07/01/2026
እንጀራው ወልድያ እየተጋገረ፤
ወጡ ጉባላፍቶ ሲሸተኝ አደረ።
የማሽላው አገር አላገዶ ነው፤
ጥንቅሹን ወልድያ ምን አበሸለው።
እየተባለ ይዜምላታል!
የወሎዋ ሁለተኛ መድናም ይሏታል።
የመሰረቷት ታላቁ እራስ አሊ ናቸው። ከተመሰረተች ደግሞ ከ200 አመት እድሜ በላይ አስቆጥራለች። ይህች ጥንታዊት ከተማ ማን ትባላለች?
ለመሆኑ ታላቁ ራስ አሊ ማን ናቸው?
ቀዳማዊ አሊ /አሊ ጓንጉል/ እየተባሉ ይጠሩ የነበሩት ታላቁ እራስ አሊ የየጁ ስርወ - መንግስት መስራች ናቸው!
ከአባ ሴሩ ጓንጉል እና ከላስታዋ ባላባት ከወ/ሮ ገለቡ ፋሪስ የተወለዱት ታላቁ ራስ አሊ ከየጁ ወረሸህ መነሻ ከሆኑት ሸህ ዑመር 7ኛ ትውልድ ናቸው።
ራስ አሊ (ቀዳማዊ አሊ) ወይም በጊዜው ይጠሩበት የነበረው ታላቁ ራስ አሊ አባታቸው ከመሞቱ ቀደም ብሎ በ1766 የበጌምድር እንደራሴ ሆነው በመሾም ለአስር አመታት በጌምድርን ሲያስተዳድሩ ከቆዩ በኋላ ከሴሩ ጓንጉል ቤተሰብ የመጀመሪያው ሰው በመሆን የመጀመሪያው የየጁ ስርወ መንግስትን ስልጣን ይዘዋል።
ታላቁ ራስ አሊ ከ1777- 1782 በጎንደር ቤተ መንግሥት የመጀመሪያውን የየጁ መሳፍንት የበላይነት ይዘው ያስተዳደሩ ታላቅ ንጉስ ናቸው።
የታላቁ ራስ አሊ ቤተ-መንግሥት መርጦ ከተማ በምዕራብ በኩል ልዩ ውበት ና ዕይታ ባላት አምባ ላይ ተሰርቶ የነበረ ሲሆን በአካባቢው የድንጋይ ካብ መሰረት ፣ የፍሪዳና የጠጅ መጣያ የነበሩ ምልክቶች አሁንም ይገኛሉ፡፡
በመጨረሻም ታላቁ ራስ አሊ (ቀዳማዊ አሊ) በ1782 በመሞታቸው ወንድማቸው ራስ አሊጋዝ እሳቸውን በመተካት የጎንደር እንደራሴነት(የየጁ ስርወ መንግስት ሁለተኛው ራስ በመሆን) ስልጣንን ጨበጠ።
ወሎ ደሴ