10/06/2026
የጤና መኮንኑ ወጣት ምሳሌ ቡዙነህ ሕይወቱን በገዛ እጁ ማጥፋቱ ተሰማ
በሲዳማ ክልል በማዕከላዊ ሲዳማ ዞን በሎካ አባያ ወረዳ እና በአካባቢው ማኅበረሰብ ዘንድ ትልቅ ተስፋ ተጥሎበት የነበረው ወጣቱ የጤና ባለሙያ (HO) ምሳሌ ቡዙነህ፣ በትውልድ ቀዬው ሕይወቱ አልፎ መገኘቱ ተሰማ።
ከወረዳው ኩታዮ ቀበሌ ፈልቆ፣ በኦሳ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እንዲሁም በሀንጤጠ ከተማ በሚገኘው የሎካ አባያ መሰናዶ ትምህርት ቤት በነበረው የላቀ የትምህርት አፈጻጸምና ብሩህ አእምሮው የአካባቢው ኩራት መሆን የቻለው ይህ ወጣት፤ ከአርሲ ዩኒቨርሲቲ በጤና መኮንንነት (Public Health Officer) በማዕረግ ከተመረቀ ሦስት ዓመታት የሆኑት ቢሆንም፣ ለሶስት አመታት የሥራ ዕድል ሳያገኝ ቆይቶ ነበር።
በቅርቡ በሞጆ ከተማ የመንግሥት ጤና ተቋም ውስጥ በውድድር ተቀጥሮ ሥራ የጀመረ ቢሆንም፣ የሥራ ዘመኑ ሁለት ወር ብቻ እንደሞላው ባልታወቀ ምክንያት ሥራውን አቁሞ ወደ ትውልድ ስፍራው ተመልሶ ነበር። ይሁን እንጂ በትናንትናው ዕለት አመሻሽ ላይ በራሱ ላይ በወሰደው አሳዛኝ እርምጃ ሕይወቱ አልፎ ተገኝቷል። ወጣቱን ባለሙያ ለዚህ ከባድ ውሳኔ ያነሳሳውና ለሞቱ መንስኤ የሆነው ምስጢር ምን እንደሆነ እስከ አሁን ድረስ የተጣራ ነገር የለም።
ለወላጆቹ ብቸኛ ወንድ ልጅ የሆነውና በቅንነቱ፣ በትሕትናውና በታታሪነቱ የሚታወቀው ወጣት ምሳሌ ቡዙነህ በዚህ መልኩ በድንገት መለየቱ መላውን የሎካ አባያ ወረዳ፣ የኦሳ እና የኩታዮ ማኅበረሰብ በከባድ ድንጋጤና ጥልቅ ሐዘን ውስጥ ጥሏል።
የወጣት ምሳሌ ቡዙነህ የቀብር ሥነ-ሥርዓት በነገው ዕለት በተወለደበት በኩታዮ ቀበሌ ልዩ ስሙ ባዲቻ በሚባለው ቦታ ከቀኑ 6:00 ሰዓት ጀምሮ ይፈጸማል።
ለተከበሩ ወላጆቹ፣ ለወዳጅ ዘመዶቹ እና ለጠቅላላው የሎካ አባያ ወረዳ፣ የኦሳ እና የኩታዮ ማኅበረሰብ ጥልቅ መጽናናትን እንመኛለን።
ነፍሱን በአጸደ ገነት ያኑራት! 🕯️