04/06/2026
"የበሌሳ ሆስፒታል በሀድያ ምድር ከተመሰረቱ ቀደምት የጤና ተቋማት መካከል አንዱ ሲሆን፣ ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚሻገር ተቋም ሆኖ እንዲጠናቀቅ አስፈላጊው ድጋፍና ክትትል ይደረጋል" - ዶ/ር ዲላሞ ኦቶሬ
ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የበሌሳ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ግንባታ ተረከበ
ሆሳዕና 27/09/2018 ዓ.ምበሀድያ ዞን ሌሞ ወረዳ ሌሳ ቀበሌ በሕዝብ ተሳትፎ ግንባታው ተጀምሮ ለረጅም ጊዜ ሳይጠናቀቅ የቆየውን የበሌሳ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ግንባታ ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ በይፋ ተረክቦ እስከ ፍጻሜው ድረስ የማስገንባት ኃላፊነት መውሰዱን አስታውቋል።
በግንባታው ርክክብ ሥነ ሥርዓት ላይ የተገኙት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ዋና የመንግሥት ተጠሪ ድላሞ ኦቶሬ (ዶ/ር) የበሌሳ ሆስፒታል በአካባቢው ለዘመናት ጤና አገልግሎት ሲሰጥ የነበረ ታሪካዊ ተቋም መሆኑን ገልጸው፣ ተቋሙ የትውልድ ቅርስ በመሆኑ ግንባታው መጠናቀቅ አስፈላጊ መሆኑን አሳስበዋል።
ዶ/ር ድላሞ አክለውም ተቋሙ በሀድያ ምድር ከተመሰረቱ ቀደምት የጤና ተቋማት መካከል አንዱ መሆኑን ጠቅሰው፣ ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚሻገር ተቋም ሆኖ እንዲጠናቀቅ አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግ ገልጸዋል።
የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዳዊት ሀዬሶ (ዶ/ር) በበኩላቸው የዩኒቨርሲቲው አመራር ከዚህ ቀደም ፕሮጀክቱን በመጎብኘት ሁኔታውን መገምገሙን ጠቅሰው፣ ግንባታውን በመረከብ ለማጠናቀቅ የነበረውን እቅድ አስታውሰዋል።
ፕሬዚዳንቱ እንዳሉት፣ ፕሮጀክቱ ከፍተኛ በጀትና ጊዜ የሚጠይቅ ቢሆንም፣ በመንግሥት፣ በሕዝብና በተቋማት ትብብር በአጭር ጊዜ ውስጥ ተጠናቆ ለአገልግሎት እንደሚበቃ እምነታቸውን ገልጸዋል።
በመጨረሻም ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ግንባታውን እስከ መጨረሻው በኃላፊነት በመምራት ለማጠናቀቅ ቁርጠኛ መሆኑን አረጋግጠዋል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ ሳሙኤል ዳርጌ በበኩላቸው፣ ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ግንባታውን ቢመራም የክልሉ ጤና ቢሮ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልጸዋል።
አክለውም የጤና ሚኒስቴር የተጀመሩ የጤና ተቋማትን ግንባታ ወደ ፍጻሜ ለማድረስ እቅድ መያዙን ጠቅሰው፣ ሆስፒታሉ ሲጠናቀቅ የመድኃኒትና የቁሳቁስ ድጋፍ እንደሚደረግ ተናግረዋል።
የሀድያ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማቴዎስ አኒዮ በበኩላቸው ለፕሮጀክቱ መጀመርና መቀጠል አስተዋፅኦ ያደረጉ ሁሉንም አካላት አመስግነው፣ ሆስፒታሉ ለሰፊው ማኅበረሰብ ጥራት ያለው የጤና አገልግሎት እንደሚሰጥ ተናግረዋል።
ዞኑም ለግንባታው ተጨማሪ ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልጸዋል።
የሌሞ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታደለ ደምሴ በበኩላቸው፣ የ7ኛው ዙር ጠቅላላ ምርጫ በሰላም በተጠናቀቀበት ማግስት መርሐ ግብሩ መካሄዱ ለአካባቢው ልዩ ትርጉም እንዳለው ገልጸዋል።
የአካባቢው ነዋሪዎችም ሆስፒታሉ ታሪካዊ ተቋም መሆኑን ጠቅሰው፣ በሕዝብ አቅም ተጀምሮ ለረጅም ጊዜ ሳይጠናቀቅ መቆየቱን ገልጸዋል።
ይሁን እንጂ ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ግንባታውን በመረከብ ሥራውን በይፋ ማስጀመሩ ተስፋ እንደሰጣቸው እና ደስታ እንደፈጠረላቸው ገልጸዋል።