27/01/2025
የቅጣት አወሳሰን በኢትዮጵያ ህግ
መግቢያ
ወንጀል የማህበረሰብን ብሎም የሀገርን ሰላምና ደህንነት የሚጎዳ በመሆኑ በወንጀል ህግ የተመለከቱ የወንጀል ድንጋጌዎችን በመተላለፍ ወንጀል የሚፈፅም ሰው ለጥፋቱ በህጉ የተመለከተውን ቅጣት መቀጣቱ የግድ ነው፡፡ በሀገራችንም ወንጀሎችን ከነቅጣታቸው የሚደነግግ የወንጀል ህግ እና ሌሎች ልዩ አዋጆች በሥራ ላይ የዋሉ ሲሆን በወንጀለኞች ላይ የሚጣለውን ቅጣት በተመለከተ በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ሀሳቦች ሲንፀባረቁ ይስተዋላል፡፡ ከነዚህ ሀሳቦች በመነሳትም የግንዛቤ ክፍተቶች ያሉ መሆኑን መረዳት ይቻላል፡፡ በመሆኑም በዚህ አጭር ፅሁፍ የቅጣት አላማ፣ በወንጀል ህጉ የተመለከቱ የወንጀል ቅጣት አይነቶችን፣ ቅጣት የሚወሰንበትን ሂደት እና ቅጣት አወሳሰንን በተመለከተ ዐቃቤ ህግ ስላለው ሚና በዝርዝር የምንመለከት ይሆናል፡፡
የቅጣት አላማ
አሁን ባለንበት ዘመናዊ የህግ ሥርአት የቅጣት አላማ ወንጀለኛውን መበቀል አይደለም፡፡ ከዚህ ይልቅ ወንጀል የተፈፀመባቸው ሰዎች ፍትህ እንዲያገኙ እና ወንጀል ፈፃሚዎች ላይ ተገቢውን የእርምት እርምጃ በመውሰድ ለቀጣይ ከወንጀል ተቆጥበው መልካም ዜጎች እንዲሆኑ ማድረግ ዋነኛ አላማው ነው፡፡ ይህ እሳቤ በሀገራችን በ1996 ዓ.ም በወጣው የወንጀል ህግ አንቀፅ 1 ሥር በግልፅ ሰፍሮ የሚገኝ ነው፡፡ ይኸውም የወንጀል ህጉ ቅጣት የሚጥልበት ምክንያት ህጉን ጥሰው ወንጀል የሚፈፅሙ ሰዎች ተቀጥተው ሌላ ወይም ተጨማሪ ወንጀል እንዳይፈፅሙ ለመከላከል፣ ለወደፊት እንዲታረሙ ለማድረግ እና ሌሎችም ከዚህ ተምረው ወንጀል እንዳይፈፅሙ ማስተማሪያ ለማድረግ ነው፡፡ ከዚህም መረዳት የሚቻለው የወንጀል ህጉ ቅጣት ሲያስቀምጥ ወንጀል ፈፃሚዎችን ለመበቀል ሳይሆን ወንጀሎች እንዳይፈፀሙ ለመከላከልና ወንጀል ሲፈፀምም ፈፃሚዎችን አርሞ መልካም ዜጋ ለማድረግ እንደሆነ ነው፡፡
የቅጣት አይነቶች
የወንጀል ህጉ እንደ ወንጀል ፈፃሚው እድሜ የተለያዩ የቅጣት አይነቶችን አካቷል፡፡ አካላመጠን በደረሱ አዋቂዎች ላይ የሚጣሉ ቅጣቶች በወጣት ጥፋተኞች ላይ ከሚጣሉ የጥንቃቄ እርምጃዎች የተለዩ ናቸው፡፡ በወንጀል ህጉ መሰረት የወንጀል ተጠያቂነት ከሚጀምርበት ዘጠኝ አመት ጀምሮ እስከ አስራ አምስት አመት ዕድሜ ያሉ ወንጀል ፈጻሚዎች በወንጀል ህጉ አንቀፅ 157 እስከ 168 የተመለከቱት የጥንቃቄ እርምጃ ብቻ ሲወሰድባቸው ከአስራ አምስት አመት በላይ የሆኑ እና ከአስራ ስምንት አመት በታችን የሆኑት ወንጀል አድራጊዎች ደግሞ በመደበኛ ቅጣት የሚቀጡ ይሆናል፡፡
ለአዋቂ የሚጣሉ ቅጣቶችን በተመለከተ የወንጀል ህጉ በዋና ቅጣት፣ ተጨማሪ ቅጣት እና ለአዋቂ የሚሰጡ ልዩ እርምጃዎች በሚል ከፋፍሎ አስቀምጧል፡፡ ዋና ቅጣቶች እንደ ስማቸው በዋናነት በወንጀል ፈፃሚዎች ላይ የሚጣሉ መደበኛ የቅጣት አይነቶች ሲሆኑ የሚከተሉትን ያካትታል፡፡
• የገንዘብ መቀጮ፣ የንበረት ማገድ እና መውረስ፣
መቀጮ በወንጀል ጥፋተኛ የተባለ ሰው ለመንግስት የሚከፍለው ገንዘብ ነው፡፡ መጠኑን በተመለከተ በወንጀል ህጉ አንቀፅ 90 መሰረት ተቃራኒ ድንጋጌ ከሌለ በቀር ከብር 10 (አስር) እስከ ብር 10,000 (አስር ሺ) የሚደርስ ሲሆን ጥፋተኛ የተባለው ህጋዊ ሰውነት ያለው ድርጅት ከሆነ ከብር 100 (አንድ መቶ) እስከ ብር 100,000 (አንድ መቶ ሺ) ይደርሳል፡፡ ንብረት ማገድና መውረስ ደግሞ ህጉ በግልፅ በደነገገ ጊዜ ወንጀለኛው ጥፋተኛ በተባለበት ወንጀል በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ያገኘውም ሆነ በህጋዊ መንገድ ያገኘው ንብረት የሚወረስበት የቅጣት አይነት ነው፡፡