25/12/2025
በምልጃዋ ያመኑትን ሁሉ ሊምርላት ቃል ኪዳን ሰጣት
ነቢዩ ቅዱስ ሕዝቅኤልም የዘለዓለም ድንግልናዋን በትንቢት መጽሐፉ ምዕራፍ 44÷1 ሲናገር “ወደ ምሥራቅ ወደሚመለከተው በስተውጭ ወዳለው ወደ መቅደሱ በር አመጣኝ፤ ተዘግቶም ነበር። እግዚአብሔርም ይህ በር ተዘግቶ ይኖራል እንጂ አይከፈትም፣ ሰውም አይገባበትም፤ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ገብቶበታልና ተዘግቶ ይኖራል፤” ብሎአል። የተዘጋ የመቅደስ በር የተባለች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናት። “ይህ በር ተዘግቶ ይኖራል እንጂ አይከፈትም፤” የሚለው ኃይለ ቃል በድንግልና ጸንታ እስከ ዘለዓለሙ እንደምትኖር ይነግረናል። “ሰው አይገባበትም የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ገብቶበታልና ተዘግቶ ይኖራል” ሲልም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በድንግልና ፀንሳ፣ በድንግልና የወለደችው ኢየሱስ ክርስቶስ የባህርይ አምላክ በመሆኑ፣ ከርሷ በተዋህዶ ሰው የሆነ የባህርይ አምላክ እንጂ ዕሩቅ ብእሲ አይወለድምና በድንግልና እንደጸናች ትኖራለች ማለቱ ነው።
“እግዚአብሔር አንድ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወድዶአልና። ፍቅርም እንደዚህ ነው፤ እግዚአብሔር እርሱ ራሱ እንደ ወደደን ስለ ኃጢአታችንም ማስተስረያ ይሆን ዘንድ ልጁን እንደ ላከ እንጂ እኛ እግዚአብሔርን እንደ ወደድነው አይደለም፤” ይላል። ዮሐንስ 3÷17፣ 1ኛ ዮሐንስ 4÷10። ይህን መውደድ ይህን ፍቅር የገለጸው ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በሕቱም ድንግልና በመወለድ ነው። የእመቤታችን ድንግልና በሦስት ወገን ነው፤ በሥጋዋ÷ በነፍሷና በልቡናዋ ነው። ይህ ድንግልና የዘለዓለም ድንግልና ነው። ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ኢሳይያስ “ስለዚህ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል፤ እነሆ ድንግል ትፀንሳለች፣ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፣ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች፤” ብሎአል። ኢሳይያስ 7÷14።
እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከመጽነሷ በፊት፣ በጸነሰችም ጊዜ፣ ከጸነሰችም በኋላ ድንግልናዋ የጸና ነው፤ ከመውለዷ በፊት፣ በወለደችም ጊዜ፣ ከወለደችም በኋላ ኅትምት በድንግልና ናት። የውዳሴ ማርያም አንድምታ ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ገብርኤል አንቺ ከሴቶች ሁሉ ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ ያላትን አብራርቶ ይነግረናል፡፡ እመቤታችን መልአኩ ሲያበስራት “ወንድ ሳላውቅ ይህ ነገር እንደምን ይሆንልኛል?” የሚል ጥያቄ አንስታ ነበር፡፡ ይህን ያለችው ክብር ይግባትና የወንድ ሀሳብ በአእምሮዋ ፈጽሞ ተመላልሶ ስለማያውቅ ነው፡፡ ሌሎች ሴቶች ስለወንድ ከመናገርና በሕጋዊ ሩካቤ ከመገናኘት ቢታቀቡ ከማሰብ ግን አይነጹም፡፡ እምቤታችን ግን ከመናገር ከማድረግ ከማሰብ ንጽህት ናት፡፡ ከዚህች ቅድስት ድንግል ጋርም በመቃብሩ ስፍራ በጎልጎታ ተደፍታ ስትለምነው በምልጃዋ ያመኑትን ሁሉ ሊምርላት ቃል ኪዳን ሰጣት፡፡
በሥላሴ አኗኗር ወልድ ለአብ ተቀዳሚና ተከታይ የሌለው አንድ ልጅ እንደሆነ ሁሉ ለእናቱ ለቅድስት ድንግል ማርያምም ተቀዳሚና ተከታይ የሌለው አንድ ልጇ ነው። በጳጳስ ወንበር ቄስ፣ በንጉሥ ዙፋን ራስ ደፍሮ እንደማይቀመጥ ሁሉ በአምላክ ዙፋን በቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ማን ያድራል? ለዚህም ነው እግዚአብሔር ለነቢዩ ለሕዝቅኤል አስቀድሞ የነገረው። ጠቢቡ ሰሎሞንም በመኃ 4÷12 “እኅቴ ሙሽራ የተቈለፈ ገነት፣ የተዘጋ ምንጭ፣ የታተመ ፈሳሽ ናት፤” ብሎአል። እንደተቆለፈች አምላክ ብቻ አድሮባት የወጣባት ገነት፣ እንደተዘጋች የዘለዓለምን ሕይወት ክርስቶስን ያመነጨች፣ እንደታተመች የሕይወትን ውኃ ክርስቶስን በአራቱም ማዕዝን አፍስሳ የተጠሙ ነፍሳትን ያረካች፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ብቻ ናት።