
21/08/2025
የዲላ ከተማ የኮሪደር ልማት ከውበት ባሻገር ምቹ የመኖሪያ አካባቢ ፈጥሯል
የዲላ ከተማ የኮሪደር ልማት ከውበት ባሻገር ምቹ የመኖሪያ አካባቢ መፍጠር ያስቻለ መሆኑን የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጭነት በአዲስ አበባ ከተማ የተጀመረው የኮሪደር ልማት በክልሎችም ተስፋፍቶ ውብ ከተሞችና ለመኖሪያ ምቹ አካባቢዎችን እየፈጠረ መሆኑ ይታወቃል።
በዚህ የልማት ፕሮግራም በአጭር ጊዜ ውስጥ አስደማሚ ለውጥ ካሳየችው አዲስ አበባ ባሻገር የተለያዩ የክልል ከተሞችም እየተዋቡና ለኑሮ ምቹ እየሆኑ መጥተዋል።
በከተሞች እየተከናወኑ ካሉ የኮሪደር ልማት ሥራዎች መካከል በዲላ ከተማ የተሰራው የኮሪደር ልማትን በተመለከተ ኢዜአ የከተማዋን ነዋሪዎች አነጋግሯል።
ከከተማዋ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ነጻነት በሪሶ እና ወይዘሮ ምስጋና ግዛው፤ የኮሪደር ልማት ከተማን የማሳመር ጉዳይ ብቻ ሳይሆን በተመቸና ጤናማ አካባቢ የመኖር እድል መሆኑን አንስተዋል።
የኮሪደር ልማቱ ከቱሪዝም መስህብ፣ ከንግድና የመስሪያ ቦታዎች እንዲሁም ሌሎች አገልግሎቶች ጋር የተሰናሰለ አስደናቂ ስራ መሆኑንም ገልጸዋል።
በመሆኑም በተከናወኑት የልማት ስራዎች እየተጠቀምን፣ እየጠበቅንና እየተንከባከብን ዘላቂ ልማትንና ብልጽግናን እውን ማድረግ የሁላችንም ሃላፊነት ሊሆን ይገባል ሲሉ ተናግረዋል።
ወጣት እዝራ አየለ እና መቅደስ ዓለማየሁ፤ የከተማዋ የኮሪደር ልማትና የመሰረተ ልማት ሥራዎች ከተማዋን ይበልጥ ውብና ማራኪ እያደረጓት መሆኑን ገልጸዋል።
የልማት ስራዎቹ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል የፈጠሩ፣ የመዝናኛ አማራጮችን ያሰፉ እና የዲላን የቱሪስት መስህብነት ይበልጥ የሚያጠናክሩ መሆናቸውን አንስተዋል።
በመሆኑም በከተማው በሚከናወኑ ሁለንተናዊ የልማት ተግባራት በንቃት መሳተፍ ማገዝና የልማት አጋር ሆኖ መዝለቅ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል።
የዲላ ከተማ ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ሥራ አስኪያጅ አቶ ማዘንጊያ ኢያቶ፤ በከተማዋ የኮሪደር ልማት ሥራዎች በምዕራፍ ተከፋፍለው በጥራትና በተፋጠነ ሁኔታ እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።
ለልማት ሥራው መፋጠን አጠቃላይ የከተማዋ ነዋሪዎች በተለይም የወጣቶች እገዛና ተሳትፎ ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ተናግረዋል።
በሁለተኛው ዙር የኮሪደር ልማት የአስፓልት መንገድን ጨምሮ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ግንባታ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አንስተው በተያዘላቸው ጊዜ በጥራትና በፍጥነት ገንብቶ ለማጠናቀቅ እየተሰራ መሆኑንም አመልክተዋል።
በተጨማሪም የቪዲዮና ሌሎች መረጃዎቻችንን ለማግኘት የትክክለኛ አድራሻዎቻችን አባል በመሆን ይከታተሉ፡-
ዩቲዩብ- https://www.youtube.com/southradioandtelevisionagency
ቴሌግራም -https://t.me/southRadioAndTelevisionAgency
ዌብ ሳይት - https://srta.gov.et/
ትዊተር - https://twitter.com/SouthRadioandTv