12/05/2026
የደም ልገሳ መርሃ-ግብር ተካሄደ
******************************************
ቢሾፍቱ፣ ግንቦት 04 ፣ 2018(ኢመዩ)በኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ኢንጂነሪንግ ኮሌጅ የስታፍ አባላት፣ ተማሪዎች እና ሰራተኞች “ህይወቱን ለሚሰጥ ሰራዊት ደሜን በመለገስ ከጎኑ እቆማለሁ” በሚል መሪ ቃል ከመከላከያ ደም ባንክ ጋር በትብብር የተደረገ የፈቃደኝነት የደም ልገሳ መርሃ-ግብር ተካሂዷል።
ይህ የሰብዓዊነት ተግባር በግዳጅ ላይ ለሚገኘው የመከላከያ ሰራዊት አባላት እንዲሁም ለሲቪል ማህበረሰቡ የህይወት አድን ድጋፍ እንዲውል ታስቦ መዘጋጀቱን የኢንጂነሪንግ ኮሌጅ ደረጃ አንድ ሆስፒታል አስተባባሪ ሻለቃ ኤርሚያስ ግርማ ተናግረዋል።
ሻለቃ ኤርሚያስ ኮሌጁ ከትምህርትና ስልጠና ተግባራት ጎን ለጎን እንዲህ ያሉ ማህበረሰብ አቀፍ የሰብዓዊ አገልግሎቶችን በመፈጸም ሀገራዊ ኃላፊነቱን በትጋት እየተወጣ መሆኑን አብራርተዋል። በዚሁም የኮሌጁ ማህበረሰብ እና ተማሪዎች በመርሃ ግብሩ ላይ ያሳዩት ከፍተኛ ተሳትፎ በእጅጉ እንደሚያደነቅ ገልፀዋል።
ከመርሃ ግብሩ ተሳታፊዎች ተማሪ መቶ አለቃ ምንይችል ሞላ እና ወ/ሮ አዜብ ስዩም ደም መለገስ የሰብዓዊነት ከፍተኛ መገለጫ መሆኑን በመግለጽ፣ ለሀገር መከላከያ ሰራዊት የሚደረግ ክብር እና ድጋፍ እንደሆነ አስረድተዋል።
ሀገርን መውደድ ማለት ሰራዊቱ የሚያከናውነውን የሀገር ሉዓላዊነት ጥበቃ ተልዕኮ በተግባር መደገፍ ነውም ብለዋል።
ኮሌጁ ለማህበራዊ እና ለሰብዓዊ እሴቶች ያለውን ክብር በመርሃ -ግብሩ አሳይቷል።
ዘጋቢ፡ ሰኢድ አሊ
ፎቶግራፍ፡ ለታ አለማየሁ
ለመከላከያ ሰራዊታችን ልህቀት እንተጋለን!
የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ