07/11/2025
በሴቶች ላይ የሚከሰቱ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ለመከላከል ባለድርሻ አካላት በትኩረት መስራት እንደሚገባቸዉ ተገለፀ
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ በሽታ መከላከልና ጤና ማጎልበት ዳይሬክቶሬት የጡት እና የማህፀን ጫፍ ካንሰር የንቅናቄ መድረክ ከባለድርሻ አካላት ጋር በጂንካ ከተማ አካሂዷል፡፡
የንቅናቄ መድረኩን በንግግር የከፈቱት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊና የጤና ፕሮግራሞችና የኤች አይ ቪ ኤድስ መከላከልና መቆጣጠር ዘርፍ ኃላፊ አቶ መና መኩሪያ፤ ተላላፊ ካልሆኑ በሽታዎች በሴቶች ላይ ከፍተኛ ጫናና ሞት ከሚያስከትሉት መካከል የማህፀን ጫፍ ካንሰርና የጡት ካንሰር ዋነኞች ናቸዉ ብለዋል፡፡
የጡት ካንሰር ከመከሰት አንፃር በ1ኛ ደረጃ ሴቶችን የሚያጠቃ ሲሆን ከገዳይነት አንፃር የማህፀን ጫፍ ካንሰር 1ኛ ደረጃን የሚይዝ በሽታ መሆኑን የገለፁት ኃላፊዉ፤ ሴቶች ወደ ጤና ተቋማት በመሔድ ልየታ በማድረግና በሽታዉ ከተከሰተም ህክምና ማግኘት ከቻሉ በሽታዉን መታደግ እንደሚቻልና ይህ ሳይሆን ሲቀር ለሞት እንደሚዳርጉ ተናግረዋል፡፡
አክለዉም ሴቶችን ከጡት ካንሰርና ከማህፀን ጫፍ ካንሰር ለመታደግ በተሰሩ ስራዎች ጠንካራ አፈፃፀም ያላቸዉ መዋቅሮች እንዳሉ ሁሉ በአንፃሩ ዝቅተኛ አፈፃፀሞችም ስላሉ በየደረጃዉ ያሉ ባለድርሻ አካለት የህበረተሰቡ ግማሽ አካል የሆኑትን ሴቶች ከበሽታዉ ለመታደግ ትኩረት ሰጥተዉ ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ በሽታ መከላከል ዳይሬክቶሬት ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ፕሮግራም አስተባባሪ ሲስተር ትዕግስት ተሰማ፤ በየዓመቱ ከሚታመሙት ወደ 17 ሺ የሚጠጉ ወደ 7 ሺ የሚሆኑት በየአመቱ እንደሚሞቱ እና በተመሳሳይ ከ6 ሺ በላይ የሚሆኑ ሴቶች በየዓመቱ የማህፀን ጫፍ ካንሰር እንደሚታመሙና ከእነዚህም ከ4 ሺ በላይ የሚሆኑት በበሽታዉ እንደሚሞቱ ተናግረዋል፡፡
በጤናዉ ዘርፍ የመድረኩ ተሳታፊ ከሆኑት መካከል የአሪ ዞን ጤና መመሪያ ኃላፊ አቶ በድሉ በጊማስ የወላይታ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ ፀጋዬ ኤካና የጋሞ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ ሰይፉ አነቃና ሌሎችም በጋራ፤ የማህበረሰቡን ጤና መጠበቅ ዋና ኃላፊነታቸዉ በመሆኑ ከዚህ ቀደም ትኩረት ሳይሰጣቸዉ በበርካታ ሴቶች ላይ ጉዳት ሲያደርሱ የቆዩ አሁን ግን መንግስት ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራባቸዉ ካሉ ተላላፊ ካልሆኑ በሽታዎች መካከል ከማህፀን ጫፍ ካንሰርና የጡት ካንሰር ሴቶችን ለመታደግ ከዚህ ቀደም ከነበረዉ አሰራር በተሻለ ሁኔታ በገጠር ያሉ ሴቶችን ተደራሽ በማድረግ እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል፡፡
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊና የማህበራዊ ዘርፍ ኃላፊ ወ/ሮ ምህረት በላይ በበኩላቸዉ፤ ከክልሉ ጤና ቢሮ ጋር በመሆን በጡት ካንሰርና በማህፀን በር ካንሰር በርካታ ስራዎች ሲሰሩ ቢቆዩም የተመዘገቡ ዉጤቶች አሁንም ትኩረት የሚሹ በመሆናቸዉ ሴቶችን ከስቃይና ሞት ለመታደግ በቀጣይ የተሻለ ስራ እንደሚሰራ ተናግረዋል፡፡
በመድረኩ የክልሉ ጤና ቢሮ የጤና ኢንስቲትዩት ምክትል ቢሮ ኃላፊዎችና ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች፣ የክልሉ ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊና የዞን ጤና መምሪያ ኃላፊዎች፣ የበሽታ መከላከል ዘርፍ ኃላፊዎችና ሌሎች ተገኝተዋል፡፡
ዘጋቢ፡ በናወርቅ መንግስቱ - ከጂንካ ጣቢያችን
በተጨማሪም የቪዲዮና ሌሎች መረጃዎቻችንን ለማግኘት የትክክለኛ አድራሻዎቻችን አባል በመሆን ይከታተሉ፡-
ዩቲዩብ- https://www.youtube.com/southradioandtelevisionagency
ቴሌግራም -https://t.me/southRadioAndTelevisionAgency
ዌብ ሳይት - https://srta.gov.et/
ትዊተር - https://twitter.com/SouthRadioandTv