09/06/2026
ከ43 ሺህ በላይ የከተማው ነዋሪዎች የፋይዳ ዲጂታል ብሔራዊ መታወቂያ ተጠቃሚ ሆነዋል።
በምዕራብ ጎጃም ዞን ፍኖተ ሰላም ከተማ አስተዳደር የመንግስትና የግል አገልግሎቶችን ለማዘመን በተከናወነው የብሔራዊ መታወቂያ ምዝገባ ሥራ ከ43 ሺህ በላይ የሚሆኑ የከተማው ነዋሪዎች ተጠቃሚ መሆናቸውን ከተማ አስተዳደሩ ገልጿል።
ያነጋገርናቸው የብሔራዊ መታወቂያ ተጠቃሚ የሆኑ ነዋሪዎች ለእያንዳንዱ ግለሰብ አንድ ጊዜ ብቻ የሚሰጠውና 12 አሃዝ የፋይዳ ቁጥር ያለው ነው ይህ መታወቂያ በርካታ ጥቅሞችን ከመስጠቱ ባሻገር ብልሹ አሠራሮችን በመከላከል ረገድም ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል።
ነዋሪዎቹ እንደገለጹት፣ የቀበሌ መታወቂያ በተለያዩ ቦታዎች ሊወጣ የሚችል በመሆኑ ለተለያዩ የማጭበርበር ድርጊቶች ተጋላጭ ነበር። ብሔራዊ መታወቂያው ግን ሙሉ ባዮሜትሪክ መረጃ (አሻራ) ስለሚይዝ ከአንድ በላይ ጊዜ ማውጣት የማይቻል ሲሆን ለብድር ፣ለዋስትና እና ለሌሎች ዘመናዊ አገልግሎቶችም ጠቃሚ መሆኑን ገልጸዋል።
የፍኖተ ሰላም ከተማ አስተዳደር የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አለሙ በየነ እንደገለጹት፣ ብሔራዊ መታወቂያ አዲስ የመንግስት ኢኒሼቲቭ በመሆኑ ማኅበረሰቡ በስፋት ተጠቃሚ እንዲሆን ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች ተከናውነዋል።
መታወቂያው የሚሰጥባቸውን ቦታዎችና ሂደቶች በተቀናጀ መንገድ ለማስተዋወቅ የተሠራው ሥራ ጉልህ የግንዛቤ ለውጥ በማምጣቱ በርካታ ነዋሪዎች ተጠቃሚ ሆነዋል ብለዋል።
በተጨማሪም የብሔራዊ መታወቂያውን እስከ ሰኔ 20 ድረስ ከባንክ ሥርዓት ጋር በማስተሳሰር የሚገኙ ጥቅሞችን በመጠቀም ሁሉም ነዋሪዎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ ጥሪ አቅርበዋል።
የፍኖተ ሰላም ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ወርቁ በላይ በበኩላቸው፣ የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ማኅበረሰቡን የዲጂታል መታወቂያ ተጠቃሚ በማድረግ አሠራሮችን ለማዘመን የታለመ የመንግስት ኢኒሼቲቭ መሆኑን ገልጸዋል።
ይህ መታወቂያ ብልሹ አሠራሮችን ለመከላከል፣ የንግድ ሥርዓቱን ለማዘመን እና ትክክለኛ የሕዝብ ቁጥር መረጃን ለማግኘት ጠቃሚ ሲሆን፣ በተደረገው የቅንጅት ሥራ ከ43 ሺህ በላይ የከተማው ነዋሪዎች የብሔራዊ መታወቂያ ተጠቃሚ ሆነዋል በዚህም የተያዘው እቅድ መቶ በመቶ መፈጸሙን ተናግረዋል።
#ፍኖተ ሰላም ኮሙኒኬሽን