15/09/2026
በክልሉ በትምርት ዘርፍ የተመዘገበው ስኬት የጉዞው መጀመሪያ እንጂ መዳረሻ አይደለም፦ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ
***
በሐረሪ ክልል በ2018 የትምህርት ዘመን በዘርፉ ለተገኘው አመርቂ ውጤት አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላት የእውቅናና የሽልማት መርሐ ግብር ተካሄዷል።
በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ በክልሉ በዘርፉ የተመዘገበው ስኬት የብዙ ዓመታት ጥረት ፍሬ በመሆኑ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል።
የተመዘገበው የላቀ ውጤት የጉዞው መጀመሪያ እንጂ መዳረሻ አለመሆኑን የጠቆሙት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ ስኬቱን አስጠብቆ ለመቀጠል የበለጠ ትጋትና ጥረት እንደሚጠይቅ አሳስበዋል።
ተማሪዎች ያመጡት ውጤት የኃላፊነት ካባ እንጂ ማረፊያ አለመሆኑን በመገንዘብ፣ ለነገው ትልቅ ስኬት በትህትናና የመማር ፍላጎታቸውን ሳይቀንሱ አዲስ እውቀትን ለመገብየት ዝግጁ መሆን እንዳለባቸው ጠቁመዋል።
የተመዘገበው የላቀ ውጤት የአንድ ጊዜ አጋጣሚ ሳይሆን የትምህርት ቤቶች ቋሚ ባህልና መለያ ሊሆን እንደሚገባም አሳስበዋል።
የተማሪዎች ስኬት ከጀርባው የቤተሰብ ያልተቋረጠ ድጋፍና መስዋዕትነት ያለበት በመሆኑ፣ ልጆቻቸው ወደ ላቀ ደረጃ በሚሸጋገሩበት ወቅት ድጋፋቸው ይበልጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል።
ርዕሰ መስተዳድሩ አክለውም፣ ትምህርት ቤቶች የተሻለ የመማር-ማስተማር አካባቢ እንዲኖራቸው ለማድረግ፣ የአቅም ግንባታ ሥራዎችን ለማጠናከርና ዝቅተኛ ውጤት ያመጡ ትምህርት ቤቶች ድክመታቸውን አርመው ወደ ተሻለ ደረጃ እንዲመጡ ልዩ ክትትል እንደሚደረግ አረጋግጠዋል።
በተጨማሪም በትምህርት ቤቶች መካከል ያለውን የውጤት ልዩነት ማጥበብ እንደሚገባ ጠቁመው፣ በቀጣይ የ12ኛ ክፍል ሀገራዊ ፈተና የማለፍ ምጣኔን ወደ 50 በመቶ እና ከዚያ በላይ ለማድረስ ታቅዶ መሠራት እንዳለበት አሳስበዋል።
በክልሉ ዕድሜያቸው ለትምህርት የደረሱ ሕፃናት በሙሉ ወደ ትምህርት ገበታ እንዲገቡ የተቀናጀ ንቅናቄ እንደሚያስፈልግም አቅጣጫ አስቀምጠዋል።
ጥራት ያለው ትምህርት በውጤት ብቻ ሳይሆን በሥነ-ምግባር፣ በክህሎትና በእውቀት የሚለካ በመሆኑ ሙሉ አቅምን አውጥቶ መሥራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ጌቱ ነገዎ በበኩላቸው፤ በሐረሪ ክልል በትምህርት ጥራት፣ በሥርዓተ ትምህርት ሪፎርም እና በመሠረተ ልማት ላይ በተከናወኑ ሰፊ ሥራዎች በክልላዊና ሀገር አቀፍ ፈተናዎች አመርቂ ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል።
በተጨማሪም በርካታ አዳዲስ ትምህርት ቤቶችና የመማሪያ ክፍሎች መገንባታቸውን፣ የመጽሐፍ ጥምርታ መሻሻሉን እና በ"ትምህርት ለትውልድ" ንቅናቄ 34 ሚሊዮን ብር ማሰባሰብ መቻሉንም አመልክተዋል።
በ2018 የትምህርት ዘመን 6ኛ ክፍል ፈተና ከወሰዱት ተማሪዎች መካከል 78.31 በመቶ የሚሆኑት 50 እና ከዚያ በላይ ውጤት ማምጣታቸውን የገለጹት አቶ ጌቱ፣ በ8ኛ ክፍል ፈተናውን ከወሰዱት ውስጥም 72.64 በመቶ የሚሆኑት ማለፍ መቻላቸውን ጠቁመዋል።
በ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና ከተፈተኑት ተማሪዎች መካከል 22.76 በመቶ የሚሆኑት ከ300 በላይ ያመጡ መሆናቸውንም ጠቁመዋል።
በእውቅናና ሽልማት መርሐ ግብሩ ላይ የክልሉ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ሱልጣን አብዱሰላም፣ የሐረሪ ብሔራዊ ጉባኤ አፈ ጉባኤ አቶ ሙህየዲን አህመድ፣ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ ሮዛ ኡመር፣ የክልሉ ብልፅግና ፓርቲ ቅ/ጽ/ቤት ሃላፊ አቶ ጌቱ ወዬሳን ጨምሮ ሌሎች የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ፣ መምህራን፣ ተማሪዎችና ወላጆች ተገኝተዋል።
በገዛኸኝ አራጌ
05/01/18