05/12/2025
ያለፉት ሁለት ዓመታት ጉዞ አድካሚ ቢሆንም በርካታ ያጋጠሙ ችግሮችን ማስተካከል በመቻሉ ክልሉ በትክክለኛ አቅጣጫ ላይ መሆኑን ተገንዝበናል :- ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
(ሆሳዕና፣ህዳር 26/2018)የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)20ኛውን የኢትዮጵያ የብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በዓል በማስመልከት ከመገናኛ ብዙሀን ጋር ቆይታ አድርገዋል
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር )እንደገለጹት ከሌሎች የሀገሪቱ ህዝቦች ጋር ያለንን መስተጋብር ወደ ላቀ ደረጃ በማድረስ በወዳጅነት፣በወንድማማችነትና በእህታማማችነት ላይ የተመሰረተ ስራ ለመስራት ጽኑ ፍላጎት አለን ብለዋል።
በክልሉ በተለያዩ አካባቢዎች የሚከበሩ የመስቀል እና የዘመን መለወጫ በዓላት ብራንድ አድርጎ ማውጣት ይቻላል ሲሉም ርዕሰ መስተዳድሩ አስረድተዋል።
በክልሉ በኢንዱስትሪ፣በቱሪዝም እንዲሁም ለኤክስፖርት የሚሆኑ የእርሻ ምርቶችን በማስፋፋት ብራንድ ማድረግ የሚያስችል ስርዓት መዘርጋት ተገቢ ስለመሆኑም አመላክተዋል።
በእነዚህ እና በመሳሰሉት ነጥቦች ላይ ጠንክረን በመስራት የክልሉ መገለጫ የሚሆኑ ጉዳዮች ላይ ብራንድ እንዲኖረን እንሰራለን ብለዋል።
ባለፉት ሁለት ዓመታት ያጋጠሙ ተግዳሮቶች በርካታ ናቸው ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ መጀመሪያ ችግሮችን በደንብ መለየት እና መረዳት፣ለችግሮች መፍትሄ ለማበጀት ደረጃቸውን ጭምር መለየት ላይ ትኩረት አድርገናል ሲሉም ጠቁመዋል።
ካጋጠሙን ተግዳሮቶች ውስጥ የሰላም እጦት፣የደመወዝ ፣የማዳበሪያ፣ የጥሬ ገንዘብ እዳ እና ሌሎች በርካታ ችግሮችን መጥቀስ ይቻላል ብለዋል።
ሰራተኛው እና አመራሩ ለረጅም ጊዜ ስራ ላይ ባለመኖሩ በተቀዛቀዘ ስሜት ላይ ነበር ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ በሌላ በኩል ከአፈር ማዳበሪያ ጋር የተያያዘ ስርዓት አልበኝነትም ተስተውሎ እንደነበር ጠቅሰዋል።
የእነዚህን ችግሮች ደረጃ በመለየት እንዴት እንፍታቸው፣መቼ እልባት እንስጣቸው በሚል እሳቤ አቅደን ወደ ተግባር ገብተናል በማለት አብራርተዋል።
አሁን ካለው ነባራዊ ሁኔታ አንጻር አብዛኛዎቹን ችግሮች በጊዜ ሂደት መፍታት ተችሏል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ አልፎ አልፎ የሚመላለሱ ችግሮች ሊኖሩ ስለሚችሉ እያስተካከልን እንሄዳለን ብለዋል።
ባለፉት ሁለት ዓመታት ሁሉም አመራር ርብርብ ያደረገበት ስራ የሰላም ማስከበር ተጠቃሽ ስለመሆኑ የገለጹት ርዕሰ መስተዳድሩ በተደጋጋሚ ስለ ዘላቂ ሰላም ስናነሳ ሰላም ወዳዱ ህብረተሰብ ከመንግስት ጋር በቅንጅት እየሰራ ይገኛል ብለዋል።
ነገር ግን በክልላችን በተለያየ ጊዜ ችግር ለመፍጠር የሚፈልጉ አካላት ይሄ ጉዳይ በጥብቅ ዲሲፕሊን እየተመራ መሆኑን ሲገነዘቡ ይከፋቸዋል ሲሉም ጠቁመዋል።
በዘርፉ የሚደረገውን ጥረት ለመቀልበስ በፕሮፓጋንዳ ስራ ላይ መጠመዳቸውንም ጠቅሰዋል።
በሰላም ጉዳይ ላፍታም ሳንዘናጋ ዛሬም፣ነገም ለሚቀጥሉት ቀናት ወራትና ዓመታት ስለ ሰላም እንሰራለን ብለዋል።
ሌላው ትኩረት አድርገን የሰራንበት ጉዳይ ግብርና ነው ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ በክልሉ ቅድመ በልግና ጸደይን ጨምረን በቂ የምርት እድገት እንዲኖር በትኩረት እየተሰራ ስለመሆኑም በአብነት ጠቅሰዋል።
ከዚህ ቀደም በክልሉ በጣም አነስተኛ መጠን ያለው ገቢ ሲሰበሰብ እንደነበር ያስታወሱት ርዕሰ መስተዳድሩ አሁን ከዛሬ ሁለትና ሶስት ዓመታት ሲሰበሰብ ከነበረው ገቢ በእጥፍ አሳድገናል ብለዋል።
አንድ ከተማ አሊያም ክልል እራሱን ማሳደግ የሚፈልግ ከሆነ የገቢ እና የንግድ ስርዓቱን ፈትሾ ማስተካከል አለበት ሲሉም ርዕሰ መስተዳድሩ አመላክተዋል።
በትምህርት፣በጤና በኢንቬስትመንት ፣በወጣቶች የስራ እድል ፈጠራ እንዲሁም በመሰረተ ልማት ዘርፍ እንደ ውሃ፣መንገድ፣መብራት ቴሌኮም እና መሰል የልማት መስኮችን ማሟላት የክልሉ መንግስት የእለት ተዕለት ስራ ስለመሆኑም ርዕሰ መስተዳድሩ አጽንኦት ሰጥተዋል።
በክልሉ ህገወጥነትን መከላከል ሌላው አብይ የትኩረት መስክ መሆኑን የገለጹት ርዕሰ መስተዳድሩ ህገወጥነትን ስንከላከል ደግሞ የኑሮ ውድነትን መቀነስ ያስችላል ብለዋል።
የመጣንበት መንገድ አድካሚ ቢሆንም በርካታ ጉዳዮችን ለማሻሻል ሞክረናል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩእነዚህ በቂ ባለመሆናቸው ተጨማሪ ስራ መስራት ያስፈልጋል።
በክልሉ የቤተሰብ ብልጽግናን ለማሳካት በልዩ ትኩረት እየተሰራ ነው ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ በግብርናው መስክ ጠንክሮ በመስራት ከእለት ፍጆታ ባለፈ ገበያውን ማረጋጋት የሚያስችል አቅም መፍጠር ያስፈልጋል ሲሉም ርዕሰ መስተዳድሩ አብራርተዋል።
የመደመር ፍልስፍና እና እሳቤ ከተለያዩ ችግሮች ወጥተን ወደ አንድ እንምጣ፣ወደ ኋላ ከሚጎትተን አጀንዳ በመውጣት በጋራ ጉዳዮቻችን ላይ በማተኮር መስራት ተገቢ ስለመሆኑም አመላክተዋል።
የጋራ አጀንዳችን ከሆኑ ጉዳዮች ውስጥ ልማት፣ዘላቂ
ሰላም እንዲሁም የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ስራዎች ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል።
የሁለት ዓመታት ጉዞችንን ስንፈትሽ ክልሉ በትክክለኛ አቅጣጫ ላይ መሆኑን ተገንዝበናል በማለት ነበር ርዕሰ መስተዳድሩ የገለጹት።
ለኢትዮጵያ ከፍታ ከግብርና መር ኢኮኖሚ በተጓዳኝ ማዕድን፣ቱሪዝምን፣ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ማድረግ እንዲሁም በኢንዱስትሪ ዘርፉ ላይ ትኩረት ማድረግ ይገባል ብለዋል።