባድ ነው ብዬ ነው የማስበው:: ሙዚቃ የማቀናብረው በማንኛውም ጊዜ ነው:: በምሽትም በሌሊትም ሊሆን ይችላል:: ጊዜ አይገድበኝም::

“የኢትዮጵያ ሙዘቃ ድሮ ቀረ” የሚሉ አሉ፤ ይህን እንዴት ታየዋለህ?
የሀገራችን ሙዚቃ ሁሉም በዘመኑ ልክ ነው ብዬ ነው የማስበው:: የድሮዎቹ ዘመን አይሽሬ ናቸው በሚለው ብስማማም አሁንም ዘመን አይሽሬ ሙዚቃዎች አሉ የሚል እምነት አለኝ:: በድሮው ዘመን በራሱ ቆንጆ ሙዚቀኛ አለ፤ ቆንጆ ያልሆነም አለ:: በአሁኑ ጊዜ ደግሞ ጥሩ ጥሩ ዜማና ግጥም ቅንብር ያላቸው ሙዚቃዎችና ድምጻዊያን አሉ:: እንደዚሁ ጥሩ ድምጽ የሌላቸው ግጥሙ እዚህ ግባ የማይባል፣ ቅንብሩም እንደዚሁ ጥሩ ያልሆነ ሙዚቃ አለ:: ሁለቱም በየራሳቸው ዘመን መጥፎም ጥሩም ጎን አላቸው ብዬ ነው የምፈርጃቸው::

በአሁኑ ዘመን ድምጻዊያን የሚያሰሙን በኮምፒዩተር የታገዘ ተፈጥሯዊ ያልሆነ ድምጽ ነው፤ ይህን እንዴት ታየዋለህ?
ይህ ቴክኖሎጂ ወደኛ ሀገር የገባው በቅርብ ጊዜ በመሆኑ እንጅ በውጪው ዓለም የተለመደ ነው:: የሰው ልጅ ሙሉ በሙሉ ትክክል አይደለም:: ኮምፒዩተር በመኖሩ የሙዚቃውን ደረጃ እንዲጠብቅ ያደርገዋል እንጅ እየጎዳው አይደለም ብዬ ነው የማስበው:: በእርግጥ ማንኛውም ሰው በኮምፒዩተር በመታገዝ ሊዘፍን ይችላል:: ነገር ግን ስሜት አልባ ነው የሚሆነው:: ለአድማጭ ጆሮ ተስማሚ አይሆንም:: ቅንብሩ ብዙ የአርትኦት ሥራ (ኤዲቲንግ) ስለሚኖረው ስሜት አይሰጥም እንጅ መዝፈን ይችላል:: ሙዚቃ ስሜት የሚሰጥ መሆን አለበት:: አንዳንድ የድሮ ሙዚቃዎች ከእንደገና በዘመናዊ መንገድ ቢሠሩ ብለን የምናስባቸው አሉ:: እንደ ባለሙያ ስናገር ፈርሰው እንደገና ቢቀናበሩ ተብለው የሚፈረጁ አሉ:: ያኔ ከነ ጉድለታቸው የወጡት ቴክኖሎጂው ስለሌለ ነው ብዬ ነው የማስበው::
ከዛ ይልቅ የአሁኑ ጊዜ ሙዚቃዎች ቶሎ የሚሰለቹት የአብዛኛዎቹ ግጥምና ዜማዎች ጥልቅ መልዕክት ማስተላለፍ ስለማይችሉ ነው:: ግጥሞቹና ዜማዎቹ ለባለሙያው ስላልተሰጡ ነው:: ሙዚቃ በተፈጥሮ የሚሰጥ ችሎታ ነው:: ብዬ ነው የማስበው:: እናም ችሎታ ያላቸው ሰዎች ግጥሙንና ዜማውን ቢሠሩት መልካም ነው:: ይሁንና አሁን ላይ ጀማሪ ድምጻዊያን የግጥም እና የዜማ ተሰጥኦ ያላቸውን ሰዎች ከፍለው ለማሠራት ከፍተኛ ገንዘብ ስለሚጠይቋቸው እነሱን ማሠራት አይችሉም:: በዚህ ምክንያት ራሳቸው ግጥሙንም ዜማውንም ለመሥራት ይገደዳሉ:: በጀማሪ ገጣሚም ስለሚጠቀሙ ዘፈኑ ያን ያህል ሳቢ እና ማራኪ ሳይሆን ይቀራል:: እኔ በዚህ ጉዳይ የምመክረው ድምጻዊያን የግጥም እና የዜማ ችሎታ ከሌላቸው በዘርፉ ችሎታ ላላቸው ባለሙያዎች ግጥሙንና ዜማውን ቢተውሏቸው መልካም ነው:: በእርግጥ ለታዋቂ የሙዚቃ ግጥም ደራሲ እና የዜማ ባለሙያ እንዲሳተፉ ማድረግ ከባድ ነው:: ክፍያው በጀማሪ የማይታሰብ ነው:: አሁን ላይ ከ30ሺህ እስከ አንድ መቶ ሺህ ይጠየቃሉ::

የሀገራችንን አንድነትና ሰላም እንዲጎለብት የሚያደርጉ ሙዚቃዎች በበቂ ሁኔታ ተሰርተዋል ብለህ ታስባለህ?
ሙዚቃ በባሕሪው የራሱ የሆነ ነጻነትን የሚጠይቅና የሚፈልግ ሙያ ነው:: ነገን የሚያሳይ መሆን አለበት:: እንዳለመታደል ሆኖ በኛ ሀገር ይህ ሁኔታ አልተለመደም:: ሙዚቃችን ሕጸጽ አዉጪ ቢሆን ኖሮ ነጋችንን ለማስተካከል ይረዳን ነበር:: ሕዝብንም መንግሥትንም የሚያስተምር መሆን ነበረበት:: ነገር ግን ያ አልሆነም፤ ለዚህ አልታደልንም:: ሰላምን የሚሰብኩ ሙዚቃዎች በበቂ ሁኔታ አልተሠሩም ብዬ ነው የማስበው:: ምክንያቱም አድማጭ የላቸውም:: ስለፍቅር (የወንድ እና የሴት) እና የሰላም ሙዚቃ አንድ ላይ ቢወጡ ገዥ የሚኖረው ስለፍቅር የተዜመው ነው:: ለአብነትም ከሰሞኑ ስለ ሰላም የተቀነቀነ ያቀናበርኩት ሙዚቃ ነበር:: ሆኖም እስካሁን ስፖንሰር የሚያደርገው አልተገኘም:: ስለዚህ ገዥ ከሌለው ትርፉ ድካም ነው:: ሆኖም በዚህ ጉዳይ የሚመለከተው አካል እና ሕብረተሰቡም ቢሆን ትኩረት ሊሰጠው ይገባል::

የኢትዮጵያ ሙዚቃ አሁን ባለበት ደረጃ አድጓል ብለህ ታስባለህ?
ሙዚቃችን አድጓል ብዬ መናገር አልችልም:: ምክንያቱም የሀገራችን ሙዚቃ ዘርፈ ብዙ ችግር አለበት ብዬ ነው የማስበው:: ሙያተኛው በተፈጥሮ በተቸረው ችሎታ ተገፋፍቶ ይመጣል እንጅ በትምህርት ታግዞ ያመጣው ነገር የለም:: ከፍተኛ የትምህርት ተቋሞቻችን በቂ የሙዚቃ ማስተማሪያ የትምህርት ክፍሎች (ዲፓርትመንቶች) የሏቸውም:: ይህ ባለመሆኑ ሙዚቃው ላይ ተጽእኖ እየፈጠረ ነው:: ጥራት የሌላቸው የሙዚቃ መሳሪያዎች ናቸው ያሉን:: ሌላው የቅጂ መብት (የኮፒ ራይት) ችግር ነው:: አንድ ሰው ሙዚቃ ሢሰራ ጊዜውን፣ ገንዘቡን አዕምሮውን ተጠቅሞ ነው የሚሠራው:: ታዲያ ይህን ሁሉ ነገር መሰዋዕት ከፍሎ ተጠቃሚ አይደለም:: ገቢው እዚህ ግባ የሚባል አይደለም:: በተቃራኒው የመገናኛ ብዙኃን፣ ሆቴሎች እና ሌሎች ሙዚቃዎችን የሚጠቀሙ አትራፊ ናቸው:: እነዚህ ተቋማት ተገቢውን ክፍያ ለሙያተኛው ቢከፍሉ ዘርፉ ያድግ ነበር፤ ሙያተኛውም ተጠቃሚ ይሆን ነበር::

በሙዚቃ ሥራ የት ቦታ ሂደህ ታውቃለህ?
ከሀገር ውጪ የሙዚቃ መሳሪያ ለመጫዎት ሱዳን ካርቱም ሄጃለሁ:: የክልሉን ከተሞች አዳርሻለሁ:: ከክልሉ ውጭ ደግሞ አዋሳ፣ አዲስ አበባ፣ መቀሌ የመሄድ እድሉ አጋጥሞኛል:: በዚህም ሙዚቃ ቋንቋ ነው የሚለውን አረጋግጫለሁ::

በሙዚቃ ማቀናበር ሥራህ ችግር አጋጥሞህ ያውቃል?
እኔ ሙዚቃ ሳቀናብር በቂ ክፍያ አላገኝም:: እንደ ድካሜ አይደለም የሚከፈለኝ:: ሆኖም ፍላጎት ስላለኝ ወደ እኔ የሚመጡ ድምጻዊያን ያላቸውን የመክፈል አቅም ግምት ውስጥ በማስገባት እሠራለሁ:: በሙዚቃ ሕይዎቴ ከባድ ችግር ወይም ሥራየን የሚፈትን ነገር አጋጥሞኝ አያውቅም:: ሆኖም እንደ ችግር ከተቆጠረ ድምጻዊያን ከእኔ ጋር ለማቀናበር ሲመጡ በመጀመሪያ ግማሽ ክፍያ (ቀሪውን) ተቀብዬ ነው የማቀናብርላቸው:: ሙዚቃው ካለቀ በኋላ ደግሞ ግማሹን ክፍያ ያልከፈሉኝ ድምጻዊያን አሉ:: ሆኖም ሙያውን ስለምወደው አሁንም አከፋፈሉን አላስተካከልኩትም:: ማንኛውም ሰው ለሚወደው ሙያ እስትንፋሱ እስኪወጣ መታገል እና መስዋዕት መክፈል አለበት ብዬ የማምን ሰው ነኝ:: ለአንዳንድ ሰዎች የምትወዱትን ሥራ ሥሩ:: ያኔ ችግር ወይም ፈተና ቢያጋጥማችሁ አንኳ በቀላሉ ታልፉታላችሁ፤ እንደፈተናም አትቆጥሩትም ማለት እወዳለሁ::

ለነበረን ቆይታ አመሰግናለሁ!
እኔም ለተሰጠኝ ዕድል አመሰግናለሁ!፡፡

(ሳባ ሙሉጌታ)
በኲር የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

21/07/2025

የሰብአዊ መብቶች ፎረም ተመሠረተ
የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ክልል የሰብአዊ መብቶች ፎረም ተመሥርቷል። ፎረሙ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤትን፣ ፍትሕ ቢሮን፣ የክልሉ ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያን፣ ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽንን፣ የሃይማኖት ተቋማትን እና ልዩ ልዩ የኅብረተሰብ ክፍሎችን ያካተተ ነው።

በፎረሙ ምሥረታ የተገኙት የአማራ ክልል ፍትሕ ቢሮ ኀላፊ ብርሃኑ ጎሽም እንዳሉት ሰብዓዊ መብቶች ከሰው ልጅ ተፈጥሮ የሚመነጩ፣ የማይጣሱ እና የማይገፈፉ በመኾናቸው ሊጠበቁ ይገባል።
መሠረታዊ መብቶችን ለማክበር እና ለማስከበር ደግሞ ዓለም አቀፍ ሥምምነቶች በሀገሪቱ ሕግ ተካትተው እየተሠራ ይገኛል። ይሁን እንጂ በክልሉ በተፈጠረው ግጭት የዜጎች ሰብአዊ መብቶች ጥሰት ማጋጠሙን አንስተዋል።

ለዚህ ደግሞ በጸጥታ፣ በፍርድ ቤት እና በፍትሕ ተቋማት እና በሰብዓዊ መብቶች ላይ የሚሠሩ አካላት በተናበበ እና በተቀናጀ መንገድ ባለመሥራት የተፈጠረ መኾኑን ገልጸዋል። ችግሩን ለመፍታት የሰብዓዊ መብት ፎረም ማቋቋም ማስፈለጉን ገልጸዋል። ፎረሙ የፍትሕ ተቋማት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በተቀናጀ መንገድ ሰብዓዊ መብቶችን አክብረው እንዲያስከብሩ አቅም እንደሚኾን ገልጸዋል።

የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት ሙሉዓለም ቢያዝን የሰብዓዊ መብቶች ጥበቃ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ውሳኔዎች እና በሀገራት ሥምምነቶች መሰረት ጥበቃ የተደረገላቸው መኾናቸውን ገልጸዋል። በኢትዮጵያም በ1987 ዓ.ም በጸደቀው የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት ልዩ ጥበቃ እንደተደረገለት አንስተዋል። ሕግ አውጭው፣ ሕግ አስፈፃሚው እና ሕግ ተርጓሚው ሰብዓዊ መብቶችን የማክበር እና የማስከበር ኀላፊነታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል። ሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶችም የራሳቸውን ሚና እንዲወጡ ጠይቀዋል።
በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ባሕር ዳር ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኀላፊ ፊቶል ሲያኮር በአማራ ክልል በተቀሰቀሰው ግጭት ሰብዓዊ እና ቁሳዊ ጉዳት፣ መፈናቀል እና የንብረት ውድመት መድረሱን አንስተዋል።

አሁንም ንጹሐን ሰዎች ችግር ውስጥ መኾናቸውን ገልጸዋል። የታጠቁ ኀይሎች የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምክክር ኮሚሽን የጀመረውን የሰላም ጥረት ተቀብለው በሰላማዊ መንገድ ችግሮቻቸውን እንዲፈቱ ጠይቀዋል።
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንም በክልሉ ብሎም በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ለመደገፍ ቁርጠኛ መኾኑን ገልጸዋል።

የሰብአዊ መብቶች ፎረም መቋቋሙ መንግሥታዊ እና መንግሥታዊ ያልኾኑ ድርጅቶች በሰብዓዊ መብት ጉዳዮች ላይ በትብብር እንዲሠሩ አቅም እንደሚኾን ተናግረዋል።
የሰብዓዊ መብቶች ፎረም ገንቢ ውይይቶችን ለማመቻቸት፣ ተጠያቂነትን ለማስፈን እና የሰብዓዊ መብቶችን ዘላቂነት ለማረጋገጥ እንደሚያገለግል ተገልጿል።

(ዳግማዊ ተሰራ)
በኲር የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

የተጠናቀቁ ፕሮጀክቶች ወደ ማልማት ተሸጋግረዋል ተባለየሐምሌ 14  ቀን 2017 ዓ.ም ዕትምበ2017 በጀት ዓመት በ815 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነቡት 16 የመስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ወደ ልማት ...
21/07/2025

የተጠናቀቁ ፕሮጀክቶች ወደ ማልማት ተሸጋግረዋል ተባለ
የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

በ2017 በጀት ዓመት በ815 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነቡት 16 የመስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ወደ ልማት መሸጋገራቸውን የሰሜን ሸዋ ዞን መስኖ እና ቆላማ አካባቢዎች ልማት መምሪያ አስታወቀ።
የመምሪያው ኃላፊ ችሮታው አስፋው ለአገልግሎት የበቁት የመስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ለዘመናት የመልካም አሥተዳደር ችግር ሲነሳባቸው የነበሩ ናቸው፡፡ ፕሮጀክቶቹ ከአራት ሺህ 200 ሄክታር በላይ መሬት ማልማት የሚችሉ መሆናቸውንም ጠቁመዋል፡፡ ፕሮጀክቶቹ ከስምንት ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ያደርጋሉ ብለዋል፡፡

ከ16ቱ የመስኖ ፕሮጀክቶች በተጨማሪ 63 አነስተኛ ጉድጓዶችም ተዘጋጅተዋል፡፡ እነዚህም ከ240 ሄክታር በላይ መሬት ማልማት የሚያስችሉ ናቸው ተብሏል፡፡
በበጀት ዓመቱ በአጭር ጊዜ ፕሮጀክቶችን ገንብቶ መጨረስ ላይ የተሠራው ሥራ ተሞክሮ ሊወሰድበት የሚገባ ተግባር መሆኑንም ጠቅሰዋል።

በዓመቱ በተከናወኑ የመስኖ አውታር ግንባታዎች ከዘጠኝ ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች በጊዜያዊ እና በቋሚነት የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉንም መምሪያ ኃላፊው ተናግረዋል።
ግንባታዎቹ ከዘላቂ ልማት ግብ፣ ከምግብ ማጠናከሪያ ሥርዓት መርሐ ግብር፣ ከሰቆጣ ቃልኪዳን እና ከሴፍቲኔት በተገኙ የገንዘብ አማራጮች የተሠሩ ናቸው።
ከሰቆጣ ቃል ኪዳን በተገኘ ድጋፍ በዞኑ ለሰባት የመስኖ ካናሎች (ግድቦች) ጥገና መደረጉንም አቶ ችሮታው ገልጸዋል።
መምሪያው በ2018 በጀት ዓመት 151 ፕሮጀክቶችን ለመገንባት የሚያስችል የፕሮጀክት ጥናት እና ዲዛይን ሥራ አጠናቅቆ በጀት በማፈላለግ ላይ ይገኛል።።

(ገንዘብ ታደሰ)
በኲር የሐምሌ 7 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

ለሰላም ግንባታ ከቤት ጀምሮ መሥራት ይፈልጋል ተባለየሐምሌ 14  ቀን 2017 ዓ.ም ዕትምየሰላም ግንባታ ሁሉም ሰው ከቤቱ፣ ከየእምነት ተቋሙ ሠርቶ ወደ ሀገር የሚያሳድገው ነው፤ በመሆኑም የእ...
21/07/2025

ለሰላም ግንባታ ከቤት ጀምሮ መሥራት ይፈልጋል ተባለ
የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
የሰላም ግንባታ ሁሉም ሰው ከቤቱ፣ ከየእምነት ተቋሙ ሠርቶ ወደ ሀገር የሚያሳድገው ነው፤ በመሆኑም የእምነት ተቋማት ይህን መሠረት በማድረግ ለሰላም መሥፈን በትኩረት መሥራታቸውን እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል::

የኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን መከላከል ላይ ያተኮረ ውይይት ከሚለከታቸው አካላት ጋር አካሂዷል፤ የኢትዮጵያ ኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ የሴቶች ህፃናት እና ወጣቶች መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ ጥሩወርቅ ገና ከተለያየ ቤተ ዕምነት የተሰባሰቡ ተወካዮች ሰላምን በማስፈን የዘመኑ ባለ አደራ እንደሆኑ ነው የገለፁት::
ሰላም እንዲሰፍን መፍትሔው እና ውጤቱ ከኃይማኖት አባቶች ይገኛል ያሉት ወ/ሮ ጥሩወርቅ ለሰላም ግንባታ ከቤት ጀምሮ መሥራት እንደሚገባ ጠቁመዋል፤ ሰላም ከቤት ሲሰፍን ወደ ጎረቤት፣ ወደ አካባቢ እየተሸጋገረ ሰላም ይጸናል ብለዋል:: ለዚህ ሁሉ መፍትሔው እና ውጤት ደግሞ ከዕምነት ተቋማት እንደሚመጣ ነው ያነሱት::

በኢትዮጵያ ኦርዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የባሕር ዳር እና አካባቢው ሃገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መላከ ሰላም ፍሰሃ ጥላሁን የኃይማኖት አባቶች የመጀመሪያ ድርሻ ለአምላካቸው ሰላም እንዲመጣ መፀለይ መሆኑን በመጠቆም ቀጥሎ ደግሞ ከመንግሥትም ይሁን ከሌላው ባለድርሻ ጋር ሰላም እንዲመጣ ማስተማር እና የማቀራረብ ሥራ ይሠራል ብለዋል::

የአማራ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት የትምህርት እና ዳዕዋ ዘርፍ ኃላፊ ሼህ ሙሐመድ ኢብራሂም ሰላም ከቤት ጀምሮ ሲወራ ሰው ሰላም ወደ ማሰብ ይመጣል ነው ያሉት፤ ሕብረተሰቡም የኃይማኖት አባቶቹን ማዳመጥ እንደሚገባው ነው የተናገሩት::

(ማራኪ ሰውነት)
በኲር የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp://

በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን በየሳምንቱ የሚታተም የሰኞ ጋዜጣ በሳምንት አንድ ጊዜ ከ9500 በላይ ቅጅዎች በማተምና በማሰራጨት፣ ለአንባቢያን የክልሉን ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ምጣኔ ሀብታዊ .....

ሕዳሴ ግድብ - የአንድነት እና የይቻላል መንፈስ ማሳያየሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም  ዕትምዓባይ የኢትዮጵያ መታወቂያ ከሆኑ በርካታ ሐብቶች መካከል አንዱ ቢሆንም ባለፉ ዘመናት ለኢትየጵያውያ...
21/07/2025

ሕዳሴ ግድብ - የአንድነት እና የይቻላል መንፈስ ማሳያ
የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

ዓባይ የኢትዮጵያ መታወቂያ ከሆኑ በርካታ ሐብቶች መካከል አንዱ ቢሆንም ባለፉ ዘመናት ለኢትየጵያውያን ያበረከተው ጥቅም እንደ ግዝፈቱና ታላቅነቱ አልነበረም::
ለዚህ ግብሩ ደግሞ “ዓባይ ማደሪያ የለው ግንድ ይዞ ይዞራል” የሚለው የሀገሬው አባባል ምስክር ነው:: ዓባይ ከመነሻው ሰከላ ጀምሮ ለም አፈርን፣ በውድ ከውጭ ተገዝቶ ለሰብል ማፋፊያ አፈር ጋር የተቀላቀለን ማዳበሪያ እና ሌሎችንም ምጣኔ ሐብታዊ ዕድገትን ዕውን ሊያደርጉ የሚችሉ ግብዓቶችን ሁሉ ጠራርጎ ለሱዳን፣ ግብጽ እና ለሌሎች የተፋሰሱ ሀገራት ሲያድል ለመኖሩም ማረጋገጫ ነው::

ኢትዮጵያን እንዲያለማ በነገሥታቱ ተጀምሮ የነበረውን ውጥን ዕውን ለማድረግ የሚያስችል ዓባይን ለኤሌክትሪክ ኅይል የመገደብ የመሠረት ድንጋይ መጋቢት 24 ቀን 2003 ዓ.ም በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ጉባ ወረዳ በቀድሞው የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚንሥትር መለስ ዜናዊ በይፋ ተቀመጠ:: 80 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውኃን ይዞ ከሀገር ውጭ ሱዳንን እና ግብጽን ሲያለማ ለኖረው ዓባይ ወንዝ የግድብ ግንባታ ዕውን መሆን ከሕጻን እስከ አዋቂ፣ ከተማሪ እስከ ምሁር፣ ከአርሶ አደር እስከ ወታደር… ሁሉም በቻለው ለማበርከት ቃል ገባ፤ በቦንድ ግዥ፣ በልገሳ እና በሌሎች የክፍያ አማራጮች አጋርነቱን በተግባር አረጋገጠ::

ተስፋን በጽናት
የባሕር ዳር ከተማ ነዋሪው እና ጡረተኛው አቶ ፋንታ መስተሳህል መፍለቂያውን ሳይጠቅም ግብጽ እና ሱዳንን ለዘመናት ሲያለማ ማየታቸው እጅጉን ሲያስቆጫቸው የቆየ ጉዳይ እንደሆነ ተናግረዋል:: እነዚህ ሀገራት ደግሞ ከኢትዮጵያ መልማት በተቃራኒ የቆሙ ናቸው::
በዓባይ ወንዝ ላይ ግድብ ሊገነባ መሆኑን በ2003 ዓ.ም ሲሰሙ የዓመታት ቁጭታቸው ማክሰሚያ እንደሚሆን ተማመኑ:: ከቁጭትም ባለፈ ግድቡ በኤሌክትሪክ የኀይል ምንጭነት እንደሚያገለግል በወቅቱ መስማታቸው የኀይል እጥረቱን እና መቆራረጡን ለመፍታት ሚናው ከፍተኛ እንደሚሆን አመኑ::
ግድቡ ሊያሳካው የሚችለውን ዓላማ ከዳር ለማድረስም መንግሥት ከሚያወጣው ወጪ በተጨማሪ ግድቡ ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ አቅማቸው በፈቀደ መጠን ሁሉ ድጋፍ ለማድረግ ወሰኑ:: ግድቡ በአምስት ዓመታት ጊዜ ውስጥ እንደሚጠናቀቅ ሲነገር በወቅቱ በየዓመቱ ሳያቋርጡ ድጋፍ ለማድረግ ለራሳቸው ቃል ገቡ:: አቶ ፋንታ ቃላቸውን አክብረው ድጋፋቸውን ጀመሩ::
አቶ ፋንታ ግድቡ ተጨማሪ ዘጠኝ ዓመታት ቢጠይቅም ድጋፋቸውን ከመቀጠል ወደ ኋላ አላሉም፤ ተስፋቸው አልመከነም:: በ14 ዓመታት የግንባታ ጊዜ ውስጥም የ168 ሺህ ብር ቦንድ እንደገዙ ከአሚኮ ጋር በነበራቸው ቆይታ ተናግረዋል::

“የእኛ በጨለማ መኖር የሚያበቃው፣ በልቶ ለማደር ስጋት የማይሆነው ዓባይ ሲገደብ ነው” የሚለው የአቶ ፋንታ ቁጭት በመስከረም ወር 2018 ዓ.ም ፍጻሜውን አግኝቶ ይመረቃል:: ግድቡ አሁን ካለበት የፍጻሜ ደረጃ ላይ የደረሰው በውጭ ኀይሎች የተሰነዘረውን ዲፕሎማሲያዊ ጫና በጽናት በማክሸፍ እና በሕዝቡ የነቃ ተሳትፎ እንደሆነ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት መረጃ ያመላክታል::
ግንባታው ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ሕዝቡ ከ23 ቢሊዮን ብር በላይ ድጋፍ ማድረጉም ተመላክቷል:: ይህ ሐብት የተሰበሰበው በቦንድ ሽያጭ እና ስጦታ፣ በ8100 አጭር የጽሑፍ መልዕክት እና ከውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን /ከዳያስፖራዎች/ ነው::
አርሶ አደሩ እና አርብቶ አደሩም ሕዳሴን በደለል ከመሞላት ለመታደግ ባከናወነው የተፋሰስ ሥራ ከ120 ቢሊዮን ብር በላይ የጉልበት አስተዋጽኦ ማድረጉን የግብርና ሚኒሥቴር መረጃ ያሳያል::
የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ እውን መሆን የመንግሥት ቁርጠኝነት፣ የሕዝብ ተሳትፎ እና የጠንካራ ዲፕሎማሲ ጥረት ውጤት መሆኑን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ምሁር እና የሕዳሴ ግድብ ተደራዳሪው ፕሮፌሰር ያዕቆብ አርሳኖ ሀገራዊ እና አህጉራዊ ጉዳዮች ላይ ባተኮረ የፓርላማ የዜጎች ፎረም ላይ አስታውቀዋል::

የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ግዙፍነት ማሳያዎች
ዓለም ካላት ግዙፍ የኤሌክትሪክ ኅይል ማመንጫ ግድቦች መካከል አንዱ የሆነው የኢትጵያ ታላቁ ሕዳሴ ግድብ 145 ሜትር ከፍታ እና አንድ ነጥብ ስምንት ኪሎ ሜትር ርዝመት አለው:: ከማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤቱ የተገኘው መረጃ እንደሚጠቁመዉ የዋናው ግድብ ውፍረት ግርጌው ላይ 130 ሜትር፣ የግድቡ ጫፍ ወይም የላይኛው ክፍል 11 ሜትር፣ የሚሸፍነው ቦታ አንድ ሺህ 680 ስኩዌር ኪሎ ሜትር ነው:: የግድቡ ውኃ የመያዝ አቅምም 74 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ነው:: ይህም በሀገሪቱ ግዙፉ የሰው ሠራሽ ኃይቅ ያደርገዋል:: በዚህም የተነሳ በሐይቁ ላይ 78 ደሴቶች ይፈጠራሉ::
የኢትዮጵያዉያን የአንድነት እና የይቻላል መንፈስ ማሳያ የሆነው ግድቡ አሁን ላይ ኀይል በማመንጨት እና የአሣ ምርት መገኛ በመሆን እያሳየ ይገኛል:: ግድቡ በዓመት ከ10 እስከ 15 ሺህ ቶን አሣ ማምረት ያስችላል ተብሎ ይታመናል:: በ2017 በጀት ዓመት ብቻ አምስት ሺህ 895 ቶን የዓሣ ምርት ተገኝቷል:: በስምንት ወራት ውስጥም የተገኘው ገቢ ከአንድ ነጥብ አራት ቢሊዮን ብር በላይ እንደሆነ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት መረጃ ያረጋግጣል::

ግድቡ በአሁኑ ወቅት በስድስት ዩኒቶች ኀይል እያመነጨ እንደሚገኝም መረጃው ያክላል:: ሁለቱ እያንዳንዳቸው በሙሉ አቅማቸው 375 ሜጋ ዋት ኀይል፤ ቀሪዎቹ አራቱ ዩኒቶች ደግሞ 400 ሜጋ ዋት ኀይል የማመንጨት አቅም እንዳላቸው አስታውቀዋል::
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የኤሌክትሪክ ኀይልን በማመንጨት ከአፍሪካ ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛል:: የሀገር ውስጥ የኤሌክትሪክ ሽፋንን 75 በመቶ ያሳድጋል:: የሕዳሴ ግድቡ አምስት ሺህ 150 ሜጋ ዋት ኀይል ያመነጫል ተብሎም ይጠበቃል::
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኅይል በ2016 ዓ.ም እንዳስታወቀው ባለፉት ዓመታት ሀገሪቱ ከምታመነጨው ኀይል እስከ 13 በመቶ የሚሆነውን ወደ ሱዳን፣ ጅቡቲ እና ኬንያ በሽያጭ በማቅረብ በዓመት 100 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ተገኝቷል:: ወደ ፊትም ዓመታዊ የኅይል ሽያጭ ገቢው አንድ ነጥብ አምስት ቢሊዮን ዶላር እንደሚሆን ተገልጿል::

ሕዳሴ በመጭው መስከረም
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 4ኛ ዓመት፣ 42ኛ መደበኛ ስብሰባውን ባካሄደበት እና የ2017 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸሙን በገመገመበት ወቅት ጠቅላይ ሚንሥትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) የሕዳሴን ግድብን አስመልክቶ ለተነሳላቸው ጥያቄዎች ምላሽ እና ማብራሪያ ሰጥተዋል:: የሕዳሴ ግድብ ተጠናቆ በመጭው መስከረም በድምቀት ለማስመረቅ ዝግጅት መደረጉን አስታውቀዋል:: የህዳሴ ግንባታ ተጠናቆ ወደ ልማት መሸጋገሩም የተፋሰሱን ሀገራት ተጎጂ የሚያደርግ ሳይሆን ለቀጣናዊ የጋራ ልማት በረከት እንደሚሆን አረጋግጠዋል::
ጠቅላይ ሚኒሥትሩ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሱዳን እና ግብጽን ጨምሮ በሌሎች የተፋሰሱ ሀገራት ላይ ጉዳት እንደማያመጣባቸው በጊቤ ሦስት የኀይል ማመንጫ ግድብ ግንባታ ላይ ተነስቶ የነበረውን ውዝግብ በማሳያነት አንስተዋል:: በወቅቱ ኢትዮጵያ የምታከናውነው የኅይል ማመንጫ ግድብ የኬንያውን ቱርካና ሀይቅ ሊያደርቀው ይችላል የሚል ስጋት ተነስቶ እንደነበር አስታውሰዋል:: ጊቤ ሦስት ተጠናቆም ግን የቱርካና ሀይቅ ሞልቶ ፈተና መሆኑን የጠቆሙት ጠቅላይ ሚንሥትሩ፤ ሕዳሴም ለግብጽም ሆነ ለሌሎች የተፋሰሱ ሀገራት በረከት እንጂ ስጋትን ይዞባቸው እንደማይመጣ አስታውቀዋል::
“የግብጹ አስዋን ግድብ ሕዳሴ በመገደቡ ብቻ አንድ ሊትር ውኃ አልቀነሰም፤ ወደ ፊትም ኢትዮጵያ እስከበለጸገች እና እስካለች ድረስ የግብጽ ወገኖቻችንን ጉዳት እኛ አናይም:: ፍላጎታችን ተባብሮ በጋራ ማደግ ነው:: ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ልማት ልማታችሁ ነው፤ የሚመነጨውም ኀይል ሁሉንም ጎረቤት ሀገራት የሚያዳርስ ነው” ሲሉ የተፋሰሱ ሀገራት የጋራ ልማትን መርህ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል::

“እኛ እያልን ያለነው በራሳችን ምድር እና ሀብት እየተሠራ ያለውን ልማት ‘አትሥሩ‘ አትበሉን ነው እንጂ ከግብጽ ጋር አሁንም ለመነጋገር እና ለመደራደር ዝግጁ ነን” ሲሉ ኢትዮጵያ የያዘችውን ”በጋራ እንጠቀም” አቋም ዛሬም አረጋግጠዋል::
”ግብጽ በተደጋጋሚ የምታነሳው ‘ድርቅ ሲያጋጥም እጎዳለሁ‘ ለሚለው ስጋት ግብጽ በድርቅ የምትጎዳው ድርቁ ኢትዮጵያን ካጠቃት ነው” ሲሉ መከራከሪያቸውን ውድቅ አድርገዋል:: ድርቅ የኢትዮጵያ ስጋት ሆኖ ኢትዮጵያንም ሆነ ሌሎች ጎረቤት ሀገራትን ተጎጂ እንዳያደርግ አረንጓዴ ልማት ላይ በስፋት እየተሠራ መሆኑን አመላክተዋል:: በመሆኑም የተፋሰሱ ሀገራት ቅንነትን መሠረት ያደረገ የጋራ ልማትን መርህ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል::
”የጋራ ሀብታችን የሆነውን ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ከተፋሰሱ ሀገራት ጋር በጋራ የምናስመርቅ በመሆኑ ሀገራቱ በዚህ ታላቅ ዝግጅት ላይ እንዲገኙ ግብዣ አቅርበዋል::

(ስማቸው አጥናፍ)
በኲር የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

የብሪክስ ጉዞየሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትምብሪክስ የተፈጠረው በመስራች ሀገራት  ፖለቲካዊ ተነሳሽነት ነው። የመጀመሪያ ግቡ በዓለም አቀፍ አጀንዳዎች ውስጥ ስላሉት ዋና ዋና መሪ ሃሳቦች...
21/07/2025

የብሪክስ ጉዞ
የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

ብሪክስ የተፈጠረው በመስራች ሀገራት ፖለቲካዊ ተነሳሽነት ነው። የመጀመሪያ ግቡ በዓለም አቀፍ አጀንዳዎች ውስጥ ስላሉት ዋና ዋና መሪ ሃሳቦች ውይይት ማድረግ እና የጋራ አቋማቸውን በፖለቲካዊ መልኩ በማጠናከር የዓለምን ስርዓት ዴሞክራሲያዊ፣ ሕጋዊ እና ሚዛናዊ ለማድረግ ነው።
እንደ ብራዚል፣ ሩሲያ፣ ህንድ፣ ቻይና እና ደቡብ አፍሪካ ያሉ ሀገራት ስብስብ ምህፃረ ቃል የሆነው ብሪክስ ዓላማው ሰላምን፣ ደኅንነትን፣ ልማትን እና ትብብርን ማበረታታት ነው። የመጀመሪያው የብሪክስ ስብሰባ የተካሄደው በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ደረጃ እ.አ.አ. በ2006 በኒውዮርክ በሚገኘው የተባበሩት መንግሥታት ጠቅላላ ጉባኤ ጎን ለጎን ነው። እ.አ.አ. በ 2008 የፋይናንስ ቀውስ ተፈጥሮ በነበረበት ጊዜ በወቅቱ አራቱ ሀገራት (ብራዚል፣ ሩሲያ፣ ህንድ፣ ቻይና) ከቡድን ሃያ (G20)፣ ከዓለም አቀፍ የገንዘብ ፈንድ (አይኤምኤፍ) እና ከዓለም ባንክ አንፃር የተቀናጀ አካሄድ በመከተል የዓለም አቀፍ ኢኮኖሚያዊ እና የፋይናንስ አስተዳደርን ለማሻሻል ሀሳቦችን በማቅረብ ታዳጊ ሀገራት በዓለም ኢኮኖሚ ውስጥ ያላቸውን አንፃራዊ ክብደት ለማንፀባረቅ ሞክረዋል። ሀገራቱ የመጀመሪያውን የብሪክስ መሪዎች ጉባኤን ያካሄዱት እ.አ.አ 2009 ሲሆን አስተናጋጇም ሩሲያ ነበረች::

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የብሪክስ አባል ሀገራት በአፍሪካ ያላቸውን ተሳትፎ አስፋፍተዋል። በውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ገቢ እና በንግድ መጠን ያላቸው ድርሻም በፍጥነት ከፍ ብሏል። አብዛኛዎቹ አባል ሀገራቱ በተለያዩ አህጉራት ላይ ጉልህ ተዋናዮች ናቸው። ለዓለም ኢኮኖሚ ጠቃሚ የሆኑ ከፍተኛ የነዳጅ ክምችት እና ሌሎች ወደ ውጭ የሚላኩ ጥሬ እቃዎች አሏቸው።
ግሎባል ታይምስ ላይ ያገኘነው መረጃ እንደሚያትተው ብሪክስ በዓለም አቀፉ ስርዓት ለውጥ እና በዓለም አቀፍ የኃይል ሚዛን ላይ ተጽእኖ የሚያሳድር ወሳኝ መድረክ ሆኗል። የብሪክስ አባል ሀገራት ዛሬ 31 በመቶውን የዓለም የመሬት ስፋት፣ 46 በመቶውን የዓለም ሕዝብ እና 20 በመቶውን የዓለም ንግድ ይሸፍናሉ። የዘይት ምርታቸው እና የመጠባበቂያ ክምችቱም ከዓለም አቀፍ የኃይል ገጽታ 40 በመቶውን ይይዛል።

ስታርት አፕ ኢንዲያ (tartupindia) የተባለ ድረገጽ ላይ ያገኘነው መረጃ ደግሞ እንደሚያመላክተው የብሪክስ ሀገራት ኢኮኖሚያቸውን በምናይበት ጊዜ 37 ነጥብ ሦስት በመቶ የሚሆነውን ከዓለም አቀፉ የሀገር ውስጥ ምርት (GDP) ያዋጣሉ:: ይህም ጉልህ የሆነ ኢኮኖሚያዊ ክብደታቸውን ያሳያል።
//ipea.gov.br// ላይ ያገኘነው መረጃ እንደሚያሳየው “ጎልድ ማን ሳችስ” የተባለ የኢንቨስትመንት ባንክ እ.አ.አ በ2032 የብሪክስ ሀገራት አጠቃይ ኢኮኖሚ ከቡድን ሰባት (G7) እኩል ይሆናል ብሎ አስቀምጧል::
በብሪክስ ውስጥ ቻይና ለታዳጊ ሀገራት እና ለታዳጊ ገበያዎች እውነተኛ እና ተዓማኒ ድምጽ እንደምትወክል ይታመናል። ከብሪክስ ሀገራት ግዙፍ ኢኮኖሚ ያላት እንደመሆኗ መጠን ቻይና የብሪክስ ትብብርን በማጠናከር፣ በመምራት እና በማስተዋወቅ ረገድ ወሳኝ ሚና ተጫውታለች።

ብሪክስ በመጀመሪያ አቅዶት የነበረው በ2050 የዓለምን ኢኮኖሚ ሊቆጣጠሩ የሚችሉ በፍጥነት በማደግ ላይ ያሉ ኢኮኖሚዎችን ማሰባሰብ ነበር። እንደ አይኤምኤፍ እና የዓለም ባንክ ያሉ የምዕራባዊያን የበላይነት ያላቸውን ዓለምአቀፍ ተቋማት ሚዛን ለመጠበቅ ጂኦፖለቲካዊ ቡድን ለመፍጠር አልሞ ነበር። በመሆኑም ብሪክስ እስያን፣ አፍሪካን፣ አውሮፓን እና ላቲን አሜሪካን በማካተቱ የበለጸገ የስልጣኔ ስብጥርን ያመጣል ተብሎ ተስፋ ተጥሎበታል::
አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች ግን ብሪክስ እርስ በርስ የተራራቁ የሀገሮች ስብስብ ብቻ በመሆኑ ፖለቲካዊ ወይም ኢኮኖሚያዊ ውህደታቸው ተስፋ የለውም ብለው ያስባሉ። ለዚህ ሀሳባቸው በምክንያት የጠቀሱት አብዛኛዎቹ የብሪክስ አባል ሀገራት እርስ በርስ ፉክክር ውስጥ ስለሚገኙ እና አንዳንዶችም የአሜሪካ አጋሮች በመሆናቸው ነው:: ተንታኞች በህንድንና በቻይና የኢኮኖሚ፣ የግብጽ እና የኢትዩጵያን በሕዳሴው ግድብ ያለውን ፉክክር እንዲሁም ሳዑዲ አረቢያ እና ዩናይትድ አረብ ኤምሬቶች አሜሪካ ጋር ያላቸውን ወዳጅነት ግምት ውስጥ በማስገባት አላማቸው ላይሳካ ይችላል ይላሉ:: የአሜሪካን ዶላር ላለመጠቀም የወሰኑት ውሳኔም እስካሁን ይህ ነው የሚባል ፍሬ አንዳላፈራ ነው የሚናገሩት:: ትራምፕም ይህንን ካደረጉ በአባል ሀገራቱ ላይ ተጨማሪ ታሪፍ እጥላለሁ የሚል ከዛቻ ያልተናነሰ አቋም ይዘዋል:: ሩሲያ እና ቻይና በጂኦፖለቲካዊ አላማቸው ምክንያት ዶላርን ላለመጠቀም ቀዳሚ ሆነዋል። እ.አ.አ. በ 2023 ሩሲያ እና ቻይና የሁለትዮሽ የንግድ ልውውጥን ከአሜሪካ ዶላር ውጭ ለማሳደግ ማቀዳቸውን አሳውቀው ነበር::

ከሰሞኑ በሪዮ በተካሄደው የብሪክስ ጉባኤ አባላቱ በፋይናንስ፣ ጤና፣ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ፣ የአየር ንብረት ለውጥ፣ ሰላምን፣ ደኅንነትን እንዲሁም ዓለም አቀፍ መረጋጋትን ለማሳደግ የሚያስችል ስምምነት ተፈራርመዋል። አስራአንድ አባላትን የያዘው የብሪክስ ውህድ እንደ ቤላሩስ፣ ቦሊቪያ፣ ኩባ ፣ካዛኪስታን፣ ማሌዥያ፣ ናይጄሪያ፣ ታይላንድ፣ ኡጋንዳ እና ኡዝቤኪስታን የመሳሰሉ አጋር ሀገራትም አሉት:: ከሰሞኑም የብራዚል መንግሥት በጊዜያዊነት የብሪክስ ሊቀ መንበር ሆኖ ሲሾም ወደ 100 ሚሊዮን የሚጠጋ ህዝብ ያላትን ቬትናም የቡድኑ አጋር ሀገር አድርጎ መቀበሉን አስታውቋል:: ቬትናምም አሥረኛዋ የብሪክስ አጋር ሀገር ሆናለች።

አልጀዚራ እንደዘገበው ብሪክስ በዓለም ፖለቲካ ውስጥ፣ በዓለም አቀፍ ብዝሃነት እና በዓለም አቀፍ ግንኙነቶች ዴሞክራሲያዊ አሰራር ሂደት ውስጥ ቁልፍ ሚና ይጫወታል:: በመሆኑም የብሪክስ ህብረት መሪዎች ከአንድ ወር በፊት አሜሪካ እና እስራኤል ኢራን ላይ ያደረሱትን የቦምብ ድብደባ “የዓለም አቀፍ ህግን በግልጽ የጣሰ” በሚል መተቸታቸው አንዱ ማሳያ ነው::
ከብሪክስ መግለጫ እጅግ አስደናቂ ከሆኑት አንዱ በ1967 ለተመሰረተው ለፍልስጤም ሀገርነት ያለው የማያሻማ ድጋፍ ሲሆን ምሥራቃዊ እየሩሳሌም ዋና ከተማቸው እንድትሆን ወስነዋል:: እንዲሁም ህብረቱ በጋዛ ላይ አፋጣኝ እና ያለምንም ቅድመ ሁኔታ የተኩስ አቁም እንዲደረግ፣ የእስራኤል ወታደሮች ከጋዛ እንዲወጡ፣ ታጋቾች እንዲፈቱ እና ሰብአዊ ርዳታዎችን ያለምንም እንቅፋት እንዲደርሱ መጠየቁ ነው። ምንም እንኳን አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች ሕብረቱ በምዕራቡ ዓለም የሚመራውን ዓለም አቀፍ ሥርዓት ሊያደናቅፍ እንደሚችል ቢያስቡም ነገር ግን የራሱን ገንዘብ ለመፍጠር እና አሁን ካሉ ተቋማት ጋር ሊሠራ የሚችል አማራጭ የማዘጋጀት ፍላጎቱ የማይታለፉ ፈተናዎች እንዳሉበት ያመላክታሉ።

የጥምረቱ ራዕይ ኢኮኖሚያዊና ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶችን በጋራ ግብ ዙሪያ የሚያቀናጅ ልቅ ከሆነው የምዕራባዊያን ኢኮኖሚ ተፅዕኖ ስብስብ ነፃ መውጣት ነው። የብሪክስ ሀገሮች የምዕራቡ ዓለም የበላይነት ከሚንጸባረቅበት የዓለም ባንክ፣ የቡድን ሰባት (G7) እና የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት ባሉ ዋና ዋና የባለብዙ ወገን ቡድኖች ትይዩ ሌላ አማራጭ መገንባት ይፈልጋሉ።
ብሪክስ ከዓለም ባንክ ትይዩ የሚቆም አማራጭ የፋይናንስ ሥርዓት መፍጠር አላማው በመሆኑ የቡድኑ አዲስ ልማት ባንክ (ኤንዲቢ) እና የተጠባባቂ ሪዘርቭ አደረጃጀት (ሲአርኤ) እንደየቅደም ተከተላቸው የዓለም ባንክን እና ዓለም አቀፍ የገንዘብ ፈንድ (አይኤምኤፍን) ለመገዳደር የሚያስችሉ ናቸው።
የብሪክስ ቡድን በዓለም አቀፍ ተቋማት ላይ የምዕራባውያን ተጽዕኖን ለመከላከል ካለው ፍላጎት በመነሳት ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ውስጥ ትልቅ የፖለቲካ ኃይል ሆኗል::
እ.አ.አ. ሐምሌ 6 እና 7 በ2025 በሪዮ ዴጄኔሮ ብራዚል የተካሄደው የመሪዎች ጉባኤ በዓለም አቀፍ የአስተዳደር ማሻሻያዎች እና በዓለምአቀፍ ደቡብ ማህበረሰብ ትብብር ላይ ያተኮረ ነበር። ነገር ግን በዚህ ጉባኤ የቻይና እና የሩስያ መሪዎች ለዓመታዊው ስብሰባ ወደ ሪዮ አለመሄዳቸው የሕብረቱን ዘላቂነት ላይ ጥያቄ ውስጥ ማስገባቱን ካውንስል ኦፍ ፎሬን አፌርስ ላይ ያገኘነው መረጃ ያትታል::

(ሳባ ሙሉጌታ )
በኲር የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

ከተከላ ባሻገር ...የሐምሌ 14  ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም“ዛፉ ዛፉ እስትንፋሴ፣ልጠብቅህ እንደራሴ!ዛፉ ዛፉ አረንጓዴ፣አንተ ባትኖር እኛስ አለን እንዴ?”እንደ መንደርደሪያ የተነሱት ስንኞች ...
21/07/2025

ከተከላ ባሻገር ...
የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

“ዛፉ ዛፉ እስትንፋሴ፣
ልጠብቅህ እንደራሴ!
ዛፉ ዛፉ አረንጓዴ፣
አንተ ባትኖር እኛስ አለን እንዴ?”
እንደ መንደርደሪያ የተነሱት ስንኞች የዕጽዋትን እና ሌሎች ፍጥረታትን (በተለይ የሰው ልጅ) የማይነጣጠል መስተጋብር፣ አንዱ ለሌላው የመኖር ምክንያት እንደሆኑ ለማሳየት የተጠቀሱ ናቸው:: ይህን በመረዳትም ነው ታዋቂው አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) በስንኞቹ የተቀኜው::
በኢትዮጵያ በ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከሀገሪቱ የመሬት ቆዳ ስፋት ውስጥ 60 በመቶው የሚሆነው በደን የተሸፈነ እንደነበር ድርሳናት ያስነብባሉ። በተለይም በዐፄ ዳዊት፣ በንጉሥ ዘርዐ ያዕቆብ፣ አፄ ምኒልክ፣ በአፄ ኃይለ ሥላሴ እና በኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ዘመነ መንግሥታት ለዘርፉ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ።

እነዚህ የየዘመኑ መንግሥታት የደን ጭፍጨፋን ለመከላከል የሚያስችሉ ጥብቅ የሕግ ማዕቀፎችን ከማውጣት ጀምረው በተለያዩ መንግሥታት የነበሩ ተሞክሮዎችን አስቀጥለዋል:: ለአብነትም አፄ ምኒልክ ችግኝ የዜጎች ጉዳይ እንዲሆን የመሬት ግብር ምሕረት እስከማድረግ የሚደርስ ማበረታቻ ማድረጋቸው ይጠቀሳል:: ከዚህ ባለፈ በደን ጭፍጨፋ የሚሳተፉ አካላት ንብረታቸው እንዲወረስ እና የማያዳግም ቅጣትን የሚያበረታታ የሕግ ማዕቀፍ ማውጣታቸው ለዘርፉ የሰጡት ትኩረት ማሳያ ነው::
ይህ በእንዲህ እንዳለ ለዓመታት ትኩረት በመነፈጉ፣ የሕዝብ ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ በመጨመሩ፣ የእርሻ ሥራ በመስፋፋቱ፣ የባለቤትነት ስሜት በማጣቱ እና መሰል ምክንያቶች የሀገራችን የደን ሽፋን እየተመናመነ ወደ ሦስት በመቶ አሽቆልቁሎ እንደነበር ታሪክ ያስረዳል። ይህም ለበረሃማነት መስፋፋት፣ ለዱር እንስሳት መሰደድ፣ ለዝናብ እጥረት እና መሰል ችግሮች ምክንያት ሆኖ ቆይቷል።

ይህን ለመቀልበስ በተሠሩ ሥራዎች ታዲያ የደን ሽፋኑን ከመመናመን መታደግ ተችሏል፤ ለዚህ ደግሞ በተለይ በቅርብ ዓመታት የተጀመረው ዓመታዊው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ማሳያ ነው። ኢትዮጵያ የተራቆተ መሬቷን ለማከም፣ ዓለምን እየፈተነ ያለውን እና ለብዙ ተፈጥሯዊ አደጋዎች ምክንያት የሆነውን የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ላይ በብርቱ እየሠራች መሆኑን ከግብርና ሚኒስቴር የሚወጡ መረጃዎች ያሳያሉ::
ባለፋት ስድስት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል በከፍተኛ ደረጃ ተጎድቶ የነበረ መሬት እንዲያገግም እና በአካባቢ ጥበቃ ሥራውም ላይ ለውጥ እንዲያመጡ መደረጉን የሚኒስቴሩ መረጃ ያክላል:: አረንጓዴ አሻራ ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የምትፈተንበትን እንደ ድርቅ፣ የመሬት መንሸራተት፣ ቅፅበታዊ ጎርፍ እና አሲዳማነትን ለመቀነስ አስተዋጽኦው ከፍተኛ መሆኑንም ባለሙያዎች ይናገራሉ::

በመሆኑም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በተለይም ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ ለአረንጓዴ አሻራ በተሰጠው ልዩ ትኩረት የኢትዮጵያ የደን ሽፋን ወደ 23 ነጥብ ስድስት በመቶ መድረሱን ከኢትዮጵያ ደን ልማት ድረ ገፅ የተገኘው መረጃ ያመለክታል። በ2030 ዓ.ም የደን ሽፋኗን ወደ 30 በመቶ ከፍ ለማድረግ በትጋት እየሠራች እንደምትገኝ መረጃው አክሏል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በተለይ ባለፉት ስድስት ዓመታት በተሻለ መነቃቃት እየተከናወነ የሚገኝ ተግባር ነው። በዚህም የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ ሳይጨምር ከ40 ቢሊዮን በላይ ችግኞች መተከላቸውን ከኢትዮጵያ ግብርና ሚኒስቴር ማሕበራዊ ትስስር ገጽ ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል::

እንደ ሀገር በ2017 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከሰባት ነጥብ አምስት በላይ ችግኝ ይተከላል ተብሎ ይጠበቃል።
በአማራ ክልልም በ2017 ዓ.ም በክረምት ወራት በሚከናወነው የችግኝ ተከላ በክልሉ አሁን ያለውን 16 ነጥብ ሦስት በመቶ የደን ሽፋን ወደ 17 ነጥብ ሦስት በመቶ ያሳድገዋል ተብሎ ይጠበቃል። በአማራ ክልል ባለፉት ስድስት ተከታታይ ዓመታት በተካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከዘጠኝ ቢሊዮን በላይ ችግኞች የተተከሉ ሲሆን የፅድቀት ምጣኔም በየዓመቱ ዕድገት እያሳየ ነው። ለዚህም የኅብረተሰቡ እና የተቋማት ቅንጅታዊ አሠራር መዳበር፣ ኅብረተሰቡ የተሻለ ግንዛቤ መኖሩ እና የፅድቀት መጠን የሚጨምሩ የተሻሻሉ ሥራዎች በመሠራታቸው ስለመሆኑ ነው የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ያስታወቀው።

አረንጓዴ አሻራ የአፈር ለምነትን ለመጨመርና ለመጠበቅ፣ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ፣ የቱሪስት ሀብቱን ለማሳደግ፣ የአየር ንብረት መዛባትን ለመከላከል፣ ለአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ፣ የውኃ አካላትን ለማጎልበት (የውኃ ምንጮች እንዲበራከቱ)፣ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ በደለል እንዳይሞላ፣ ለአካባቢ ውበት፣ ለኢንዱስትሪ ጥሬ ዕቃ፣ ለሥነ ምህዳር ጥበቃ፣ ለመድኃኒት መቀመሚያ፣ ለዱር እንስሳት መጠለያ፣ የአፈር መሸርሸርን ለመከላከል፣ ለማገዶ፣ ለከሰል፣ ለቤት መገንቢያ፣ ለውጭ ምንዛሬ ማስገኛ፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራ እና ለኢትዮጵያ ምጣኔ ሀብት ዕድገት ጉልህ ሚናን እንደሚጫወት በአማራ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የደን ምርምር ዳይሬክተር ከፍተኛ ተመራማሪ ዶክተር ምናለ ወንዴ አስረድተዋል።
በአማራ ክልል በ2017/18 የክረምት ወቅት አንድ ነጥብ ስድስት ቢሊዮን ችግኞች ለመትከል ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል። እስካሁን አንድ ነጥብ 55 ቢሊዮን ችግኞች እና አንድ ነጥብ አምስት ቢሊዮን የተከላ ጉድጓድ ተዘጋጅቷል። ከ205 ሺህ ሄክታር በላይ የተከላ ቦታ የተለየ ሲሆን ከ53 ሺህ በላይ ሄክታር የተከላ ቦታ ላይ የካርታ ሥራም ተሠርቷል።

ይህን ሁሉ ዝግጅት በማድረግ ክልላዊ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ሐምሌ 01 ቀን 2017 ዓ.ም በይፋ መጀመሩ የሚታወስ ነው። “በመትከል ማንሰራራት” በሚል መሪ መልዕክት የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘንድሮ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞች ይተከላሉ ተብሎ ይጠበቃል። አሁን ላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለተከላ ዝግጁ መደረጋቸውም ተገልጿል። ከተዘጋጁ ችግኞች ውስጥ የፍራፍሬ፣ ሀገር በቀል የደን ችግኞች፣ የእንስሳት መኖ እና ሌሎች የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ናቸው። በቀጣይ በሀገር አቀፍ ደረጃ በሚካሄደው የአንድ ጀምበር የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እንደ ክልል 278 ሚሊዮን ችግኝ ለመትከል አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ከቢሮዉ የተገኘው መረጃ ይጠቁማል::
የክልሉ የደን ምርምር ዳይሬክተር ከፍተኛ ተመራማሪ ዶክተር ምናለ ወንዴ እንዳሉት በኢትዮጵያ የደን ልማትን ለማፋጠን የደን ፖሊሲ እና የደን ጥበቃ አዋጅ ተቀርፆ ወደ ሥራ ተገብቷል። የደን ዘርፉ በሀገር አቀፍ ደረጃ 12 ነጥብ 9 በመቶ ኢኮኖሚያዊ ድርሻ እንዳለውም አመላክተዋል። አረንጓዴ አሻራ ምጣኔ ሀብታዊ፣ ማሕበራዊ እና አካባቢያዊ ፋይዳው የጎላ መሆኑን ጠቅሰዋል። ለአብነትም የተለያዩ ባሕላዊ እና ሃይማኖታዊ ተግባራት የሚከናወኑት በደን ውስጥ መሆኑን ጠቅሰዋል።

ዳይሬክተሩ ከአሚኮ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደተናገሩት የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ሲከናወን ሳይንሳዊ ዘዴን እና በዕውቀት ላይ ተመሥርቶ መሆን እንዳለበት አስረድተዋል። የአማራ ክልል ለደን ልማት የሚውል የተለያዩ ሥነ - ምህዳሮች፣ ምቹ የአየር ንብረት እና ተስማሚ አፈር እንዳለው ገልፀዋል።
የተመናመነን የደን ሽፋን መልሶ እንዲያገግም ለማድረግ እና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል። ከመትከል በላይ የጽድቀት ምጣኔን ማሳደግ ዋናው ጉዳይ ሊሆን ይገባልም ብለዋል:: የጽድቀት ምጣኔ ሊያድግ የሚችለው ደግሞ የተተከሉት ችግኞች ባለቤት ሲኖራቸው መሆኑን ጠቅሰዋል::

እንደ ክልል የደን ሽፋንን ለማሳደግ እየገጠሙ ያሉ ዋና ዋና ተግዳሮቶችን ዳይሬክተሩ ዘርዝረዋል። እነዚህም ተፈጥሯዊ፣ ቴክኒካዊ፣ ማሕበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፓሊሲያዊ መሆናቸውን ነው ያስረዱት። ተፈጥሯዊ ተግዳሮቶች ደን ምርት ለመስጠት ከአምስት እስከ 15 ዓመት ጊዜ የሚወስድ እና የግብርና ሥራ በሰብል ልማት ላይ ያተኮረ መሆኑን አንስተዋል። ነገር ግን ብዙ ሀገሮች በሰብል ምርት ብቻ ለውጥ እንደማያመጡ ተረድተው በደን ልማት ላይ ማተኮራቸውን ገልፀዋል።
ቴክኒካዊ ችግር ሌላው ተግዳሮት ሲሆን የተከላ ቦታ እና የችግኝ ዝርያ አለመጣጣም፣ የሚተከሉ ችግኞች ለምን ዓላማ እንደሚተከሉ አለመረዳት፣ ተገቢውን እንክብካቤ አለማድረግ እና ሌሎችን ጠቅሰዋል። ማሕበራዊ የሚባው ተግዳሮትም የሕዝብ ቁጥር መጨመር፣ የሰደድ እሳት፣ ሕገ ወጥ የደን ጭፍጨፋ እና መሰል ችግሮች ናቸው። ኢኮኖሚያዊ፦ በታዳሽ ኃይል አለመተካት (የኃይል ምንጫችን በደን ውጤቶች ላይ የተንጠለጠለ በመሆኑ) የደን መጨፍጨፍ መንስኤ ሆኗል ብለዋል።

ሌላው ፖሊሲያዊ ተግዳሮት ሲሆን፤ የሚወጡ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በታቀደው መሠረት አለመፈፀም እየታዩ ያሉ ተግዳሮቶች ናቸው ብለዋል።
የሚተከሉ ችግኞች እንዳይፀድቁ የሚያደርጉ ዋና ዋና ምክንያቶችንም ከፍተኛ ተመራማሪው ገልፀዋል። እነዚህም የቅድመ ዝግጅት ማነስ፣ ያለ ፕላስቲክ ማፍላትና መትከል፣ የተከላ ቦታ አለመለየት፣ ቀድሞ ጉድጓድ አለማዘጋጀት (ወዲያው ቆፍሮ መትከል)፣ ከአረም ነፃ አለማድረግ፣ የችግኝ ፍል ዕድገቱን አለመከታተል፣ ጥራት ያለው ችግኝ አለመትከል፣ በወቅቱ አለመትከል፣ በቂ የአፈር እርጥበት በሚኖርበት ሰዓት አለመትከል እና መሰል ጉዳዮች መኖራቸውን ጠቅሰዋል።
ችግኝ ከንፁህ ዘር መረጣ ጀምሮ የዘር ጥራቱን ፍተሻ ማድረግ፣ የእያንዳንዱን የችግኝ ዘር ዓይነት ማወቅ፣ የበቀለው ችግኝ በችግኝ ጣቢያው ምን ያህል ጊዜ እንደሚቆይ መረዳት፣ ተገቢውን እንክብካቤ አድርጎ ጠንካራና ጤናማ ችግኝ ወደ ተከላ ቦታ መውሰድ፣ የተከላ ቦታን ማፅዳት፣ ደረጃውን የጠበቀ የችግኝ ጉድጓድ ማዘጋጀት፣ ሳይንሳዊ ዘዴን በመከተል ርቀቱን እና ስፋቱን መለካት እንደሚገባ ተናግረዋል።
ከተከላ በኋላም ወቅቱን ጠብቆ መኮትኮት፣ ማረም፣ ውኃ ማጠጣት፣ ማጠር፣ ከእንስሳት ንክኪ ነፃ ማድረግ፣ ልክ እንደ ሰብል ልማቱ ተገቢውን ግብዓት መጨመር (የአፈር ማዳበሪያ እና ኮምፖስት)፣ ካደጉ በኋላም መመልመል፣ ተገቢውን ጥበቃ እና እንክብካቤ ማድረግ እንደሚገባ ምክረ ሐሳባቸውን አቅርበዋል።

መረጃ

በኢትዮጵያ የተለያዩ የደን ዓይነቶች ይገኛሉ። ከነዚህ መካከልም፦ የተፈጥሮ ደን፣ ሰው ሠራሽ ደን፣ ዘርዛራ ደን፣ የጣንና ሙጫ፣ የቅርቀሀ እና ቁጥቋጦ ደኖች ተጠቃሽ ናቸው።

(መልካሙ ከፋለ)
በኲር የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

Address

Bahir Dar

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when አሚኮ በኲር/AMECO BEKUR posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to አሚኮ በኲር/AMECO BEKUR:

Share