30/05/2025
የጦርነት ሥጋት ያጠላበት የኢትዮጵያና የኤርትራ ሰሞነኛ ውጥረት
ኩዌት፣ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ፣ ግሪክ፣ ኒካራጓ፣ የመንና ሱዳንን ጨምሮ በርካታ አገሮች የእንኳን አደረሳችሁ የደስታ መግለጫ መልዕክት መላካቸው እንደሌላው ጊዜ የመገናኛ ብዙኃንን ቀልብ አልገዛም፡፡ ሌላው ቀርቶ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበርም ሆነ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ማርኮ ሩቢዮ የደስታ መልዕክት መላካቸውም ቢሆን ብዙም ትኩረት አላገኘም ነበር፡፡ ዘንድሮ 34 ዓመቱን የደፈነው ቅዳሜ ግንቦት 16 ቀን 2017 ዓ.ም. የተከበረው የኤርትራ የነፃነት በዓል ከዚህ ሁሉ ይልቅ በሌላ መንገድ የሚታወስ ሆኖ ነው ያለፈው፡፡ ከአገሪቱ የነፃነት በዓል እኩል በፕሬዚዳንታዊ ሥልጣን የቆዩት የዕድሜም የሥልጣንም ባለፀጋው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ፣ በዓሉ በአስመራ በደማቁ ሲከበር ያስተላለፉት መልዕክት ነው የአየር ሞገዱን ከሁሉ በላይ ተቆጣጥሮት የነበረው፡፡
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ የእንኳን አደረሳችሁ መግለጫ ኤርትራ ደማቅ ታሪክና ባህል ያላት ብቻ ሳይሆን፣ በአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ሰላምና ብልፅግና እንዲሰፍን እንደ አሜሪካ የምትፈልግ አገር መሆኗን ዕውቅና እንደሚሰጠው ያትታል፡፡ ይሁን እንጂ የኢሳያስ አፈወርቂ የበዓሉ መልዕክት በብዙ ታዛቢዎች ዘንድ በአፍሪካ ቀንድ አዲስ ጦርነት የማስጀመሪያ ፊሽካ ተደርጎ ነው የተወሰደው፡፡ ኢሳያስ አገራቸው ኤርትራ ከጎረቤት ኢትዮጵያ ጋር ለምታደርገውና ለአይቀሬው ጦርነት የ ‹‹ክተት ሠራዊት፣ ምታ ነጋሪት›› አዋጅ እያወጁ ይሆን ወይ የሚለውን በርካቶች በየራሳቸው የተለያዩ ግምቶች ሲሰጡት ሰንብተዋል፡፡ የፕሬዚዳንቱ ንግግር ለምን ትኩረት ሳበ ከሚለው ጀምሮ፣ የተላለፉ መልዕክቶች ለምን ዋና የመነጋገሪያ አጀንዳ ሆኑ የሚሉ ጉዳዮችን በተመለከተ ንግግሩን በጥንቃቄ መመርመር የሚጋብዝ ነው፡፡
የኢትዮጵያ ሕመም ከጀመረ ከ80 ዓመታት ወይም ከሦስት ትውልድ ያላነሰ ዕድሜ መቆጠሩን የጠቀሱት ኢሳያስ እንደ አሜሪካና ሶቪየት ኅብረት ባሉ አገሮች ጣልቃ ገብነትና የተዛባ ፖሊሲ የተነሳ፣ በኢትዮጵያ ለአገረ መንግሥት ምሥረታ አጋጥመው የነበሩ ዕድሎች ሲመክኑ መቆየታቸውን ያወሳሉ፡፡ በሒደት የተፈጠረው የብሔር ፌዴራላዊ ሥርዓት የኢትዮጵያን ፖለቲካ ሕመም እንዳጠናውና ብዙ ቀውስም እንዳስከተለ ነው የተናገሩት፡፡
ኢሳያስ ይህን ብለው ሲያበቁም፣ ‹‹የዛሬ ሰባት ዓመት በኢትዮጵያ ተፈጥሮ የነበረው የፖለቲካ ለውጥ ወይም ሪፎርም በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን፣ በኤርትራና በሌሎች ጎረቤት አገሮች ሕዝቦች ዘንድ ጭምር በጎ ተስፋ የፈጠረ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡ ይሁን እንጂ ይህን ያልወደዱ የውጭ ኃይሎች ያሳደሩት ጫና እና የእነሱን ጫናም ለመቀበል የብልፅግና መንግሥት በመፍቀዱ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ከባድ ቀውስ ያስከተለ ጦርነትና ግጭት እንዲከሰት አድርጓል፤›› ብለዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ኢሳያስ በኢትዮጵያ የመጣውን ለውጥ አገራቸው ለመደገፍ እንደሞከረች ገልጸዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የኤርትራ ሕዝብና መንግሥት በኢትዮጵያ የመጣው ለውጥ እንዳይደናቀፍ ድጋፍ ማድረጋቸውን እንደማይፀፀቱበት የጠቀሱት አቶ ኢሳያስ፣ በሰሜን ኢትዮጵያ በተካሄደው ከባድ ጦርነት ኤርትራ ጦሯን ማስገባቷንና የኢትዮጵያን መንግሥት መደገፏንም በዚሁ መንገድ ሊታይ የሚገባው መሆኑን ነው ያስረዱት፡፡
‹‹ጥቂት ጊዜ እንደቆየ የኢትዮጵያን ሪፎርም እንመራለን የሚሉት ብልፅግናዎች ማንነታቸው በገሀድ መታየት ጀመረ፡፡ የፕሪቶሪያ ሰላም ስምምነትን ተከትሎ በሌላ ማንነት ሲከሰቱ ባለፉት ጥቂት ዓመታት እናያቸው ጀመር፡፡ ዛሬ ኃላፊነት የጎደለው አጀንዳና አቋም እያራመዱም ይገኛሉ፡፡ የውኃ አጀንዳን በመቀስቀስ አንድ ጊዜ የዓባይ ውኃ ሌላ ጊዜ ደግሞ ቀይ ባህር፣ እንዲሁም የባህር በር ይላሉ፡፡ ሲፈልጉ የኦሮሞ ሕዝብን የማይወክለውን የኦሮሙማ ርዕዮተ ዓለምን ያራግባሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የኩሻዊያንና የሴማዊያንን ጠላትነት አጀንዳ ያቀጣጥላሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የአፋርን መሬት ለሚፈልጉት የብሔር ግጭት መቀስቀሻ አጀንዳነት ሊያውሉት ይቃጣቸዋል፤›› በማለት ነው ጠንከር ባሉ ቃላት የኢትዮጵያ መንግሥትን የተቹት፡፡
የኢትዮጵያን መንግሥት በጠጣር ቃላት ሲተቹ የተደመጡት ኢሳያስ አፈወርቂ በማሳረጊያቸው፣ የመከላከያ ኃይል ጠንካራ ዝግጅትን አስፈላጊነት በትኩረት አውስተዋል፡፡ ኤርትራ በመከላከያ ብቻ ሳይሆን በሁለንተናዊ አገራዊ ጥንካሬዎች ራሷን እንደምታዘጋጅ ያብራሩ ሲሆን፣ አገራቸው ለሚመጣው ነገር ሁሉ ምላሽ መስጠት የሚያስችል ሁለንተናዊ ጥንካሬ በመፍጠር ላይ ተግታ እየሠራች ስለመሆኑ አስምረውበታል፡፡ ይህ የኤርትራ ነፃነት በዓል ላይ የተነገረው የኢሳያስ መልዕክት ደግሞ ለአይቀሬው ጦርነት አገራቸው እየተሰናዳች ስለመሆኑ አመላካች ነው ተብሎ በሰፊው መነጋገሪያ ሆኗል፡፡
ተቃዋሚ ፖለቲከኛው ጃዋር መሐመድን ጨምሮ የመንግሥት ባለሥልጣኑ ብርሃኑ ሌንጂሶ (ዶ/ር)፣ የሚዲያ ሰዎችና በርካታ የማኅበራዊ ትስስር ገጾች ተዋንያን የኢሳያስ አፈወርቂን ንግግር በተለይም ‹‹ኦሮሙማ›› ብለው ስለጠሩት ርዕዮተ ዓለም ስህተት በሰፊው ሲተቹ ሰንብተዋል፡፡ ከዚህ በመለስ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ምክትል (ኦፌኮ) ተቀዳሚ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ሙላቱ ገመቹ፣ የኤርትራውን ፕሬዚዳንት ንግግር ጠብ ጫሪና ተንኳሽ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
‹‹አቶ ኢሳያስ የኢትዮጵያን ጠንካራ አገር ሆኖ መኖር አይፈልጉም፡፡ ኢሳያስ ኦሮሙማን እንደ ርዕዮተ ዓለም ቆጥረው መወንጀላቸው ስህተት ነው፡፡ ኦሮሙማ የኦሮሞ ሕዝብ እሴት፣ ባህልና ማንነት እንጂ ርዕዮተ ዓለም አይደለም፡፡ ብልፅግና የኢትዮጵያ መንግሥት ነው እንጂ ከኦሮሞ ሕዝብ ብቻ የወጣ የፖለቲካ ሥርዓት አይደለም፡፡ ኢሳያስ ከዚህ ባለፈም የሴማዊያንንና የኩሻዊያንን ግጭት ማንሳታቸው በኢትዮጵያ ሕዝቦች መካከል የተቧደነ ጦርነት ለመለኮስ የተደረገ ጥረት ነው፤›› በማለት ነው አቶ ሙላቱ ያስረዱት፡፡
ከተለያየ አቅጣጫ ለኢሳያስ ንግግር የሚሰጡ መልሶች በቀጠሉበት በዚህ ወቅት ለፕሬዚዳንቱ በእንግሊዘኛ ግልጽ ደብዳቤ ብለው ሰፊ መጣጥፍ ያስነበቡት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲው የፖለቲካ ሳይንስ መምህር መብራቱ ከለቻ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ጠለቅ ያሉ ሐሳቦችን አስፍረዋል፡፡ ‹‹ፕሬዘዳንት ኢሳያስ ስለውጭ ኃይሎች ጣልቃ ገብነት ያወራሉ፡፡ ይሁን እንጂ የእሳቸው ጦር ኢትዮጵያ ጦርነት ውስጥ ገብቶ መሳተፉና ከፍተኛ ጭፍጨፋና ዕልቂት መፈጸሙ ጣልቃ ገብነት ካልተባለ ሌላ የውጭ ጣልቃ ገብነት ከየት ሊመጣ ነው?›› በማለት መብራቱ (ዶ/ር) ይሞግታሉ፡፡ ኢሳያስ የሌለ የእጅ አዙር ጣልቃ ገብነት ትርክት በመሳል በጎረቤት ኢትዮጵያ ጦር አስገብተው የፈጸሙትን ወንጀል ለመሸፋፈን መሞከራቸው፣ እጅግ አደገኛና ጨካኝ አቋም መሆኑን ነው ጸሐፊው የጠቀሱት፡፡
‹‹ኢትዮጵያ በብሔር ፖለቲካ ቀውስ ውስጥ ገብታለች ብለው ኢሳያስ መናገራቸው ተገቢነት የለውም፡፡ የብሔር ፖለቲካ ቀውስ ፈጥሮ ከሆነም የኢትዮጵያ ብዝኃነትን በአግባቡ የማስተናገድ ችግር ከገጠማት እሱን ማስተካከል ለእኛው ለኢትዮጵያውያን የሚተው የቤት ሥራ እንጂ፣ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ እርስዎን ሊያስጨንቅና ከንፈር ሊያስመጥጥ የሚገባው ጉዳይ መሆን የለበትም፡፡ ከብሔር ፖለቲካ በተጨማሪም ስለኦሮሙማ ርዕዮተ ዓለም፣ እንዲሁም ስለኩሽና ሴም ግጭት ማንሳትዎም ቢሆን የመነጨው እርስዎ ብዝኃነትን ለሚያስተናግድ ፖለቲካ ያለዎትን ጥላቻ እንጂ ሌላ አይደለም፤›› በማለት ነው የፖለቲካ መምህሩ ኢሳያስን የሚተች ሐሳባቸውን ያንፀባረቁት፡፡
በኢትዮጵያ ወገን ከተሠለፉ መንግሥትን ከሚቃወሙና ከሚደግፉ መካከል በርካታ ልሂቃን የኢሳያስን ንግግር በመተቸት በተጠመዱበት በዚህ ወቅት ግን፣ የኤርትራው መሪ መልዕክት ጥቂት የማይባሉ ሰዎችን በተቃራኒው ጮቤ ሲያስረግጣቸው ታይቷል፡፡ ኤርትራም ሆነ መሪዋ ኢሳያስ የተከተሉት አቋም ትክክል ስለሆነ ጥፋተኛውና ሊወገዝ የሚገባው፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ነው የሚሉ ድምፆችም ሲስተጋቡ ነበር፡፡
አንዳንድ የማኅበራዊ ትስስር ገጾችና ማኅበራዊ አንቂ ነን የሚሉ ወገኖች የኤርትራን 34ኛ የነፃነት በዓል አከባበር ደማቅነት አጉልተው የሚያሳዩ ቪዲዮዎች፣ ፎቶዎችና መረጃዎች በማጋራት ሥራ ተጠምደው ሰንብተዋል፡፡ የአስመራ ከተማው የምሽት ርችት ተኩስ ምሥል ከሁሉ በላይ ከፍተኛ ትኩረት አግኝቶ ነበር፡፡ ለመሬት ቀረብ ብለው የሚበሩ ጄቶች ድምፆች ሲያጓሩ የሚደመጥበትና በአስመራ ስታዲየም የተስተናገደው የባህር ኃይል፣ የምድር ኃይልና የሌሎች ወታደራዊ ክፍሎች ሠልፎች ምሥሎችም ቢሆኑ በሰፊው ሲጋሩ ታይተዋል፡፡ የነፃነት በዓሉ ላይ የቀረበው ሙዚቃና ድግስ ሁሉ አንድ በአንድ በሰፊው ሲሠራጭ ነው የሰነበተው፡፡
የኤርትራ ደጋፊ ነን የሚሉ ወገኖች፣ ‹‹ኤርትራ ሁሉም ወጣት ተሰዶ ባዶዋን የቀረች አገር ሆናለች፡፡ ወጣቱ የግዳጅ ውትድርና ጠልቶ ከአገር በመሰደዱ የቀሩ ዜጎች አዛውንቶችና አረጋዊያን ብቻ ናቸው፡፡ አገሪቱ ዛሬ የሚዋጋ ኃይል የሌላት ደካማ ናት፤›› ብለው የሚናገሩና ኤርትራን ሊያጠቁ የሚሞክሩ ሁሉ ይህን የመሰለ ጦርና ኃይል አደርጅተናል የሚሉ መልዕክቶች የሚያስተላልፉ መረጃዎችን በሰፊው በማሠራጨት ተጠምደው ነው የሰነበቱት፡፡
ከዚህ ጎን ለጎን ደግሞ ‹‹ጽምዶ›› እየተባለ ስለሚጠራውና የኤርትራና የሕወሓት አዲስ የፖለቲካ ጋብቻን መግለጫ ሆኖ በማገልገል ላይ ስለሚገኘው የትብብር ፖለቲካ በሰፊው ሲያራግቡ የሰነበቱም ነበሩ፡፡ ሻዕቢያና ሕወሓት አሁን ዳግም የፖለቲካ መቀራረብና ትብብር መጀመራቸውን የሚናገሩት እነዚሁ ወገኖች የትግራይና የኤርትራ አዋሳኝ ድንበሮች መከፈታቸውንና የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትና መቀራረብ እንደገና መጀመሩን እየተናገሩ ነው፡፡ እነዚህ ወገኖች ከዚህ በተጨማሪም በሻዕቢያና በአማራ ፋኖ ኃይሎች መካከል ግንኙነትና ወዳጅነት መጠናከሩን በማከል ጭምር፣ የኢትዮጵያ መንግሥት በሰሜን ኢትዮጵያ አቅጣጫ ጦርነት ቢከፍት በተባበረ ክንድ ለመመከት የተዘጋጀ ጥምር ግንባር/ቅንጅት ስለመፈጠሩ ለማስገንዘብ ሲጣጣሩ ነው የታዩት፡፡
ስለዚሁ ጉዳይ የተጠየቁት ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ አንድ የፖለቲካ ተንታኝ በበኩላቸው፣ ሻዕቢያን ከሕወሓት ሊያቀራርብ የሚችል አጋጣሚ እንደተፈጠረው ሁሉ ሻዕቢያን ከፋኖ ጋር በጋራ ለመሥራት የሚያመች አጋጣሚ መኖሩን በመጥቀስ ነገር ግን የፋኖ ኃይሎች ከሕወሓት ጋር በጋራ ተባብረው ይሠራሉ የሚለው ግምት አስቸጋሪ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ‹‹ከሰሞኑ ፋኖዎች የራሳቸውን የመደራደሪያ ነው ያሉትን የጋራ አቋም በጽሑፍ ይፋ አድርገዋል፡፡ ከዚህ አቋም መረዳት እንደቻልኩት ደግሞ የፋኖ ጥያቄ ከሕወሓትም ሆነ ከሻዕቢያ ጉዳይ ጋር የማይገናኝና በጋራ ለመሥራትም እንቅፋት መሆኑን ነው፤›› በማለት ገልጸዋል፡፡
የኤርትራው መሪ ኢሳያስ አፈወርቂ በዚህ ደረጃ በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ጠንካራ ትችትና ውግዘት ለማሰማት የፈለጉት ምን አስበው፣ እንዲሁም ምን ተማምነው ነው የሚል ጥያቄ የቀረበላቸው ተንታኙ የራሳቸውን ግምት አስቀምጠዋል፡፡
‹‹ሻዕቢያ አሁን የሠለጠነና የውጊያ ልምድ ያለው ጦር ባለቤት የሆነውን የሕወሓትን ኃይል አጋርነት አግኝቶ ቀርቶ፣ በትግራይ ጦርነት ወቅትም ቢሆን የእኔ ዕርዳታ ባይኖር የኢትዮጵያ መንግሥት ተሸንፎ ነበር የሚል ግምገማ አለው፡፡ ይህ ደግሞ የኢትዮጵያ መንግሥት ባለሥልጣናትም ሆነ የጦር አመራሮች ጭምር የሻዕቢያ ውለታን ሲያወድሱ ከመታየታቸው ጋር ተዳምሮ ጠንካራ እምነት ሆኗል፡፡ ሻዕቢያ ከዚህ በተጨማሪም የሱዳን፣ የግብፅና የሳዑዲ ዓረቢያ ድጋፍ እንደሚኖረውም በደንብ ያሠላ ይመስላል፡፡ የኢትዮጵያ በጦርነት መዳከምና ዓለም አቀፍ መቀነስ በቅርብ ጊዜ በባህር በር ጥያቄ ጉዳይ ከጎረቤት አገሮች ጋር ከገባችበት ውጥረት ጋር ተዳምሮ፣ ሻዕቢያ በቂ ዝግጅት አለኝ የሚል በራስ መተማመን እንዲፈጠርበት የሚጋብዝ ነው፡፡
ይሁን እንጂ ኢትዮጵያም ብትሆን ወደ ጦርነት ከተገባ ደጋፊ አጋሮች እንደሚኖሯት መገመት ቀላል ነው፡፡ ሱዳን ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ናት፡፡ የሳዑዲ ዓረቢያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ ተቃራኒ ጎራ ለይቶ በሱዳን ጦርነት መሠለፍ ግጭቱ ከሁለት ዓመታት በላይ ሳይበርድ እንዲቀጥል ምክንያት መሆኑ ይታወቃል፡፡ በኢትዮጵያም ቢሆን አንዴ ጦርነቱ ከፈነዳ ጎራ ለይቶ የሚያዋጋ ደጋፊ ወገን ማግኘት አይቸግርም፤›› በማለት ነው የኤርትራና የኢትዮጵያ ሰሞነኛ ውጥረት ወደ ከፋ ቀውስ ሊያመራ የሚችልበት ዕድል የተዘጋ አለመሆኑን ያብራሩት፡፡
ኤርትራ ነፃና ሉዓላዊ አገር ሆና ከተመሠረተችበት ጊዜ ጀምሮ ባለፉት 34 ዓመታት፣ በዙሪያዋ ካሉ በርካታ አገሮች ጋር ስትጋጭና ስትዋጋ ነው የኖረችው፡፡ በቀይ ባህር ባሉት በሀኒሽ ደሴቶች ይገባኛል ከየመን ጋር እ.ኤ.አ. በ1995 ተዋግታለች፡፡ ከዚያ ወዲህ ደግሞ እ.ኤ.አ. ከ1996 እስከ 1998 የሱዳን ተቃዋሚዎችን ደግፋ የሱዳን መንግሥትን ስትዋጋ ቆይታለች፡፡ እ.ኤ.አ. ከ1998 እስከ 2000 ደግሞ ከኢትዮጵያ ጋር በባድመ ድንበር ይገባኛል የተነሳ ከባድ ጦርነት ስታካሂድ ቆይታለች፡፡ እ.ኤ.አ. በ2008 ዓመት በራስ ዱሜራ ድንበር ይገባኛል የተነሳ ከጂቡቲ ጋር ወደ ግጭት ገብታለች፡፡ ከእነዚህ ሁሉ በተጨማሪም በሶማሊያ የእርስ በእርስ ግጭት ውስጥ ጣልቃ በመግባት ከኢትዮጵያ ጋር የእጅ አዙር ግጭት ውስጥ ገብታ መቆየቷ፣ እንዲሁም በሶማሊያ የሚንቀሳቀሱ ቀጣናዊ ሥጋት የደቀኑ አሸባሪ ኃይሎችን ስትደግፍ መኖሯም በታሪክ መዛግብት ሰፍሮ ይገኛል፡፡
የፕሬዚዳንት ኢሳያስ መንግሥት በተከተለው ቀጣናዊ ግጭትና ውጥረትን በሚያጭሩ ፖሊሲዎች የተነሳ፣ ኤርትራ በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ማዕቀብ ስትማቅቅ እንደኖረች ይወሳል፡፡ ከአሥር ዓመታት በላይ የዘለቀውን በኤርትራ ላይ የተጣለውን ማዕቀብ ለማስነሳት ኢትዮጵያ በቅርብ ዓመታት ዓለም አቀፉን ማኅበረሰብ በይፋ እስከ መጠየቅ የደረሰ ዕርምጃ ወስዳለች፡፡ ይህ ደግሞ የሆነው አዲሱ የዓብይ አህመድ (ዶ/ር) መንግሥት ከአስመራ መንግሥት ጋር ዕርቅ በማውረዱ እንደሆነ ይታወሳል፡፡ የኤርትራና የኢትዮጵያ መንግሥታት ከ20 ዓመት በኋላ ዳግም መታረቅ በወቅቱ ቢደግፍም ወዲያው ወደ መቃወም የገባው የሕወሓት ቡድንም የሁለቱ አገሮች መንግሥታት መቀራረብ ትግራይን ለመውጋት ሆን ተብሎ የተጀመረ ጥረት ነው የሚል ተቃውሞ ወደ ማቅረብ መግባቱ ይታወሳል፡፡
ይህ ደግሞ በሕወሓትና በኢትዮጵያ መንግሥት መካከል የተፈጠረውን አለመተማመን እያሰፋው ሄዶ ከባድ ውጥረት መፍጠሩ በሒደትም ከባድ ጦርነት ማስከተሉ አይዘነጋም፡፡ በዚህ ጦርነትም የኤርትራ ኃይል ከኢትዮጵያ ጎን የተሠለፈ ሲሆን፣ ሕወሓት በጦርነቱ ወቅትም ሆነ ከፕሪቶሪያ ስምምነት በኋላ የኤርትራ፣ የአማራና የኢትዮጵያ መንግሥት ኃይሎችን የጠላትነት ስም ሲሰጣቸው መቆየቱም አይዘነጋም፡፡ አሁን ግን ይህ የኃይል አሠላለፍ የተለወጠ ሲሆን፣ ሻዕቢያ ከሕወሓትና ከአማራ ፋኖ ኃይሎች ጋር ተባብሮ ጦርነት ሊከፍት ነው የሚል ስሞታ ተደጋግሞ ይደመጣል፡፡
የትግራይ ፖለቲካን በቅርበት የሚከታተሉት ጌታቸው አሰፋ (ፕሮፌሰር) ዩኤምዲ በተባለው በግል የማኅበራዊ ገጽ ሚዲያቸው ላይ ስለኤርትራና ስለኢትዮጵያ የጦርነት ዳግም መፈጠር ሥጋት የሕዝብ አስተያየት መጠይቅ ለተከታታዮቻቸው አቅርበው እንደነበር፣ ቅዳሜ ለንባብ በበቃው የሪፖርተር እንግሊዘኛ ጋዜጣ ላይ ሐሳባቸውን አጋርተዋል፡፡
እሳቸው ቃለ መጠይቁን እስከሰጡበት ቀን ድረስ ወደ 521 ሰዎች ድምፃቸውን መስጠታቸውን የገለጹት ጌታቸው (ፕሮፌሰር)፣ ከእነዚህ መላሾች መካከልም 57 በመቶዎቹ በኤርትራና በኢትዮጵያ መንግሥት መካከል ጦርነት ቢፈጠር ትግራይ መሳተፍ የለባትም የሚል ስሜት ማንፀባረቃቸውን ጠቁመዋል፡፡ ትግራይ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጎን መቆም አለባት ያሉት 27 በመቶ መሆናቸውን የተናገሩት ፕሮፌሰሩ፣ ቀሪዎቹ አነስተኛ የ11 በመቶ አኃዝ ያላቸው አስተያየት ሰጪዎች ግን ከኤርትራ ጎን ተሠልፎ የኢትዮጵያ መንግሥትን መውጋት ይሻላል ማለታቸውን በመለስተኛ የሕዝብ አስተያየት መገምገሚያ ሙከራቸው ለማወቅ እንደቻሉ አብራርተዋል፡፡
‹‹እኔ ጦርነት አላበረታታም፣ ጦርነትም መቼም የትም ቢሆን አልደግፍም፡፡ ነገር ግን የጦርነቱ መምጣት አይቀሬ ከሆነ ግን በግሌ የትግራይ ሕዝብ ከኢትዮጵያውያን ጎን ሆኖ ሻዕቢያን ቢያስታግስ እመርጣለሁ፡፡ ሻዕቢያን ማስታገሱ ለትግራይም፣ ለኢትዮጵያም ሆነ ለኤርትራና ለቀጣናው ጭምር ትልቅ እፎይታ የሚሰጥ ነው፤›› በማለት ነበር ጌታቸው (ፕሮፌሰር) ለሪፖርተር ሐሳባቸውን ያጋሩት፡፡
ኤርትራና ኢትዮጵያ አሁን ወደ አይቀሬው ጦርነት እያዘገሙ ነው የሚሉ ስለሁኔታው የሠጉ አንዳንድ ወገኖች በበኩላቸው፣ ይህ ጦርነት የሚካሄድበት ዋና የመስተናገጃ ቦታ ሊሆን የሚችለው ደግሞ ከጦርነት ገና ያላገገመው ሰሜን ኢትዮጵያ መሆኑ ብዙ እንደሚያሳስባቸው ይገልጻሉ፡፡ የኤርትራና የኢትዮጵያ ወደ ጦርነት መግባት እንደ ከዚህ ቀደሞቹ ጦርነቶች ሊሆን እንደማይችል የሚጠቅሱት እነዚህ ወገኖች፣ ወደ ጦርነቱ አንዴ ከተገባ ለሁለቱም ኃይሎች የመጨረሻቸው ሊሆን እንደሚችል ያሰምሩበታል፡፡ ሱዳን ውስጥ ያልበረደ ትኩስ ጦርነት እያለ ምሥራቅ አፍሪካ ቀንድ በብቁ ውጥረቶች በሚገኝበትና ከቅርብም ከሩቅም የራሳቸውን ፍላጎት አንግበው የተሠለፉ ኃይሎች በበዙበት በዚህ ወቅት፣ ሁለቱ አገሮች ሌላ ዙር ጦርነት ማስተናገድ ፈጽሞ እንደማይችሉ በመጠቆም ሁለቱም አካላት ሆኑ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የሰላም አማራጭ መፍትሔዎችን እንዲያማትሩ ነው የሚያሳስቡት፡፡
Ethiopian Reporter - ሪፖርተር
በዮናስ አማረ
May 28, 2025