04/11/2025
ይኼንን ጽሑፍ ቁጭ ብለህ እያነበብህ ያለኸው በዚህ ሰዓት ምሥራቅ አርሲ ገጠር ውስጥ ስላልተገኘህ ብቻ ነው:: በዚህች ቅጽበት በሥጋት ውስጥ ሆነው "ከአሁን አሁን ምን ይመጣብን ይሆን?" እያሉ ያሉ የኦሮሚያ ምእመናን ቁጥራቸው ብዙ ነው:: ከቀናት በፊት የተገደሉትን ተናግረን ሳናበቃ አሁን ደግሞ ሌላ ቦታ አምስት እንደተገደሉ እየሰማን ነው::
ሰሞኑን ከሁለት ሺህ ዓመታት በፊት ሔሮድስ ስላሳደዳት እመቤታችን "ሰቆቃወ ድንግል" እያልን እያዘንን ነው:: ከሰይፍ ልጅዋን ማስጣል ያልቻለች የአርሲዋን እናትስ እንዴት ዝም እንበላት? ይህንን የማያቆም ሞት ዜና ሰምተን ወደ ጉሮሮአችን የሚወርድ ምግብና መጠጥ የምንተኛውም እንቅልፍ የለም:: የእነርሱ ሞት የእኛ ሞት ነው:: የእነርሱ መቁሰል የእኛ ቁስል ነው:: የቦታ ለውጥ እንጂ በእነርሱ የደረሰው በእኛም ሊደርስ ይችላል::
ቤተ ክርስቲያን ምሕላ እንድታውጅ ፣ ለተሠዉት ተገቢውን ክብር እና ጸሎተ ፍትሐት እንድታደርግ እንጠብቃለን:: ቤተ ክርስቲያን በየትኛውም ቦታ የንጹሐን ደም ዳግመኛ እንዳይፈስስ እንደ ራሔል ዕንባዋን የምትረጭበት ጊዜ አሁን ነው::
የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ትኩረት ያልሠጠውን ችግር ሌላ አካል ሊጨነቅበት አይችልም:: ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን በአስተዳደራዊ መዋቅርዋ መንግሥት ተገቢውን እርምጃ እንዲወስድ በሙሉ ትኩረት የምትሠራበት ጊዜም አሁን ነው:: ቅዱስ ሲኖዶስ በዚህ ዓይነት ጊዜ የሚያሳየው ምላሽ ከሌለ ሌላ ቀን ቢጣራ የማይሰማውን ቤተ ክርስቲያን አልባ ክርስቲያን በራሱ ላይ ይፈጥራል:: ሐዋርያዊትዋ ቤተ ክርስቲያንም በክህነት የማትመራ የመሆን አደጋ ይገጥማታል:: ክህነት ከሌለ ደግሞ ቤተ ክርስቲያንም ምሥጢራትም የሉም::
ኦርቶዶክሳውያን ምእመናንም ይህንን ጊዜ ለመካሰስ ፣ አባቶችን ለመሳደብ ፣ አንዱ ሌላውን ለማስጠቆርና ለመናቆር ሳይሆን ለጸሎት ለምሕላና ለሰብአዊ ሥራና መሬት ላይ ቢወርዱ ችግሮችን የሚፈቱ ዘላቂ መፍትሔዎች ላይ በትብብር ለመሥራት ምክንያት ብናደርገው የተሻለ ነገር ማምጣት እንችላለን::
የሌላ እምነት ተከታዮች ሆነው ይህ በኦርቶዶክሳውያን ላይ ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያውያን ላይ የተቃጣ ጥቃት ብለው ጉዳዩን በተቋምም በግልም ያወገዙ ሰዎችን እናከብራለን:: "ይበላችሁ" ብለው የተሳለቁትን እና በክፉ ቀን ክፋታቸውን ላሳዩን ደግሞ እውነተኛ ማንነታቸውን ስላሳዩን እያመሰገንን "አቤቱ፥ በኢየሩሳሌም ቀን የኤዶምን ልጆች አስብ፦ “እስከ መሠረትዋ ድረስ አፍርሱ አፍርሱ፡” ያሉአትን" ብለን ለሰማያዊው ዳኛ ሠጥተናቸዋል:: መዝ. 137:7