አሚኮ በኲር/AMECO BEKUR

አሚኮ በኲር/AMECO BEKUR በኲር
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን የምትዘጋጅ ሳምንታዊ የቤተሰብ ጋዜጣ

18/08/2025
ከሁሉም አካላት የሚጠበቅ ኃላፊነትየነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትምሃይማኖታዊ እና ባህላዊ ክብረ በዓላት የቱሪዝም ዘርፉን ለማስፋፋት ከሚያግዙ ተግባራት መካከል ዋናዎቹ ናቸው:: ቱሪዝምም ...
18/08/2025

ከሁሉም አካላት የሚጠበቅ ኃላፊነት
የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

ሃይማኖታዊ እና ባህላዊ ክብረ በዓላት የቱሪዝም ዘርፉን ለማስፋፋት ከሚያግዙ ተግባራት መካከል ዋናዎቹ ናቸው:: ቱሪዝምም ለሀገር እድገት እና ልማት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያለው ሲሆን ለተቋማት እና ለግለሰቦች የነፍስ ወከፍ የገቢ ምንጭ በመሆን ያገለግላል::

በተጨማሪም የማህበረሰቡን እሴት፣ ባህል፣ ወግ፣ ልማድ እንዲሁም ሃይማኖታዊ ክዋኔ ለማስተዋዋቅ እና ለማጎልበት ሚናው የጐላ ነው:: ኢትዮጵያ በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) ያስመዘገበቻቸው በርካታ የሚዳሰሱ እና የማይዳሰሱ የመስህብ ሀብቶች ይገኛሉ:: በአማራ ክልል:: የአማራ ክልል በዩኔስኮ ከተመዘገቡት የመስህብ ሀብቶች በተጨማሪ በርካታ ሃይማኖታዊ እና ባህላዊ የመስህብ ኩነቶች ባለቤትም ነው:: ይሁንና ክልሉ በዘርፉ እያገኘ ያለው ጥቅም ግን እዚህ ግባ የሚባል አይደለም::

በመሆኑም ክልሉ ባለው የተፈጥሮ፣ ሰው ሠራሽ፣ የታሪክ፣ የሃይማኖት እና ባህላዊ ፀጋዎቹን ለመጠቀም እና የቱሪዝም ዘርፉን ለማስፋፋት ይረዳው ዘንድ ያሉትን ሀብቶች በአግባቡ ማስተዋወቅ፣ መንከባከብ እንዲሁም ለማህበረሰቡ በየወቅቱ መረጃ መስጠት እና ማነቃቃት ይኖርበታል::

በክልላችን የተለያዩ አካባቢዎች ከያዝነው የነሐሴ ወር አጋማሽ ጀምሮ የቡሔ፣ ሻደይ፣ አሸንድዬ፣ ሶለል፣ እንግጫ ነቀላ እና የከሴ አጨዳ ሃይማኖታዊ እና ባህላዊ ኩነቶች ወይም ክዋኔዎች በድምቀት ይከበራሉ:: በዓላቱ ሲከበሩም ዋነኛ መገለጫቸው የክልሉን ሕዝብ ባህል፣ ወግ፣ ልማድ፣ ማንነት፣ ተቀባይነት… በሚያሳይ መልኩ ነውና እነዚህን መገለጫዎች ማስቀጠል አለበት::

እነዚህን ክዋኔዎች በማክበር ማስቀጠልም ማህበራዊ አንድነትን ለማጠናከር እና ምጣኔ ሃብቱን ለማነቃቃት እንዲሁም አካባቢውን ለማስተዋዋቅ ይረዳል::
በዓላቱ ሃይማኖታዊ እና ባህላዊ ትውፊትን በማጣመር የሚከናወኑ በመሆናቸው ተቀባይነታቸው የጐላ ነዉ። ይህም የቱሪዝም ዘርፉ እንዲያንሰራፋ፣ አካባቢውም ምጣኔ ሀብታዊ ዕድገት እንዲያመጣ እና ለማህበራዊ መስተጋብር ሁነኛ ፋይዳ አላቸው።
በመሆኑም በዓላቱ እና ክዋኔያቸው ሳይደበዝዙ እና ሳይበረዙ በድምቀት ይከበሩ ዘንድ ከባለድርሻ አካላት እንዲሁም ከእያንዳንዳችን ትኩረት መስጠት እና ሰፊ ሥራ መሥራት ይጠበቃል::

የክልሉ ባህል እና ቱሪዝም ቢሮ ከሰሞኑ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳስታወቀው የዘንድሮው በዓል መሪ ቃል “ባህላዊ እሴቶቻችን ለዘላቂ ሰላማችን፣ የነበርንበት፣ ያለንበት እና የምንደርስበት” የሚል ነው::
ክልሉ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ጐብኝዎች መዳረሻ ሲሆን ክብረ በዓላቱ ደግሞ የክልሉን ሕዝብ ባህል፣ ታሪክ፣ ትውፊት፣ ቅርስ… ማሳያ እና ማስመስከሪያዎች እንደሆኑ ቢሮው አውስቷል:: በዓላቱ በያካባቢዉ ሲከበሩ የክልሉ ሕዝብ የቀደመ የእንግዳ ተቀባይነት ባህሉን በተግባር እንዲያሳይም ቢሮው ጥሪ አቅርቧል::

የክልሉ ልዩ መገለጫ የሆኑትን እነዚህን በዓላት ማክበር የማህበረሰቡን እሴት ለማስጠበቅ እና ትውልዱ ጠንካራ የማንነት ስሜት እንዲላበስ በማድረግ ረገድ ሁነኛ ሚና ከመጫዎቱም በተጨማሪ ለቱሪዝም ዘርፉ መነቃቃትም አስተዋጽኦው ከፍተኛ ነዉ።

በመሆኑም በክልሉ ውስጥ በተለያዩ አካባቢዎች የሚከበሩ በዓላትን በወጉ እንዲከበሩ እና ጐብኝዎችም ወደየአካባቢዎች እንዲንቀሳቀሱ መረጃ በመስጠት፣ ድጋፍ በማድረግ እና በዓላቱ ለቀጣዩ ትውልድ እንዲተላለፉ እንዲሁም ኩነቶቹ ወደ ቱሪዝም ገበያው እንዲገቡ ያላሰለሰ ድጋፍ እና ትብብር ማድረግ ከሁሉም ባለድርሻ አካላት የሚጠበቅ ኃላፊነት ነው::

በኲር የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

ቅምሻ 12-12-2017
18/08/2025

ቅምሻ 12-12-2017

ሻደይን ባሕላዊ እሴቱን በጠበቀ መልኩ ለማክበር ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ ተጠቆመየሐምሌ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትምበዋግኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር የሻደይ በዓልን ባሕላዊ እሴቱን በጠበቀ መል...
18/08/2025

ሻደይን ባሕላዊ እሴቱን በጠበቀ መልኩ ለማክበር ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ ተጠቆመ
የሐምሌ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

በዋግኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር የሻደይ በዓልን ባሕላዊ እሴቱን በጠበቀ መልኩ በአብሮነት ለማክበር ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የብሔረሰብ አስተዳደሩ ባሕል እና ቱሪዝም መምሪያ ገለጸ።

የመምሪያው ኃላፊ አቶ እዮብ ዘውዱ ለአሚኮ እንደተናገሩት የአብሮነት፣ የአንድነት እና የመተባበር እሴት መገለጫ የሆነውን የሻደይ በዓል ለማክበር ከወዲሁ ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ ነው። በዓሉ በአደባባይ በሰቆጣ ከተማ እና በብሔረሰብ አስተዳደሩ ስር በሚገኙ ከተሞች ከነሐሴ ወር አጋማሽ ጀምሮ እንደሚከበር ገልጸዋል።
በዓሉ ጥንታዊነቱን እና ባሕላዊ እሴቱን በጠበቀ መልኩ በመንደር፣ በቀበሌ እና በወረዳ ደረጃ ልጃገረዶች በባህላዊ አልባሳት እና ጌጣጌጦች ተውበው ለማክበር ዝግጅት እያደረጉ መሆኑን አንስተዋል። የዘንድሮው የሻደይ በዓል በባህል ፌስቲቫል እና በሌሎች ዝግጅቶችም ታጅቦ በሰቆጣ ከተማ በድምቀት እንደሚከበር ተናግረዋል። ሻደይን ለመታደም ለሚመጡ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ጎብኝዎች ምቹ የሆቴል እና የመዝናኛ ስፍራዎች መዘጋጀታቸውንም አቶ እዮብ አንስተዋል።

በሰቆጣ ወረዳ የሽመድር ቀበሌ ነዋሪ ወጣት አለምናት ቢበይን በሰጠችው አስተያየት ”የሻደይ በዓል በጉጉትና በፍቅር የምንጠብቀው ታላቁ ባህላችን ነው፤ የዘንድሮውን የሻደይ በዓል እንደወትሮው ሁሉ በደመቀ መልኩ ለማክበርም የሻደይ ቀሚስ፣ ድሪ ፣ማርዳ፣ መስቀል እና የመሳሰሉ ጌጣጌጦችን ገዝተን አዘጋጅተናል” በማለት ተናግራለች።
”ሻደይ ከነፃነት ባለፈ የአንድነት፣ የአብሮነት፣ የመተባበር እና የመተጋገዝ እሴት ያለው በመሆኑ የምናፍቀው በዓል ነው” ያለችው ደግሞ በወረዳው የቲያ ቀበሌ ነዋሪ ወጣት መቅደስ ሞላ ናት። የዘንድሮውን የሻደይ በዓል በደመቀ መልኩ ለማክበር ከሌሎች የአካባቢው ሴቶች ጋር ቡድን መስርተው ለበዓሉ አስፈላጊውን ዝግጅት እያደረጉ መሆኑን ጠቁማለች።

(መልካሙ ከፋለ)
በኲር የሐምሌ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

ከ58 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑ ተገለፀየነሐሴ 12  ቀን 2017 ዓ.ም ዕትምበኦሮሞ ብሔረሰብ አሥተዳደር በ2017/18 የምርት ዘመን 58 ሺህ 800 ሄክታር መሬት በሰብል ለመሸ...
18/08/2025

ከ58 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑ ተገለፀ
የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

በኦሮሞ ብሔረሰብ አሥተዳደር በ2017/18 የምርት ዘመን 58 ሺህ 800 ሄክታር መሬት በሰብል ለመሸፈን አቅዶ እየሠራ መሆኑን አስታዉቋል፡፡
የብሔረሰብ አሥተዳደሩ ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊ ሀሰን ሰይድ ለበኵር እንደገለፁት በብሔረሰብ አሥተዳደሩ የመኸር እርሻን በወቅቱ ለማከናወን የተለያዩ ቅድመ ዝግጅት ተደርጎ ወደ ሥራ ተገብቷል። በዞን፣ በወረዳ እና በቀበሌ ለሚገኙ የግብርና ባለሙያዎችም የአቅም ግንባታ ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡

የብሔረሰብ አሥተዳደሩን ምርት እና ምርታማነት ለማሳደግ ሙሉ ፓኬጅን ተጠቅመው አርሶ አደሮች እንዲሠሩ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ መሆኑንም ኃላፊው ገልፀዋል። ይህ መረጃ እስከተጠናቀረበት ነሐሴ 08 ቀን 2017 ዓ.ም 58 ሺህ 839 ሄክታር መሬት መታረሱን ነው የገለፁት። ከታረሰው መሬት ውስጥም 58 ሺህ 750 ሄክታር መሬት በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ተሸፍኗል። ከዚህ ውስጥ 37 ሺህ ሄክታር መሬት በማሽላ የተሸፈነ መሆኑን ኃላፊው ገልፀዋል። ማሽላን ጨምሮ ጤፍ፣ በቆሎ እና ማሾ አሁን ላይ ተዘርተው እንክብካቤ እየተደረገላቸው የሚገኙ ሰብሎች መሆናቸውንም ጠቅሰዋል።

የታለመው ዕቅድ እስከ መጨረሻው እንዲሳካም ለግብዓት አቅርቦት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን ኃላፊዉ ተናግረዋል። በምርት ዘመኑ ለብሔረሰብ አሥተዳደሩ ከሚያስፈልገው 50 ሺህ ኩንታል ሰው ሠራሽ የአፈር ማዳበሪያ 28 ሺህ ኩንታል ደርሷል፡፡ በተመሳሳይ 804 ኩንታል ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሩ ተሰራጭቷል።

በብሔረሰብ አሥተዳደሩ በርካታ አካባቢዎች የተፈጥሮ ማዳበሪያ (መደበኛ ኮምፖስት፣ ቨርሚ ኮምፖስት እና ባዮ ሳላሪ ኮምፖስት) የመጠቀም ልምድ እያደገ ነው። የታቀደውን ምርት ለማግኘት አርሶ አደሩ ዘወትር የሰብል ጥበቃ ማድረግ፣ አረምን በወቅቱ ማረም፣ መኮትኮት፣ ሰብልን በተገቢው መንገድ መንከባከብ፣ ዕለታዊ የተባይ እና የበሽታ አሰሳ ማድረግ እና ሌሎች ምርትና ምርታማነትን ሊያሳድጉ የሚችሉ ተግባራትን ማከናወን እንዳለባቸው አሳስበዋል። የግብርና ባለሙያዎችም ለአርሶ አደሩ ምክረ ሐሳብ ማቅረብ፣ ክትትል እና ድጋፍ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝበዋል።
በምርት ዘመኑ በብሔረሰብ አስተዳደሩ ከአንድ ነጥብ ሰባት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይገኛል ተብሎም ይጠበቃል።

(መልካሙ ከፋለ)
በኲር የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

18/08/2025

ኢንስቲትዩቱ ዘጠኝ የተሻሻሉ የሰብል ዝርያዎችን መልቀቁን አስታወቀ
የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

የአማራ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ምርታማነትን እና ጥራትን የሚያሳድጉ፣ ድርቅን፣ ተባይን፣ በሽታን እና አረምን መቋቋም የሚችሉ የሰብል ዝርያዎች መልቀቁን አስታውቋል። አንድ የጤፍ፣ ሦስት የማሽላ፣ ሁለት የእንቁ ዳጉሳ፣ ሁለት የአተር እና አንድ የምስር ዝርያዎች መልቀቁን ነው ምርምር ኢንስቲትዩቱ የገለፀው።
ባለፉት ሰባት ዓመታት ምርምር ሲደረግባቸው የቆዩ በሀገር አቀፍ ዘር አጽዳቂ ኮሚቴ የምርምር ደረጃዎችን ያለፉ ዘጠኝ የሰብል ዝርያዎች መለቀቃቸውን ነው የአማራ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አስማረ ደጀን (ዶ.ር) ለበኵር የተናገሩት። ስሪንቃ የግብርና ምርምር ሰባት እንዲሁም ሰቆጣ የዝናብ አጠር የምርምር ማዕከል ሁለት የሰብል ዝርያዎችን እንደለቀቁ ነው የጠቀሱት። እነዚህን ዘጠኝ ዝርያዎች በቀጣይ በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች የማላማድ እና የማስተዋወቅ ሥራዎች በስፋት እንደሚከናወን አስረድተዋል። ዝርያዎቹ ከአማራ ክልል አልፎ ለሀገር የሚጠቅሙ እንደሆኑም አመላክተዋል።
የአማራ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት በበጀት ዓመቱ ለመሥራት ካቀደው 584 የምርምር ሥራዎች ውስጥ 83 በመቶ ማከናወኑን ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸዋል። የምርምር ሥራዎቹ ሰብል፣ እንስሳት፣ የዘር ብዜት፣ አፈር እና ውኃ አያያዝ፣ ደን እና የተለያዩ ምርምሮችን ያካተቱ ናቸው። ዳይሬክተሩ እንዳሉት ኢንስቲትዩቱ የምርምር ሥራዎችን እና አዳዲስ ተክኖሎጂዎችን የማፍለቅ፣ የማባዛት እና የማስተዋወቅ ሥራዎችን እያከናወነ ይገኛል። ምርምሮችን ያካሂዳል፣ የሚያወጣቸውን መስራች ዘሮችን ያሰራጫል፤ የአቅም ግንባታ ሥራም ያከናውናል።
ፈጥነው የሚደርሱ፣ የተሻለ ምርት የሚሰጡ እንዲሁም አሲዳማ አፈርን መቋቋም የሚችሉ የሰብል ዝርያዎች ለአርሶ አደሩ እየተሰራጩ መሆኑን ገልፀዋል። በተፈጠረው የፀጥታ ችግር ምክንያት በተለይም በአንዳሳ እና በአዴት ግብርና ምርምር ማዕከል ሥራዎችን ለማከናወን አስቸጋሪ እንደነበር አንስተዋል።
በምርምር ኢንስቲትዩቱ ከተለቀቁት ዝርያዎች መካከል ሦስት የማሽላ ዝርያዎች ይገኙበታል። “ስሪንቃ አንድ” የተባለው የማሽላ ዝርያ በሄክታር 52 ኩንታል ምርት የሚሰጥ ሲሆን ከበፊቱ ማወዳደሪያ ዝርያ 30 በመቶ የምርት ብልጫ አለው። “ወለዲ” የተባለው የማሽላ ዝርያ ደግሞ በሄክታር 47 ኩንታል የሚሰጥ ሲሆን ከበፊቱ የማወዳደሪያ ዝርያ 29 በመቶ ብልጫ አለው። “ዳግም” የተባለው የማሽላ ዝርያ ሌላዉ ሲሆን በሄክታር 44 ኩንታል እንደሚሰጥ ተገልጿል።
ሌላው “እንቁ ዳጉሳ” በንጥረ ነገር ይዘቱ የተሻለ፣ ድርቅን መቋቋም የሚችል እና ፈጥኖ በመድረስ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችል ዓይነተኛ ሰብል ነው። ምርታማነታቸው አንደኛው የተሻሻለው ዝርያ በሄክታር 17 ነጥብ ሁለት ኩንታል፤ ሁለተኛው የተሻሻለው ዝርያ ደግሞ 20 ነጥብ ስምንት ኩንታል እንደሚሰጡ በጥናቱ ተረጋግጧል፡፡
ሌላኛው በምርምር የተለቀቀው የተሻለ ምርት መስጠት የሚችል “ዛቲ” የተባለ የጤፍ ዝርያ ነው፡፡ በሄክታር 25 ኩንታል ምርት የሚሰጥ እና ከተሻሻለው ማወዳደሪያ ዝርያ ደግሞ 20 በመቶ የምርት ብልጫ አለው ተብሏል። በስሪንቃ፣ ጃሪ፣ ጨፋ፣ ዓለም ከተማ እና ሰቆጣ አካባቢዎች መመረት የሚችል መሆኑም ተረጋግጧል፡፡
ቀድሞ የሚደርስ እና ድርቅን የሚቋቋም፣ የተሻለ ምርት መስጠት የሚችሉ “ሰርክ” እና “ለኪ” የተባሉ የአተር ዝርያዎችም ተለቀዋል፡፡ በሄክታር ከ28 እስከ 32 ኩንታል ምርት መስጠት የሚችሉ ናቸው። ከአካባቢው ማወዳደሪያ ዝርያ በ27 በመቶ የምርት ብልጫ አለው። በወረኢሉ፣ ጃማ፣ መቄት፣ አዴት እና ተመሳሳይ ቦታዎች መመረት የሚችል መሆኑም ተረጋግጧል። “የምስራች” የተባለው የምስር ዝርያ ደግሞ በምርምር የተለቀቀ ሲሆን በሄክታር 19 ኩንታል ምርት የሚሰጥ እና ከአካባቢው ማወዳደሪያ ዝርያ 57 በመቶ የምርት ጭማሪ እንዳለው አመላክተዋል።
(መልካሙ ከፋለ)
በኲር የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

“የመሃል ሜዳ ሆስፒታል 30 በመቶ እንኳ ግብዓቶች አልነበሩትም”የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም  ዕትምበሰሜኑ ጦርነት ከፍተኛ ውድመት የደረሰባቸውን የአጣዬ እና የወልድያ ሆስፒታሎችን ከሌሎች ...
18/08/2025

“የመሃል ሜዳ ሆስፒታል 30 በመቶ እንኳ ግብዓቶች አልነበሩትም”
የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

በሰሜኑ ጦርነት ከፍተኛ ውድመት የደረሰባቸውን የአጣዬ እና የወልድያ ሆስፒታሎችን ከሌሎች አጋሮቻቸው ጋር ሆነው ድጋፍ አድርገዋል:: በኮቪድ 19 ወቅትም ለሀገራቸው ድጋፋቸው አልተለየም፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተራድኦ ድርጅት ሆስፒታል አማካኝነት በመላው ሀገራችን የሚሰራጭ 40 ጫማ (feet) ኮንቴነር የሕክምና ቁሳቁስ እና አልባሳት ከሌሎች ኢትዮጵያዊያን ወገኖቻቸው ጋር በመሆን እረድተዋል:: ለመሃል ሜዳ አጠቃላይ ሆስፒታል እና በሰሜን ሸዋ ለሚገኙ አምስት አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ከ217 ሚሊዮን በላይ ብር የሚያወጡ ቁሳቁሶችን ድጋፍ አድርገዋል::

የተወለዱት በሰሜን ሸዋ ዞን መሃል ሜዳ (መንዝ መናገሻ) ነው:: ትምህርታቸውን እስከ ሰባተኛ ከፍል ድረስ በመሃል ሜዳ ተከታትለዋል:: ከዚያም ወደ አዲስ አበባ ከተማ አቅንተው እስከ 12ኛ ክፍል ድረስ ተምረዋል:: የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ ወደ አውስትራሊያ ሄደዋል:: በዚያ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በዱር እንስሳት ፎቶግራፍ ሳይንስ እና ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በማዕድን ጂኦሎጂ ይዘዋል፤ የዚህ ሳምንት የበኩር አንግዳችን የተሸሪክ ተመራማሪ እና ጸሐፊ፣ ፕሮፌሽናል የዱር እንሰሳ እና የተፈጥሮ የፎቶግራፍ ባለሙያ እንዲሁም ጂኦሎጂስት ልዑል ሰገድ እርገጤ ናቸው:: በማኅበረሰብ ግልጋሎት እና በጎ አድራጎት ዙሪያ ያደረግነው ቆይታ እነሆ:: መልካም ንባብ!

ወደ በጎ አድራጎት እና የማኅበረሰብ ግልጋሎት ሊገቡ ያስቻለዎት ምክንያት ምንድን ነው?
የሰው ልጅ ሲያድግ በአካባቢው የሚያየው ነገር ይኖራል:: ሌላ አካባቢ ደግሞ ሄዶ ሲኖር የተለየ ነገር ያያል:: የሚያየውን ነገር የአደገበት አካባቢ እንዲኖረው ይፈልጋል፤ መለወጥ የሚፈልጋቸው ነገሮችም ይኖራሉ:: ከሀገር ከወጣሁ ከሁለት ዓመት በኋላ አባቴ ነው የመጀመሪያውን ጥያቄ፡የጠየቀኝ፤ እሱም ሰው ስትሆን የአያቶችህን ትምህርት ቤት የመሃል ሜዳ ሆስፒታል እንዲሁም ማኅበረሰብህን እና ሀገርህን ኢትዮዽያን አትርሳ፤ በአቅምህ እርዳ ነበር ያለኝ:: እሱም በአቅሙ ለአካባቢው የአስፓልት መንገድ እንዲሠራ፣ ለከተማው የ24 ሰዓት የመብራት አገልግሎት እንዲያገኝ፤ በመንገድ፣ ሆስፒታል፣ ትምህርት እና የመሳሰሉት እንዲሟሉ ከኅብረተሰቡ ጋር ሆኖ ይታገል ነበር፤ በአጠቃላይ የአካባቢውን እና የመሃል ሜዳን እድገት እና ለውጥ ይመኝ ነበር:: እሱ ማድረግ የሚገባውን ነገር አድጎ ጨርሶ አልፏል።

እኔም አባቴ የሚያደርገው ነገር ከልጅነት ጀምሮ ከኔው ጋር አድጎ ስለነበር ዛሬ ላይ እንድደርስ አድርጎኛል:: ሆስፒታሉን እና በአካባቢው ያሉ ትምህርት ቤቶችን (በመሃል ሜዳ እና ዙሪያው) በሚቻለኝ አቅም ሁሉ እንድረዳ ጠይቆኛል:: በተለይ ሆስፒታሉ በኅብረተሰቡ እና በዎርልድ ቪዢን የተገነባ እንደሆነ፣ አባቴም በዚህ ሂደት ውስጥ ዋነኛውን ድርሻ ይዞ እንዳሠራ ፣ የሕክምና መሣሪያዎች ከውጪ ሲመጡ በኢትዮጵያ የመንግሥት ለውጥ እንደነበር እና እቃዎቹም ከሆስፒታሉ ሳይደርሱ ወደ ሌላ አካባቢ በጉልበት እንደተወሰዱ አባቴ ይነግረኝ ነበር:: ይህ ቁጭት እንዳለ ሆኖ ከሀገር ስወጣ ደግሞ የማየው በጎ ነገር ሁሉ በሀገሬ እንዲኖር እመኝ ነበር::
የመሃል ሜዳ አጠቃላይ ሆስፒታል ብዙ ነገሮች የሚጎሉት ነበር:: የሕክምና መሣሪያዎች አልተሟሉለትም ነበር:: አልጋዎቹ ጥቂት እና ካርቶን የተነጠፈባቸው ነበሩ:: በአጠቃላይ ተገቢውን አገልግሎት ለማኅበረሰቡ እየሰጠ አልነበረም::

የስረደጅ የመጀመሪያ ደረጃ ሙሉ ሳይክል ት/ቤት ደግሞ ዓመታዊ በጀቱ 4000 ብር ብቻ ነበር፤ ይህም ለቾክ እና ለሰሌዳ ማጥፊያ መግዣ ብቻ የሚመደብ ነው:: መንዝ ጌራ ምድር ወረዳ የሚገኙ ሌሎች አራት አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችም እንደዚሁ ተመሳሳይ ችግር ነበረባቸው፤ ትምህርት ቤቶቹ በጣም ከከተማ የራቁ ናቸው፤ አይደለም ለመኪና ለበቅሎ እንኳን ጥሩ የሚባል የጠጠር መንገድ የላቸውም፤ አራቱም ት/ቤቶች ከ200- 500 ብር ነው ዓመታዊ በጀታቸው:: በዚህ ምክንያት መምህራንም ተማሪዎችም ይቸገሩ ነበር:: ይህንን ሀገር ቤት እያለሁ አስተውል ነበር:: ነገር ግን ምንም ጠንካራ ሠራተኛ ብሆን ይህን ሥር የሰደደ ችግር ለመፍታት አቅም አልነበረኝም::

ለመሃል ሜዳ አጠቃላይ ሆስፒታል እና ለሌሎች በአካባቢው ለሚገኙ ትምህርት ቤቶች ድጋፍ አድርገዋል፤ ድጋፉን እንዴት ጀመሩት? የነበረውስ ሁኔታ ምን ይመስል ነበር?
አውስትራሊያ ገብቼ ሁለት ዓመት እንደቆየሁ ትምህርቴን እየተማርኩ ጥሩ ሥራ ያዝኩ:: አባቴ ይለኝ የነበረው ነገር አልተረሳኝም፤ ቃል የዕምነት እዳ ስለሆነ:: በዚህ በውጭ ካሉ የአካባቢው ተወላጆች ጋር ምን ማድረግ እንችላለን በሚል ውይይቶችን አካሄድኩ:: አብዛኛው ሰው በራሱ ሕይወት ላይ ነው ማተኮር የሚፈልገው:: ስለሆነም ተባባሪ ማግኘት ከባድ ነበር:: በዚህ ምክንያት ብቻየን መንቀሳቀስ ጀመርኩ::

በመጀመሪያ መሃል ሜዳ እና አካባቢው ቀዝቃዛ ነው፤ ሞቀ ከተባለ እስከ 16 ዲግሪ ሴንቲግሬድ ነው፤ በአንዳንድ ወቅት ደግሞ ከዜሮ በታች ስድስት ይወርዳል፤ የመሃል ሜዳ አጠቃላይ ሆስፒታል ማዋለጃው ማሞቂያ የለውም፤ በዛ ወቅት የተወለዱ ሕጻናት በብዛት ይሞታሉ:: የማዋለጃ እና የታካሚ አልጋዎች በቁጥር ትንሽ እና እንደ ድሃ ልብስ የተቀደዱ ነበሩ:: ጉዳዩ መፈታት የነበረበት በመንግሥት ነበር፤ መንግሥት አልደረሰለትም:: በሰሜኑ ጦርነትም ጉዳት ደርሶበታል፤ ተዘርፏል፤ ኮርኒስ ሳይቀር ቀዳደው ነው የሄዱት:: ስለሆስፒታሉ እና መሟላት ስላለባቸው ነገሮች የሆስፒታሉን አመራሮች ሳማክር፣ በፎቶግራፍ የተደገፉ መረጃዎችን ላኩልኝ::

በቅድሚያ የማዋለጃ ክፍል ማሞቂያ መሣሪያዎችን ነው መሰብሰብ የጀመርኩት:: ቀጥሎም ሌሎች የሕክምና መሣሪያዎችን ለማሰባሰብ የዘርፉ ዕውቀት ያስፈልጋል:: በመሆኑም ቤተሰቦቼ የመሃል ሜዳ ጠቅላላ ሆስፒታል ነርሲንግ ዳይሬክተር ከሆኑት ከአቶ መርከብ ባልከው ጋር አስተዋወቁኝ:: ሆስፒታሉ 30 በመቶ እንኳ ግብዓቶች አልነበሩትም፤ ይሄንን በፎቶ አስደግፈው መረጃ ሰጡኝ:: በባዶ ነበር ያንን ትልቅ ስም የያዘው:: በዋናነት ከአቶ መርከብ ጋር እየተመካከርን የሚያስፈልጉትን ቁሳቁሶች ሰበሰብኩ::

ለመሃል ሜዳ አጠቃላይ ሆስፒታል ድጋፍ ከተደረጉት የህክምና ዕቃዎች መካከል ዳይሌሲስ ማሽን ብዛት ሦስት፣ ዲጂታል ኤክስሬይ ዊዝ ፍሮሎስኮፒ ብዛት አንድ፣ አንስቴዥያን ማሽን ብዛት ሰባት፣ የሕፃናት ሟሞቂያ ብዛት 41፣ ዘመናዊ የአምቡላንስ አልጋ ብዛት ሁለት፣ ኢንፊውቭን ማሽን ብዛት 11፣ አይ.ሲ.ዩ ማሽን ብዛት 14፣ ደረጃቸውን የጠበቁ በኤሌክትሪክ በቻርጅ እና በሪሞት የሚሠሩ አልጋዎች ብዛት 43፣ አልትራሳወንድ ብዛት አምስት፣ አይ .ሲ.ዩ. ማሽን ብዛት አምስት፣ ኢኮ እና ኢሲጅ ማሽን ብዛት ስድስት፣ ዊልቸር፣ ልዩ ልዩ ክራንች፣ አልጋዎች፣ ደረጃ ሰባት (seven star) የህሙማን አንሶላ፣ ዘመናዊ ፍራሾች እና ሌሎች ብዛት ያላቸው የህክምና እቃዎች ይገኙበታል::

ትምህርት ቤቶቹን በተመለከተ ደግሞ እኔ ምንም ከተማ ብማርም ገጠር ላይ ያለውን ችግር አውቃለሁ፤ እሱን መሠረት አድርጌ ምን ምን ድጋፍ ትፈልጋላችሁ ብዬ ጠየቅኩ:: ትምህርት ቤቶቹን ለማገዝ ሀሳብ ሳቀርብላቸው አላመኑኝም ነበር፤ የምነግራቸው ነገርም ቅዠት ነበር የሚመስላቸው:: እንኳን በገጠሩ በከተማ ባሉ ትልልቅ ትምህርት ቤቶችም መደረግ የማይችሉ ነገሮችን ነበር ሳነሳላቸው የነበረው:: የማይሆን ተስፋ እንደማላሲዛቸው ነግሬ አግባባኋቸው:: “ስናይ እናምናለን” የሚል አቋም ነበራቸው:: ከእነሱ ጋር እየተመካከርኩ አስፈላጊ ግብዓቶችን መሰብሰብ ቀጠልኩ:: እነሱ ጠይቀውኝ የነበረው እንደ ቾክ፣ እስክርቢቶ፣ ደብተር ከተቻለ ጫማ እና ልብስ ነበር:: እኔ ያሰብኩት እንደ ዲጂታል ላይብራሪ ያሉ ትልልቅ ነገሮችን ነው:: ይህ ለእነሱ ሕልም ነው:: በእርግጥ በአብዛኛው የሀገራችን ክፍል ይህ እንደ ቅዠት ሊቆጠር ይችላል:: ትምህርት ሚኒስቴር ውስጥ ያሉ ሰዎች ሳይቀር ጉዳዩን ሲሰሙ ትንሽ ተገርመው ነበር፤ ምክንያቱም አካባቢው እጅግ በጣም ከከተማ ሩቅ ነው::

በፎቶ የምልክላቸውን ቁሳቁሶች እያሳየሁ፣ ሞራል እየሰጠሁ ቆየሁ:: መብራት ስለሌለው የፀሐይ ኃይል ማመንጫ አሟላሁ፤ ከዚያ ዴስክቶፖች፣ ላፕቶፖች፣ ፕሮጀክተር፣ ቴሌቪዢን ሞኒተር (እስከ ስምንተኛ ክፍል ላለው ትምህርት ቤት) ነጭ ሰሌዳ፣ የስፖርት ቁሳቁስ አሰባስቤ አስረከብኩ:: ለተማሪዎችም መለያ ልብሶችን አቀረብኩ::
በአጠቃላይ ለመሃል ሜዳ አጠቃላይ ሆስፒታል፣ ለስረደጅ የመጀመሪያ ደረጃ ሙሉ ሳይክል ትምህርት ቤት እና ሌሎች ተጨማሪ አራት አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ከ217 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጡ ቁሳቁሶች ድጋፍ ተደርጓል:: ይህም ሌሎች ወጪዎችን ሳይጨምር ነው::

ድጋፉን የሚያሰባስቡበት መንገድ ምን ይመስላል?
ከዚህ በፊት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ተራድኦ ድርጅት ሥር የቤተክርስቲያኗም ልጆች ሆነ ከቤተክርስቲያን ውጪ ያሉ ልጆች ተሰባስበን 40 ጫማ ኮንቴነር መድሐኒት በኮቪድ ወቅት ልከን ነበር:: በኋላ በሰሜኑ ጦርነት ውድመት ለደረሰባቸው ለአጣዬ እና ለወልድያ ሆስፒታሎች ድጋፍ አድርገናል:: ይህ ተሞክሮ ነበረኝ::

የመሃል ሜዳ አጠቃላይ ሆስፒታልን እና ትምህርት ቤቶቹን ግን በግሌ ነው ድጋፉን የማደርገው:: አብዛኞቹን ቁሳቁሶች በጨረታ ነው የምገዛቸው:: አንዳንድ ጊዜ እርዳታ እጠብቃለሁ:: ብዙ መርዳት የሚፈልጉ ሰዎች እና ድርጅቶች አሉ:: ነገር ግን ይሄን የአወኩት በግሌ ከ90 ከመቶ በላይ ቁሳቁሶቹን ገዝቼ ከጨረስኩ በኋላ ነው:: ከጅቡቲ ቃሊቲ ከዚያ እስከ መጨረሻ መዳረሻው ቁሳቁሶቹን ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ አውጥቶ ያጓጓዘልኝ ደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ነው::

እቃው ወጪው ብቻ ሳይሆን መሰብሰቡም ብዙ ውጣ ወረድ አለው:: ከአንድ ግዛት ወደ ሌላ ግዛት በመኪና ከ1700 ኪሎ ሜትር በላይ እየተጓዝኩ ነበር የምሰበስበው፤ ምክንያቱም የአውሮፕላን ወጪ እጅግ ውድ ስለሆነ ማለት ነው፤ ደርሶ መልስ 3400 ኪሎ ሜትር እያሽከረከርኩ እጓዝ ነበር:: ሀገሩ ሰላም፣ መንገዱ ጥሩ፣ የምነዳቸው መኪናዎች ምቹ ስለሆኑ እንጂ 3400 ኪሎ ሜትር ቀላል አይደለም፤ ከኢትዮጵያ ግብጽ መጓዝ እንደማለት ነው:: በዚህ መንገድ ተሰብስበው ነው ለህዝባችን አገልግሎት እንዲሰጡ የተደረገው::

በዚህ ሁሉ ሂደት የገጠሙ ችግሮች ምን ምን ናቸው?
አድካሚ ረዥም ርቀት ተጓጉዞ ቁሳቁሶችን መሰብሰቡ አንዱ አስቸጋሪ ነገር ነበር:: ትልቁ ችግር ግን ኢትዮጵያ ውስጥ ከመጣ በኋላ ነው:: ሁሉም ተቋማት የየራሳቸው መመሪያ እና አሠራር አላቸው:: ነገር ግን አብዛኞቹ ተቋማት የተንዛዛ እና ምቹ ያልሆነ ቢሮክራሲ አላቸው:: እቃዎቹ ጅቡቲ ደርሰው የመጨረሻ መዳረሻቸው ለመግባት ስምንት ወራት ነው የፈጀባቸው:: በስምንት ወራት ውስጥ ብዙ አገልለግሎቶች መስጠት እየቻሉ በአየር ላይ ቆይተዋል::

ትልቁ ችግር የነበረው ጉምሩክ ላይ ሳይሆን የኢትዮጵያ ምግብ እና መድሃኒት ቁጥጥር ባለሥልጣን ላይ ነበር:: እቃዎቹ ያገለገሉ ስለነበሩ ባለሥልጣኑ ባለው መመሪያ ምክንያት ነው ችግሩ የተፈጠረው:: ተነጋግሮ ነገሮችን በአጭሩ መፍታት እየተቻለ ነገር ግን ሞራል የሚነኩ እና ተነሳሽነትን የሚያሳጡ ሁኔታዎች ነበሩበት:: ጥቅም የመፈለግ አዝማሚያዎችም ነበሩ፤ የተቋሙ ኃላፊዎች በመጨረሻ ስለ ጉዳዩ ከሰሙ በኋላ ወዲያው ተፈጣጥኖ አልቋል:: ትምህርት ሚኒስቴር እና የጤና ሚኒስቴር ላይ ምንም ችግር አልገጠመኝም:: ጉምሩክ ላይም የተወሰነ ቢሆንም ብዙ ችግር አልነበረም፤ ነገር ግን ከቀበሌ ጀምሮ ኃይለኛ ማስረጃ ይጠይቃሉ:: ለወደፊቱ ብዙ ነገሮችን ተምሬበታለሁ::

በሌላ በኩል የመሃል ሜዳ እና አካባቢው ማኅበረሰብ “የሆስፒታሉ አምባሳደር ይሁን!” የሚል ሀሳብ አንስቶ ከቃለ ጉባዔ ጋር ጉዳዩ ወደ ክልል ተልኮ ነበር:: ነገር ግን እስካሁን ምላሽ አላገኘም:: ለሆስፒታሉ የበለጠ ድጋፍ ለማግኘት እና ተዓማኒነትን ለማግኘት እውቅናው አስፈላጊ ነው:: የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱም የእውቅና ደብዳቤ ሊሰጠኝ የክልል ማረጋገጫ ተጠይቆ እስካሁን ምላሽ አልተሰጠውም፤ ይህ በፍጥነት ሊፈጸም ይገባል እላለሁ::
መንግሥት በውጪ ያሉ ሀገራቸውን መርዳት የሚፈልጉ ሰዎችን የሚያማርሩ አሠራሮችን ማስተካከል አለበት:: ሰው ተማሮ ከዚህ በኋላ በጭራሽ ብሎ መውጣት የለበትም:: ይህ ከሆነ በዕውቀት፣ በገንዘብ፣ በቁሳቁስ እና በሌሎች ሀብቶች ሀገራቸውን ለመርዳት፣ ሕዝባቸውን ከችግር ለማላቀቅ የሚፈልጉ ብዙ ዜጎች አሉ:: ሀገራችንም በደንብ ካገዝናት ከችግሯ የምትላቀቅበት ጊዜ ሩቅ አይሆንም::

ለወደፊት ያሰቡት ነገር ካለ?
እንደ ፈጣሪ ፈቃድ በሆስፒታሉ እና በትምህርት ቤቶቹ እንዲሁም በሌሎች የሕዝብ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት የተለያዩ ነገሮችን ለማድረግ በእቅድ ይዣለሁ:: ከታች ያሉ ተቋማት ወደ ላይ የሚያድጉባቸውን ሥራዎች ለመሥራት አስቤያለሁ፤ ለምሳሌ የጤና ኬላዎችን ወደ ጤና ጣቢያ ከዚያም ወደ ክሊኒክ እያለ ወደ ላይ ማሻሻል አንዱ ዓላማዬ ነው:: ከመሃል ሜዳ አልፎ ወረዳ እና ክልል ላይ ለመሥራት እቅዱ አለ፤ እየተነጋገርናቸው ያሉ አካላትም አሉ::
“ገሎ መፎከር ይሻላል” እንደሚለው የሀገሬ ሰው መሬት ላይ ወርዶ በተግባር ሲሠራ ቢወራ ይሻላል ብየ ነው እንጂ ብዙ ነገሮች አሉ:: በታሪክ፣ በሃይማኖት፣ በባሕል፣ በዱር ሃብት፣ በተፈጥሮ ሃብት፣ በመልክዓ ምድር እና በሌሎች ዘርፎች ላይ እንደ ክልል ብቻ አይደለም እንደ ሀገር ብዙ ነገር እያሰብኩ ነው:: ትልልቅ ፕሮጀክቶች አሉ:: እነዚህ ፕሮጀክቶች መሬት ላይ ይወርዳሉ ብየ አስባለሁ::

ሥራዎች ሲሠሩ ለብቻ ከሚሆን በትብብር ቢሆን የበለጠ ስኬታማ ይሆናሉ:: ሀገራቸውን እንዴት ላግዝ ሕዝቤን እንዴት ልርዳ ብለው የሚያስቡ ብዙ በውጪ እና በሀገር ውስጥ ያሉ ሰዎች አሉ:: ከእነሱ ጋር በመጣመር የተሻለ ሥራ መከወን ይቻላል:: መንግሥት ቢሮክራሲውን ክፍት ካደረገው የበለጠ ለመሥራት ሀሳቡ አለ:: ሀገራችን ትልቅ አቅም እና ሀብት አላት:: አብዛኞቹ ሀገራት ላይ ብትሄድ ብዙ ነገር አንድ ላይ አታገኝም፤ ኢትዮጵያ ግን ባሕሉን፣ መልክዓ ምድሩን፣ ታሪኩን፣ ሃይማኖቱን እና ሌሎች እሴቶችን በአንድ ላይ የምታገኝባት ሀገር ናት:: ለምሳሌ ኬንያ ብትሄድ የዱር እንስሳትን እና የማሳይ ጎሳን ባሕል አይተህ ነው የምትመለሰው:: ግብጽ ብትሄድ ፒራሚድ ነው የምታየው:: እስራኤል ብትሄድ ታሪክ እና ሃይማኖት ወይም ቴክኖሎጂ ነው የምታየው:: ኢትዮጵያ ግን ከዚህ በተጻራሪ ሁሉንም ነገር የምታገኝባት ናት:: ይህ በክልል የታጠረ አይደለም፣ በመላው ኢትዮጵያ ነው ያለው::

የፀጥታው ሁኔታ ችግር ከመፍጠሩ ውጪ ለመሥራት ምቹ ሁኔታ አለ:: ፀጥታው ከተስተካከለ ትልልቅ ፕሮጀክቶች አሉ፤ የሚታተሙ መጻሕፍትም ዝግጅታቸው ተጠናቋል:: እስከ 30 ዓመት የፈጁ በተለያዩ መስኮች ያተኮሩ ጥናቶችም ይቀርባሉ:: እነዚህ ሲወጡ ለሀገር ዕድገት የራሳቸውን አስተዋጽኦ ያበረክታሉ:: በውጪም በሀገር ውስጥም ላሉ አቅሙ ላላቸው ኢትዮጵያዊያን ሕዝባችንን ከድህነት፣ ከመሃይምነት፣ ከስደት እና ሌሎች ችግሮች ተባብረን እናውጣው ስል መልዕክቴን አስተላልፋለሁ::

የሚያመሰግኗቸው አካላት ወይም ሰዎች ካሉ?
በቅድሚያ ሁሉን ላደረገ ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይግባው፤ በመቀጠል በዚህ ውጣ ውረድ ውስጥ እስከመጨረሻው ከጎኔ ላልተለዩኝ ለሃይማኖት አባቶቼ እና ለመላው ቤተሰቤ ላቅ ያለ ምስጋናዬን አቀርባለሁ። በተጨማሪ ለዶ/ር አየለ ተሾመ የኢትዮዽያ ጤና ሚኒስቴር ዴታ፣ ለአቶ ጣልባቸው በቀለ የመንዝ ጌራ ምድር ዋና አስተዳዳሪ፣ ለአቶ ጌታቸር ባይሳሳው የመሃል ሜዳ ከተማ አስተዳዳሪ፣ ለአቶ ወርቅነህ ዘውዴ የመሃል ሜዳ አጠቃላይ ሆስፒታል ሥራ አስኪያጅ፣ ለአቶ ወንድወሰን አድማሴ የመንዝ ጌራ ምድር ወረዳ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል እና በየደረጃው ለአሉ የሚንስቴር፣ የወረዳ፣ የክልል እንዲሁም የዞን መሥሪያ ቤት ኃላፊዎች ላቅ ያለ ምስጋናዬን አቀርባለሁ። በመጨረሻም ዶ/ር ቴዎድሮስ ክፍለ ዮሃንስ በደ/ብርሃን ዩንቨርስቲ የአስራት ወልደየስ ጤና ሳይንስ ካምፓስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ እንዲሁም ጠቅላላ ሐኪም፣ አቶ ማሙየ መንገሻ የደ/ብርሃን ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ዲን፣ አቶ መርከብ ባልከው የመሃል ሜዳ ጠቅላላ ሆስፒታል ነርሲንግ ዳይሬክተር እና አቶ ሽፈራው ግርማ የስረደጅ የመጀመሪያ ደረጃ ሙሉ ሳይክል ት/ቤት ርዕሰ መምህር፣ ላደረጉልኝ የማማከር እገዛ ማመስገን እፈልጋለሁ::

ስለነበረን ቆይታ እናመሰግናለን!
እኔም አመሰግናለሁ!

(ሳባ ሙሉጌታ)
በኲር የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

የአዲስ ዓመት አብሳሪዎች  የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም  ዕትምአሮጌው ዓመት በአዲስ ሊተካ ከወር ያነሰ ጊዜ ቀርቶታል:: ደብረ ታቦር (ቡሄ) ሻደይ፣ አሸንድዬ፣ ሶለል፣ የእንግጫ ነቀላ እና...
18/08/2025

የአዲስ ዓመት አብሳሪዎች
የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

አሮጌው ዓመት በአዲስ ሊተካ ከወር ያነሰ ጊዜ ቀርቶታል:: ደብረ ታቦር (ቡሄ) ሻደይ፣ አሸንድዬ፣ ሶለል፣ የእንግጫ ነቀላ እና የከሴ አጨዳ በዓላት እና ክዋኔዎች ደግሞ የአዲስ ዓመት መቃረብን የሚያበስሩ ናቸው:: የዝናባማው ወራት ማብቂያ ነጋሪት፣ የአዝመራው መድረስ ምልክት ተደርገውም ይወሰዳሉ::
በየዓመቱ በቡሄ ተጀምሮ በእንግጫ ነቀላ የሚጠናቀቀው የነሐሴ ወር በዓላት ዘንድሮም በተለያዩ አካባቢዎች በተለያዩ ክዋኔዎች ይከበራሉ:: ለመሆኑ የበዓላቱ አከባበር እና ፋይዳ ምንድን ነው? የትንታኔያችን አንኳር ጉዳይ ነው::

ቡሄ
የክረምቱ ጨለማ ተገፎ የብርሐን ወጋገን ሲፈነጥቅ፣ ሰማይ ከጭጋጋማነት ወደ ብሩሀማነት ሲለወጥ ከሚከበሩ በዓላት መካከል የቡሄ በዓል ይገኝበታል:: ቡሄ በአማራ ክልል አብዛኛው አካባቢዎች በሙልሙል ዳቦ እና በተለያዩ ዝግጅቶች የሚከበር ቢሆንም በደብረታቦር ከተማ አስተዳደር ግን በልዩነት ይከበራል:: ሙል ሙል ዳቦ መድፋት፣ ጅራፍ መገመድ እና ማጮኽ፣ ችቦ ማብራት የበዓሉ ድምቀቶች ናቸው::
የደብረታቦር ከተማ አስተዳደር ዓመታዊ የቡሄ በዓልን በድምቀት ለማክበር መዘጋጀቱን የባህልና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊው አቶ አለበል ደመላሽ ለበኵር ጋዜጣ በስልክ አስታውቀዋል:: ቡሄን ጨምሮ ሌሎች ሃይማኖታዊ እና ሕዝባዊ በዓላት በየዓመቱ እንደሚከበሩ የገለጹት አቶ አለበል፣ እነዚህም ለቱሪዝሙ ዘርፉ መነቃቃት ጉልህ ሚና ማበርከታቸውን ተናግረዋል:: የአካባቢውን ነዋሪ የገቢ ምንጭ የማነቃቃት ሚናውም ከፍተኛ ነው:: ማኅበራዊ መስተጋብር እንዲጠናከርም የማድረግ አጋጣሚ ከፍ ያለ መሆኑን ተናግረዋል:: ይህም በዓሉን ለመታደም ከተለያዩ አካባቢዎች ወደ ደብረ ታቦር በርካታ ሕዝብ የሚገባ በመሆኑ ነው ይላሉ::

የዘንድሮው የቡሄ በዓልም ሳይበረዝ እና ሳይከለስ ታሪካዊ አከባበሩን ተከትሎ በድምቀት እንደሚከበር ተናግረዋል:: ለዚህም አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅትም መጠናቀቁን ጠቁመዋል:: የበዓሉ መነሻ ሃይማኖታዊ ይዘት ያለው መሆኑ ከደብረ ታቦር ርእስ አድባራት ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ጋር በጋራ ለማዘጋጀት መታቀዱንም ተናግረዋል:: ከዋናው የቡሄ ክብረ በዓል ቀደም ብሎ የፓናል ውይይት እና የጎዳና ላይ ትርኢት እንደሚካሄድም ታውቋል:: ከቡሄ በዓል አንድ ቀን ቀደም ብሎ ደግሞ የእቴጌ ጣይቱ የልደት ቀን በመሆኑ ታስቦ እንደሚውል አስታውቀዋል:: በዓሉም በሰላም እንዲከበር ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሠራ ነው ያሉት አቶ አለበል፣ ሕዝቡም የሚታወቅበትን እንግዳ ተቀባይነት በተግባር እንዲያሳይ ጥሪ አቅርበዋል::

ሻደይ፣ አሸንድዬ እና ሶለል
ሻደይ፣ አሸንድዬ እና ሶለል በዋግ ኸምራ ብሄረሰብ አስተዳደር እና በሰሜን ወሎ ዞን በድምቀት የሚከበሩ በዓላት ናቸው:: እነዚህ በዓላት ሃይማኖታዊ መሠረትነት ያላቸው በወንዶች ታጅበው በልጃገረዶች ብቻ የሚከወኑ በዓላት ናቸው:: ሁሉም በዓላት በሀገር ውስጥ አልባሳት እና ጌጣጌጦች ተውበው የሚከወኑ በዓላት ናቸው:: ልጃገረዶች በዓላቱን የሚያከብሩት ጸጉራቸውን ሹሩባ ተሠርተው፣ አካባቢያቸውን የሚገልጹ ነጫጭ አልባሳትን ለብሰው እና ጫማዎችን ተጫምተው፣ ከአንገታቸው ላይ የተለያዩ ጌጣ ጌጦችን አጥልቀው፣ ከወገባቸውም ለምለም ሳር (ቄጤማ) አስረው ነው:: የተለያዩ ጣዕመ ዜማዎች የበዓላቱ ሌላው ድምቀት ናቸው::

በዋግ ኸምራ ብሄረሰብ አስተዳደር የሚከበረውን የሻደይ በዓል ጨምሮ አሸንድዬ እና ሶለል በዓላት የፍልሰታ ጾምን መገባደጃ ተከትሎ የሚከበሩ በዓላት ናቸው:: በአጸደ ተፈራ (ዶ/ር) በተሰናዳው የሻደይ መጽሔት ላይ “ፍልሰታ” የቅድስት ድንግል ማርያም ስጋ ከጌቴሰማኒ ወደ ገነት መፍለሱን፣ በኋላም በገነት በእፀ ሕይዎት ስር ከነበረበት መነሳቱን የሚያመላክት እንደሆነ ተጠቁሟል::

ሻደይ በልጃገረዶች ብቻ የሚከወን ሲሆን የወንዶች ሚና ልጃገረዶችን ከበው ጥበቃ ማድረግ ነው:: የቀድሞው የዋግ ኽምራ ሀገረ ስብከት የስብከት ወንጌል መምሪያ ኃላፊ የነበሩት መጋቤ ምስጢር ገብረሕይዎት ኪዳነማርያም “በዓሉ በልጃገረዶች የሚከበረው በሔዋን ምክንያት የተዘጋው ገነት በእመቤታችን አማካኝነት በመክፈቱ ነው” ማለታቸውን የዋግ ኸምራ ብሄረሰብ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም የማኅበራዊ ትስስር ገጽ ያሳያል:: ይህም የበዓሉ ሃይማኖታዊ መሠረትነት ማሳያ ነው::

በሻደይ በዓል ቀሚስ፣ መቀነት፣ ጫማ እና ሻሽ ይለበሳል:: የፀጉር ሥሬቱም ግልብጭ፣ አንድ እግራ፣ ግጫ፣ አልባሶ፣ ሳዱላ፣ ጋሜ እና ቁንጮ፣ ጐፈሬ እና ከእንጨት የተሠራ ማበጠሪያን ያጠቃልላል:: እንደ ኩል፣ ድሪ፣ ድኮት፣ አልቦ፣ ዛጎል፣ ጠልሰም፣ መስቀል፣ አምባር፣ ማርዳ፣ ድባ፣ አሸን ክታብ፣ ስቃጫ… የመሳሰሉት ጌጣጌጦችም የበዓሉ ድምቀቶች ናቸው::

ሻደይ በዋግ ኸምራ ብሄረሰብ አስተዳደር በሚገኙ አካባቢዎች ለሚኖረው ሕዝብ የሚፈጥረው ማኅበራዊ መስተጋብር ከፍተኛ መሆኑን ያስታወቁት ደግሞ የብሄረሰብ አስተዳደሩ ባሕልና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ አቶ እዮብ ዘውዴ ናቸው:: ሻደይ ዘንድሮም ባሕላዊ ገጽታውን ሳይለቅ ለማክበር ከወረዳ ጀምሮ የቅድመ ዝግጅት ሥራ ሲከናወን መቆየቱን አቶ እዮብ አስታውቀዋል:: በዓሉን በተሳካ ሁኔታ ለማክበር ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት እየተሠራ ነው ብለዋል::

ሕዝቡም ባህሉን እና ወጉን ጠብቆ እንዲያከብረው ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ መሆኑን መምሪያ ኃላፊው ጠቁመዋል:: ”ሻደይ ከድንግል ማርያም ማረግ ጋርም የተያያዘ በመሆኑ በዓሉ በቤተ ክርስቲያናትም በድምቀት ይከበራል” ያሉት አቶ እዮብ የሃይማኖት አባቶችም አከባበሩን አስመልክተው ምክረ ሐሳቦችን እንዲሰጡ እየተደረገ ነው ብለዋል::

እንግጫ ነቀላ እና ከሴ አጨዳ
የአዲስ ዓመት መቃረብ ዋናው ምልክት እንግጫ ነቀላ እና ከሴ አጨዳ ነው:: ይህ ባሕላዊ ክዋኔ በምዕራብ እና ምሥራቅ ጎጃም ዞኖች በሚገኙ ወረዳዎች በስፋት የሚዘወተር እንደሆነ የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ መረጃ ያሳያል::

የእንግጫ ነቀላ በዓል ልክ እንደ ሻደይ፣ አሸንድዬ እና ሶለል ሁሉ በወንዶች ጠባቂነት በልጃገረዶች የሚከወን በዓል ነው:: ልጃገረዶች በየመንደራቸው ቡድን በመመስረት እንግጫ ለመንቀል በሀገር ባህል አልባሳት ተውበው እንግጫው ወደሚገኝበት መስክ ይወርዳሉ፤ እንግጫም ይነቅላሉ፤ ከሶሪት እና አደይ አበባ ጋር በመጎንጎን ለስጦታ ያዘጋጃሉ:: በበዓሉ ቀንም የተጎነጎነውን እንግጫ ይዘው በየቤቱ በመሄድ “እንኳን አደረሳችሁ!” በማለት በስጦታ መልክ ያበረክቱታል:: በስጦታ የተበረከተው የእንግጫ ጉንጉንም በየቤቱ ምሰሶ ወይም አጥር ላይ የመልካም ዘመን መምጣት ምሳሌ ተደርጎ ይታሰራል:: ይህ የሕዝቡን የእርስ በእርስ የመጠያቅ ባሕል በእጅጉ እንደሚያሳድገው ይታመናል::

የድንቅ ባህል ማሳያዎቻች እንዴት ይከበሩ?
የአማራ ክልል ባሕል እና ቱሪዝም ቢሮ በነሐሴ እና ጳጉሜ ወራት የሚከበሩ ሃይማኖታዊ እና ባሕላዊ በዓላትን ምክንያት በማድረግ ነሐሴ 02 ቀን 2017 ዓ.ም መግለጫ ሰጥቷል። መግለጫውን የሰጡት የቢሮ ኃላፊው መልካሙ ጸጋዬ ናቸው:: በመግለጫቸውም “ባሕላዊ ዕሴቶቻችን ለዘላቂ ሰላማችን የነበርንበት፣ ያለንበት እና የምንደርስበት” በሚል መሪ መልዕክት በዓላቱ እንደሚከበሩ አስታውቀዋል:: የመሪ ቃሉ መልዕክትም በዓላቱ አስቀድመው የነበሩን፣ አሁንም እየተከወኑ ያሉ እና ወደፊትም ተጠብቀው ለትውልድ የሚተላለፉ መሆናቸውን የሚገልጽ መሆኑን ተናግረዋል::
ክልሉ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ጎብኝዎች መዳረሻ መሆኑን ጠቁመዋል:: የሻደይ፣ አሸንድዬ፣ ሶለል፣ ቡሔ፣ እንግጫ ነቀላ እና የከሴ አጨዳ ክብረ በዓላት ደግሞ የክልሉ ሕዝብ ባሕል፣ ታሪክ፣ ትውፊት እና ቅርስ ማሳያ እና ማስመስከሪያ መሆናቸውን አስታውቀዋል::

ከቡሄ ጀምሮ መከበር የሚጀምሩት የነሐሴ ወር ሃይማኖታዊ እና ባሕላዊ በዓላትም በታሪክ ሂደት በተቀረጹበት የተለየ እና ተወዳጅ ክዋኔ ምክንያት ሚሊዮኖች በጉጉት እና በፍቅር የሚጠብቋቸው እና በቦታው ተገኝተው የሚያከብሯቸው ድንቅ ሀብቶች መሆናቸውን ተናግረዋል::
የሻደይ፣ አሸንድዬ፣ ሶለል፣ ቡሔ፣ እንግጫ ነቀላ እና የከሴ አጨዳ ክብረ በዓላት ላይ የሚታደሙ የኅብረተሰብ ክፍሎች በዕድሜ ወይም በጾታ የተገደቡ ቢሆነም ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል የሚያከብራቸው በዓላት መሆናቸውን ተናግረዋል:: ማጀብ፣ ማስተናገድ እና መመረቅ ከእያንዳንዱ የኅብረተሰብ ክፍል የሚጠበቅ መሆኑን አንስተዋል::
የሻደይ፣ አሸንድዬ፣ ሶለል፣ እንግጫ ነቀላ እና የከሴ አጨዳ ክዋኔዎች ልጃገረዶች ባሕላቸውን እና ትውፊታዊ አደራቸውን በአደባባይ ለተተኪዎች የሚያጋሩበት ነው:: ነፃነታቸውን የሚያውጁበትም እንደሆነ ተናግረዋል:: አስደናቂ ባሕላዊ ትዕይንቶችን ለዓለም ለማሳየት፣ የየአካባቢው ባህላዊ ምግብ እና መጠጥ የሚገለጥባቸው በዓላት ናቸው::

ቡሔ በደብረ ታቦር፣ ሻደይ በዋግ ኽምራ፣ አሸንድዬ እና ሶለል በሰሜን ወሎ፣ የከሴ አጨዳ እና እንግጫ ነቀላ በምሥራቅ ጎጃም በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚከበሩ አስታውቀዋል:: የበዓላቱ የማጠቃለያ ዝግጅትም እንደ ክልል በባሕር ዳር ከተማ እንደሚከናወን አስታውቀዋል :: ለበዓላቱ በድምቀት መከበርም ከሐምሌ ጀምሮ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸውን ገልጸዋል:: ለዝግጅቱም ቢሮው የተቀናጀ የግብዓት እና ሙያዊ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል::
እንደ ቢሮ ኃላፊው መግለጫ በዓላቱ የክልሉን ሕዝብ ባሕል እና እሴት በመጠበቅ ትውልዱ በጠንካራ ማንነት ላይ እንዲቆም ያግዛሉ:: በዓላቱ ለቱሪዝም ዘርፉ መነቃቃት ከሚያበረክቱት አስተዋጽኦ በተጨማሪም ምጣኔ ሀብታዊ መነቃቃት ይፈጥራሉ:: ይህም የበዓሉ ቀጥተኛ ባለቤት የሆነውን ማኅበረሰብ በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ያደርጋል::

ባሕልና ቱሪዝም ቢሮ በሚፈለገው ልክ እንዲለሙ እና እንዲጠበቁ ሠፊ ሥራዎች መሥራቱን አቶ መልካሙ ተናግረዋል:: ይህም በዓላቱ ለቀጣይ ትውልድ እንዲተላለፉ እና ወደ ቱሪዝም ገበያው እንዲገቡ ያግዛል:: ክብረ በዓላቱ በሚከናወኑባቸው አካባቢ ብቻ ተወስነው የቆዩትን የቡሔ፣ የሻደይ፣ አሸንድዬ፣ ሶለል እና የእንግጫ ነቀላ በክልል ደረጃ በማክበር እና በማስተዋወቅ ከፍተኛ ተቀባይነትን እንዲያገኙ መደረጉን ለተሠራው ሥራ አብነት አድርገው አንስተዋል::
የክልሉ ሕዝብ እና በየደረጃው ያለው የመንግሥት መዋቅር በዓላቱ በድምቀት እንዲከበሩ እና ለበዓሉ ከተለያዩ አካባቢዎች የሚመጡ እንግዶችን በማስተናገድ የተለመደ እንግዳ ተቀባይነቱን በተግባር እንዲገልጥ ጥሪ ቀርቧል::

(ስማቸው አጥናፍ)
በኲር የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

አፍሪካየነሐሴ 12  ቀን 2017 ዓ.ም ዕትምአፍሪካ ከሌላው ዓለም በተለየ መልኩ ከዕድገት ወደ ኋላ ለምን ቀረች? የሚለው ጥያቄ ውስብስብ እና ዘርፈ ብዙ ነው። የአህጉሪቱን የዕድገት ጉዞ የገ...
18/08/2025

አፍሪካ
የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

አፍሪካ ከሌላው ዓለም በተለየ መልኩ ከዕድገት ወደ ኋላ ለምን ቀረች? የሚለው ጥያቄ ውስብስብ እና ዘርፈ ብዙ ነው። የአህጉሪቱን የዕድገት ጉዞ የገቱት የታሪክ፣ መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ፣ የፖለቲካ እና የአካባቢ ሁኔታዎች ጥምረት እንጂ የአንድ ነጠላ ጉዳይ ብቻ አይደለም። አፍሪካ ሰፊ ናት፤ 54 ሀገራት አሏት:: ከአንድ ነጥብ አምስት ቢሊዮን በላይ ሕዝብ እና የሚያስደንቅ የባህል፣ የቋንቋ እና የመሬት አቀማመጥ ባለቤትም ናት:: ታዲያ አፍሪካ በሰዎች ዘንድ ስትታሰብ ቀድሞ የሚመጣው ድህነቷ ነው::

በአፍሪካ እንዳታድግ ተጽእኖ ከፈጠሩት መካከል በጣም ግልፅ እና ገላጭ ከሆኑ ምክንያቶች አንዱ የመልካዓ ምድራዊ አቀማመጧ ነው። አህጉሪቱ ግዙፍ ናት፤ 30 ሚሊዮን ስኩዌር ኪሎ ሜትር ትሸፍናለች:: ይህም ከእስያ ቀጥሎ ከዓለም ሁለተኛዋ ትልቋ አህጉር ያደርጋታል። ይሁንና የአፍሪካ ሰፊው ክፍል በረሃማ ነው:: 60 በመቶ የሚሆነው ግዛቷ በሰሃራ እና በካላሃሪ በረሃዎች የተሸፈነ ነው። እንዲሁም በርካታ ቦተዎቿ ወጣ ገባ የበዛበት በመሆኑ በግብርናው ዘርፍ አመርቂ ውጤት ማስመዝገብ ላለመቻሏ እንደ አንድ ምክንያት ይጠቀሳል::

ኢንዲፔንደት (independent.co) ድረ ገጽ ላይ ያገኘነው መረጃ እንደሚያትተው ብዙውን ጊዜ የሰው ልጅ መገኛ ተብላ የምትታወቀው አፍሪካ ድህነቷን ታሪክ ያላደረጉ ባልጠቀሙ የተፈጥሮ ሀብቶች የተሞላች አህጉር ናት። እንደተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (እ.አ.አ 2024) መረጃ በዓለም ላይ እጅግ ድሀ ከሚባሉት ከ46ቱ ያልበለጸጉ ሀገራት መካከል 33ቱ የሚኖሩባት የዓለም ድሃ አህጉር ሆና ቀጥላለች። እንደ ዓለም ባንክ መረጃ ከ1960ዎቹ ወዲህ ከአንድ ነጥብ ሦስት ትሪሊዮን የአሜሪካ ዶላር በላይ የውጭ እርዳታ ቢለገሳትም ድህነቷ አሁንም ቀጥሏል።
ሌላው ሊንክኢዲን (linkedin.com) ላይ ያገኘነው መረጃ እንደሚያትተው ለአፍሪካ ዕድገት መጓደል ትልቅ ምክንያት የሆነው የቅኝ ግዛት መዘዝ ነው። ከ19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መገባደጃ ጀምሮ እስከ 20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አጋማሽ ድረስ አብዛኛዎቹ የአፍሪካ ሀገራት በአውሮፓ ኃያላን ቅኝ ግዛት ሥር ነበሩ:: ይህ ጊዜ ከ60 እስከ 80 ዓመታት ድረስ የዘለቀ ነው። የቅኝ ግዛት መዘዞች እጅግ በጣም ብዙ እና በጣም ጎጂ ነበሩ:: ቅኝ ገዥዎች ለመሰረተ ልማትም ሆነ ለተቋማት ልማት መዋዕለ ነዋያቸውን ፈሰስ ሳያደርጉ ከአፍሪካ ሀገራት ከፍተኛ መጠን ያለው ሀብት አሟጠው ወደ ሀገራቸው ወስደዋል።

የአውሮፓ ኃያላን የዘፈቀደ ድንበሮች የአህጉሪቱን የዘር እና የባህል ክፍፍል ግምት ውስጥ አላስገቡም። በዚህም እስከ ዛሬ ድረስ የቀጠለ ውጥረትና ግጭት ፈጥሯል። ለምሳሌ በሱዳን እና በደቡብ ሱዳን መካከል ያለው ድንበር ወይም እንደ ናይጄሪያ እና ሩዋንዳ ያሉ ሀገራት ውስጥ ያለው ውጥረት ሁሉም በቅኝ ግዛት ውሳኔዎች ላይ የተመሰረተ የድንበር አከላለል ውጤት ነው። ይህ ለአፍሪካ ሕዝብ ማሕበራዊ ትስስር ትኩረት አለመሰጠቱ በሀገራቱ መካከል አለመረጋጋት እና ግጭት እንዲፈጠር አስተዋጽኦ አድርጓል:: ይህም ለዕድገቷ የበለጠ እንቅፋት ሆኗል።

በተጨማሪም ከነጻነት በኋላ ብዙ የአፍሪካ ሀገራት የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ ሥርዓትን ሳይዘረጉ ቀርተዋል። የቅኝ ገዢ ኃይሎች ሆን ብለው በሀብት ማውጣት ላይ ያማከለ እንጂ ራሳቸውን የሚደግፉ ኢንዱስትሪዎችን አልፈጠሩም።
የአፍሪካ ሀገራት ነፃነታቸውን ሲያገኙ ወደ ዘመናዊ ኢኮኖሚ ለመሸጋገር የሚያስችላቸውን አስፈላጊው መሠረተ ልማት፣ ዕውቀትና ተቋም ሳይኖራቸው ነበር። በዚህ ምክንያት ብዙ የአፍሪካ ሀገራት ነፃነታቸውን ካገኙ በኋላ የተረጋጋ መንግሥት ለመገንባት፣ በትምህርት ላይ ኢንቨስት ለማድረግ ወይም መሠረተ ልማት ለማስፋፋት ቢታገሉም አመርቂ ውጤት አላገኙም።

ለአብነትም በቤልጄየም ቅኝ ግዛት ስር የነበረችው ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ በጣም ድሃ ከሆኑ ሀገራት መካከል ትመደባለች። የዓለም ባንክ የ2023 (እ.አ.አ) ሪፖርት እንደሚያመላክተው 63 በመቶ የሚሆነው ሕዝቧ በቀን ከሁለት ነጥብ 15 ዶላር ባነሰ ገንዘብ ኑሮውን የሚገፋ ነው። የመልካም አስተዳደር ጉድለት እና ሙስና አሁንም ድረስ የሀገሪቱ ከባድ ፈተናዎች ናቸው። በ2023 በወጣው በትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል የሙስና አስተሳሰብ ጠቋሚ መረጃ መሰረት በዓለም ዙሪያ ከተዘረዘሩት 30 ሀገራት ውስጥ 18 የአፍሪካ ሀገራት በዝርዝሩ የተካተቱ ሲሆን ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎም አንዷ ናት። ይህ ሙስና አስፈላጊ የሆኑ ሀብቶችን የሚያሟጥጥ ከመሆኑም በላይ ዕድገትን ይገታል:: ለምሳሌ ናይጄሪያ በ1960 ነፃነቷን ካገኘችበት ጊዜ አንስቶ በሙስና ምክንያት 582 ቢልዮን የአሜሪካ ዶላር ገደማ እንደተመዘበረች ተዘግቧል። ሙስና የሕዝብን አመኔታ ከማበላሸቱም በላይ የውጭ መዋዕለ ንዋይን ያግዳል:: ባለሀብቶችን እንደ ትምህርት እና የጤና አገልግሎት ካሉ ወሳኝ መስኮች ያርቃል።

ሌላው አፍሪካ በድህነት እንድትዘፈቅ ካደረጓት ምክንያቶች መካከል እርዳታ ተጠቃሽ ነው:: አፍሪካ በ2021 እ.አ.አ 54 ነጥብ 4 ቢሊዮን ዶላር የልማት እርዳታ አግኝታ ነበር። አፋጣኝ እርዳታ የሚያስፈልግ ቢሆንም ብዙውን ጊዜ በራስ የመተማመን መንፈስ ከማግኘት ይልቅ ጥገኛ መሆንን ያበረታታል። ለምሳሌ ማላዊ እ.አ.አ. በ2022 37 በመቶ የሚሆነውን በጀቷን የበጀተችው ከእርዳታ ባገኘችው ገንዘብ እንደነበር የአይ ኤም ኤፍ መረጃ ያሳያል።
እ.አ.አ በ2023 የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እንዳስታወቀው በ2050 የአፍሪካ ሕዝብ ቁጥር በእጥፍ ወደ ሁለት ነጥብ አምስት ቢሊዮን ይደርሳል ተብሎ ይገመታል። ይህ የሕዝብ ቁጥር መጨመር ለኢኮኖሚ ዕድገት ዕድል የሚያመጣ ቢሆንም ሥራ አጥነትን ይዞ ይመጣል የሚል ስጋትም አለ::

ኢንተርናሽናል ሌበር ኦርጋናይዜሽን በ2023 እንዳስታወቀው (ILO) በደቡብ አፍሪካ እና በናይጄሪያ ከ30 በመቶ በላይ የወጣቶች ሥራ አጥነት አለ። እንደ ዓለም ባንክ መረጃ ደግሞ አፍሪካ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣውን የጉልበት ሠራተኛ ወደ ሥራ ለማስገባት በየዓመቱ 20 ሚሊዮን ሥራ አጥ ዜጎችን የሚያሳትፍ የሥራ ዕድል መፍጠር ያስፈልጋታል። ይሁንና አህጉሪቱ ይህን የሥራ ክፍተት ሳትሞላ በማህበራዊ አለመረጋጋት እና በድህነት ንረት አደጋ ላይ ትገኛለች።

ሌላው የአንድ ሀገር ዕድገት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክተው ትምህርት እንደሆነ ቢታወቅም በአፍሪካ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሠራበት አይደለም:: ሂውማን ራይትስ ዎች እንዳስታወቀው በአፍሪካ በተያዘው ዓመት( 2025) ዕድሜያቸው ከ6 እስከ 18 የሚሆኑ 98 ሚሊዮን ሕፃናት እና ወጣቶች ከትምህርት ገበታ ውጪ ናቸው። ይህ የትምህርት ክፍተት አህጉሪቱ ለኢንዱስትሪ ዕድገት እና ፈጠራ አስፈላጊ የሆነ የተካነ ሠራተኛ የማፍራት አቅሟን ያደናቅፈዋል።
የአፍሪካ ልማት ባንክ እንዳስታወቀው አህጉሪቱ ከዓለማችን የማዕድን ክምችት ውስጥ 30 በመቶ እና 65 በመቶ አርሶ አደሮች ቢኖሯትም አሁንም ችግር ላይ ትገኛለች። ሀብቷ ብዙ ጊዜ ለሙስና፣ ለግጭት እና ለኢኮኖሚ አለመረጋጋት ሲዳርጋት ይስተዋላል::
ለአብነትም በአህጉሪቱ ውስጥ ትልቋ የነዳጅ አምራች የሆነችው ናይጄሪያ እ.አ.አ ከ1960 ወዲህ ከ340 ቢልዮን በላይ የአሜሪካ ዶላር የነዳጅ ዘይት አገኝታለች፤ ሆኖም የዓለም ባንክ እንደገለጸው ከ40 በመቶ በላይ የሚሆነው ሕዝቧ ከድህነት ወለል በታች ነው።

ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎም 24 ትሪሊዮን ዶላር የማዕድን ሀብት ቢኖራትም በሂውማን ዴቨሎፕመንት ጠቋሚ መረጃ መሰረት ከ191 ሀገራት መካከል 179ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች።
ዩ ኤን ዲ ፒ እ.አ.አ በ2023 ይፋ ባደረገው መረጃ በአፍሪካ አብዛኛውን ጊዜ የውጭ ሀገር ኩባንያዎች የተፈጥሮ ሀብት ማውጣትን ሥራ በበላይነት ይቆጣጠራሉ:: ትርፋቸውንም ወደ ሌላ ሀገር ስለሚልኩ ለአካባቢው ኢኮኖሚ አነስተኛ ጥቅም ነው እያስገኙ የሚገኙት።

ሌላው አፍሪካን ወደ ኋላ ካስቀሯት መካከል የአየር ንብረት ለውጥ ተጠቃሽ ነው:: አፍሪካ ከዓለም አቀፉ ግሪንሃውስ ጋዝ ልቀት ውስጥ ሦስት በመቶውን ብቻ የምታዋጣ ቢሆንም በአየር ንብረት ለውጥ ውጤት በእጅጉ ትሠቃያለች። በተደጋጋሚ በተለያዩ የአህጉሪቱ ሀገራት የተከሰቱ ድርቅ እና የጎርፍ መጥለቅለቅ ማሳያዎች ናቸው:: የዓለም ባንክ እንዳስታወቀው እ.አ.አ እስከ 2050 ድረስ 86 ሚሊዮን የሚሆኑ አፍሪካዊያን ከአየር ንብረት ጋር በተያያዙ ተፅእኖዎች ምክንያት ወደ ሌላ አካባቢ ሊሰደዱ ይችላሉ። 60 በመቶ የሚሆኑት በግብርና ዘርፍ የተሰማሩ ሰዎችም ለአደጋ ይጋለጣሉ። የአየር ንብረት ለውጥ የምግብ አለመረጋጋት እንዲባባስ ያደርጋል፣ የውኃ እጥረት ያስከትላል እንዲሁም በሀብት ላይ የሚፈጠሩ ግጭቶች እንዲባባሱ ምክንያት ይሆናል:: ይህ ደግሞ ዕድገትን ያደናቅፍል።

እ.አ.አ. በ2015 የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዓለም አቀፍ ድህነትን ለማስወገድ የሚያስችሉ እና ለዘላቂ ልማት የሚያግዙ ግቦችን አስቀምጧል። ግቦቹም በ2030 በጤና፣ በትምህርት፣ በፍትሕ፣ በኢኮኖሚ ልማት እና በአየር ንብረት ለውጥ መሻሻል ላይ የሚያተኩሩ ናቸው። ሆኖም በዚህ ወቅት አፍሪካ እነዚህን ግቦች ለማሳካት መንገድ ላይ አይደለችም። ማሳያ የሚሆነውም አፍሪካ በዓለም አቀፍ ደረጃ እጅግ የከፋ የድህነት ደረጃ ላይ መገኘቷ ነው::
በተጨማሪም ለአፍሪካ ድህነት አስተዋፅኦ ካደረጉ ቁልፍ ምክንያቶች አንዱ በየጊዜው የሚያጋጥማት ከፍተኛ የሆነ የተማረ ሰው ኃይል ፍልሰት ነው። ይህም አህጉሪቱን ለልማት የሚያስፈልገውን የተማረ የሰው ካፒታል አሳጥቷታል። የሰለጠነ ሠራተኞች ፍልሰት በአካባቢው ኢንዱስትሪዎች ላይ ተጽእኖ በማሳደር የቴክኖሎጂ እና ኢኮኖሚያዊ ዕድገቶችን ያግዳል። ለአንድ ሀገር የሰለጠነ እና የተማረ ማሕበረሰብ መኖር ለዘላቂ ዕድገት ወሳኝ ነው።
በርካታ ተግዳሮቶች ያሉበት የአፍሪካ አህጉር የውጪ ብድርም ዕድገቷን ከገቱባት ምክንያቶች ውስጥ ተጠቃሽ ነው:: የአይ ኤም ኤፍ 2023 መረጃ እንደሚያሳየው የአፍሪካ ሀገራት በየዓመቱ 22 ቢሊዮን ዶላር እዳ ይከፍላሉ። ይሁን እንጂ በአፍሪካ ያለው የተትረፈረፈ ሀብት እና የወጣት ሕዝብ መበራከት የአህጉሪቱን የድህነት ታሪክ ሊቀይር ይችላል የሚሉ ተስፈኞች አሉ::

(ሳባ ሙሉጌታ )
በኲር የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

የልማቱ ምሰሶ...የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትምበኢትዮጵያ የግብር አጀማመር ከመንግሥታት አመሠራረት ጋር የተቆራኘ እንደሆነ ታሪክ ያስረዳል። በሀገራችን የግብር ሥርዓት በአፄ ዘርዓያዕቆ...
18/08/2025

የልማቱ ምሰሶ...
የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

በኢትዮጵያ የግብር አጀማመር ከመንግሥታት አመሠራረት ጋር የተቆራኘ እንደሆነ ታሪክ ያስረዳል። በሀገራችን የግብር ሥርዓት በአፄ ዘርዓያዕቆብ ተጀምሮ በአፄ ኃይለ ሥላሴ አዋጅ ወጥቶለት ማሻሻያዎች እየተደረጉበት አሁን እስከደረስንበት ዘመን ተሻግሯል። በወቅቱ ግብር የሚከፈለውም በጉልበት ወይም አገልግሎት በመስጠት፣ በዓይነት፣ አልፎ አልፎ ደግሞ በገንዘብ እንደነበር ድርሳናት ያስረዳሉ። መንግሥት በሕግ እና በመመሪያ ተመስርቶ ከሕዝብ እና ከድርጅት ገቢ የሚያገኝበት ዋነኛ መንገድ ነው። ይህም ለሀገር ልማት የሚውል የሀብት ምንጭ ሆኖ ያገለግላል።
በሀገራችን በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት እና በታክስ ሕግጋት መሠረት መንግሥት የተለያዩ የግብር ዓይነቶችን በመጣል ገቢ ይሰበስባል። ዜጎች ቤታቸውን በማከራየት፣ ዕውቀታቸውን በመሸጥ፣ በሥራ እና በሌላ መንገድ ከሚያገኘው ገቢ በሕግ በተቀመጠው አሠራር እና ሕግ መሰረት ግብር ይከፍላሉ።

ግብር የመንግሥት የልማት እና የማኅበራዊ አገልግሎት ዕቅዶች ማስፈጸሚያ፣ የሀገር ሉዓላዊነት ማስከበሪያ፣ የኢንቨስትመንት ማበረታቻ እና የኅብረተሰቡን የመልካም አስተዳድር ችግሮች መፍቻ አይነተኛ መሳሪያ ነው።
በመሆኑም በአማራ ክልል ግብር መሰብሰብ የህልውና ጉዳይ መሆኑን በመረዳት በተለያዩ አካባቢዎች ግብር ወቅቱን ጠብቆ በመሰብሰብ ላይ ይገኛል። ለአብነትም የአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር በበጀት ዓመቱ ግብር በወቅቱ እየሰበሰበ መሆኑን አስታውቋል። የብሔረሰብ አስተዳድሩ ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ ፈጠነ ጥላሁን የግብር ከፋዩ ግንዛቤ እንዲያድግ አስፈላጊ የሚባሉ የቅስቀሳ ሥራዎች እንደተከናወኑ አስረድተዋል። ቀድሞ መረጃ የመሰብሰብ እና የማጥራት ሥራም ተከናውኗል። ይህን ተከትሎም ሐምሌ 01 ቀን 2017 ዓ.ም የበጀት ዓመቱ የግብር አሰባሰብ ሂደቱ በይፋ የተጀመረ መሆኑን አንስተዋል።
ግብር በወቅቱ እና በአግባቡ ካልተሰበሰበ አዳዲስ እና የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን በፍጥነት ለማጠናቀቅ እንቅፋት መሆኑን በማንሳት ያለ ግብር ልማት እንደማይመጣም አስረድተዋል። “ግብር መቼም ቢሆን መቼም አይቀሬ እና በወቅቱ እንኳን ባይከፈል ዕዳ ሆኖ እንደሚቀጥል” ለበኵር ጋዜጣ በስልክ ተናግረዋል።

የማኅበረሰቡን የልማት ጥያቄ ለመመለስ እና መሰረተ ልማቶችን ለማሟላት ግብር መሰብሰብ ቀዳሚ ተግባር ሊሆን እንደሚገባም አስገንዝበዋል። የተሰበሰበው ግብር ደግሞ ለደመወዝ፣ ለመሠረተ ልማት ግንባታ (ለመንገድ፣ ለትምህርት ቤት፣ ለጤና ጣቢያ፣ ለሆስፒታል፣ ለንፁህ መጠጥ ውኃ፣ ለድልድይ፣ ለቴሌኮም፣ ለኤሌክትሪክ ኀይል አቅርቦት) እና ለሌሎች አገልግሎቶች እንደሚውል ነው ያስረዱት። የግብር አሰባሰብ ሂደቱ ፍትሐዊ በሆነ መንገድ እንዲከናወን ኮሚቴ ተቋቁሞ እየተሠራ መሆኑን የጠቆሙት መምሪያ ኃላፊው በአሠራሩ ቅሬታ ያለው ግብር ከፋይ ቅሬታውን የሚያቀርብበት መንገድ እንዳለም አመላክተዋል።

እንደ መምሪያ ኃላፊው ማብራሪያ የገቢ አሰባሰቡን የተሻለ ለማድረግ አሠራርን ማዘመን፣ ባለሙያዎችን ማሰልጠን፣ ደረሰኝ በአግባቡ እንዲቆረጥ ማድረግ፣ የታክስ ማስከፈያ ምጣኔን ማሻሻል፣ ነጋዴው ባለበት ሆኖ እንዲከፍል ማድረግ፣ ግብር ከፋዮችን በደረጃቸው ማስከፈል፣ የግብር ከፋዩን ግንዛቤ ማሳደግ እና ሌሎች በትኩረት እየተሰራባቸው ያሉ መሰረታዊ ጉዳዮች ናቸው።
በብሔረሰብ አስተዳደሩ በ2017 በጀት ዓመት ከመደበኛ ገቢ እና ከከተማ አገልግሎት ለመሰብሰብ ከታቀደው 3 ቢሊዮን 148 ሚሊዮን 643 ሺህ 494 ብር ውስጥ 1 ቢሊዮን 980 ሚሊዮን 840 ሺህ 495 ብር መሰብሰቡን አቶ ፈጠነ ተናግረዋል፡፡ ዕቅዱን ሙሉ ለሙሉ ማሳካት ያልተቻለውም በክልሉ የተከሰተው የሰላም እጦት መሆኑን በምክንያትነት አስቀምጠዋል። በገቢ አሰባሰብ ሂደቱ በርካታ ፈተናዎች እና ጫናዎች እንደነበሩም አስታውሰዋል። ሆኖም በ2017 በጀት ዓመት የተሰበሰበው ግብር ከ2016ቱ በ449 ሚሊዮን 86 ሺህ 116 ብልጫ እንዳለው አመላክተዋል።

የአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ገቢዎች መምሪያ በ2018 በጀት ዓመት ግብርን በተሻለ ሁኔታ ለመሰብሰብ ቅድመ ዝግጅቱን አጠናቆ የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን አቶ ፈጠነ አስረድተዋል። ከእነዚህ ቅድመ ዝግጅቶች መካከል እያንዳንዱ ነጋዴ ከአንድ ወር በፊት የሚከፍለውን የግብር መጠን ቀድሞ እንዲያውቅ እና ቅድመ ዝግጅት እንዲያደርግ የመረጃ መለዋወጥ ሂደት እንደነበር መምሪያ ኃላፊው ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ 3 ቢሊዮን 551 ሚሊዮን 983 ሺህ 432 ብር ለመሰብሰብ ታቅዷል።
በብሔረሰብ አስተዳደሩ 20 ሺህ 223 የደረጃ ሐ፣ 2 ሺህ 162 የደረጃ ለ፣ 1 ሺህ 639 የደረጃ ሀ በአጠቃላይ አርሶ አደሩን ሳይጨምር 24 ሺህ 24 ነጋዴዎች እንዳሉ ተናግረዋል። እነዚህም በተቀመጠላቸው የጊዜ ገደብ እንዲከፍሉ እየተደረገ ነው። ለአብነትም የደረጃ ሐ ግብር ከፋዮች (ከ20 ሺህ 223ቱ ውስጥ) ከ17 ሺህ በላይ ግብራቸውን በወቅቱ መክፈላቸውን ተናግረዋል። እስካሁንም 202 ሚሊዮን 70 ሺህ 704 ብር ተሰብስቧል።

ነጋዴው ግብሩን በአካል ተገኝቶ አሊያም በሞባይል ባንኪንግ እንዲከፍል ምቹ ሁኔታ መፈጠሩንም አቶ ፈጠነ ጠቁመዋል። 11 ወረዳዎች ማስከፈል የሚገባቸውን ግብር እያስከፈሉ ነው። ለአብነትም ዚገም፣ ቻግኒ፣ ጓንጓ እና እንጅባራ ከተማ በግብር አሰባሰቡ የተሻለ አፈፃፀም ያላቸው አካባቢዎች መሆናቸውን ጠቅሰዋል። ፋግታ ለኮማ እና ዳንግ ከተማ ዙሪያ በፀጥታ ችግሩ ምክንያት አፈፃፀማቸው ዝቅተኛ ነው።
መምሪያ ኃላፊው እንዳስታወቁት ግብር በወቅቱ አለመክፈል ለቅጣት እና ለወለድ ይዳርጋል። በመሆኑም ”ግብር እና ሞት የማይቀር ዕዳ ነው” እንደሚባለው ግብር ከፋዩ በወቅቱ የተጣለበትን ግብር በመክፈል ለተጨማሪ ወጪ እንዳይዳረግ አሳስበዋል።
የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ የግብር ትምህርት እና ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ታዘባቸው ጣሴ ለበኵር ጋዜጣ እንደገለፁት ግብር ለአንድ ሀገር እድገት መሰረታዊ ጉዳይ ነው። በክልሉ የሚገኙ ግብር ከፋዮች የንግድ ትርፍ ግብር፣ የሥራ ግብር፣ የከተማ አገልግሎት ግብር፣ የተጨማሪ እሴት ታክስ እና ሌሎች የግብር ዓይነቶችን እንደሚከፍሉም ዳይሬክተሩ ገልፀዋል።

ቢሮው በ2017 በጀት ዓመት በክልሉ ከመደበኛ 56 ነጥብ 15 ቢሊዮን ብር እንዲሁም ከከተማ አገልግሎት 15 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በድምሩ 71 ነጥብ 65 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ አቅዶ ከመደበኛ 53 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ፤ ከከተማ አገልግሎት ገቢ 6 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በድምሩ 60 ነጥብ አንድ ቢሊዮን ብር መሰብሰብ መቻሉን ዳይሬክተሩ ተናግረዋል። ሰሜን ሽዋ ዞን፣ ዋግኸምራ እና ኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደሮች፣ ደቡብ ወሎ እና ወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ በክልሉ በግብር አሰባሰቡ ከፍተኛ አፈፃፀም ነበራቸው፡፡ በአንፃሩ ደብረ ማርቆስ፣ ጎንደር ከተማ፣ አዊ ብሔረሰብ አስተዳደር፣ ደብረ ታቦር እና ደሴ ከተማ ዝቅተኛ አፈፃፀም ያስመዘገቡ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በክልሉ የተከሰተው የሰላም እጦት በገቢ አሰባሰቡ ላይ ጫና አሳድሮ እንደነበር አስረድተዋል።

ቢሮው በ2018 በጀት ዓመት ከመደበኛ ገቢ 84 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር እንዲሁም ከከተማ አገልግሎት 15 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ አቅዶ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ማከናወኑን አብራርተዋል። ከተሠሩ ሥራዎች መካከልም የግብር አሰባሰብ ሥርዓቱን ከተለምዷዊ አሠራር ለማውጣት ከባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር አዲስ የኤሌክትሮኒክስ ታክስ አሥተዳደር ሥርዓት (ኢ-ታስ የዲጂታል አሠራር) በማበልጸግ ወደ ሥራ መገባቱን ነው የተናገሩት፡፡
የግብር ከፋዮችን ሙሉ መረጃ ወደ መተግበሪያው (ሲስተሙ) በማስገባት የሚከፈለውን የገንዘብ መጠን ለግብር ከፋዮች ቤታቸው ሆነው በሞባይል መልዕክት እንዲደርሳቸው ያደርጋል ብለዋል፡፡ ግብር ከፋዮች መልዕክቱ ከደረሳቸው በኋላ በሞባይል ባንኪንግ ወይም በአካል በባንክ መክፈል እንደሚችሉ ገልጸዋል። መተግበሪያው (ሲስተሙ) የክልሉን የግብር አሰባሰብ የሚያሻሽል መሆኑንም ዳይሬክተሩ ገልጸዋል፡፡

እንደ አቶ ታዘባቸው ማብራሪያ አዲሱ አሠራር የመደበኛ እና የከተማ አገልግሎት ገቢ አሰባሰብ ሂደትን በማዘመን የሕግ ተገዥነትን ያሳድጋል፤ የአገልግሎት አሰጣጥንም ያሻሽላል፡፡ ከዚህ በተጓዳኝ የግብር ከፋዮችን እንግልት እና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ሊፈታ የሚችል መሠረት የተጣለበት ነው። የግብር ከፋዩን ረጅም ሰልፍ እና ወረፋንም ያስቀራል፡፡
ያነጋገርናቸው ግብር ከፋዮችም ያረጋገጡልን ይህንኑ ነው፡፡ ነዋሪነታቸው በባሕር ዳር ከተማ የሆኑት ግለሰቦች ለበኵር ጋዜጣ በሰጡት አስተያየት በየዓመቱ የአከራይ ተከራይ ግብር ይከፍላሉ፡፡ ሁሌም ፋይል (የግል ማህደር) ለማስወጣት፣ የሚጠበቅባቸውን የግብር ገንዘብ በባንክ ለመክፈል፣ ማዘዣ ለማጻፍ እና ክፍያ ፈጽሞ ደረሰኙን ከግል ማህደራቸው ጋር ለማያያዝ ከሳምንት ላላነሰ ጊዜ ይመላለሱ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ በዚህ ዓመት ግን የሚከፍሉት የግብር መጠን በሞባይላቸው ስለደረሳቸው በቀላሉ ያለምንም እንግልት እና የጊዜ ብክነት ክፍያ መፈፀማቸው አስደስቷቸዋል፡፡

ኢ-ታስን (የኤሌክትሮኒክስ ታክስ አስተዳደር ሥርዓት) በተመለከተ ከአንድ ሺህ በላይ በየደረጃው ያሉ ፈፃሚዎችን ለማብቃት በክልሉ ባሉ ዩኒቨርሲቲዎች የተግባር ስልጠና መሰጠቱን ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል፡፡ ስለ አዳዲስ አሠራሮች የግንዛቤ ማስጨበጥ በሁሉም የገቢ ተቋማት ውጤታማ የንቅንቄ መድረኮች ተካሂደዋል። በመድረኮቹ ከግብር ከፋዮች፣ ከአመራሮች፣ ከአጋር እና ባለድርሻ አካላት፣ ከተቋሙ ባለሙያዎች ጋር ውይይት ተካሂዷል።

በክልሉ የተፈጠረው የፀጥታ ችግር የንግዱን እንቅስቃሴ ማቀዛቀዙ፣ ግብር ከፋዮች እንደፈለጉ ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሰው መሥራት አለመቻላቸው፣ በተለይ የአዲስ አበባ ከተማ አንዳንድ አስመጭዎች ደረሰኝ ለመስጠት ፈቃደኛ አመሆናቸው፣ ግብር ከፋዮች ለሸጡት ዕቃም ሆነ ለሰጡት አገልግሎት ደረሰኝ አለመስጠታቸው፣ ማኅበረሰቡ ለገዛው ዕቃም ሆነ ላገኘው አገልግሎት ደረሰኝ የመጠየቅ ልምዱ በሚፈለገው ደረጃ አለመሆኑ እና ሆን ተብለው የሚፈፀሙ የታክስ ስወራ በገቢ አሰባስቡ ላይ ተግዳሮቶች መሆናቸውን አብራርተዋል።
ዳይሬክተሩ ሐሳባቸውን ሲያጠቃልሉ ግብር በአግባቡ በመሰብሰቡ ለማኅበረሰቡ አስፈላጊ የመሠረተ ልማቶችን ለማሟላት አቅም የሚፈጥር መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡

(መልካሙ ከፋለ)
በኲር የነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp:// www.ameco.et/Bekur
በቴሌግራም - https://t.me/bekur123 ላይ ማግኘት ይችላሉ።

Address

Bahir Dar

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when አሚኮ በኲር/AMECO BEKUR posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to አሚኮ በኲር/AMECO BEKUR:

Share