30/07/2021
ሐምሌ 23 ቀን 2013
ማሳሰቢያ
የ“FDRE Defense Force - የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት” ፌስ ቡክ ገፅ ተከታዮችና ይህ መረጃ የሚደርሳችሁ ኢትዮጵያውያን ወገኖች ፤ የውስጥና የውጭ ጠላቶቻችን የህዝባችንን ስነ-ልቦና ለመስለብና የተፈጠረውን አንድነታችንን ለማፍረክረክ ማህበራዊ ሚዲያን በመጠቀም የስነ-ልቦና ጦርነት አጠናክረው ቀጥለዋል፡፡
ውድ ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ይህን መረጃ ሼር በማድረግ ለሁሉም በማዳረስ የዜግነት ግዴታችንን እንወጣ፡፡
ሁሉም ሀገር ወዳድ ዜጋ በሚችለው ሁሉ ከሠራዊታችን ጎን በመቆም "ኢትዮጵያ ፈረሰች" ብለው ያሻቸውን በህዝባችን ላይ ለመፈፀም ያሰፈሰፉ የውስጥ ቅጥረኞች ፣ ባንዳዎች እና የኢትዮጵያ ልማት የራሳቸው ጥፋትና ውድቀት የሚመስላቸው የውጭ ጠላቶችን በማሳፈር ላይ ይገኛል፡፡
ህዝባችን የሠራዊታችን የማይነጥፍ አስተማማኝ ደጀን በመሆን በሎጂስቲክስ ድጋፍ ፣ ከዳር አስከ ዳር በመነቃነቅ በሰው ሃይል ሰራዊታችንን በማጠናከር ታሪካዊ ሀገርን የማዳን ስራ እየሰራ ነው ፡፡ ለዚህ የህዝባችን የማይነጥፍ ድጋፍ የድላችን ቁልፍ በመሆኑ እናመሰግናለን፡፡
ይህ ደግሞ ለሰራዊታችንና ለመላው ህዝባችን ከፍተኛ የሞራልና ስነ-ልቦና ከፍታ ያሳየ ሆኗል ፡፡ በጠላቶቻችን የተደቀነብን የህልውና አደጋ በጣጥሰን ለመሻገር ሁሉም ዜጋ ከመቼውም ግዜ በላይ መተባበር ፣ ጠላት ከሚነዛው አሉባልታ ወሬ ራስን መጠበቅ ፣ አንድነታችንን እና ህብረታችንን ማጠናከር ወቅቱ የሚጠይቀው አብይ ጉዳይ ነው፡፡
በመላው ኢትዮጵያ ህዝብ የታየው ህብረትና በአንድነት መቆም ጠላቶቻችንን አስደንግጧል ፡፡ የአሸባሪው ጁንታ ጎራ በፍርሃት እንዲርድ አድርጓል፡፡ ሆኖም የህዝባችን አንድነትና ፅናት ለመሸርሸር ጠላት እየፈበረከ የሚረጨው አሉባልታዎችን መከላከል ፣ ሳያውቁ ጠላት ሆን ብሎ የሚለቀውን አሉባልታ በመቀባበል የጠላት ወኪል የሚሆኑ ወገኖችን መምከር ፣ መገሰፅ ያስፈልጋል፡፡
በአሸባሪው ህወሓት እየተፈበረኩ በማህበራዊ ሚዲያ የሚረጩ የውሸት መረጃዎችን ፣ በየአገልግሎት መስጫዎች የሚነዙ አሉባለታዎች ፣ ስለ ሠራዊታችን የግዳጅ ውሎ ሰው የሚቀባበለው ወሬ ለጠላት ግብዓት የሚሆኑና የወገንን እንቅስቃሴን የሚጎዱ ናቸው፡፡ ስለዚህ ወገኖች ሁሉ ከዚህ ቀጥሎ የተዘረዘሩ ጉዳዮችን በማህበራዊ ሚዲያና እርስ በርስ እንዳንቀባበል እና ሼር እንዳናደርግ እናሳስባለን፡፡
1.የመረጃ ምንጩ ያለታወቁ ቀልብ የሚስቡ መረጃዎችን ሼር ከመድረግ እንቆጠብ፤
2.የሠራዊታችን ከቦታ ቦታ እንቅስቃሴ ፣ የሚጓጓዙ የጦር መሳርያዎች አይነትና ብዛት ፣ የሎጂስቲክስ ድጋፍ እንቅስቃሴዎችን ፎቶ በማንሳት በማህበራዊ ሚዲያ አንለጥፍ ፡፡ የህን የሚፈፅም ከተመለከቱም ያስቆሙ፡፡ ፍቃደኛ ካልሆነ ለፀጥታ ሃይሎች ወዲያው ይጠቁሙ፡፡
3.በመንግስታችን በተወሰነው የተናጠል ተኩስ አቁም ወቅት የሚደረግ የጠላትን ትንኮሳ መከላከል ሥራ በማህበራዊ ሚዲያ አንለጥፍ፤
4.አንዳንድ ዩ-ቲዩበሮች ለሽርፍራፊ ሳንቲም ብላችሁ ሰበር ! ሰበር ! እያላችሁ ምንጩ ያለታወቀና ያለተረጋገጠ አሉባልታ በመንዛት የወገናችሁንና የሀገራችሁን ጥቅም አሳልፋችሁ ለጠላቶቻችን አትስጡ፤
5.ወቅታዊ ወታደራዊ እንቅስቃሴን በሚመለከት በታወቀ መንግስታዊ ወይም በሚመለከተው የመከላከያ ሃላፊ ወይም አዛዥ ያልተሰጠ መረጃ ከሆነ አንመን ፣ ሼርም አናድርግ፤
6.ሁሉም ሀገር ወዳድ ዜጋ በሰራዊታችን ግዳጅ አፈፃፀምና በህዝባችን ሞራልና ስነ-ልቦና የበላይነት ላይ ተፅዕኖ የሚፈጥሩና ጠላት ሆን ብሎ የሚለቃቸውን መረጃዎች ባለማሰራጨት እንተባበር፡፡
እናመሰግናለን
“FDRE Defense Force - የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት” ፌስ ቡክ ገጽ ፡፡