06/09/2026
በምስራቅ ሐረርጌ ዞን በኩርፋ ጨሌ ፣ በግራዋ ፣ በመዩ ሙሉቄና በቁንቢ ወረዳዎች በኤልኒኖ ምክንያት የዝናብ እጥረት በመከሰቱ በግብርና ስራቸው ላይ ችግር መፍጠሩን ነዋሪዎች ገለጹ
በምስራቅ ሀረርጌ ቆላማ አካባቢዎች የኤልኒኖ ተጽዕኖ በተለይ ዝናብን ጠብቀው የግብርና ስራዎችን የሚያከናውኑ አካባቢዎች ላይ ከፍተኛ ስጋት መፍጠሩን የአካባቢዎቹ ነዋሪዎችና አመራሮች ተናግረዋል፡፡
የቁንቢ ወረዳ ሞጆ ለገ ሆሜ ቀበሌ ነዋሪ ወ/ሮ ጀነቲ ሀራድ እንደተናገሩት የቀበሌያቸው ነዋሪ አርሶና አርብቶ አደሮች የዘሩት በቆሎና ማሽላ ዝናብ ባለመዝነቡ ሙሉ በሙሉ መውደሙንና ነዋሪው ለችግር መዳረጉን ተናግረዋል፡፡
አርሶና አደር ጀነቲ በሞጆ ወንዝ አካባቢ የሚኖሩና ውሀውን የሚስቡበት ሞተር የሌላችው አርሶ አደሮች ከድርቁ አደጋ ማምለጥ እንደማይችሉ ተናግረዋል፡፡
አርሶ አደር ኡርጌ መሃመድ ፣ ጃፈር መሃመድ ፣ መሃመድ ጀማል መሃመድ ለሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብ ሬዲዮ ሐ.ዩ. ኤፍ ኤም 91.5 እንደተናገሩት በአካባቢያቸው የዝናብ ዕጥረት የበቆሎና ማሽላ ሰብሎችን ሲያወድም ድንች እና ሌሎች አትክልቶች አፈር ውሰጥ በተከሰቱ ነፍሳት በመውደማቸው ለምግብ እጥረት እንደገጠማቸውና ይህንን ችግር ለማሳለፍ የቀን ስራ ፍለጋ ወደ ግራዋ ከተማ መምጣታቸውን ገልጸዋል፡፡
በመዩ ሙሉቄ የሞጆ ወልደያ ነዋሪ አርሶ አደር ሃስን ኡመር በበኩሉ ከዚህ ቀደም የስንዴ ምርት ይመረትባቸው የነበሩ ሰፋፊ የእርሻ ማሳዎች በዝናብ እጥረት የተነሳ ጾም ማደራቸውን ገልጸዋል፡፡
በቁንቢ ወረዳ የከራ ባልጪ ቀበሌ አስተዳዳሪ አቶ አህመድ አሊዪ ዱሪ አካባቢው በተደጋጋሚ በድርቅ ከመመታቱ ጋር ተያይዞ ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በየጊዜው ድጋፍና ክትትል በማድረግ አርብቶ አደሮችን በሞጆ ወንዝ ዳርቻ በመውሰድ ወደ ግብርና ስራ እንዲገቡ ከስልጠና እሰከ ግብርና ግብአቶች በመስጠት አካባቢውን ምርታማ ለማድረግ ሲሰራ እንደነበር አስታውሰው ኤልኒኖ ባስከተለው የዝናብ እጥረት በዚህ መኅር ወቅት የተላከላቸውን ምርጥ የማሽላ ዘር በ20 ሄክታር ላይ በክላስተር ቢዘሩም ድርቁ ማሳ ላይ ሙሉ ለሙሉ አውድሞታል ብለዋል፡፡
በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ግብርናና አካባቢ ሳይንስ ኮሌጅ መምህር ዶክተር አብዱለጢፍ አህመድ በበኩላችው በሞጆ ስምጥ ሸለቆ የተሰራውን ውጤታማ የግብርና ስራ በደጋማው የወረዳው አካባቢዎች ለማስፋፋት ከፍተኛ ጥረት ሲደረግ እንደነበር ጠቁመው በከራ ባልጪ 20 ሔክታር ላይ የተዘራው ማሽላ የኤልኒኖ ተጽዕኖ ሙሉ ለሙሉ ወድሞ በማየታቸው ማዘናቸውን ገልጸው የአካባቢውን ነዋሪዎች ችግር ለማቃለል በቀጣይ የሚዘንበውን ዝናብ በመጠቀም ደራሽ የሆኑ ለሰውና እንስሳት የሚሆኑ እንደ ስኳር ድንች ፣ ካውፒናና ሌሎች የአደንጓሬ ሰብሎችን ከባለድርሻ አባላት ጋር በመሆን ለማቅረብ ጥረት እናደርጋለን ብለዋል፡፡
የቁንቢ ወረዳ ምክትል አስተዳዳርና የወረዳው የአርብቶና አርሶ አደር ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አብዱልበሃሪ ሲራጅ የኤልኒኖ ቀውስ በአካባቢያቸው ወንዞችና የውሀ ጉድጓዶችን መጠን በመቀነሱ ችግሩ በዚሁ ከቀጠለ ንጹህ የመጠጥ ውሀ ማግኘት ስለማይቻል በሰውና በከብቶች ላይ ከፍተኛ አደጋ ሊያሰከትል ስለሚችል ስጋት ውስጥ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
በቀጣይም የኤልኒኖ ተጽእኖ ጠንካራ ሊሆን እንደሚችል ትንበያ ስላለ ችግሩን ለማቃለል ሁሉም ባለድርሻ አካላት ርብርብ እንዲያደርጉ አቶ አብዱልበሃሪ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ዘጋቢ፦ ሲሳይ ዋቄ