12/05/2026
ወጣት ኢያሱ ክፍሌ በአጠቃላይ የ750 ካሬ ሜትር የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ ተሸለመ
ለሀገር ሰላምና ለጀግኖች አርበኞች መታሰቢያነት ትልቅ ዓላማ ሰንቆ ከጌዴኦ ዞን ቡሌ ከተማ እስከ አዲስ አበባ ድረስ ለ11 ቀናት 388 ኪሎ ሜትሮችን በእግሩ የተጓዘው ወጣት ኢያሱ ክፍሌ፣ ወደ ትውልድ ስፍራው ሲመለስ በደማቅ ሁኔታ ተቀብሎታል። ይህ ጉዞ ወጣቱ ለሀገሩ ያለውን ፍቅርና የሰላምን አስፈላጊነት ለመስበክ ያደረገው ጥረት ተደርጎ የተወሰደ ሲሆን፣ በከተማውና በዞኑ አስተዳደሮች ዘንድም ትልቅ ግምት ተሰጥቶታል።
የወጣቱን ቁርጠኝነትና በጎ ተነሳሽነት ለማበረታታትም ልዩ ልዩ ሽልማቶች ተበርክተውለታል። የጌዴኦ ዞን አስተዳደር በዲላ ከተማ በነበረው ቆይታ የ500 ካሬ ሜትር የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ የሰጠው ሲሆን፣ የቡሌ ከተማ አስተዳደር ደግሞ ተጨማሪ 250 ካሬ ሜትር መሬት በስጦታ አበርክቶለታል። ይህም ወጣቱ በአጠቃላይ የ750 ካሬ ሜትር መሬት ባለቤት እንዲሆን አስችሎታል።
ከመሬት ስጦታው በተጨማሪ፣ የቡሌ ወረዳ አስተዳደር ለወጣቱ ቀና አስተሳሰብ እውቅና በመስጠት የ50,000 (ሃምሳ ሺህ) ብር የገንዘብ ሽልማት ሰጥቶታል። የከተማው አስተዳደር በሰጠው መግለጫ፣ ኢያሱ ክፍሌ የጥንካሬና የሰላም አምባሳደር በመሆን የትውልድ አካባቢውን በበጎ ስም ማስጠራቱን ገልጿል።
ይህ ታሪካዊ አቀባበልና ሽልማት ሌሎች ወጣቶችም በተመሳሳይ መልኩ ለሀገራቸው በጎ ተግባር እንዲሰለፉ የሚያበረታታ መሆኑ ተመላክቷል።